በግብጽ አብያተ ክርስቲያናት በደረሰ የቦምብ ጥቃት ከዐርባ አራት በላይ ክርስቲያኖች ዐረፉ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ቀን ፳፻፱ .

egypt10

በግብጽ አገር የቅዱስ ማርቆስ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናት

በግብጽ አገር በአሌክሳንደርያ እና ታንታ ከተሞች በቅዱስ ማርቆስ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ የግብጽ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ሚያዝያ ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በደረሰ ከፍተኛ የቦምብ ጥቃት ከዐርባ አራት በላይ ክርስቲያኖች ሲያርፉ፣  ከአንድ መቶ በላይ የሚኾኑት ደግሞ ለአካል ጉዳት ተዳረጉ፡፡

egypt11

ጥቃቱ የተፈጸመባቸው አብያተ ክርስቲያናት ውስጣዊ ክፍል እና ጥቃቱ በሕንጻዎቹ ላይ ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ጥቃቱ የደረሰው በርካታ የግብጽ ምእመናን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተሰባስበው በዓለ ሆሣዕናን ሲያከብሩ በነበሩበት በዕለተ ሰንበት ረፋድ ላይ ሲኾን፣ በሁለቱም አብያተ ክርስቲያናት በምእመናን በምእመናን ላይ ለደረሰው አሰቃቂ ጥቃትም ‹አይ ኤስ አይ ኤስ› ተብሎ የሚጠራው የጥፋት ቡድን ‹‹ሓላፊነቱን እወስዳለሁ›› ማለቱን፤ የሟቾች ቍጥርም ከተጠቀሰው አኃዝ በላይ እየጨመረ መምጣቱን ልዩ ልዩ የብዙኃን መገናኛዎች ዘግበዋል፡፡

bishop-angaelos

ብፁዕ አቡነ አንጌሎስ – በእንግሊዝ አገር የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ

በእንግሊዝ አገር የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አንጌሎስ የደረሰውን ጥቃት በማስመልከት በሰጡት ቃለ ምዕዳን፡- ‹‹… በዛሬው ዕለት በዓለ ሆሣዕናን እና የክርስቶስን ወደ ኢየሩሳሌም መግባት እንዳከበርን ዅሉ፣ በዚህች ዕለት ያለፉ ወገኖቻችንም ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም መግባታቸውን እናጠይቃለን፡፡ የመድኃኒታችንን ቅዱስ ሳምንት (ሰሙነ ሕማማት) ስናከብርም የቤተሰቦቻቸውን ሐዘን እና በዚህ ጥቃት ጉዳት የደረሰባቸውን  ወገኖቻችንን ሕመም እንጋራለን፡፡ በዚህ ሳምንት መጨረሻ ታላቁን በዓለ ትንሣኤ በምናከብርበት ወቀትም ምድራዊ ሕይወታችን ብዙ ጊዜ በመከራ የተመላ የሕይወት ጉዞ እንደ ኾነና ይህ መከራም በመጨረሻው ዘመን ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔር መንግሥት ለመውረስ እንደሚያበቃን እናስተውላለን›› የሚል መልእክት አስተላፈልዋል፡፡

egypt12

‹‹ስለ እርሱ ዅልጊዜ ይገድሉናል፤ እንደሚታረዱ በጎች ኾነናል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ በመላው ዓለም የሚገኙ ክርስቲያኖች በተለይ ግብጻውያን በተደጋጋሚ በአፅራረ ቤተ ክርስቲያን ጥቃት እየደረሰባቸው ነው፡፡ በዚህ ዓመት በግብጽ ከደረሱ አሰቃቂ ጥቃቶች መካከል ታኅሣሥ ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በካይሮ ከተማ የደረሰው የቦምብ ፍንዳታ ከሃያ አምስት በላይ ግብጻውያን ክርስቲያኖችን መቅሠፉና ከአምሳ በላይ የሚኾኑትን ማቍሰሉ የሚታወስ ነው፡፡ በትናንትናው ዕለት የደረሰው ከፍተኛ ጥቃትም መላው የግብጽ ሕዝብን አስጨንቋል፡፡ የግብጽ መንግሥትም ለሦስት ወራት የሚቆይ የአስኳይ ጊዜ አዋጅ አውጥቷል፡፡

ምንጮች፡

  • Alahram /Daily News Egypt
  • Aljazeera
  • BBC
  • Christian Today
  • CNN
  • Orthodoxy Cognate Page
  • Reuters

የ፲፪ኛው ሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በፎቶ

መጋቢት ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን ለ፲፪ኛ ጊዜ ያዘጋጀው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በቾ ወረዳ ቤተ ክህነት ከአዲስ አበባ ከተማ በሰባ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ቱሉ ጉጂ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዛሬው ዕለት ተካሒዷል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም ከዐሥራ ሦስት ሺሕ ሁለት መቶ አምሳ በላይ ምእመናን መሳተፋቸው ታውቋል፡፡ መርሐ ግብሩ ከሰዓታት በፊት በጸሎት የተፈጸመ ሲኾን፣ የጉባኤውን አጠቃላይ ኹኔታም በሚከተሉት ፎቶዎች ትመለከቱ ዘንድ ጋበዝናችሁ፤

img_0137

ቱሉ ጉጂ ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን

img_0275

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0348

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ

img_0317

ብፁዕ አቡነ ዳንኤል ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ

img_0092

img_0097

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

img_0103

img_0098

የጉባኤው ተሳታፊዎች ቆመው ጸሎተ ወንጌል ሲያስደርሱ

img_0290

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0237

ምክረ አበው አቅራቢ መምህራን

img_0243

img_0227

img_0271

የማኅበረ ቅዱሳን ዘማርያን የበገና ዝማሬ ሲያቀርቡ

img_0113

የመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ሰ/ት/ቤት የጎልማሶች መዘምራን መዝሙር ሲያቀርቡ

img_0213

መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ የበገና ዝማሬ ሲያቀርቡ

img_0121

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0110

img_0160

img_0326

img_0329

img_0153

img_0180

img_0169

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0216

በጉባኤው የተገኙ የቱሉ ጉጂና የአካባቢው ምእመናን በከፊል

img_0005

የጉዞው ቅድመ ዝግጅት

img_0018

img_0021

img_0012

img_0047

ጉዞ ወደ ቱሉ ጉጂ

img_0076

የቱሉ ጉጂ አካባቢ ወጣቶች መንገድ ሲያስተካክሉ

img_0078

img_0081

የመኪኖች መቆሚያ እና የጉባኤው ቦታ በከፊል ከርቀት ሲታይ

img_0122

img_0087

ምእመናን ከመኪና ወርደው ወደ ጉባኤው ሲያመሩ

img_0083

img_0132

የጉባኤው ሥፍራ በከፊል

img_0350

ጉባኤው በጸሎት ከተፈጸመ በኋላ ምእመናን ወደ ተዘጋጁላቸው መኪኖች ሲመለሱ

img_0355

img_0352

img_0353

img_0360

በበልበሊት ኢየሱስ ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ ጠፋ

የምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ ገዳም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን

በዝግጅት ክፍሉ

መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በእንሳሮ ወረዳ ቤተ ክህነት በምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ መጥፋቱን የገዳሙ አበምኔት ገለጹ፡፡

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከምሽቱ ፲፩ ሰዓት ገደማ በግልጽ ባልታወቀ ምክንያት የተነሣው ይህ የእሳት ቃጠሎ በገዳሙ መነኮሳት፣ በአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን እና በወረዳው የመንግሥት አካላት ጥረት ከሌሊቱ ፭ ሰዓት ገደማ ጠፍቷል፡፡

01

የአካባቢው መልክዐ ምድር

ቃጠሎው በቤተ ክርስቲያኑ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ባያደርስም በግምት አምስት ሄክታር የደን ሽፋንና ሦስት ሄክታር የአትክልት ቦታ በድምሩ ስምንት ሄክታር የሚኾነውን የገዳሙ መነኮሳት ያለሙትን የገዳሙን ይዞታ ማውደሙን የገዳሙ አበምኔት በኵረ ትጉሃን ቆሞስ አባ ሐረገ ወይን አድማሱ አስታውቀዋል፡፡

ከሥፍራው ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አገልጋዮች መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በገዳሙ ተገኝተው ማኅበረ መነኮሳቱን ያጽናኑ ሲኾን፣ ማኅበረ መነኮሳቱም ተረጋግተው ወደ ቀደመ የጸሎት ተግባራቸው ተመልሰዋል፡፡

?

ገዳሙ ከሁለት መቶ አምሳ በላይ መነኮሳት እና መነኮሳይያት፤ እንደዚሁም ወደ ሁለት መቶ የሚደርሱ የቅኔ፣ የድጓ እና የቅዳሴ ደቀ መዛሙርት የሚገኙበት ሲኾን፣ ገዳሙ የሚተዳደርበት በቂ ገቢ የሌለው ከመኾኑ ባሻገር የአብነት ተማሪዎቹም በመጠለያ እና በምግብ እጥረት ምክንያት ትምህርታቸውን በአግባቡ ለመከታተል ተቸግረዋል፡፡ ‹‹ስለዚህም የገዳሙን ህልውና ለመጠበቅ እና የአብነት ተማሪዎችን ከስደት ለመታደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፋችሁ አይለየን›› ሲሉ የገዳሙ አበምኔት በገዳሙና በማኅበረ መነኮሳቱ ስም ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

02

ቃጠሎው ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም መልክዐ ምድራዊ አቀማመጡ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ በመኾኑ በየጊዜው በግምት ስድሳ ሄክታር የሚደርስ የገዳሙ ይዞታ በጎርፍ መወሰዱን፤ በአሁኑ ሰዓትም በክልሉ መንግሥት በጀት በገዳሙ ዙርያ የአፈር ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መኾኑን ከገዳሙ ጽ/ቤት ለመረዳት ተችሏል፡፡

መረጃውን ያደረሰን በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ነው፡፡

የተወደዳችሁ ምእመናን! በየጊዜው በገዳሞቻችን ላይ የሚደርሰውን የእሳት ቃጠሎ እና መሰል አደጋ ከፍተኛ ጉዳት ከማድረሱ በፊት ዅላችንም ተግተን፣ ነቅተን ቤተ ክርስቲያናችንን እንጠብቅ ስንል መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

እርማት

በዚህ ዜና ሦስተኛው አንቀጽ ላይ ‹… ስምንት ሺሕ ሄክታር …› በሚል የተገለጸው በስሕተት ስለ ኾነ ስምንት ሄክታር› ተብሎ መስተካከሉን ከይቅርታ ጋር ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

‹‹መኑ ውእቱ ገብር ኄር፤ ታማኝ አገልጋይ ማነው?››

በመ/ ምስጢረ ሥላሴ ማናየ

መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስያሜ የዐቢይ ጾም ስድስተኛው እሑድ ወይም ሳምንት ‹ገብር ኄር› ይባላል፡፡ ሰያሜውን የሰጠውም ኢትዮጵያዊ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በኾነው ጾመ ድጓ መጽሐፍ ሳምንቱን የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ ስለዚህ በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብር ኄርን የሚያወሳ ነው ማለት ስለ ታማኝ አገልጋይ የሚያስረዳ ነው፡፡ በማቴዎስ ወንጌል ፳፭፥፲፬-፳፭ የተገለጸውና በዕለቱ የሚነበበው ወንጌል የሚነግረንም ይህንኑ ትምህርት ነው፡፡

አንድ ባዕለ ጸጋ ሰው ባሪያዎችን ጠርቶ ለአንዱ አምስት መክሊት ሰጠው፣ ሁለት መክሊት የሰጠውም አለ፣ አንድ መክሊትም የሰጠው አለ፡፡ ከዚህ በኋላ ወደሩቅ አገር ሔደ፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ ወርዶ ሌላ አምስት አትርፎ ዐሥር አደረገ፡፡ ሁለት የተቀበለውም አትርፎ አራት አደረገ፡፡ አንድ የተቀበለው ግን መሬቱን ቆፍሮ በሻሽ ጠቅልሎ የጌታውን መክሊት ቀበራት፡፡ ከብዙ ጊዜ በኋላ ጌታቸው መጥቶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው ቀርቦ ‹‹ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ አምስት አተረፍኩ›› አለው፡፡ ‹‹ገብር ኄር ወምዕመን ዘበውሁድ ምእምነ ኮንከ ዲበ ብዙህ እሰይመከ ባእ ውስተ ፍሥሐሁ ለእግዚእከ፤ አንተ ታማኝ ባሪያ! በጥቂቱ ታምነሃልበብዙ እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ ሁለት የተቀበለውም ቀርቦ ‹‹ጌታዬ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ ወጥቼ ወርጄ ሌላ ሁለት አትርፌ አራት አድርጌአለሁ፤›› ብሎ መክሊቱን አቀረበ፡፡ ጌታውም፡- ‹‹አንተ ታማኝ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃልበብዙ እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ‹‹ጌታዬ፣ አንተ ክፉና ጨካኝ፤ ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ፤ እንደ ኾንክ ስለ አወቅሁ መሬቱን ቆፍሬ ቀበርኋት እነኋት መክሊትህ›› አለው፡፡ ‹‹አንተ ሰነፍ ባሪያ! መክሊቴን በጊዜ ልትሰጠኝ በተገባህ ነበር፡፡ እኔም ወጥቶ ወርዶ ለሚያተርፍ በሰጠሁት ነበር፤›› አለና ‹‹ኑ፤ የዚህን ሐኬተኛ መክሊት ውሰዱና ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ላለው ይሰጡታል ይጨመርለታል ለሌለው ግን ያለውን ይቀሙታል›፡፡ ንዑ ይህን ሰነፍና ሐኬተኛ ባርያ እጅ እግሩን አሥራችሁ ጽኑ ጨለማ ወደ አለበት ውሰዱት! ጩኸትና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨምሩት!›› የሚል ፍርድ ወሰነበት፡፡

ባዕለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፡፡ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት ጌታችን በዕለተ ምጽአት ለዅሉም በሠራው ምግባር መጠን ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ ያሳየናል፡፡ ያገለገሉትን ‹‹ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አላቸው ማለት ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉና፡፡ ሰነፉ አገልጋይ ወደ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ቦታ መወርወሩም ኀጥአን ወደ ሲኦል መግባታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

ከላይ ያነሳነው የቅዱስ ወንጌል ቃል፡- ‹‹ታማኝ አገልጋይ ማነው?›› ይላል፡፡ ይህ እያንዳንዱ በአርአያ እግዚአብሔር የተፈጠረ የሰው ልጅ ጥያቄ ነው፡፡ ለዚህ አምላካዊ ጥያቄ ምላሽ መስጠት ከሰው ልጆች ይጠበቃል፡፡ ከዚህ ቀጥለን በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪካቸው ከተመዘገበላቸው ታማኝ አገልጋዮች መካከል ሦስቱን ጠቅሰን ከእነርሱ ሕይወት እንድንማር የሚያነሣሣ መጠነኛ ትምህርት እናቀርባለን፤

ሙሴ

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ታማኝ አገልጋይ መኾኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፤ ‹‹በመካከላችሁ ነቢይ ቢኖር እኔ እግዚአብሔር በራእይ እገለጥለታለሁ ወይም በሕልም አናግረዋለሁ፡፡ ባሪያዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም እርሱ በቤቴ ዅሉ የታመነ ነው፤›› እንዲል (ዘኍ.፲፪፥፮)፡፡ ይህ የፍጡር ቃል ሳይኾን በፈጣሪው የተሰጠ ምስክርነት ነው፡፡ በውኑ በዘመናችን እንኳን ፈጣሪ ፍጡራን ታማኝነቱን የሚመሰክሩለት አጋልጋይ ይኖር ይኾን? እንጃ! የሙሴን ታማኝ አገልጋይነት በረኃ፣ ስደት፣ መከራ፣ የፈርዖን ግርማ እና ቁጣ አልበገረውም፡፡ ዐርባ ዓመት ስለ ወንድሞቹ በመሰደድ ዐርባ ዓመት ደግሞ የተሰደደላቸው ወንድሞቹን በመምራት፣ ባሕር በመክፈል፣ ጠላት በመግደል፣ መና በማውረድ፣ ደመና በመጋረድ ውኃ ከዓለት አፍልቆ በማጠጣት መከራውን ከወገኖቹ ጋር በመቀበል የቀኑን ኃሩር፣ የሌሊቱን ቁር (ብርድ) ታግሦ በታማኝነት አገልግሏል፡፡ ታማኝነቱም እስከ ሞት ድረስ ነበር፡፡

‹‹ሙሴም ወደ እግዚብሔር ተመልሶወዮ እኒህ ሕዝብ ታላቅ ኃጢአት ሠርተዋል፡፡ ለራሳቸውም የወርቅ አማልክት አድርገዋል፡፡ አሁን ይህን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍከው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ? ከባለሟልነትህ አውጣኝ?›› ተብሎ ተጽፏል (ዘፀ.፴፪፥፴፩)፡፡ ታማኝ አገልጋይ የሚባለው እንደ ሙሴ ‹‹እኔ ልሙት ሌሎች ይዳኑ›› የሚል ሰው ነው፡፡ አሁን የምናየው ግን ፈጽሞ ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ‹‹ሰዎች ይሙቱ፤ እኔ ልኑር፡፡ ሰዎች ጦም ይደሩ፤ እኔ ልብላ፡፡ ሰዎች ይራቆቱ፤ እኔ ልልበስ፡፡ ሰዎች ይዘኑ፤ እኔ ልደሰት›› ነው፡፡ ይህም ታማኝ አገልጋይ ያለ መኾን መገለጫ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ለሚያገለግላቸው ሰዎች ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጥ እንጂ የራሱን ጥቅም የሚያስቀድም አይደለም፡፡

ዛሬ በዓለማችን የምንመለከተው ድርጊት ግን ‹‹ጩኸት ለአሞራ መብል ለጅግራ›› የሚባለውን ዓይነት ነው፡፡ በታማኝ አገልጋዮች ድካም የሚሸለሙ፤ ታማኝ አገልጋዮች በሠሩት ሪፖርት የሚያቀርቡ፤ ባልሠሩት ሥራ የሚወደሱ፤ ከጥቅሙ እንጂ ከድካሙ መካፈል የማይሹ ጥቂቶች አይደሉም፡፡ እንቅፋት የሚመታው እግርን ነው፡፡ አክሊል የሚቀዳጀው ግን ራስ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ማለት እንደራስ አክሊል ዘውድ የሚጸፋ ብቻ ሳይኾን እንደ እግር እንቅፋቱን፣ እሾኹን፣ ውጣ ውረዱን፣ መከራውንና ድካሙን የሚቀበል ነው፡፡ በጥቅም ጊዜ ለራሱ በአካፋ የሚዝቅ፤ ሌሎች በጭልፋ የሚቆነጥር አይደለም፡፡ ሙሴ ባሕር የከፈለው፣ መና ያወረደው ደመና የጋረደው ውኃ ያፈለቀው ለራሱ አልነበረም፤ ለሚመራቸው ሕዝብ ነበር እንጂ፡፡ ታማኝ አገልጋይ ያሰኘውም ይኸው ነው፡፡ በዚህ ከብሮበታል፤ ተመስግኖበታልም፡፡

ዳዊት

ነቢዩ ዳዊት ዘመነ መሳፍንት አልፎ ዘመነ ነገሥት ሲተካ እስራኤልን በንጉሥነት እንዲመራ እግዚአብሔር ከበግ ጥበቃ የመረጠው ንጉሥ ነው፡፡ እርሱም በተሰጠው ሥልጣን ሳይታበይ በታማኝነት ሕዝበ እስራኤልን መርቷል፡፡ እግዚአብሔር ለሙሴ እንደ መሰከረው ዅሉ ስለ ለዳዊትም መስክሮለታል፡፡ ‹‹እግዚአብሔር እንደ ልቡ የኾነ ሰው መርጧልናየዘይቱን ቀንድ ሞልተህ በልጆቹ መካከል ለእኔ ንጉሥ አዘጋጅቻለሁና ወደ እሴይ ወደ ቤተ ልሔም እልክሃለሁ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (፩ሳሙ. ፲፫፥፲፫፤ ፲፮፥፪)፡፡

በመዝሙረ ዳዊትም ‹‹ወረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ወቀባዕክዎ ቅብዐ ቅዱስ፤ ባሪያዬ ዳዊትን አገኘሁት የተቀደሰ ዘይትንም ቀባሁት›› ተብሎ ተነግሮለታል (መዝ. ፹፰፥፳)፡፡ ይህንንም አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በመጽሐፈ ሰዓታት ድርሰቱ፡- ‹‹ረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ብእሴ ምእመነ ዘከመ ልብየ፤ አገልጋዬ ዳዊትን እንደ ልቤ የታመነ ሰውን አገኘሁት›› ሲል ተርጕሞታል፡፡ ንጉሥ ዳዊት ከመንገሡ በፊት የተገኘው በታማኝነት ነበር፡፡ ከነገሠ በኋላም ታማኝ ነበር፡፡ አሁን በዚህ ዓለም የምንኖር እኛ ግን በድኅነት ታማኝ እንኾንና ሀብት፣ ሹመት፣ ሥልጣን ሲመጣ ታማኝነትን እናጣለን፤ እንዲያውም ታማኝነትን እንንቀዋለን፡፡ መስረቅ ጀግንነት ይመስለናል፡፡ መዋሸት ሥልጣኔ ይኾንልናል፡፡

ዳዊት ሳይሾም በጎቹን በመጠበቅ ታማኝ ነበር፡፡ በጎቹን የሚነጥቅ ተኩላ አንበሳ ቢመጣ በኋላው ተከትሎ ነብሩን በጡጫ፣ አንበሳውን በእርግጫ ብሎ በጎቹን ያስጥል ነበር፡፡ ‹‹እኔ ባሪያህ የአባቴን በጎች ስጠብቅ አንበሳ ወይም ድብ ይመጣ ነበር፡፡ ከመንጋውም ጠቦት ይወስድ ነበር፡፡ በኋላውም እከተለውና እመታው ነበር፤ ከአፉም አስጥለው ነበር፡፡ በተነሣብኝም ጊዜ ጉሮሮውን አንቄ እመታውና እገድለው ነበር፡፡ ይህም ፍልስጥኤማዊ ከነዚያ እንደ አንዱ ይኾናል፤ እንግዲህ እገድለው ዘንድ፤ ከእስራኤል ተግዳሮትን አስወግድ ዘንድ ዛሬ አልሔድምን? የሕያው አምላክ ጭፍሮችን ይገዳደር ዘንድ ይህ ቆላፍ ምንድን ነው? ከአንበሳና ከድብ ያስጣለኝ እግዚአብሔር ከዚህ ያልተገረዘ ፍልስጥኤማዊ እጅ ያስጥለኛል!›› በማለት እርሱ እንደ ተናገረው (፩ኛሳሙ.፲፯፥፴፬)፡፡

ዛሬም ቢኾን በእስራኤል ዘነፍስ በምእመናን ላይ የሚገዳደሩ ብዙ ፍልስኤማውያን ተሰልፈዋል፡፡ እነዚህን ድል የሚነሣ፤ በጎቹን ምእመናን ከተኩላ፣ ከአንበሳና፣ ከድብ አፍ የሚታደግ ታማኝ አገልጋይ ማነው? ከምእመናን ተግዳሮት የሚያርቅ ፈጣሪዬ ከመከራ ያድነኛል ብሎ የሚታመን የኢ አማንያን ብዛት የማያስፈራው ማን ነው? ከትንሽነቱ እስከ ታላቅነቱ የታመነ አገልጋይ ማነው? ለተሾመበት ሓላፊነት ታማኝ ማነው? አሁንም ዓለማችን ከሥጋውያን ባለ ሥልጣናትም ኾነ ከመንፈሳውያን መሪዎች የምትሻው ታማኝ ሰው ነው፡፡ በሙስና ያልተዘፈቀ፤ ጉቦ አይኑን ያላጨለመበት፤ ለመንጋው አርአያና ምሳሌ የሚኾን ሰው፤ ታማኝ አገልጋይ ማለት እርሱ ነው፡፡ በመሐላ የተቀበለውን የአገልግሎት ሓላፊነት የማይዘነጋ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ ሰባኪ፣ መምህር፣ ሐኪም፣ ዳኛ፣ ነጋዴ፣ ተማሪ፣ ወታደር፣ የቤት ሠራተኛ፣ የቢሮ ሠራተኛ ታማኝ መኾን አለበት፡፡

መንጋው በክህደት ሲጠፋ ዝም ብሎ የሚያይ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ መምህር፣ ሰባኪ፣ ታማኝ አይደለም፡፡ ታማሚው እየተሰቃየ የሚዝናና ሐኪም ታማኝ አይደለም፡፡ ፍርድ የሚያጎድል፤ ድሆችን የሚበድል፤ ለደሃ አደጎች የማይፈርድ ዳኛ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡ ቅቤ በሙዝ እና በድንች ቀላቅሎ፣ በርበሬ በሸክላ አፈር ጨምሮ፣ ሌሎችን አጭበርብሮ የሚሸጥ ነጋዴ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡ እየነገደ ያለው በሰው ሕይወት መኾኑን መዘንጋት የለበትም፡፡ ዅሉም እንደየአቅሙ በተሰጠው የአገልግሎት ዘርፍ ታማኝ መኾን አለበት፡፡

ዮሴፍ

ዮሴፍ ለወንድሞቹ ምግባቸውን ተሸክሞ የእርሱ ስንቅ ቢያልቅ የወንድሞቹን ስንቅ ያልበላ በትንሹ የታመነ ሰው ነበር፡፡ ወንድሞቹ ሸጠውት በቤተ ጲጥፋራ በሚያገለግልበት ጊዜም ታማኝ ነበር፡፡ ታማኝነቱ በጲጥፋራ ቤት ጌታ አድርጎታል፡፡ ‹‹ዮሴፍ ተሸጠአገልጋይም ኾነ፡፡ እግሮቹ በእግር ብረት ሰለሰሉ፡፡ ሰውነቱም ከብረት አመለጠች፡፡ ቃሉ ሳይደርስ የእግዚአብሔር ቃል ፈተነው፡፡ ንጉሥ ላከ፤ ፈታውም የሕዝብ አለቃ አድርጎ ሾመው፡፡ የቤቱም ጌታ አደረገው፡፡ በገንዘቡ ዅሉ ላይ ገዢ አደረገው፡፡ አለቆቹን እንደ እርሱ ይገሥፅ ዘንድ፤ ሽማግሌዎችን እንደ እርሱ ጥበበኞች ያደርጋቸው ዘንድ፤›› ተብሎ እንደ ተነገረለት (መዝ.፻፬፥፲፯)፡፡

በዚህ ኹኔታ የነበረው ዮሴፍ የጌታው ሚስት ሲወጣ ባቱን፣ ሲገባ ደረቱን እያየች ዐይኗን ጣለችበት፤ በዝሙት አይን ተመለከተችው፡፡ ‹‹ከእኔ ጋር ተኛ›› እያለችም በየቀኑ አስቸገረችው፡፡ እርሱ ግን ‹‹እምቢ›› አላት፡፡ ለጌታው ሚስትም፡- ‹‹እነሆ ጌታዬ በቤቱ ያለውን ዅሉ ለእኔ በእጄ አስረክቦኛል፡፡ በቤቱ ያለውን ምንም የሚያውቀው የለም፡፡ በዚህ ቤት ከእኔ የሚበልጥ ሰው የለም፡፡ ሚስቱ ስለ ኾንሽ ከአንቺ በቀር ያልሰጠኝ ነገር የለም፡፡ እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? እንዴትስ በእግዚአብሔር ፊት ኀጢአትን እሠራለሁ?›› በማለት የዝሙት ጥያቄዋን ውድቅ አደረገባት (ዘፍ.፴፱፥፯)፡፡

በዮሴፍ ታማኝነት የጌታው ቤት ተባርኳል፡፡ ሀብቱ በዝቷል፡፡ በታማኝነቱ በቤቱ ያለውን ዅሉ ተረክቦ ነበር፡፡ የቀረበለት ፈተና ግን ከባድ ነበር፤ ኾኖም ግን በታማኝነቱ ለማለፍ ችሏል፡፡ ዮሴፍ በታማኝ አገልጋይነቱ በመጣበት መከራ ቢታሰርም እንኳን ያለ ሹመት አላደረም፤ የእስረኞች አለቃ ነበር፡፡ ከእስር ቤት ሲወጣም ግብጽን በሙሉ መርቷል፡፡ በግብጻውያን ላይ ተሾሟል፤ በጥቂቱ ታምኗልና፡፡ ‹‹በጥቂቱ የታመነ በብዙ ይሾማል›› እንዲል (ማቴ.፳፭፥፳፬)፡፡ዛሬ በእየአንዳንዱ ጓዳ እንደ እሳት የሚያቃጥሉ አገልጋዮች ናቸው ያሉት፡፡ ልጅ በፈላ ውኃ የሚቀቅሉ ናቸው የሚበዙት፡፡ እንኳን በዅሉ ገንዘብ ለመሾም በጥቃቅን ዕቃዎች እንኳን የሚታመን ሰው ጠፍቷል፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ፡- ‹‹አቤቱ አድነኝ፤ ደግ ሰው አልቋልና፡፡ ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሏልና፤›› በማለት እንደ ተናገረው በመካከላችን መተማመን የለም (መዝ.፲፩፥፩)፡፡

እናም ከእነዚህ ሦስት ታማኝ አገልጋዮች (ሙሴ፣ ዳዊት እና ዮሴፍ) ሕይወት ዅሉም የሰው ልጅ ታማኝ አገልጋይነት የሚያሰጠውን ክብርና ጸጋ ተመልክቶ በታማኝነት ማገልገል ይገባዋል፡፡ ታማኝ መኾን መጀመሪያ የሚጠቅመው ራስን ነው፤ ከዚያ በኋላ ለአገር፣ ለወገን፣ ለቤተ ክርስቲያን፣ ላመኑትም ላላመኑትም ዅሉ ጠቃሚ ይኾናል፡፡ በመጨረሻም የጽድቅ አክሊልን ይቀዳጃል፤ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳል፡፡ ታማኝነት በሰውም፣ በእግዚአብሔርም ፊት ያስከብራልና፡፡ ጻድቃን፣ ሰማዕታት ቅዱሳን በታማኝነት በማገልገላቸው ፈጣሪአቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡

በሓላፊው ገንዘብ ያልታመኑት እነይሁዳ፣ ሐናንያ እና ሰጲራ የደረሰባቸውን ጉዳት አይተናል፡፡ አካን ወልደ ከርሚንም ተመሳሳይ ቅጣት ደርሶበታል (ሐዋ.፭፥፩-፳፭)፡፡ ስለ ኾነም ዅሉም በተሰማራበት የአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ኾኖ ‹‹አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙ እሾምሀለሁ፤›› የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል ለመስማት ተዘጋጅቶ መጠበቅ ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን፣ በእግዚአብሔር ‹አግብርት ኄራን፤ ታማኝ አገልጋዮች› እንድንባል፤ መንግሥቱንም እንድንወርስ አምላካችን ይርዳን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ አዘንተኞቹን አጽናኑ

6w5a3729

ቅዱስ ፓትርያኩ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ከሌሎችም የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ጋር ወደ አዘንተኞቹ ድንኳን ሲገቡ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በአዲስ አበባ ከተማ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ሥፍራ መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በድንገተኛ አደጋ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩ ምእመናን ቤተሰቦችን በትናንትናው ዕለት መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በሥፍራው ተገኝተው አጽናኑ፡፡

በደረሰው ድንገተኛ አደጋ ላለፉና ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የተሰማቸውን ኀዘን ቅዱስነታቸው ገልጸው በቃለ እግዚአብሔርና በአባታዊ ምክራቸውም አዘንተኞቹን አጽናንተዋል፡፡

ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር በሥፍራው የተገኙት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በክልል ትግራይ ደቡባዊ ዞን ማይጨው፣ ደቡባዊ ምሥራቅ ትግራይና ምሥራቃዊ ዞን አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስም እንደዚሁ ለአዘንተኞቹ የማጽናኛ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

ቆሼ ሠፈር

አደጋው የደረሰበት ቦታና አስከሬን የማውጣቱ ሥራ በከፊል

ቋሚ ሲኖዶሱ ከወሰነው የገንዘብ ድጋፍ በተጨማሪ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም በአደጋው ምክንያት በጊዜአዊ መጠለያ ለሚገኙ ወገኖች የአንድ መቶ ሺሕ ብር ድጋፍ ማድረጉን ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አስታውቀዋል፡፡

በመጨረሻም ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ከሰጡ በኋላ ቅዱስ ፓትርያርኩ ወደ መንበረ ፓትርያርካቸው ተመልሰዋል፡፡

መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቋሚ ሲኖዶስ በአደጋው ላለፉ ምእመናን የተሰማውን ኀዘን መግለጹና ቤታቸው በአደጋው በመፍረሱ ምክንያት በጊዜአዊ መጠለያ ለሚገኙ ወገኖችም ከቤተ ክርስቲያኒቷ የሁለት መቶ ሺሕ ብር ርዳታ እንዲሰጥ መወሰኑ የሚታወስ ነው፡፡

‹‹የአሁኑ እሳት በቍጥጥር ሥር ቢውልም ለወደፊቱ ግን ያሠጋናል … ልጁ ዐረፈ እንጂ ሞተ አይባልም፡፡›› የገዳሙ አበምኔት

ze1

ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በሊበን ወረዳ ቤተ ክህነት ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም አካባቢ (ዙርያ) መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቀትር ላይ ተነሥቶ የነበረው ከፍተኛ የእሳት ቃጠሎ በቍጥጥር ሥር መዋሉን የገዳሙ አበምኔት መምህር አባ ገብረ ሕይወት አስታወቁ፡፡

ከገዳሙ አባቶች አንዱ አባ ጥላኹን ስዩም እንዳብራሩት እሳቱ የተነሣበት አካባቢ ከገዳሙ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ ከመኾኑ ባለፈ ቃጠሎው በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ስለነበር በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመቈጣጠር ባይቻል ኖሮ ከደኑም አልፎ ተርፎ በገዳሙ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርስ ነበር፡፡

zuquala

የዝቋላ ገዳም መገኛና የአካባቢው መልክዐ ምድር

የማኅበረ ቅዱሳን አባላትና የልዩ ልዩ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች እሳቱን ለማጥፋት በመረባረብ ክርስቲያናዊ ሓላፊነታቸውን የተወጡ ሲኾን፣ በወቅቱ ከገደል ላይ ወድቆ በመጎዳቱ ሕክምና ሲደረግለት የነበረው ኦርቶክሳዊ ወጣት ሸገና ሉሉ (የክርስትና ስሙ ወልደ ዮሐንስ) ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱን የአዳማ ማእከል ያደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ የገዳሙ አበምኔት መምህር አባ ገብረ ሕይወት ‹‹ልጁ ዐረፈ እንጂ ሞተ አይባልም፡፡ ከሰማዕታት እንደ አንዱ የሚቈጠር ነው›› ሲሉ የወልደ ዮሐንስ መጠራት ሰማያዊ ዋጋ የሚያስገኝ ሞት መኾኑን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ወቅቱ ሌሊት በመኾኑ፣ በዚያውም ላይ ልጁ የአካባቢውን ተፈጥሮ ባለማወቁ ለኅልፈት ቢዳረግም ሞቱ ግን የሚወደድ እንጂ የሚያስቈጭ አይደለም›› ያሉት ደግሞ አባ ጥላኹን ስዩም ናቸው፡፡ በመጓጓዣ እጦት ምክንያት ማኅበረ መነኮሳቱ በሥርዓተ ቀብሩ ላይ ለመገኘት እንዳልቻሉ ያስታወሱት አበምኔቱ ለወጣቱ በገዳሙ ጸሎተ ፍትሐት እንደተደረገለትና ለወደፊቱም ቤተሰቦቹን ለማጽናናት ኹኔታዎችን እያመቻቹ እንደሚገኙ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

%e1%8b%9d2

የእሳት ቃጠሎውን ለማጥፋት የምእመናን ተሳትፎ

አበምኔቱ ለዝግጅት ክፍላችን እንደ ገለጹት በገዳሙ አባቶች፤ በአካባቢው ነዋሪዎችና ከልዩ ልዩ ቦታዎች በመጡ የቤተ ክርስቲያን የቍርጥ ቀን ልጆች፤ እንደዚሁም በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፣ አየር ኃይል፤ በኦሮምያ ፖሊስ እና በሊበን ወረዳ ፖሊስ ርብርብ ለገዳሙ ሥጋት የነበረው ይህ ከባድ ቃጠሎ በቍጥጥር ሥር ውሏል፡፡ የበረኃውን ሐሩር፣ የእሳቱን ወላፈን፣ እሾኽና ጋሬጣውን፣ ረኃቡንና ጥሙን ተቋቁመው እሳቱን በማጥፋት ገዳሙን ከጥፋት የታደጉ አካላትን ዅሉ አበምኔቱ በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ስም አመስግነዋል፡፡

‹‹ገዳማችን በስም የገነነ ነገር ግን በብዙ ችግርና ፈተና ውስጥ ያለ ገዳም ነው፡፡ የአሁኑ እሳት በቍጥጥር ሥር ቢውልም፤ ለወደፊቱ ግን ያሠጋናል፡፡ በየዓመቱ በየካቲትና መጋቢት ወሮች ‹እሳት መቼ ይነሣ ይኾን?› እያልን እንጨነቃለን፡፡ ችግሩን ለማስቀረትና ጋታችንን ለመቀነስ ዘላቂ መፍትሔ ያስፈልገናል፤›› ያሉት አበምኔቱ፣ በመጨረሻም ገዳሙ ያለበትን ችግር ለመፍታትና የእሳት ቃጠሎውንም በዘላቂነት ለመቈጣጠር ያመች ዘንድ በገዳሙ የታቀዱ የገቢ ማስገኛ ተግባራትንና በጅምር የቀረውን የውኃ ጕድጓድ ለመፈጸም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍ ቢያደርግልን፣ ገዳሙ የቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን የአገርም ሀብት ነውና መንግሥትም መንገድ ቢሠራልን ሲሉ በቤተ ክርስቲያን ስም የርዳታ ጥሪአቸውን ያቀርባሉ፡፡

ziquala

ቃጠሎው በደኑ ላይ ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዕፀዋቱን ለማገዶና ለልዩ ልዩ አገልግሎት የሚጠቀሙ አካላት በመበራከታቸውና በተደጋጋሚ በደረሰው የእሳት ቃጠሎ በደን የተሸፈነው ግዙፉ የዝቋላ ተራራ በመራቆት ላይ እንደሚገኝ፤ በሰሞኑ ቃጠሎም አብዛኛው የደን ክፍል እንደወደመ ከልዩ ልዩ ምንጮች ለመረዳት ተችሏል፡፡ ታሪካዊው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳምም ቍጥቋጦ በሚበዛበት፣ ነፋስ በሚበረታበት፣ በረኃማና ወጣገባ መልክዐ ምድር ላይ የሚገኝ በመኾኑና በሌላም ልዩ ልዩ ምክንያት በተደጋጋሚ በእሳት ተፈትኗል፡፡ ለአብነትም መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም በገዳሙ ዙርያ ተነሥቶ በነበረው ከባድ ቃጠሎ በደኑ ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ የሚታወስ ነው፡፡

መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በገዳሙ አካባቢ የተነሣውን እሳት ለማጥፋት ሲሯሯጥ በሞት ለተለየው ወጣት ሸገና ሉሉ (ወልደ ዮሐንስ) ሰማያዊ ዕረፍትን፣ ለቤተሰቦቹም መጽናናትን እየተመኘን የቤተ ክርስቲያችንንና የአገራችንን ሀብት የዝቋላ ገዳምን ህልውና ለማስጠበቅ፣ ገዳሙ ያለበትን ችግር በዘላቂነት ለመፍታትና ደኑንም ወደ ነበረበት ተፈጥሮ ለመመለስ ይቻል ዘንድ የሚመለከተን ዅሉ ብናስበበት መልካም ነው እንላለን፡፡

የኀዘን መግለጫ

img_0005

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የቅዱስ ሲኖዶስ ርእሰ መንበር እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ስሙ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ሥፍራ በድንገተኛ አደጋ ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩ ወገኖቻችን፣ ዛሬ መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠውን የሐዘን መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በአዲስ አበባ ከተማ መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ምሽት በወገኖቻችን ላይ የደረሰውን የሞት አደጋ አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ የዘን መግለጫ፡፡

መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከምሽቱ ፪ ሰዓት ሲኾን በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ስሙ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ስፍራ በሚኖሩ ወገኖቻችን ላይ ድንገተኛ የሞት አደጋ ደርሷል፡፡ በደረሰውም አሳዛኝ አደጋ ከፍተኛ ዘን ተሰምቶናል፡፡

በመኾኑም እግዚአብሔር አምላካችን በደረሰው ኅልፈተ ሕይወት ለተጎዱ ወገኖች ቤተሰቦች መጽናናትን፣ ብርታትን እንዲሰጥልን፤ የሟቾችንም ነፍሳት በመንግሥቱ እንዲቀበልልን በመጸለይ የተሰማንን ዘን እየገለጽን፣ ለእነዚሁ በድንገተኛ አደጋ ለተለዩ ወገኖቻችን ከመጋቢት ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ጀምሮ ለሰባት ቀናት በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማት ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግላቸው፤ እንዲሁም ቤታቸው በመፍረሱ ምክንያት በመጠለያ ለሚገኙ ወገኖቻችን ከቤተ ክርስቲያችን ብር 200,000.00 (ሁለት መቶ ሺሕ) ርዳታ እንዲሰጥ ቋሚ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በክርስቶስ ሰላም

(ክብ ማኅተምና የብፁዕ አቡነ ገሪማ ፊርማ አለው)

አባ ገሪማ ሊቀ ጳጳስ ዶክተር

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት፣

የውጭ ግንኙነት የበላይ ሓላፊ

በዝቋላ ገዳም አካባቢ የተነሣው የእሳት ሰደድ እየተባባሰ መኾኑ ተነገረ

001

በዝግጅት ክፍሉ

መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም አካባቢ መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቀትር ላይ የተነሣው ከፍተኛ የእሳት ሰደድ እየተባባሰ መኾኑን የገዳሙ አባቶች ተናገሩ፡፡

እሳቱ የተነሣበት ምክንያት በግልጽ ባይታወቅም ትናንትና ረፋድ ላይ በቅርብ ርቀት ላይ ይጤስ የነበረው አነስተኛ እሳት ቀትር ላይ መባባሱንና እሳቱን ለማጥፋትም የገዳሙ መነኮሳት ከቅዳሴ በኋላ ወደሥፍራው መሔዳቸውን ከገዳሙ አባቶች መካከል አንዱ የኾኑት አባ ጥላኹን ስዩም ዛሬ ረፋድ ላይ ለዝግጅት ክፍላችን በስልክ አስታውቀዋል፡፡

‹‹ዓርብ ረቡዕ›› በሚባለው አካባቢ የነበረውን እሳት ሌሊት ላይ በቍጥጥር ሥር ለማዋል ቢቻልም ‹‹የቅዱሳን ከተማ›› በተባለው ቦታ በኩል በአዱላላ ተክለ ሃይማኖት አካባቢ ያለው ቃጠሎ እየተስፋፋ መምጣቱንና ሰደዱን ለመከላከልም አስቸጋሪ መኾኑን አባ ጥላኹን ተናግረዋል፡፡

እሳቱ ወደ ገዳሙ እንዳይጠጋ የመከላከሉ ሥራ እንደቀጠለ መኾኑን የጠቀሱት አባ ጥላኹን እሳት ለማጥፋት ከደብረ ዘይት ከተማ ወደ ገዳሙ ከሔዱ ምእመናን መካከል አንድ ወንድም ከገደል ላይ ወድቆ እንደተጎዳና በአሁኑ ሰዓትም ሕክምና እየተደረገለት እንደሚገኝ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

እንደ አባ ጥላኹን ማብራሪያ የገዳሙ መነኮሳት፤ የደብረ ዘይት እና የአካባቢው ነዋሪዎች፤ እንደዚሁም የፌደራል፣ የክልሉና የወረዳው ፖሊስ ኃይል ከትናንትና ጀምሮ እሳቱን ለማጥፋት ከፍተኛ ርብርብ በማድረግ ላይ ቢገኙም የአካባቢው መልክዐ ምድር በረኃማ፣ ቍጥቋጦ የበዛበትና ነፋስ የሚበረታበት ወጣገባ ቦታ መኾኑ ሰደድ እሳቱን በቍጥጥር ሥር ለማዋል የሚደረገውን ጥረት ከባድ አድርጎታል፡፡

በመጨረሻም ሰደዱ እየተስፋፋ ሔዶ በገዳሙ ላይ ጉዳት ከማድረሱ በፊት እሳቱን ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት እንዲቻል መላው ሕዝበ ክርስቲያን በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ ትብብር ያደርጉ ዘንድ አባ ጥላኹን ስዩም በገዳሙና በመነኮሳቱ ስም ጥሪአቸውን ያስተላልፋሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ይቅርታ ልትጠየቅ እንደሚገባ ተገለጸ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የካቲት ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዐድዋ ጦርነት ጊዜ በአገሩ ላይ የደረሰውን ሽንፈት ለመበቀል ሲል የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት ላይ ላደረሰው ቃጠሎ፤ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በአባቶች ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና መነኮሳት እንደዚሁም በምእመናን ላይ በግፍ ለፈጸመው ጭፍጨፋ የጣልያን መንግሥት እና የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን (ቫቲካን) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እና ኢትዮጵያን ይቅርታ መጠየቅ፤ የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት ከየገዳማቱና አድባራቱ የዘረፋቸውን ንዋያተ ቅድሳት፣ ጥንታውያን የብራና መጻሕፍትን እና አገራዊ ቅርሶቻችንንም መመለስ እንደሚገባቸው ተገለጸ፡፡

img_0725

በስተቀኝ እና በስተግራ አቅጣጫ፡- ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢዎቹ ቀሲስ ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል እና ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ አለባቸው፤ ከመካከል፡- የጥናቶቹ አወያይ አቶ መስፍን መሰለ (በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ባህሎች እና ቋንቋዎች አካዳሚ ተመራማሪና የፎክሎር መምህር)

ይህ ሐሳብ የተገለጸው በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አዘጋጅነት የማኅበሩ አባላት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራንና ተማሪዎች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በአጠቃላይ በርከት ያሉ ምእመናንና ምእመናት በታደሙበት በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል አዳራሽ የካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በተካሔደው የጥናት መርሐ ግብር ላይ ሲኾን ፣ በዕለቱ ‹‹በኢትዮጵያ ላይ የፋሽስት ኢጣልያ ወረራ እና የሮሙ ፖፕ ፒዮስ ፲፩ኛ አቋም›› እና ‹‹ቅኔ ዘዝክረ ዐድዋ›› በሚሉ አርእስት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፤ በጥናቶቹ ዙሪያ ከታዳሚዎች ለተነሡ ጥያቄዎችም በጥናት አቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

img_0723

የመርሐ ግብሩ ተሳታፊ አባቶች እና ወንድሞች በከፊል

‹‹በኢትዮጵያ ላይ የፋሽስት ኢጣልያ ወረራ እና የሮሙ ፖፕ ፒዮስ ፲፩ኛ አቋም›› የሚለው ርእሰ ጉዳይ አቅራቢ ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል ፋሽስት ኢጣልያ አገራችን ኢትዮጵያን በ፲፱፻፳፰ ዓ.ም በወረረበት ወቅት የጊዜው የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ፖፕ ወረራውን እና በኢትዮጵያ ላይ የተፈጸመውን ግፍ በዝምታ መመልከታቸው ተገቢ አለመኾኑን አስታውሰው ፖፑ ወረራውን ሊያወግዙ ያልቻሉበት ምክንያትም፡- በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እና በኢጣልያ መንግሥት መካከል ጥላቻ እንዳይፈጠር በመስጋታቸው፤ በዘመኑ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እና በካህናቱ መካከል ከባድ ተቃውሞ ስለነበር በመካከላቸው ግጭት እንዳይፈጠር በማሰባቸው እንደኾነና ዋነኛው ምክንያት ግን የኢጣልያ ኢትዮጵያን መውረር የካቶሊክ ሃይማኖትን በኢትዮጵያ ለማስፋፋት መልካም ዕድል ይፈጥራል ብለው በማመናቸው እንደኾነ በጥናታቸው አትተዋል፡፡

img_0729

ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል (በቤተ ክርስቲያናችን በምርምር ሥራ እና በልዩ ልዩ ሓላፊነት ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ሲሰጡ የኖሩ፣ አሁን በጡረታ ላይ የሚገኙ አባት)

ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ አያይዘውም ፖፑ የወቅቱ የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት ‹‹በእግዚአብሔር ፈቃድ የተነሣ፣ በሊበራሊዝም አስተሳሰብ ያልተሞኘ መንግሥት ነው›› ብለው ያምኑ እንደነበር፤ በወቅቱ ስለወረራው ሲጠየቁ ለሚድያዎች የሰጡት ምላሽም ፖፑ ለጦርነቱ የነበራቸውን ጥሩ አቋም እንደሚያመለክት፣ ለአብነትም በአንድ ወቅት ‹‹ራስን የመከላከል ጦርነት ነው›› ሲሉ ስለ ወረራው አስፈላጊነት እንደተናገሩ፤ የአገሪቱ መንግሥት ኢትዮጵያን ሊወርር ሲዘጋጅ ሙሶሎኒ በሮም ከተማ ንግግር በሚያደርግበት ጊዜ መላው የሮም ካቶሊክ አብያተ ክርስቲያናት ደወሎች ለረጅም ሰዓት ሲደወሉ እንደነበር፤ ይህም የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያ በኢጣልያ እንድትወረር የነበራትን ፍላጎት እንደሚያመለክት ባለጥናቱ ጠቁመዋል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ወረራውን በገንዘብ ደግፋለች ተብላ ቤተ ክርስቲያኗ ተከሳ እንደነበር ያወሱት ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ፣ ፋሽስት ኢጣልያ ከኢትዮጵያ ከወጣ በኋላም ‹‹እጅግ የሚያስደስት ድል›› በማለት ፖፕ ፒዮስ ፲፩ኛ ጦርነቱን ማድነቃቸው ፖፑ የፋሽስት መንግሥት እና የወረራው ደጋፊ እንደነበሩ አንዱ ማሳያ መኾኑን ልዩ ልዩ ምንጮችን ዋቢ አድርገው የፖፑን አቋም ለጉባኤው አስረድተዋል፡፡

img_0724

የመርሐ ግብሩ ተሳታፊ እናቶች እና እኅቶች በከፊል

የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ለፋሽስቱ ሠራዊት በስውር የሞራል ድጋፍ ከማድረጓ ባሻገር የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት በየጊዜው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አድባራትና ገዳማት ላይ ቃጠሎና የቅርስ ዘረፋ ሲያካሒድ፤ እንደዚሁም ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስን እና ብፁዕ አቡነ ሚካኤልን በግፍ ሲረሽን፤ በአባቶች ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና ምእመናን ላይ የጅምላ ጭፍጨፋ ሲፈጽም በዝምታ መመልከቷ (ድርጊቱን አለማውገዟ) የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የወረራው ደጋፊ እንደነበረች የሚያስገነዝብ ሌላኛው ነጥብ መኾኑን በመጥቀስ ለዚህ ዅሉ በደልም የጣልያን መንግሥት እና የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን (ቫቲካን) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እና የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ መጠየቅ፤ ለጥፋታቸውም ተመጣጣኝ ካሣ መክፈል፤ ከየገዳማቱና አድባራቱ የተዘረፉ ንዋያተ ቅድሳትን፣ ጥንታውያን የብራና መጻሕፍትን እና አገራዊ ቅርሶቻችንንም ለአገራችን መመለስ እንደሚገባቸው ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገልጸዋል፡፡ ለዚህ ሐሳብ መሳካትም የኢትዮጵያ መንግሥት፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶች እና መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍ እንዲያደርጉ በማሳሰብ ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አጠቃለዋል፡፡

img_0735

ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ አለባቸው (በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፊሎሎጂ ትምህርት ክፍል ፫ኛ ዓመት የፒ ኤች ዲ ተማሪ)

‹‹ቅኔ ዘዝክረ ዐድዋ›› የሚለው ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ አለባቸው ደግሞ ከአድዋ ጦርነት በፊት፣ በጦርነቱ ወቅት እና ከድሉ በኋላ የተደረጉ አንዳንድ ጥንታውያን የግእዝ ቅኔያትን ትርጕምና ምሥጢር ከታሪክ መጻሕፍት ጋር አነጻጽረው በማቅረብ በቅኔአቸው ንጉሡንና ሠራዊቱን በማበረታታት ለአገራችን ድል ማግኘት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያበረከቱትን ከፍተኛ አስተዋጽዖ በጥናታቸው አተተዋል፡፡

አባቶቻችን በዐድዋው ጦርነት ኢጣልያን ድል ማድረግ የተቻላቸው በወታደር እና በጦር መሣሪያ ብዛት ሳይኾን በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በቅዱስ ጊዮርጊስ ተራዳዒነት መኾኑን ያስታወሱት ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ ‹‹አዲስ ቅኔ መቀኘት ባንችልም እንኳን አባቶቻችን የፈጸሙትን የዐርበኝነትና የድል አድራጊነት ታሪክ እያነበብን የመወያያ አጀንዳችን ልናደርገው ይገባል›› ሲሉ ትውልዱ የአባቶቹን ውለታ መርሳት እንደሌለበት አስገንዝበዋል፡፡

በመጨረሻም በጥናታዊ ጽሑፎቹ ላይ ውይይት ከተደረገ እና ከመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች ለተነሡ ጥያቄዎች በጥናት አቅራቢዎቹ ምላሽ ከተሰጠ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት ልዩ ዐውደ ጥናት አካሔደ

te

በደመላሽ ኃይለማርያም

የካቲት ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤት የምሥረታ ታሪክ በመጀመሪያ ደረጃ ላይ የሚነሣው አንጋፋው የ‹‹ተምሮ ማስተማር›› ሰንበት ትምህርት ቤት በሚያዝያ ወር ፳፻፱ ዓ.ም የሚከበረውን ስድሳኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም የሰንበት ትምህርት ቤቱ አዳራሽ የካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ልዩ ዐውደ ጥናት አካሔደ፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም መለሰ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ፤ መጋቤ ኅሩያን አባ ኤልያስ በልሁ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም ምክትል አስተዳዳሪ እና የሰንበት ትምህርት ቤቱ ሰብሳቢ፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ጥሪ የተደረገላቸው ምሁራንና እንግዶች፤ የልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞች፤ የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች ተወካዮች፤ ቀደምት የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባላት እና በርካታ ምእመናን ታድመዋል፡፡ በዐውደ ጥናቱም ‹‹የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት አመሠራረትና አገልግሎት›› እና ‹‹የአማርኛ መዝሙራት ታሪካዊ ዕድገትና ተግዳሮቶች›› በሚሉ አርእስት የተዘጋጁ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡ በጥናቶቹ ዙሪያ ከተሳታፊዎች ለቀረቡ ጥያቄዎችም በአቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

02

የሰንበት ትምህርቱ መስማት የተሳናቸው መዘምራን በምልክት ቋንቋ መዝሙር ሲያቀርቡ

‹‹የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት አመሠራረትና አገልግሎት›› የሚለው ጥናት አቅራቢ ኢንጂነር ከፈለኝ ኃይሉ የተምሮ ማስተማርን የአመሠራረት ታሪክ እና አገልግሎት በተለይ ከ፲፱፻፴፱ — ፲፱፻፵፱ ዓ.ም የነበረውን የሰንበት ት/ቤቱን እንቅስቃሴ በጥናታቸው ዳሰዋል፡፡ በንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በተፈሪ መኮንን የወንዶች ትምህርት ቤት ተማሪዎች በመነጨ ‹‹ሰዎችን ለማስታረቅ›› የሚል በጎ ሐሳብ የ‹‹ተምሮ ማስተማር›› ሰንበት ት/ቤት እንደተመሠረተ ኢንጂነር ከፈለኝ ገልጸው ለምሥረታውም ዐሥራ ሁለት ወንድሞች ትልቁን ድርሻ እንደሚወስዱ ተናግረዋል፡፡ ከእነዚህ ሰዎች በተጨማሪ በቀድሞ ስማቸው አባ መዓዛ ይባሉ የነበሩት በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ድርሻ የላቀ እንደነበርም ኢንጂነሩ በጥናታቸው አብራርተዋል፡፡

03

ዲ/ን ዘውዱ በላይ (አወያይ) እና ኢንጂነር ከፈለኝ ኃይሉ (ጥናት አቅራቢ)

ከዅሉም በተለየ በንጉሡ ዘመን በቤተ ክርስቲያንና በማኅበራዊ አገልግሎት ላይ ከፍተኛ ድጋፍ ሲሰጡ የነበሩትና በ፲፱፻፷፮ ዓ.ም ያለ በቂ ምክንያት በደርግ ባለሥልጣናት በግፍ የተገደሉት አቶ አበበ ከበደ ለሰንበት ት/ቤቱ መመሥረትና መጽናት ግንባር ቀደሙን ቦታ እንደሚወስዱ ጥናት አቅራቢው አስገንዝበዋል፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቱ በ፲፱፻፵፱ ዓ.ም ገብረ ጊዮርጊስ አጋሼ በተባሉ አባት የተሰጠው ‹‹የተምሮ ማስተማር ማኅበር›› የሚለው ስያሜ በ፲፱፻፶ ዓ.ም በንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እንደጸደቀና ከጊዜ በኋላም ‹‹የተምሮ ማስተማር ሰንበት ት/ቤት›› የሚለው ስሙ በቅዱስ ሲኖዶስ ዕውቅና እንዳገኘ ያስታወሱት የጥናቱ አቅራቢ የሰንበት ት/ቤቱ መመሥረት ወጣቶች ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የበኩላቸውን አስተዋጽዖ እንዲያበረክቱ በር ከመክፈቱ ባሻገር ሰባክያነ ወንጌል እንዲበራከቱና ምእመናን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ማድረጉን ጠቁመዋል፡፡ በጥናታቸው ማጠቃለያም ሰንበት ት/ቤቱ እንዲመሠረት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከቱትን እንደ አቶ አበበ ከበደ ያሉ ባለውለታዎችን በጸሎት መዘከርና በስማቸው መታሰቢያዎችን ማዘጋጀት እንደሚገባ ኢንጂነር ከፈለኝ አሳስበዋል፡፡

01

ቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ

‹‹የአማርኛ መዝሙራት ታሪካዊ ዕድገትና ተግዳሮቶች›› የሚለው ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ ቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ በበኩላቸው የ‹‹ተምሮ ማስተማር›› ሰንበት ት/ቤት የምሥረታ እንቅስቃሴ ከተጀመረበት ፲፱፻፴፭ ዓ.ም አንሥቶ ለሰባ ዓመታት ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስጠቱን በጥናታቸው ጠቅሰዋል፡፡ የአማርኛ መዝሙራት መዘጋጀት የጀመሩት ሰንበት ት/ቤቱ በተመሠረተበት ወቅት አካባቢ መኾኑን ያስታወሱት ጥናት አቅራቢው በወቅቱ መዝሙራቱ ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ ቋንቋ በቀጥታ ተተርጕመው ዜማቸውም ሳይቀየር ይቀርቡ እንደነበር እና ይህም ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ውጪ የኾኑ መዝሙራት እንዲበራከቱ በር መክፈቱን በጥናታቸው አመላክተዋል፡፡

ያሬዳዊ ይዘታቸውን የጠበቁ የአማርኛ መዝሙራት እንደ ተምሮ ማስተማር ባሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶች በየዘመናቱ በጥራዝ መልክ እየታተሙ ለዛሬው ትውልድ መድረሳችውንም አስገንዝበዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓት የሚዘመሩ ጥቂት የማይባሉ መዝሙራት በሥርዓት ስለማይዘጋጁ ካሉባቸው የዘይቤ፣ የቃላት አጠቃቀም፣ የቀለም እና ሐረግ ምጣኔ ጉድለቶች ባሻገር ምሥጢርን እና ይዘትን፣ እንደዚሁም ያሬዳዊ ዜማን ከመጠበቅ አኳያም ብዙ መሥፈርቶችን እንደማያሟሉ የገለጹት ቀሲስ ሰሎሞን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም የሚቀርቡ መዝሙራት ዅሉ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ተመዝነውና ተገምግመው በተገቢው ዅኔታና በትክክለኛው መሥፈርት ሊዘጋጁ ይገባል በማለት ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አጠቃለዋል፡፡

በዚህ ዐውደ ጥናት ሊስተናገዱ መርሐ ግብር ከተያዘላቸው ጥናታዊ ጽሑፎች መካከል በሰዓት እጥረት ምክንያት ያልቀረበው ‹‹መገናኛ ብዙኃንና የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት›› የሚለው የዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ (በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የጥንታውያት መዛግብት ጥናት ተባባሪ ፕሮፌሰር) ጥናት በሌላ ጊዜ በተመሳሳይ መርሐ ግብር እንደሚቀርብ የሰንበት ት/ቤቱ ምክትል ሰብሳቢ ዲ/ን ዘውዱ በላይ ለጉባኤው ተሳታፊዎች ቃል ገብተዋል፡፡

temro

ከዚህ መርሐ ግብር በተጨማሪም ከሚያዝያ ፲፭ — ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በዐውደ ርዕይ እና በልዩ ልዩ መንፈሳውያን መርሐ ግብራት የሰንበት ት/ቤቱ ስድሳኛ ዓመት ምሥረታ በዓል እንደሚዘከር ከሰንበት ት/ቤቱ ጽ/ቤት ለመረዳት ተችሏል፡፡ ለብዙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ ለማኅበረ ቅዱሳንና ጽርሐ ጽዮን የአንድነት ኑሮ ማኅበር መመሥረት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያለው ይህ አንጋፋ ሰንበት ትምህርት ቤት በስልሳ ዓመት የአገልግሎት ጉዞው ውስጥ ያበረከተውን መንፈሳዊ አገልግሎት የሚያሳዩ ተጨማሪ የዳሰሳ ጥናቶች መደረግ እንደሚገባቸው በዐውደ ጥናቱ የተገኙ አባቶችና ምሁራን ጠቁመዋል፡፡ በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት ጠዋት የተከፈተው ይህ የዐውደ ጥናት መርሐ ግብር በአባቶች ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ አመሻሽ ላይ ተፈጽሟል፡፡