በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውን ተሳታፊዎች ተናገሩ

በዝግጅት ክፍሉ

ታኅሣሥ ፳፯ ቀን ፳፻፱ .

img_0298

ዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ማርያም ገዳም

img_0351

፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት በዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ድንግል ማርያም ገዳም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን፣ አባቶች ካህናትና ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በተገኙበት ታኅሣሥ ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም መካሔዱ የሚታወስ ነው፡፡

img_0325

በሐዊረ ሕይወቱ ጠዋትና ከሰዓት በኋላ በተከናወነው መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ በማኅበሩ ሰባክያነ ወንጌል መ/ር ምትኩ አበራና መ/ር ያረጋል አበጋዝ ልቡናን የሚገዛና ድካመ ነፍስን የሚጠግን ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

img_0296

ምክረ አበው አቅራቢ አባቶች

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ለ ‹‹ምክረ አበው›› በተጋበዙት በቆሞስ አባ ሳሙኤል በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የብሉያትና ሐዲሳት ትርጓሜ መምህር፤ በአባ ገብረ ኪዳን በደቡብ ጎንደር እስቴ መካነ ኢየሱስ ደብር የአባ ኤስድሮስ ጉባኤ ቤት የሐዲሳት ትርጓሜ መምህርና የብሉያት ደቀ መዝሙር፤ በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ በአዲስ አበባ የምሥራቀ ፀሐይ ቀበና መድኀኔ ዓለም ደብር የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር እና የስብከተ ወንጌል ክፍል ሓላፊ የብዙ ምእመናንን ጥያቄ የሚመልስ ትምህርት ቀርቧል፡፡

img_0333

የማኅበሩ መዘምራን ወረብና መዝሙር ሲያቀርቡ

በማኅበሩ ዘማርያንና በሊቀ መዘምራን ዲ/ን ቴዎድሮስ ዮሴፍ የቀረበው ያሬዳዊ ወረብና መዝሙርም የጉባኤው ክፍል ነበር፡፡

የሐዊረ ሕይወቱ ዐቢይ ኰሚቴ ሰብሳቢ አቶ ኤርምያስ ዓለሙ ለዝግጅት ክፍላችን እንዳስታወቁት ትኬት በመግዛት የመጡ ስምንት ሺሕ፤ ለልዩ ልዩ አገልግሎት ለመስጠት የተመደቡ አንድ ሺሕ፤ ከዓለም ገና እና ከአካባቢው የመጡ ደግሞ በግምት ሁለት ሺሕ፤ በድምሩ ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ የታደሙ ሲኾን በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውንም ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ቃለ ምዕዳን በሰጡበት ወቅት ‹‹ይህ ጉባኤ በዚህ ቦታ መዘጋጀቱ ለገዳሙ ብቻ ሳይኾን አጠቃላይ ለሀገረ ስብከታችን ትልቅ ዕድል ነው፤ በዚህ አካባቢ የሚገኙ ምእመናንም በመርሐ ግብሩ ትልቅ ተስፋ አግኝተዋል፤›› ካሉ በኋላ ‹‹ይህንን ጉባኤ በዚህ ቦታ በማካሔድ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስደሰቱ ማኅበሩን አመስግነዋለሁ፤›› በማለት የማኅበሩን አገልግሎት አበረታተዋል፡፡

ብ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ከከፊል የጉባኤው ተሳታፊዎች ጋር

ከመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች መካከል አንዳንዶቹ በሐዊረ ሕይወቱ በመሳተፋቸው በርካታ መንፈሳዊ ቁም ነገር ማግኘታቸውን፣ በትምህርቱ ነፍሳቸው መርካቷንና አእምሯቸውም መደሰቱን ጠቅሰው ይህን ዅሉ ምእመን በአንድ ድንኳን ሥር አሰባስቦ፤ ቍርስ እና ምሳ መግቦ ቃለ እግዚአብሔር እንዲማር በማድረጉ ማኅበረ ቅዱሳንን አድንቀዋል፡፡ አያይዘውም ‹‹መርሐ ግብሩ ከዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየወሩ ቢካሔድልን?›› የሚል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ed

የጉባኤው ተሳታፊ አባቶችና ወንድሞች በከፊል

የዓለም ገና እና የአካባቢው ማኅበረ ካህናትና ምእመናንም ሐዊረ ሕይወቱ በአካባቢያቸው በመካሔዱ ካገኙት መንፈሳዊ ትምህርት ባሻገር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መንፈሳዊ ጉባኤ የማዘጋጀት ልምድን ከማኅበረ ቅዱሳን መማራቸውንም ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በማኅበሩ ሰብሳቢ በአቶ ታምሩ ለጋ የማኅበሩ መልእክት የቀረበ ሲኾን በመልእክቱም ማኅበሩ በሚያበረክተው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በመሳተፍ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በጋራ ለመደገፍና አገልግሎቷን በሚፈለገው ደረጃ ለማሳደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን የበኩሉን እገዛ ያደርግ ዘንድ ሰብሳቢው ጥሪያቸውን በቤተ ክርስቲያን ስም አስተላልፈዋል፡፡

wo

የጉባኤው ተሳታፊ እናቶችና እኅቶች በከፊል

እንደዚሁም የማኅበሩ የስድስት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ የትኩረት አቅጣጫዎችን የስልታዊ ዕቅዱ ክንውንና ትግበራ ጽ/ቤት ሓላፊ አቶ ፋንታኹን ዋቄ አቅርበው ለዕቅዱ መሳካትም ምእመናን በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ የድርሻቸውን አስተዋፅዖ እንዲያበርክቱ አሳስበዋል፡፡

በመቀጠልም ሐዊረ ሕይወቱ በተሳካ ኹኔታ እንዲከናወን ድጋፍና ትብብር ያደረጉ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስንና የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችን፤ የሰበታ አዋስ ወረዳ ቤተ ክህነትና ወረዳ ማእከሉን፤ የደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስና ቅድስት ማርያም ገዳም ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤትን፣ ማኅበረ ካናትንና ምእመናንን፤ ከፌዴራል መንግሥት ጀምሮ በየደረጃው እስከ ከተማ አስተዳደሩ ድረስ የሚገኙ የመንግሥት አካላትን ማኅበሩ በእግዚአብሔር ስም አመስግኗል፡፡

11

መርሐ ግብሩ በጸሎት ሲፈጸም

በመጨረሻም ፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ተፈጽሟል፡፡

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

sebeta

የተቃጠለው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ወለልና የሕንጻው ቍሳቍስ በከፊል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሰበታ ወረዳ ቤተ ክህነት የሚገኘውና በጥር ወር ፳፻፮ ዓ.ም የተመሠረተው የሰበታ ዋታ ምዕራፈ ቅዱሳን አቡነ አረጋዊ እና በዓታ ለማርያም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከጠዋቱ ፪ ሰዓት ከ፴ ደቂቃ አካባቢ የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ በቆርቆሮና በኮምፖርሳቶ ከመታነጹ በተጨማሪ ቃጠሎው የደረሰው ካህናቱ አገልግሎታቸውን ፈጽመው ከቤተ ክርስቲያን ከወጡ በኋላ መኾኑ ጉዳቱን የከፋ አድርጎታል፡፡

የቃጠሎው መንሥኤ እስካሁን በግልጽ እንዳልታወቀና በቃጠሎውም ከጽላቶቹ በስተቀር ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ሙሉ በሙሉ እንደ ወደመ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መልአከ ሕይወት ሐዋዝ ተስፋ ለማኅበረ ቅዱሳን ሚድያ ክፍል አስታውቀዋል፡፡ እንደ አስተዳዳሪው ገለጻ ከአምስት መቶ ሺሕ ሰማንያ ብር በላይ የሚገመቱ ንዋያተ ቅድሳት በቃጠሎው ወድመዋል፡፡

sebeta-copy

በቃጠሎው የወደሙ ንዋያተ ቅደሳት በከፊል

የማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች ቦታው ድረስ በመሔድ እንደ ተመለከትነው ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ረፋድ ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በደብሩ ተገኝተው ማኅበረ ካህናቱንና ሕዝበ ክርስቲያኑን አጽናንተዋል፤ የደብሩን ይዞታ የሚያስከብርና ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን የሚያስገነባ የልማት ኰሚቴም አስመርጠዋል፡፡ እንደዚሁም የሰበታ ወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች፣ የየአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናትና ማኅበረ ምእመናን ለሕንጻው ማሠሪያና ለንዋያተ ቅድሳት መግዣ የሚኾን ገንዘብ በማሰባሰብ ለልማት ኰሚቴው አበርክተዋል፡፡

አቡነ ሳዊሮስ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

ብፁዕነታቸው በዕለቱ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ የልማት ኰሚቴው ከሐሜት በጸዳ መልኩ የማያድግምና ዘላቂ የኾነ ሥራ መሥራት እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ለሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ግንባታ ብቻ ሳይኾን ለሃይማኖታችን መጠበቅና ለምእመናን አንድነትም ዘብ መቆም ይገባዋል ብለዋል፡፡

‹‹ይህ ዅሉ የደረሰው በእኛ ኀጢአት ነው›› ያሉት ብፁዕነታቸው የደብሩ አገልጋይ ካህናትና የአካባቢው ምእመናን ጥላቻንና መለያየትን በማስወገድ፤ ከኀጢአት በመራቅ፤ በፍቅር፣ በሰላምና በአንድነት በመኾን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በቅንነት እንዲያገለግሉ አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በቃለ ምዕዳናቸው ማጠቃለያም በደብሩ ላይ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ ከማጥፋት ጀምሮ መቃኞ ቤት በመሥራትና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ ድጋፍና ትብብር ያደረጉትን ምእመናንና በአካባቢው የሚኖሩ የእስልምና እምነት ተከታዮችን አመስግነዋል፡፡

መቃኞ

በአካባቢው ነዋሪዎች ትብብር የታነጸው መቃኞ ቤት

በቤተ ክርስቲያኑ ላይ የደረሰውን የቃጠሎ አደጋ ሰበካ ጉባኤው ለፖሊስ ሪፖርት እንዳደረገና በቃጠሎው ዕለትም የሰበታ ወረዳ ኮማንድ ፖስት፣ የጸጥታ ዘርፍ ሠራተኞችና ሌሎችም የመንግሥት ባለሥልጣናት እንደ ተገኙ የተናገሩት አስተዳዳሪው የቃጠሎው መንሥኤ እስኪጣራ ድረስም የደብሩ ሰሞነኛ ካህናትና የጥበቃ ሠራተኞች በሕግ ከለላ ሥር ይገኛሉ ብለዋል፡፡

አማንያንም ኾኑ ኢአማንያን የአካባቢው ነዋሪዎች በጋራ በመረባረብ ለታቦተ ሕጉ መቀመጫ የሚኾን ጊዜያዊ መቃኞ ቤት ማነጻቸውን ያስታወቁት የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ እንደ ገና ታድሶ አገልግሎት ይሰጥ ዘንድም የመላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍና ርዳታ አይለየን ሲሉ በቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪያቸውን ያቀርባሉ፡፡

ትውልዱን ከሱስ ለመታደግ የቤተ ክርስቲያን ሚና

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አማካይነት በተዘጋጀው የዐውደ ጥናት ጉባኤ ታኅሣሥ ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንጻ ፫ኛ ፎቅ አዳራሽ በቀረበው ጥናታዊ ጽሑፍ ከሱስ የነጻ ትውልድ ለመፍጠር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና ከፍተኛ መኾኑ ተገለጸ፡፡

ዶ/ር

ዶክተር ጃራ ሰማ ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ

በጉባኤው ‹‹ከሱስ የነጻ ትውልድ ለመፍጠር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና›› በሚል ርእስ ጥናታዊ ጽሑፋቸውን ያቀረቡት የሕክምና እና የማኅበራዊ ሳይንስ ባለሙያው ዶክተር ጃራ ሰማ የአልኮል መጠጦች፣ አደንዛዥ ዕፀዋት፣ አሽሽ፣ ትንባሆ፣ ሻይ፣ ቡና፣ የለስላሳ መጠጦች፣ ልዩ ልዩ መድኀኒቶችና የመሳሰሉት ልምዶች፤ እንደዚሁም የኢንተርኔት አገልግሎት፤ በተመሳሳይ መልኩ ሰዶማዊነት፣ ወደ ዝሙት ተግባር የሚወስዱ ፊልሞችን በዓይን ማየትና በድምፅ መስማት፣ እንደዚሁም ራስን ለፍትወተ ሥጋ ማነሣሣት በተደጋጋሚና በብዛት ከተወሰዱ ወይም ከተተገበሩ ሱስ ሊያስይዙ እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ሳውና ባዝ፣ ስቲም ባዝና ሞሮኮ ባዝን ጨምሮ ሌሎች የመታሻ ሥፍራዎችና ጂም ቤቶችም ሱስን ሊያስይዙ የሚችሉ የምቾትና የድሎት አገልግሎቶች መኾናቸውን ጥናት አቅራቢው አስረድተዋል፡፡ ሱስ በድርጊት በመፈጸምና በመቅመስ ብቻ ሳይኾን በማየት፣ በመስማት፣ በመዳሰስ ወይም በመንካት እንደሚፈጸም ያስረዱት ጥናት አቅራቢው በማሽተት ከሚፈጸሙ ሱስ አምጪ ተግባራት መካከልም ቤንዚን፣ ትምባሆ፣ ሲጋራና ማስቲሽ የማሽተት ሱስን እንደ ምሳሌ አድርገው አቅርበዋል፡፡

ሱስ የሰውን ልጅ አእምሮውንና አካሉን በአግባቡ የማይጠቀም፤ የፈዘዘ፣ የደነዘዘ እንዲኾን ያደርጋል ያሉት ባለሙያው ሱሰኝነት ትዳር እንዲፈርስ፣ ቤተሰብ እንዲበተን፣ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲላላ፣ የማይታመን ራእይ አየን የሚሉ የሐሰት ባሕታውያን እንዲበዙ፣ ሽብርተኝነት እንዲስፋፋ፣ ወዘተ. በማድረግ ከግለሰብ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያንና በአገር ላይ የሚያደርሰው ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ጉዳት ከፍተኛ መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

የአእምሮ መታወክ፣ ጭንቀትና ውጥረት፣ የአስተዳደግ ችግር፣ የጓደኛ ተፅዕኖ፣ ቤተሰባዊ ግጭት፣ ሴሰኝነት፣ በኑሮ የሚያጋጥም ዕዳና ኪሳራ፣ ሥራ አጥነት፣ ወዘተ የመሳሰሉት አጋጣሚዎች ለሱስ የሚዳርጉ መሠረታዊ ጫናዎች መኾናቸውን ያመላከተው የዶ/ር ጃራ ጥናት ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ፣ የግብረ ገብ ትምህርቶችን በመማርና ሥልጠናዎችን በመውሰድ አመለካከትን መለወጥ (የእይታ አድማስን ማስፋት)፤ እንደዚሁም ማኅበራዊ ግንኙነትን ማሳመርና ሓላፊነትን ማሳደግ ከሱስ የማምለጫ መንገዶች መኾናቸውን ያስረዳል፡፡

tinat

የጥናቱ ታዳሚዎች በከፊል

የሰው ልጅ ከአምላኩ ውጪ በእርሱ ላይ አንዳች ኃይል ሊሠለጥንበት የማይችል በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ከፍጡራን ዅሉ የላቀ ክቡር ፍጥረት መኾኑን በጥናታቸው ያስታወሱት ዶ/ር ጃራ ሰማ የሰው ልጅ ክብሩን አዋርዶ ይሠለጥንባቸው ዘንድ የተሰጡት ፍጥረታት በእርሱ ላይ እንዲሠለጥኑ ከፈቀደ በምድር በኀጢአት አረንቋ ወድቆ እንደሚኖር፤ በዚህም ራሱን እንደሚበድልና የፈጠረውን አምላክም እንደሚያሳዝን ገልጸው ትውልዱ የተፈጠረለትን ዓላማ በመረዳት ወደ ሱስ ከሚወስዱ ነገሮች ራሱን መጠበቅ እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡

ምእመናንን ከልጅነታቸው ጀምሮ በሰንበት ት/ቤት፣ በማኅበር፣ በዐውደ ምሕረት፣ በኅትመት ውጤቶችና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ ግብረ ገብነትን በማስተማር፤ ወደ ሱስ የገቡትንም በሱባዔ፣ በቀኖና፣ በንስሐ፣ በጠበልና በሥጋ ወደሙ አማካይነት ፈውስን እንዲያገኙና በመንፈሳዊውም ኾነ በዓለማዊው ሕይወታቸው ጤናማ ኾነው እንዲኖሩ በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያበረከተችው ሚና ከፍተኛ መኾኑን የጠቀሱት ጥናት አቅራቢው ችግሩን በዘላቂነት ለመከላከል የተዘጋጀ መዋቅራዊ አደረጃጀት ባለመኖሩ፣ ካህናት ከሕክምና ባለሙያዎች ጋር ተቀናጅተው ባለመሥራታቸው፣ ሱሰኞች ከሱስ ከወጡ በኋላ የሚቋቋሙበት ተቋም ባለመመሥረቱ፣ በጉዳዩ ላይ በቂ ጥናትና ምርምር ባለመደረጉ፣ የሚድያ ሽፋን ባለማግኘቱና በጀት ባለመመደቡ የተነሣ ቤተ ክርስቲያናችን ሓላፊነቷን በአግባቡ እንዳትወጣ ካደረጓት ምክንያቶች መኾነቻውን በጥናታቸው ዳሰዋል፡፡

ዶ/ር ጃራ ሰማ በጥናታቸው ማጠቃለያም ‹‹ምእመናን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ብቻ ሳይኾን በማኅበራዊ ኑሯቸውም ከሌሎች ጋር ተስማምተው በፍቅር፣ በቅንነት፣ በሰላምና በአንድነት እንዲኖሩ የማስቻል ከማንም በላይ ከአምላክ ዘንድ የተሰጣት መንጋዋን ከጥፋት የመጠበቅ ከፍተኛ ሓላፊነት እንዳለባት ቤተ ክርስቲያናችን ተገንዝባ የአሠራር ችግሮችን በመቅረፍ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትኩረት ሰጥታ መሥራት ይገባታል›› ብለዋል፡፡

የአዳዲስ አማንያኑ ቍጥር ወደ ሰማንያ አምስት ሺሕ አደገ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

img_0090

በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት በተከናወነው የጥምቀት መርሐ ግብር ከመስከረም እስከ ታኅሣሥ ወር ፳፻፱ ዓ.ም ባለው የአገልግሎት ዘመን በመተከል ሀገረ ስብከት በአምስት ወረዳዎች ውስጥ በሚገኙ ዐሥር የጥምቀት ቦታዎች ስድስት ሺሕ ስምንት መቶ ሃያ አንድ፤ በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዐርባ ምንጭ አካባቢ ሁለት ሺሕ አንድ መቶ ሠላሳ ሰባት፤ በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት በጂንካ አካባቢ አንድ ሺሕ ስልሳ አንድ፤ በሸካ ቤንች ማጂ ሀገረ ስብከት በማጂ ወረዳ ሦስት ሺሕ ስድስት መቶ ሰማንያ ስድስት፤ በድምሩ ዐሥራ ሦስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስት በልዩ ልዩ ጠረፋማ አካባቢዎች የሚኖሩ አዳዲስ አማንያን የሥላሴ ልጅነትን አግኝተዋል፡፡

ይህም ከአሁን በፊት ማኅበሩ ካስጠመቃቸው ሰባ ሁለት ሺሕ አማንያን ጋር ሲደመር የአዳዲስ አማንያኑን ቍጥር ወደ ሰማንያ አምስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስት እንደሚያደርሰው በማኅበሩ የስብከተ ወንጌል ትግበራ ባለሙያ ቀሲስ ይግዛው መኮንን ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡ ከዐሥራ ሦስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስቱ አዳዲስ አማንያን መካከልም ከፊሎቹ ታኅሣሥ ፱፣ ፲፮ እና ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የተጠመቁ ናቸው፡፡

metekel-2

የመተከል ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሰላም ብርሃን ዓለም ጥምቀቱ በተፈጸመበት ዕለት በድባጤ ወረዳ ቤተ ክህነት አልባሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ ‹‹ዛሬ ወላጆች ከልጆቻችሁ ጋር ተጠምቃችኋል፡፡ ከዚህ በኋላ ልጆችን ስትወልዱ ወንዶችን በዐርባ፤ ሴቶችን ደግሞ በሰማንያ ቀናቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን በማምጣት ማስጠመቅ አለባችሁ፤›› በማለት ተጠማቂዎቹን አስተምረዋል፡፡ በማያያዝም ተጠማቂዎቹ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተው፣ ከኀጢአት ተለይተው መኖር እንደሚገባቸው፤ ከዚህም ባሻገር ያልተጠመቁ ዘመዶቻቸውንና ጎረቤቶቻቸውን አስተምረው ወደ ክርስትና ሃይማኖት መመለስ፤ የተጠመቁትንም በሃይማኖትና በምግባር እንዲጸኑ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው ሥራ አስኪያጁ ተጠማቂዎቹን መክረዋል፡፡

በመተከል ሀገረ ስብከት በተካሔደው የጥምቀት መርሐ ግብር ከልዑካኑ ጋር አብረው የተሳተፉት የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ንጉሤ መብራቱ አዳዲስ አማንያንን ማስጠመቅ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚሰጠው አገልግሎት ውስጥ ዐቢዩና ዋነኛው ተግባር መኾኑን አስታውሰው ለአገልግሎቱ ውጤታማነትና ለተጠማቂዎቹ ቍጥር መጨመርም የማኅበሩ አባላትና የበጎ አድራጊ ምእመናን ተሳትፎ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዳለው ተናግረዋል፡፡

metekel-3

የማኅበረ ቅዱሳን የግልገል በለስ ማእከል ሰብሳቢ አቶ አሰፋ ደሳለኝ እና ጸሐፊው አቶ ደግ አረገ አለነ በበኩላቸው ማእከሉ ከመተከል ሀገረ ስብከት ጋር ኾኖ ሰባክያንን በመመደብ፣ ቅኝት በማድረግና በመሳሰሉት ተግባራት አገልግሎቱን በማስተባበር የሚጠበቅበትን ድርሻ መወጣቱን ጠቅሰው ማእከሉ ያለበት የሰው ኃይል፣ የመምህራንና የገንዘብ እጥረት፣ እንደዚሁም የጥምቀት መርሐ ግብሩ የሚፈጽምባቸው ቦታዎች ርቀትና ለአገልግሎት ምቹ አለመኾን አዳዲስ አማንያንን የማስጠመቁን ተልእኮ ከሚፈታተኑ ችግሮች መካከል ዋነኞቹ መኾናቸውን ጠቁመዋል፡፡

በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመስጠት ላይ ከሚገኙ ሰባክያነ ወንጌል መካከል ዲያቆን ቶማስ ጐሹ እና ወንድም ፈጠነ ገብሬ ተጠማቅያኑ ቀደምት አባቶቻቸው ለዚህ ክብር ሳይበቁ በማለፋቸው እንደሚቈጩና የክርስትና ጥምቀትን ለማግኘት ሲሉም ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ጀምረው በእግራቸው እንደ ተጓዙ ገልጸው የጉሙዝ ብሔረሰብ አባላት የቃለ እግዚአብሔር ጥማት እንዳለባቸውና ‹‹ልጆቻችንን የቄስ ትምህርት አስተምሩልን?›› እያሉ እንደሚጠይቋቸውም አስረድተዋል፡፡

ወደ ፊትም ሰንበት ት/ቤቶችን በየቦታው በማቋቋም ተጠማቅያኑ በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ለማድረግ ዕቅድ ቢኖራቸውም ነገር ግን ሰባክያነ ወንጌል በብዛት አለመመደባቸው፣ ቢመደቡም የሚከፈላቸው የድጎማ ገንዘብ አነስተኛ መኾኑ፣ ሞተሮቻቸው ሲበላሹባቸው የሚያስጠግኑበት በጀት አለመኖሩ፣ እንደዚሁም የአካባቢው መናፍቃን ተጽዕኖ መበራከቱ ‹‹አገልግሎታችንን በአግባቡ እንዳንወጣ አድርጎናልና መፍትሔ እንፈልጋለን›› ሲሉ የድጋፍ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡

metekel-2

ከተጠማቅያን የጉሙዝ ብሔረሰብ አባላት መካከል አንደኛው ለዚህ ታላቅ ክብር ስላበቃቸው እግዚአብሔርን ካመሰገኑ በኋላ ‹‹አጥምቃችሁን መመለስ ብቻ ሳይኾን ለወደ ፊትም አስተማሪ፣ መካሪ ካህን አጥተን ወደ ሌላ ቤተ እምነት እንዳንወሰድ እየመጣችሁ በመምከር፣ በማስተማርና በማበረታታት በሃይማኖታችን እንድንጸና ድጋፍ አድርጉልን፤›› ሲሉ የድረሱል ድምፃቸውን ያሰማሉ፡፡ ሌላኛው ተጠማቂ ወንድምም እንደዚሁ ራሳቸውን ጨምሮ ዐሥራ አራት የቤተሰቡ አባላት በሙሉ በአንድ ቀን መጠመቃቸውን አውስተው ‹‹ያልተጠመቁ ዘመዶቼና ወዳጆቼንም ተምረው የሥላሴን ልጅነት እንዲያገኙ አደርጋለሁ›› ብለዋል፡፡

የማኅበሩ ጋዜጠኞችም በመተከል ሀገረ ስብከት ልዩ ልዩ ቦታዎች ታኅሣሥ ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በተካሔደው የጥምቀት መርሐ ግብር በተሳተፍንበት ወቅት በድባጤ ወረዳ ቤተ ክህነት በአልባሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የአዊ ብሔረሰብ ተወላጆች ተጠማቂ የጉሙዝ ብሔረሰብ ተወላጆችን ክርስትና በማንሣት በሚያስፈልጋቸው መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጉዳይ ዅሉ ከጎናቸው እንደማይለዩ ቃል በመግባት ዝምድናቸውን ሲያጠናክሩና አንድነታቸውን ሲያጸኑ ተመልክተናል፡፡

img_0143በግል መኪኖቻቸው ልዑካኑን በመያዝ በጉዞው የተሳተፉ ወንድሞችም ከአሁን በፊት ብዙ ቦታዎችን እንደሚያውቁ፤ ነገር ግን እንደዚህ ዓይነት አስቸጋሪ መንገድ እንዳላጋጠማቸውና መንገዱም ከጠበቁት በላይ ለመኪናዎቻቸው አስቸጋሪ እንደ ነበረ ገልጸው ማኅበሩ የሚሰጠውን አገልግሎት በመመልከት በመንፈሳዊ ቅናት ተነሳሥተው ብዙ ውጣ ውረዶችን በመቋቋም ተልእኳቸውን ተወጥተው መመለሳቸውን ተናግረዋል፡፡ ባለ መኪኖቹ ‹‹መንፈሳዊ ጉዞው ወደ ፊት የሚጠበቅብንን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ለመወጣት እንድንዘጋጅ አድርጎናል›› ሲሉም ቃል ገብተዋል፡፡

የጥምቀት መርሐ ግብሩን ለማስተባበር በየጠራፋማ አካባቢዎች ተሰማርተው ለነበሩ የማኅበረ ቅዱሳን ልዑካንም የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚ አባላት፣ የልዩ ልዩ ዋና ክፍሎች አገልጋዮችና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት በማኅበሩ ሕንጻ ፮ኛ ፎቅ አዳራሽ የእንኳን ደኅና መጣችሁ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

በዕለቱ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በምቹ ኹኔታዎች የሚፈጸም ተግባር ሳይኾን ፈተና የበዛበት ተልእኮ መኾኑን ገልጸው ልዩ ልዩ ፈተናዎችም ማኅበሩ መንፈሳዊ ተልእኮውን በአግባቡ እንዲወጣ ስላደረጉት በሺሕ የሚቈጠሩ ኢአማንያን የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ለማድረግ መቻሉን አስረድተዋል፡፡

metekel

‹‹በጠረፋማ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በልዩ ልዩ ቋንቋ ወንጌልን የሚሰብኩ መምህራን የሕይወት መጻሕፍት ናቸውና ዅላችንም ልንማርባቸው ይገባል፤›› ያሉት ዋና ጸሐፊው በጸሎት፣ በስብከት፣ በማስተባበር፣ በገንዘብ ድጋፍ፣ በጉልበት ሥራና በመሳሰሉት ተግባራት በመሳተፍ ለአማንያኑ መጠመቅ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከቱ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን፣ መምህራንና ካህናትን፣ እንደዚሁም በጎ አድራጊ ምእመናንን በማኅበሩ ስም አመስግነዋል፡፡

ከሥራ አመራር አባላት መካከል አንደኛው ከፈጸምነው ተልእኮ ይልቅ ገና ያልሠራነው ብዙ ተግባር እንደሚበልጥ በመገንዘብና ምእመናንን ከቤታቸው ለማስወጣት ተግተው የሚሠሩ አካላት በየቦታው እንደሚገኙ በመረዳት ወደ ፊት ለሚጠበቅብን ዘርፈ ብዙ ሥራ መዘጋጀት ተገቢ መኾኑን አስረድተዋል፡፡

አያይዘውም በጥምቀት መርሐ ግብሩ የተሳተፉ መምህራን፣ ጋዜጠኞች፣ የካሜራ ባለሙያዎች፣ ሹፌሮችና ሌሎችም የልዑካኑ አባላት በአገልግሎቱ መሳተፋቸው ምስጋና ለማግኘት ሳይኾን እናት ቤተ ክርስቲያናቸውን በተሰማሩበት የሥራ ዘርፍ ለማገልገል እና ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን ለመወጣት መኾኑን ሊረዱት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

metekel

ተጠማቂዎቹ እንዳይበተኑና በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ለማድረግ በጠረፋማ አካባቢዎች አብያተ ክርስቲያናትን ማሳነጽ፣ በየቋንቋው የሚሰብኩ መምህራንና ካህናትን ቍጥር ማሳደግ፣ የትምህርተ ሃይማኖት መማሪያ መጻሕፍትን በየቋንቋው ማዘጋጀት፣ አዳሪ ት/ቤቶችንና ሰንበት ት/ቤቶችን በየቦታው ማቋቋም፣ የስብከት ኬላዎችን ማስፋፋትና ለተጠማቅያኑ አስፈላጊውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ ማድረግ ለወደፊቱ በማኅበሩ ሊሠሩ የታቀዱ ተግባራት መኾናቸውን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ምክትል ሓላፊ አቶ ሰይፈ አበበ ጠቅሰው ይህንን ዕቅድ ከግብ ለማድረስም የበጎ አድራጊ ምእመናን ተሳትፎ እንዳይለያቸው በማኅበሩ ስም መንፈሳዊ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

ሰማንያ አምስት ሺሕ ኢአማንያንን የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንዲኾኑ ማድረግ ታላቅ ተልእኮ ቢኾንም ከዚህ የበለጠ መትጋት ከኹላችንም የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡ መላው ሕዝበ ክርስቲያን በአንድነት ኾነን ተባብረን ከሠራን ከዚህ በላይ ቍጥር ያላቸው ኢአማንያንን ለማስጠመቅና ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን ይበልጥ ለማስፋፋት እንደሚቻል ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ስለዚህም በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም (መርሐ ግብር) ለሚሠሩ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች መሳካት የበጎ አድራጊ ምእመናን ድጋፍ እንዳይለየን ሲል ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ከሃያ አምስት በላይ የግብጽ ምእመናን በቦምብ ፍንዳታ ሕይወታቸው ዐለፈ

news

ታኅሣሥ ፫ ቀን ፳፻፱ .

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በግብጽ ካይሮ ከተማ እሑድ ታኅሣሥ ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ረፋድ ላይ ከቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል አጠገብ በሚገኘው የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በደረሰ የቦምብ ፍንዳታ ከሃያ አምስት በላይ የግብጽ ምእመናን ሕይወታቸው ዐለፈ፡፡

ፍንዳታው የደረሰው በሴቶች መቆሚያ በኩል መኾኑን ከግብጽ አካባቢያዊ የመረጃ አውታሮች ለመረዳት ተችሏል፡፡

በጥቃቱ ዐርባ ዘጠኝ ሰዎች መቍሰላቸውንና ከእነዚህ መካከልም አብዛኞቹ ሴቶች መኾናቸውን የግብጽ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር አሕመድ ኢማድ ተናግረዋል፡፡ እንደ ጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ መግለጫ ከቍስለኞቹ መካከል ሦስቱ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡

egypt-7

ጕዳቱ ለደረሰባቸውና ሕክምና ላይ ለሚገኙት ቍስለኞች የደም ልገሳ እንዲደርግላቸው በማኅበራዊ ሚድያዎች አማካይነት የግብጽ ሆስፒታሎች ጥሪ ማቅረባቸውም ታውቋል፡፡

በፍንዳታው ምክንያት በግብጻውያን ምእመናን ላይ ለደረሰው ሞትና ጉዳት አገሪቱ የሦስት ቀን ኀዘን እንደምታውጅ የግብጽ ፕሬዚዳንት አብደል ፈታሕ አል ሲሲ አስታውቀዋል፡፡

ለድርጊቱ ሓላፊነቱን የወሰደ አካል ግን እስካሁን ድረስ አልተገኘም፡፡

fun-5

በፍንዳታው ሕይወታቸው ያለፈ ምእመናን ሥርዓተ ቀብርም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዎድሮስ ካልዕ መሪነት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና ብዙ ሺሕ የግብጽ ምእመናን በተገኙበት ታኅሣሥ ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በግብጽ ቅድስት ማርያም እና ቅዱስ አትናቴዎስ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡

ምንጭ፡

Orthodoxy Cognate PAGE – Media Network

http://www.dailynewsegypt.com

http://english.ahram.org.eg

ጽላተ ሕጉ ወደ ቤተ ክርስቲያን ተመለሰ

ኅዳር ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በይብረሁ ይጥና

st-mic

ከግራ ወደ ቀኝ፡- ቅዱስ ሚካኤል፣ መንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ደብር እና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጥናትና ምርምር ተቋም ሙዚየም ውስጥ የተገኘው የቅዱስ ሚካኤል ጽላት ወደ ቤተ ክርስቲያን ተመለሰ፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት የቅርስ ጥበቃ፣ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ ሓላፊ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ እንዳስታወቁት፤ ጽላቱ ወደ ፊት ለብቻው ቤተ ክርስቲያን እስኪታነጽለት ድረስ ኅዳር ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን በአደራ መልክ እንዲቀመጥ ተደርጓል፡፡

‹‹ጽላቱ መቼ፣ እንዴትና በማን አማካይነት ወደ ዩኒቨርስቲው ሊገባ ቻለ?›› ለሚለው ጥያቄአችን መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ምላሽ ሲሰጡም ‹‹ከየትና እንዴት እንደገባ የሚገልጥ ማስረጃ ባይገኝም ሰኔ ፲፪ ቀን ፲፱፻፶፫ ዓ.ም ሚስተር እስቲፈን ሮቶ በተባለ ግለሰብ ወደ ዩኒቨርስቲው እንደገባ ከዩኒቨርስቲው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፤›› ብለዋል፡፡ አያይዘውም ጽላቱ በዐፄ ኃይለ ሥላሴና በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ዘመን የነበረ መኾኑ ከጽላቱ ላይ ተጽፎ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

እንደ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ማብራሪያ ለጽላቱ መገኘትና ወደ መንበሩ መመለስ መነሻ የኾነው አቶ በለጠ ዘነበ የተባሉ የ፹ ዓመት አረጋዊ የተመለከቱት ራእይና ያደረጉት ጥረት ነው፡፡ እኒህ አባት ‹‹የቅዱስ ሚካኤል ጽላት በዩኒቨርሲቲው ሙዚየም ውስጥ ተቀብሮ ይገኛልና መውጣት አለበት›› በማለት በተደጋጋሚ መምሪያውን ሲያሳስቡ እንደነበረ ያስታወሱት መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን በልዩ ልዩ ጊዜያት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ለዩኒቨርሲቲው የተጻፉ ደብዳቤዎችን መሠረት በማድረግ ጽላቱ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመለስ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

በመጨረሻም የቅዱስ ሚካኤል ጽላት ለቤተ ክርስቲያናችን እንዲመለስ ጥረት ላደረጉትና ለተባበሩት ለአቶ በለጠ ዘነበ፣ ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ለመንግሥት አካላት በሙሉ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ በቤተ ክርስቲያን ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ንስሐን በአስተርጓሚ

ጥቅምት ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

dscn0116

ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር ጥቅምት ፳ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንጻ ፮ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ሲያካሒድ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ተገኝተው ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ በጠረፋማ አካባቢዎች የሚገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በቋንቋቸው የሚያስተምሯቸውና ንስሐ የሚሰጧቸው ሰባክያነ ወንጌልና ካህናት በብዛት እንደሚያስፈልጓቸው ገለጹ፡፡

‹‹እኛ ኢትዮጵያውያን ዕድለኞች ነን፤ እንደ ሰባቱ ኅብረ ቀለማት መልካችን ዝጕርጕር ነው›› ያሉት ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ኢትዮጵያ የብዙ ብሔረሰብና ቋንቋ መገኛ መኾኗን አድንቀው በኢትዮጵያ ጠረፋማ አካባቢዎች የሚገኙ አብዛኞቹ ምእመናን ከአባቶች ካህናት ጋር በቋንቋቸው መግባባት ባለመቻላቸው ንስሐ የሚቀበሉት በአስተርጓሚ በመኾኑ ምእመናኑ ኀጢአታቸውን ሰው እንዳይሰማባቸው ሲሉ ለአስተርጓሚዎች በአግባቡ ላይናገሩ እንደሚችሉ፣ ይህም ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት መሰናክል እንደሚኾን በአንዳንድ የሀገረ ስብከታቸው አካባቢዎች የሚታዩ ችግሮችን እንደ ምሳሌ በመጥቀስ አስገንዝበዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ቀደም ሲል እንደ ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ያሉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች በየጠረፋማ አካባቢዎች በእግራቸው እየተዘዋወሩ ወንጌልን በመስበክ ያጠመቋቸው ብዙ ሺሕ ምእመናን ቢኖሩም ነገር ግን በቋንቋቸው ወንጌልን የሚሰብኩላቸውና ንስሐ የሚሰጧቸው መምህራንና ካህናት ባለመገኘታቸው የተነሣ ወደ ሌላ እምነት እየተወሰዱ መኾናቸውን ተናግረዋል፡፡

‹‹በጠረፋማው የአገራችን ክፍል የሚኖሩ ወገኖች የሚጠይቃቸው አጥተዋልና ልንደርስላቸው ይገባል›› የሚሉት ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ አብያተ ክርስቲያናትን፣ ማሠልጠኛ ተቋማትንና የአብነት ትምህርት ቤቶችን በየቦታው በማስፋፋት በልዩ ልዩ ቋንቋ ማስተማር የሚችሉ ሰባክያነ ወንጌልንና ካህናትን ማሠልጠን ለዚህ ዅሉ ችግር መፍትሔ እንደሚኾን ጠቁመዋል፡፡

new

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

በዕለቱ ‹‹ዘፀአት›› በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል የሰጡት ዲያቆን ብርሃኑ አድማስም የእስራኤላውያንን ከግብጽ ባርነት ነጻ የመውጣት ታሪክ መነሻ አድርገው እያንዳንዱ ምእመን በፈቃዱ ከተያዘበት የሕሊና  ባርነት ነጻ በመውጣት ራሱን ከጥፋትና ከኑፋቄ ከመጠበቅ ባሻገር ሌሎችንም ወደ ክርስትና ሃይማኖት በመመለስ ክርስቲያናዊ ግዴታውን መወጣት እንደሚኖርበት አስተምረዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ አቶ ታምሩ ለጋ በበኩላቸው ማኅበሩ ከአሁን በፊት አዳዲስ አማንያንን በማስጠመቅ፣ አብያተ ክርስቲያናትን በማስገንባትና ሰበክያነ ወንጌልን በማሠልጠን በጠረፋማ አካባቢዎች ላከናወናቸው ተግባራት ዅሉ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ የሚገኙ አባቶች በጸሎትና በምክር፤ በጎ አድራጊ ምእመናን በዐሳብ፣ በቍሳቍስ አቅርቦት፣ በገንዘብና በጕልበት ላደረጉት ዕገዛና ድጋፍ ምስጋናቸውን በእግዚአብሔር ስም ካቀረቡ በኋላ ማኅበሩ ለወደፊቱ በሰፊው ዐቅዶ ለሚተገብረው የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብርም ምእመናን ከጎኑ እንዲቆሙ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በተያያዘ ዜና ጥቅምት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ባዘጋጀው ልዩ መርሐ ግብር ገዳማትንና የአብነት ትምህርት ቤቶችን መደገፍ ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለመርዳት ስለሚያስችል ዅሉም ሕዝበ ክርስቲያን የበኩሉን ድርሻ ቢወጣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስቀጠልና የመናፍቃንን ተጽዕኖ መግታት እንደሚቻል ተገልጿል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ‹‹የነገራችሁኝ ሽማግሌ አባታችሁ ደኅና ነውን?›› /ዘፍ.፵፫፥፳፯/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል የሰጡት ዲያቆን ሄኖክ ኀይሌ የቅዱሳን አባቶችን ሕይወታቸውንና የትሩፋት ሥራቸውን በማስረዳት ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ቅዱሳት መካናትንና አብነት ትምህርት ቤቶችን መከባከብና መጠበቅ ተገቢ ተግባር መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

ድረ ገጾችን በስፋት ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት መጠቀም እንደሚገባ ጥናቶች አመለከቱ

ጥቅምት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን ባዘጋጀው አዲስ ስልታዊ ዕቅድ የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን የበለጠ ለማጠናከርና ከባለድርሻ አካላት ጋር እንዴት በቅንጅት ተቀራርቦ መሥራት እንደሚቻል የሚያመለክቱ ጥናታዊ ጽሑፎች መስከረም ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በማኅበሩ አዳራሽ ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በጥናቶችም ማኅበራዊ ድረ ገጾችን በስፋት ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት መጠቀም እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡

dscf6211

ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ

በዐውደ ጥናቱ ‹‹ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮን ለማስፋፋት ፈታኝና ምቹ ኹኔታዎች›› በሚል ርእሰ ጉዳይ ጥናት ያቀረቡት ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዘመናቱ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ስትሰጥ ብትቆይም ከ፲፱፻፹-፲፱፻፺ ዓ.ም የነበራት ሐዋርያዊ አገልግሎት ይበልጥ የተጠናከረ እንደ ነበረ ጠቅሰው ለዚህም በወቅቱ የሰባክያነ ወንጌል ቍጥር መጨመር፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አገልግሎት መስፋፋትና ምእመናን ስለ ሃይማኖታቸው ለማወቅ ያላቸው ፍላጎት ከፍተኛ መኾን የመሳሰሉት ጉዳዮች ለሐዋርያዊ አገልግሎት መፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ገልጠዋል፡፡

ዲ/ን ያረጋል አያይዘውም ኦርቶዶክሳዊ መንፈስና መረዳት ያላቸውን ሰባክያነ ወንጌል በብዛት በመመደብ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርት መስጠት የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ወደተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር እንደሚያስችል አስረድተዋል፡፡

dscf6257

ዲያቆን ዶ.ር ቴዎድሮስ

‹‹በስብከተ ወንጌል የአኃት አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ›› በሚል ርእስ ባዘጋጁት ጥናታቸው የመጀመሪያዎቹን ሦስቱን ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤያት የሚቀበሉ ኦሬንታል (አኀት) አብያተ ክርስቲያናት እንደሚባሉ ያስታወሱት ዲያቆን ዶክተር ቴዎድሮስ በለጠ ደግሞ ስብከተ ወንጌልን አጠናክሮ ለመቀጠል መልካም አጋጣሚዎችንና ተግዳሮቶችንም በጥናታቸው ዘርዝረዋል፡፡

‹‹የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ተግዳሮቶችና መልካም አጋጣሚዎች›› በሚል ርእስ ጥናት ያቀረቡት አቶ ፋንታኹን ዋቄ በበኩላቸው እምነታቸውን በሕይወት የሚገልጡ ምእመናን መበራከት፣ የምእመናን መንፈሳዊ ሕይወት መጠናከር፣ የጉባኤ ቤት መምህራን እነሱን አክለውና መስለው የሚያገለግሉ ሊቃውንትን መተካትና የአፅራረ ቤተ ክርስቲያንን እንቅስቃሴ መግታት መቻል የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት መጠናከር መገለጫዎች መኾናቸውን ገልጠዋል፡፡

dscf6302

አቶ ፋንታኹን ዋቄ

‹‹የኦርቶዶክሳዊ ምእመን ተልእኮ ራስን መጠበቅ፣ ሌሎችን መጠበቅና በሌሎች ለመጠበቅ ፈቃደኛ መኾን ነው›› ያሉት አቶ ፋንታኹን አያያይዘውም የዓለም የዕውቀት ዐውድ ኢክርስቲያናዊ በኾኑ አካላት እንደተቃኘና ቴክኖሎጂውን ለጥፋትም ኾነ ለልማት መጠቀም እንደሚቻል ጠቅሰው ጊዜውን በቍሳዊ ነገር መለካትና ለመንፈሳዊ ሕይወት ትኵረት አለመስጠት በብዙዎች ዘንድ እንደሚስተዋል ተናግረዋል፡፡ ለዚህም መፍትሔው የስብከተ ወንጌል አገልጋዮችን በብዛትም በጥራትም በማፍራት ምእመናንን ከጥፋት መጠበቅ መኾኑን በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡

‹‹ስብከተ ወንጌልን ከማስፋፋት አንጻር የማኅበራዊ ድረ ገጾች አስተዋጽዖ›› የሚለው ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ አቶ ነጻነት ተስፋዬም ማኅበራዊ ድረ ገጾች የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ከቦታ ቦታ ሳይንቀሳቀሱ ወንጌልን እንዲያስተምሩ፤ ምእመናንም ባሉበት ቦታ ኾነው እንዲማሩ የሚያስችሉ መሣሪያዎች መኾናቸውን አስገንዝበዋል፡፡

አቶ ነጻነት ጥንታዊቷና ታሪካዊቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበራዊ ድረ ገጾችን በተፈለገው መጠን እየተጠቀመች አለመኾኗን በማስታዎስ ማኅበራዊ ድረ ገጾችን በመጠቀም ለቤተ ክርስቲያን ተቆርቋሪና ለአገር አሳቢ ትውልድ ማፍራት እንደሚቻል አመላክተዋል፡፡

dscf6182

አቶ ነጻነት ተስፋዬ

በቤተ ክርስቲያን ወጥ የኾነ የድረ ገጽ አጠቃቀምና ተቋማዊ አደረጃጀት አለመኖር፣ የሃይማኖት አባቶች በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ያላቸው ግንዛቤ አነስተኛ መኾን፤ የአፅራረ ቤተ ክርስቲያን የቅሰጣ መልእክት፤ ማኅበራዊ ሚዲያውን የጥፋት መሣሪያ ብቻ አድርጎ ማሰብና የመሳሰሉት ችግሮች ማኅበራዊ ድረ ገጾችን ስንጠቀም ከሚገጥሙን መሰናክሎች መካከል እንደሚጠቀሱ አቶ ነጻነት አስገንዝበው የማኅበራዊ ድረ ገጾችን አጠቃቀም ከፍ ለማድረግም የአስተሳሰብ ለውጥ ማምጣት፤ የሌሎች አብያተ ክርስቲያናትን ልምድ መውሰድ፤ በስብከተ ወንጌል ላይ ብቻ ያተኰረ ትምህርት መስጠት፤ ሰባክያነ ወንጌል፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶችና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች የራሳቸው ድረ ገጽ እንዲኖራቸውና የእርስ በእርስ ግንኙነት እንዲፈጥሩ ማድረግ አስፈላጊ መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

በመጨረሻም ማኅበራዊ ድረ ገጾች ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ዓይነተኛ ሚና እንዳላቸው ኹሉ በአግባቡ ካልተጠቀምንባቸው ደግሞ የሚያስከትሉት ጉዳት ከፍተኛ ስለሚኾን ጉዳታቸውን ከጥቅማቸው በመለየት መጠቀም እንደሚገባ አቶ ነጻነት አስታውሰዋል፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ከጥቅምት ፲፮-፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም፤ ገጽ ፩ – ፪፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በዜማ መሣሪያዎችና በልሳነ ግእዝ ያሠለጠናቸውን ፭፻፶ ተማሪዎች አስመረቀ

ጥቅምት ፲፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በይብረሁ ይጥና

mireqa

ከምሩቃኑ መካከል ከፊሎቹ

በማኅበረ ቅዱሳን የልማት ተቋማት አስተዳደር ሥር የሚገኘው የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርትና ሥልጠና ማእከል ለ፲፪ኛ ጊዜ በዜማ መሣሪያዎችና በልሳነ ግእዝ ያሠለጠናቸውን ፭፻፶ ተማሪዎች ጥቅምት ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በማኅበሩ አዳራሽ አስመረቀ፡፡

በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ለምሩቃኑ የእንኳን ደስ ያላችሁ መልእክት ካስተላለፉ በኋላ ‹‹ኹላችሁም እዚህ የተሰበሰባችሁት እግዚአብሔርን ለማገልገል ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ አገር ሰላም ሲኾን ነው፡፡ በመኾኑም እግዚአብሔር ለአገራችን ሰላሙን፣ ፍቅሩንና ቸርነቱን እንዲሰጥልን ተግተን ልንጸልይ ያስፈልጋል›› በማለት ተናግረዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የአገር ውስጥ ማእከላት ሓላፊና የማኅበሩ ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ሰይፈ ዓለማየሁ በበኩላቸው የማኅበሩ ተቀዳሚ ዓላማ የቤተ ክርስቲያንን ትውፊት ሳይበረዝና ሳይከለስ ጠብቆ በማቆየት ለተተኪው ትውልድ ማስተላለፍ መኾኑን ጠቅሰው ‹‹እናንተ ተመራቂዎችም የዚሁ ዓላማ አካል በመኾናችሁ የተማራችሁትን ትምህርት ለሌሎችም ማስተላለፍ አለባችሁ›› ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የትምህርትና ሥልጠና ማእከሉ ከ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ከ፴፻ (ሦስት ሺሕ) በላይ ምእመናንን በመንፈሳውያን የዜማ መሣሪያዎችና በልሳነ ግእዝ በማሠልጠን ለአገልግሎት እንዲበቁ ማድረጉን በማኅበረ ቅዱሳን የልማት ተቋማት አስተዳደር ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ዲያቆን ጌትነት ፍቅሬ ገልጸው በዚህ ዓመትም በበገና ድርደራ ፫፻፶፰፣ በከበሮ አመታት ፹፱፣ በመሰንቆ ቅኝት ፴፭ እና በዋሽንት ድምፅ አወጣጥ ፮፣ እንደዚሁም በልሳነ ግእዝ ፷፪ በድምሩ ፭፻፶ ተማሪዎችን አሠልጥኖ ጥቅምት ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ማስመረቁን አስታውቀዋል፡፡

ከበገና ተመራቂዎች መካከል ጋዜጠኛ መስከረም ጌታቸውና የሕክምና ተማሪዋ ቤቴል ደጀኔ በገናን ለመማር ምን እንዳነሣሣቸው ለዝግጅት ክፍላችን ሲገልጹ የበገና መሣሪያ እግዚአብሔር ከሚመሰገንባቸው መንፈሳውያን የዜማ መሣሪያዎች መካከል አንደኛው ቢኾንም እንደ መንፈሳዊ ሀብትነቱና እንደ ሀገራዊ ቅርስነቱ ትኵረት ሳይሰጠው መቆየቱን ጠቅሰው ‹‹ቅርሶቻችንን መጠበቅና ማስጠበቅ የምንችለው በትምህርት በመኾኑ በገና ድርደራ ልንማር ችለናል›› ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

በመጨረሻም ለአጋዥ ድርጅቶች፣ ለመምህራንና ለምሩቃኑ በልማት ተቋማት አስተዳደር ዋና ማኔጅንግ ዳይሬክተር አቶ ኀይሉ ፍሥሐ የምስክር ወረቀት ከተበረከተ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ቃለ ምዕዳንና ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

፴፭ኛው የሰበካ መንፈሳዊ አጠቃላይ መደበኛ ጉባኤ ተፈጸመ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጥቅምት ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

35

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ከጥቅምት ፯ – ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ለአራት ቀናት ሲካሔድ የቆየው ፴፭ኛው የሰበካ መንፈሳዊ አጠቃላይ መደበኛ ጉባኤ ተፈጸመ፡፡

በጉባኤው ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅና የየመምሪያ ሓላፊዎች፣ በመላው ዓለም የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት አህጉረ ስብከት ተወካዮች፣ የአድባራና ገዳማት አስተዳዳዎች፣ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ የመንግሥትና የግል መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞች፣ እንደዚሁም ጥሪ የተደረገላቸው የአገር ውስጥና የውጪ አገር እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

በፓትርያርኩ ርእሰ መንበርነት፣ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ መሪነት የተካሔደው ይህ ታላቅ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ጥቅምት ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በቅዱስ ፓትርያርኩና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጸሎተ ቡራኬ ከተከፈተበት ጊዜ ጀምሮ በቅዱስ ፓትርያርኩና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ቃለ በረከት ተሰጥቷል፤ እንደዚሁም የኹሉም አህጉረ ስብከትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ ክፍሎች ሪፖርቶች ቀርበዋል፡፡

በጉባኤው መክፈቻ ዕለት ‹‹እንዘ አልብነ ኵሉ ብነ፤ ምንም የሌለን ስንኾን ኹሉ የእኛ ነው፤›› /፪ኛ ቆሮ.፮፥፲/ የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ በማድረግ ቃለ በረከት የሰጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ‹‹… እኛ ካህናት ኹሌም መጨነቅ ያለብን ስለ ሀብት ሳይኾን ስለ ምእመናን ጥበቃ ነው፡፡ ምእመናን ካሉ ሀብቱ አለና፡፡ ከኀምሳ ሚሊዮን በላይ ምእመናን ካሉንና በእነርሱ ላይ ተገቢ ጥበቃና አገልግሎት ካበረከትን የሚጐድልብን አንዳች ነገር አይኖርም፡፡ የሰበካ ጉባኤ ዐቢይ ተልእኮም ይኸው ነው፡፡ ሰበካ ጉባኤ እኛ ካህናት ሀብታሞች መኾናችንን ያረጋገጠ ወንጌላዊ መሣሪያ እንደ ኾነ ከቶዉኑ ልንዘነጋ አይገባም …›› ብለዋል፡፡

ቃለ ቡራኬያቸውን ሲያጠቃልሉም ‹‹… ሌት ተቀን በመሥራት ምእመናንን እንደ እግዚአብሔር ቃል በመጠበቅና በመንከባከብ እንደዚሁም የሚጠበቅብንን መልካም ሥነ ምግባር ኹሉ ለምእመናን በማድረግ የቤተ ክርስቲያናችንን ዕድገትና ሉዓላዊ ክብር እስከ መጨረሻው እንድናረጋግጥ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን›› ሲሉ አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ የመምሪያዎችንና የድርጅቶችን የ፳፻፰ ዓ.ም የሥራ ዘመን ሪፖርት ለጉባኤው ያቀረቡ ሲኾን በድምፅ የተዘጋጀው መጽሐፍ ቅዱስ በቅዱስ ፓትርያኩ ቡራኬ መመረቁ፣ በአፋን ኦሮሞ የተዘጋጀው መጽሐፈ ቅዳሴ አገልግሎት ላይ መዋሉ፣ የ፳፬ ሰዓት የቴሌቭዥን ሥርጭት መጀመሩና በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች አብያተ ክርስቲያናት መታነጻቸው በሪፖርቱ ውስጥ ከተካተቱ ተግባራት መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

ከዚሁ ኹሉ ጋርም ማኅበረ ቅዱሳን ለአብነት መምህራንና ተማሪዎች ወርኃዊ የገንዘብ ድጎማና የቀለብ ድጋፍ ማድረጉ፤ በልዩ ልዩ አህጉረ ስብከት የአብነት ት/ቤቶችን፣ ዘመናዊ ት/ቤቶችንና የገቢ ማስገኛ ሕንጻዎችን ማስገነባቱ፤ እንደዚሁም በኢትዮጵያ በሚገኙ ፬፻፮ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚማሩ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን በትምህርተ ወንጌል አሠልጥኖ ማስመረቁ፤ በደቡብ ኦሞ፣ በመተከልና በጋሞ ጎፋ አህጉረ ስብከት በድምሩ ዐሥራ ስምንት ሺሕ አምስት መቶ ሰባ ስምንት አዳዲስ አማንያንን አስተምሮ የሥላሴ ልጅነትን ማሰጠቱ፤ አዳዲስና ነባር የኅትመት ውጤቶችን አሳትሞ ማሠራጨቱ፤ በተጨማሪም ማኅበሩ በበጀት ዓመቱ በዕቅድ ያከናወነው ተግባርና ያኘው ገቢ ከነወጪና ቀሪው በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ሪፖርት ተገልጿል፡፡

ከአህጉረ ስብከት ሪፖርች መካከል የጋምቤላ ሀገረ ስብከት በአካባቢው ቋንቋ ወንጌልን በማስተማር የሥላሴን ልጅነት እንዲያገኙ ያደረጋቸውን የአካባቢው ተወላጅ የኾኑ የመንግሥት ሠራተኞችን በጉባኤው እንዲሳተፉ ማድረጉ በጉባኤው ተሳታፊዎች ዘንድ የተደነቀና እንደ ተሞክሮ የሚወሰድ ተግባር መኾኑ ታውቋል፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው በተከፈተበት ዕለት በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አቅራቢነት በምልአተ ጉባኤው በተመረጡ ቃለ ጉባኤ አርቃቂ አባላት አማካይነት ባለ ፳ ነጥብ የጋራ ዓቋም መግለጫ የተዘጋጀ ሲኾን በቅዱስ ሲኖዶስና በቅዱስ ፓትርያኩ የሚወጡ ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችን መተግበር፣ በሕገ ቤተ ክርስቲያን መመራትና ሕግጋቱን ማስፈጸም፣ መንፈሳዊ አስተዳርን በማስፈንና ዘመናዊ ሒሳብ አያያዝን በመጠቀም ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል፣ የሕገ ወጥ ሰባክያንንና የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ መግታት፣ ለአብነት ት.ቤቶች ትኩረት መስጠት፣ ወጣቱ ትውልድ ቤተ ክርስቲያንን እንዲረከብ በትምህርተ ወንጌል አእምሮውን መገንባት፣ የተማረ የሰው ኀይልን የሚያካትቱ ተቋማትን ማስፋፋት፣ ወዘተ የመሳሰሉት ተግባራት በዓቋም መግለጨው ውስጥ ከተጠቀሱ ነጥቦች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

በጉባኤው ማጠቃለያ ጥቅምት ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቅዱስነታቸውን ጨምሮ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስና ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ቃለ በረከትና ትምህርተ ወንጌል ከሰጡ በኋላ ላለፉት ሦስት ዓመታት ጠቅላይ ቤተ ክህነትን በዋና ሥራ አስኪያጅነት፣ ቅዱስ ሲኖዶስን በዋና ጸሐፊነት ለመሩት ለብፁዕ አቡነ ማቴዎስና ለብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ እንደዚሁም በበጀት ዓመቱ የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ አህጉረ ስብከት የምስጋና የምስክር ወረቀትና ሽልማት ከቅዱስ ፓትርያርኩ ተበርክቶላቸዋል፡፡

በመጨረሻም የሰበካ መንፈሳዊ አጠቃላይ ጉባኤው በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያኩ ጸሎተ ቡራኬ ተፈጽሟል፡፡