ተአምረኛዋ ሥዕል

መስከረም ፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

እጅጉን የሚያስደንቀው የአምላክ ሥራ የተገለጠበት፣ ለሰው ልጆች ተስፋ፣ ፈውስ ሥጋ እንዲሁም ፈውስ ነፍስን ሊሰጠን በፈቀደ እርሱ ድንቅ ተአምራትን በምድር አደረገ፤ ጌታ በትስብእቱ በዓለም ተገልጦ ካደገጋቸው ተአምራትም በተጨማሪ እርሱ ካረገ በኋላም በሰዎች አድሮ ላይ አድሮም ይሁን በተለያዩ መንገዶች ዕጹብ ሥራውን አሳይቶናል፡፡

ከዚሀ ሁሉም በበለጠ መልኩ በክብርት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም የተደረገው ምሥጢር እጅግ ይልቃል፤ ነገረ ድኅነቱን የፈጸመባት እመቤታችን ለአዳም ዘር በሙሉ ተስፋ በመሆኗ ጌታ ከእርሷ በለበሰው ሥጋ ተገልጦ ያደረገልንን ለመግለጽ ቃላት ባይኖርም ምስጋና ግን ማቅረብ የሁላችንም ፈንታ ነው፡፡ አልፎ ተርፎም እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታ ካረገች በኋላ ድንቅ ተአምርም በእርሷ ተደርጓል፡፡ ቅዱሳት መጽሐፍት በተለያዩ ጊዜ እመቤታችን ያደረገችውን ተአምር ገልጸው ጽፈዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል በመጽሐፈ ስንክሳር መስከረም ፲ ቀን ተመዝግቦ የምናገኘው አንድ ተአምረኛ ሥዕል እንዳለ ነው፤ ታሪኩም እንዲህም ይነበባል፡፡

አንዲት ማርታ የምትባል ሴት እመቤታችን ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ሁሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ ኢትዮጵያዊ መነኰስ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡ ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡

አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጉዞ ጀመሩ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ሲደርሱ ወንበዴዎች ተነሱባቸው፡፡ ሊሸሹ ሲሉም ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ኹሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም ፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡

በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፤ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ሆነህ ነው?›› ስትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር ሁሉ ነገሯት፤ ራሳቸውንም ገለጡላትና ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡ ሥዕሏም ቅዱስ ሉቃስ የሳላት ነበረች፡፡

 

አንኳን ለበዓለ ጼዴንያ ማርያም አደረሳችሁ!

 

 

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የአዲስ ዓመት አባታዊ መልእክት !!!

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ የ፳፻፲፰ ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓል መግባትን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሰጥተዋል፣ የቅዱስነታቸው ሙሉ መልእክት የሚከተለው ነው።

ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰንመቱ ዓመተ ምሕረት፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ኣሜን!

  • በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
  • ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
  • የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
  • በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣
  • እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያት በሙሉ፣

አምላክነቱን ኣውቀን እንድናመልከው ዕድሜንና ዘመናትን የሚሰጠን እግዚብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺህ ዐሥራ ስምንት ዓመተ ምሕረት የርእሰ ዐውደ ዓመት በዓል አደረሰን አደረሳችሁ!

‹‹ወገብረ ኵሎ ኅቡረ ወኵሎ ኣሕዛበ እምአሐዱ ዕጓለ እመሕያው ከመ ይንበሩ ዲበ ኵሉ ገጸ ምድር፤ ወሠርዐ ዕድሜሁ ወዓመታቲሁ መጠነ ይነብሩ በዘየኃሥዎ ለእግዚአብሔር፤ እመ ይረክብዎ፤ ወያደምዕዎ፤ ወኢኮነ ርሑቀ እምኵልነ፡-

ምናልባትም እየመረመሩ ያገኙት እንደሆነ እግዚአብሔርን ይፈልጉ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ እንዲኖሩ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከኣንድ ፈጠረ፤ የተወሰኑትንም ዘመኖችና ለሚኖሩበት ስፍራ ደረጃ መደባላቸው፤ ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ ኣይደለም›› (የሐ. ሥራ. ፲፯÷፳፮)፤

ፈጣሬ ፍጥረታት እግዚአብሔር ትዕይንተ ዓለምንና በውስጡ የሚገኙ ፍጥረታትን የፈጠረ አምላክ ነው፤ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት የሚታዩና የማይታዩ ተብለው በጥቅል በቅዱስ መጽሓፍ ተገልጸዋል፤

የሰው ልጅ ከፍጥረታት መካከል ሆኖ ከኣንድ ወገን የተገኘ እንደሆነ በዚህ ጥቅስ ተጽፎአል፤

የሰው ልጅ ከፍጥረታት ሁሉ የተለየ ክብርና ደረጃ እንዳለው በቅዱስ መጽሓፍ በተደጋጋሚ ተገልጾአል፤ ልዩ የሚያደርገውም ከኣፈጣጠሩ ጀምሮ ነው፤

ሰው ልዩ ፍጡር መሆኑን ከሚገለጽባቸው መካከል እግዚአብሔር በሦስትነቱ “ሰውን በኣርኣያችንና በኣምሳላችን እንፍጠር” በሚል ልዩ ኣገላለጽ መፈጠሩ፣ ኣፈጣጠሩም በእግዚአሔር መልክና ኣምሳል መሆኑ፣ በእግዚአብሔር እፍታ ሕያው ነፍስ እንዲኖረው መደረጉ፣ በሥልጣንም የፍጥረታት ሁሉ የበላይ ሆኖ መሾሙ ከሌሎች ፍጥረታት ልዩ ያደርገዋል፡፡

ከዚህ አንጻር ሰው በዚህ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ዓለም ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ነው፤ የሁሉም ገዥ ነው፤ በተለይም በዚህ ዓለም ከሰው በላይ ሆኖ የፍጡራን ገዥ የሆነ ፍጡር እንደሌለ ሁላችንም የምናየውና የምናውቀው ነው፤

በላይኛው ዓለምም ቢሆን መላእክትን ጨምሮ ሰማይና ምድርን ከነግሣንግሡ እየገዛ ያለው ሰው የሆነ ጌታ ነው፤ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ የፍጥረት ገዥ ነው፤ እሱ ሰብእናችንን በፍጹም ተዋሕዶ የተዋሓደ በመሆኑ ሰብእናችን በተዋሕዶተ ቃል ኣምላክ ሆኖ የፍጥረታት ሁሉ ገዥ ሆኖኣልና ነው፤

ቅዱስ መጽሓፍም “ወተኰነኑ ሎቱ መላእክት ወሥልጣናት ወኵሉ ኃይል፡- መላእክት፣ ሥልጠናትና ኃይል ሁሉ ተገዙለት” በማለት ይህንን ያረጋግጣል፤ ይህ እግዚአብሔር ለኛ ለሰዎች ያጐናጸፈን ግሩምና አስደናቂ ጸጋ ነው፤ ለዚህም ነው “ወሰብእ ይከብር እምኵሉ ፍጥረት፡- ሰው ከፍጥረት ሁሉ ይከብራል” ተብሎ የሚዘመረው፤

  • የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውንና ኢትዮጵያውያት!

እኛ ሰዎች የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ ሆነን እንድንኖር በእግዚአብሔር ስንፈጠር በሕይወት እንድንኖር ነው፤ እግዚአብሔር በምድር ላይ በሕይወት ይኖሩ ዘንድ ሰውን ከኣንድ ፈጠረ የሚለው መጽሓፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮም ይህንን ያመለክታል፤

ሰዎች በምድር ላይ በሕይወት እንዲኖሩ የተፈጠሩ ሆነው እያለ በሕይወት እንዳይኖሩ ማድረግ ከፈቃደ እግዚአብሔር ጋር መጋጨትን ያስከትላል፤በዘመናችን ዓለማችንን እየፈተነ ያለው ተቀዳሚ ፈተና ሰዎች በሕይወት እንዳይኖሩ የማድረግ ዝንባሌ ነው፤

እንደዚህ ዓይነቱ ዝንባሌ በዓለም ባይኖር ኖሮ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቈጠሩ ድሆች ባሉበት ዓለም ለሰው ልጅ ሕይወት ማጥፊያ የሚሆን መሳሪያ ለማምረት ኁልቈ መሣፍርት የሌለው ገንዘብ አይወጣም ነበር፤

ይህ ክፉ የዓለም ዝንባሌ እንደ ክፋት ብቻ ሳይሆን እንደ ሞኝነትም የሚያሳይብን ነው፤ማንኛችንም ሰዎች ‹‹ሰው ማጥፋት ይሻላል ወይስ ማዳን›› ተብለን ብንጠየቅ መልሳችን ምን እንደሚሆን ይታወቃል፤

ነገር ግን ኣንፈጽመውም፣ ሞኝነት የሚያሰኘውም እዚህ ላይ ነው፤ የሚጠቅመንንና የመሰከርንለትን ትተን የሚጐዳንንና፣ ያልመሰከርንለትን እንፈጽማለንና ነው፤ ስለሆነም በሕይወት እንዲኖር የተፈጠረውን ሰው በሕይወት የመኖር መብቱን ከመንፈግ መቆጠብ የኣዲሱ ዓመት ትልቁ ኣጀንዳ ኣድርገን ብንወስድ ለሁላችንም ይበጀናልና እንቀበለው እንላለን፤

  • የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን! ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት!

ሰው በሕይወት እንዲኖር በእግዚአብሔር ሲፈጠር እግዚአብሔርን የሚፈልግበትና የሚያገኝበትን ዕድሜና ዘመንም እንደተሰጠው ከተጠቀሰው ክፍለ ንባብ እንገነዘባለን፤ መቼም እግዚአብሔር ሁሉን የፈጠረ በስራ ለስራ እንደሆነ የምንስተው ኣይሆንም፤

እግዚአብሔር ዕድሜና ዘመን ለሰዎች ሲሰጥ ሊሠራበት ነው፤ ስራውም መንፈሳዊና ዓለማዊ ነው፤ ተደምሮ ሲታይ ደግሞ ለሰው ጥቅም የሚውል ነው፤

እኛ ሰዎች በተሰጠን ዕድሜና ዘመን በመንፈሳዊው ሥራችን እግዚአብሔርን ፈልገን እንድናገኝ ተፈጥረናል፤ እሱን ማግኘት የማይቻል የሚመስለን ካለንም እሱ ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም ተብለናልና በመንፈስ ከፈለግነው በመንፈስ እንደምናገኘው መጽሐፉ ያስረዳናል፤ ስለሆነም በተሰጠን ዘመን ይህንን ሥራ መሥራት ይኖርብናል፤

በሌላ በኩል ለኑሮኣችን የሚያስፈልገንን ፍጆታ በበቂ ሁኔታ እንድናገኝ ላባችንን ኣንጠፍጥፈን መስራት ይገባናል፤ ይህም ከሰራን ያለጥርጥር የምናገኘው ነው፤ ሁለቱም የጐደሉብን በኛ አስተሳሰብ፣ አሠራርና አጠቃቀም እንጂ እግዚአብሔር ሳይፈቅድልን ቀርቶ ወይም ነፍጎን አይደለም፤

እግዚአብሔር የሰጠን ምድር በልዩ ልዩ ሀብተ ጸጋ የተሞላች እንደሆነች፣ የምንረግጠው መሬትም ወደ ሀብት መቀየር እንደሚቻል የተረጋገጠ ነው፤

ነገር ግን እኛ በምንራመድበት በእግራችን ሥር ያለውን ሀብት ትተን በሩቅ ያለውን ስንመለከት ሁሉን ያጣን ሆነን በችግር ወድቀን እንገኛለን፤ በተለይም እኛ ኢትዮጵያውያን በአሁኑ ጊዜ እየተፈታተነን ያለው ይኸው የተሳሳተ እሳቤ ነው፤

ኢትዮጵያ የሁላችንም ኢትዮጵያውያን ኣድርገን በማመን በእኩልነት፣ በኣንድነትና በስምምነት ከመጠቀም ይልቅ ያ የኔ ነው ያም የኔ ነው በሚል ኣባባል ምን ያህል ዋጋ እየተከፈለ እንደሆነ እያየን ነው፤

ይህ ግለኝነት ያየለበት አስተሳሰብ ገታ አድርገን በእኩልነትና በአብሮነት የሚያሳድገንን አስተሳሰብ በእጅጉ ይጠቅመናል፤ ይህንንም የአዲሱን ዓመት ምርጥ እሳቤ ኣድርገን ብንወስድ የተሻለ መግባቢያ ሊሆን ይችላል፤ አዲሱ ዓመት በኣዲስ እሳቤ ካላጀብነው አዲስ ሊሆን አይችልምና ነው፤

ስለሆነም ኣዲሱን ዓመት መልካም በሆነ ኣዲስ ኣሳብ ፣እግዚአብሔርንና ሰውን በሚያገናኝ ቅዱስ ተግባር፣ በልማት፣ በሰላም፣ በፍቅር፣ በዕርቅና በስምምነት እንድንቀበለው ወቅታዊ ጥሪያችን ነው፤

በመጨረሻም፣ አዲሱ ዓመት ለሀገር ሰላምና ልማት፣ ለሕዝቦች ኣንድነትና ስምምነት እንደዚሁም ኣለመግባባትን በፍትሕና  በዕርቅ ለመፍታት ከልብ የምንተጋበት መልካም የስኬት ዘመን እንዲሆንልን እንጸልይ፣ በዚህም መላ ሕዝባችን ጠንክሮ እንዲሠራ ለመላ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ሁሉ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፤

እግዚአብሔር ኣምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ኣሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣

መስከረም ቀን ፳፻፲፰ .

አዲስ አበባኢትዮጵያ

በጎ መካሪ

የሰውን ልጅ የውድቀት ታሪክ ስንመለከት፣ የመጀመሪያው መንሥኤ የክፉ ምክር ውጤት እንደሆነ እንረዳለን። አባታችን አዳም የእግዚአብሔርን ሕግ ጠብቆ ለሰባት ዓመታት ያህል በገነት ቢኖርም፣ በሰይጣን ክፉ ምክር ተታሎ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ ገነትን የመሰለ ቦታ አጥቷል። ይህ የሆነው በክፉ ምክር ምክንያት ነው። ዛሬም በዚህች ምድር፣ እንደ ጥንቱ ሁሉ፣ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ በክፉ ምክር የሚያታልሉና ላልተገባ ነገር የሚዳርጉ ክፉ አማካሪዎች አይጠፉም።

በተቃራኒው ደግሞ ለበጎ ነገር የሚያነሣሱ፣ ትክክለኛውን መንገድ የሚያሳዩ፣ መርተው ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሱ እንደ ሐዋርያው ፊልጶስ ያሉ መልካም አማካሪዎችና የልብ ወዳጆችም ብዙ ናቸው። (ዮሐ ፩፥፵፮-፶፩)

ነገረ ጳጕሜን

ኢትዮጵያ የራሷ ባህል፣ ታሪክና ሃይማኖት ያላት ይህንም በትውፊትና በመጽሐፍ ቅዱስ ይዛ የቆየች ሀገር ናት፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው ውሸት ቢናገርና በውሸታሞች መካከል ቢደገፍ ሌሎችም ውሸት ይናገሩ እንደማይባል ኢትዮጵያም ሌሎች በንጉሣቸው በጣዖታቸው ስም በየጊዜው እየቀያየሩ የዘመን ቆጠራን ቢያከብሩ የራሷን እውነት ትታ የእነርሱን ውሸት ትቀበል እንደማይባል መረዳት ይጠይቃል።

የቱን ታስታውሳላችሁ?

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? በየዓመቱ በጉጉት የምጠብቃት ጾመ ፍልሰታ እንዴት አለፈ? እንዴት አቅማችን በመጾም፣ በመጸለይ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከቤዛዊት ዓለም በረከትን ተቀብለን እንዳለፍንበት ተስፋችን እሙን ነው፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ከጾመ ፍልሰታ በፊት “የቱን ታስታውሳላችሁ?” በሚል ርእስ ስንማራቸው ከነበሩ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር መካከል የተወሰነ ጥያቄዎችን ጠይቀናችሁ እናንተም ምላሹን ልካችሁልን ነበር፤ ለጥያቄዎቹ ተገቢውን ምላሽ ለሚሰጡም እንደተለመደው ሽልማቶችን እንደምናዘጋጅ ነግረናችሁ ነበር፡፡ የሽልማት መርሐ ግብሩን በተለየ መርሐ ግብር እናዘጋጃለን፡፡

በእንተ ዕረፍቱ ለተክለ ሃይማኖት

የስሙ መነሻ ፊደሉ ትእምርተ መስቀል የሆነው፣ የወንጌል ተቀዳሚ ስም ማቴዎስ፣ የቅዱስ ወንጌል ጸሐፊዋና ሰባኪዋ ማርቆስ፣ የነፍስና የሥጋ ሐኪም ሉቃስ፣ ከሁሉ ይልቅ ሥልጣኑ ከፍ ያለ ጴጥሮስ፣ ሰማያዊ አርበኛ ሚናስ፣ አነዋወሩ በብቸኝነትና በንጽሕና የሆነ ኤልያስ፣ የቤተ ክርስቲያን የልጆቿ አባት ባስልዮስ፣ የቤተ ራባው ጸዋሚ ተሐራሚ ዮሐንስ፣ ዐሥረኛው የአርማንያው ጎርጎርዮስ፣ ግሙደ እግር ያዕቆብ ሐዋርያ፣ እንግዳ መቀበል ፍጹም ተግባሩ የሆነ አብርሃም፣ ጸሐፊ ምሥጢራት ወጥበባት ሄኖክ፣ መሥዋዕቱ የሠመረለት አቤል፣ ሕዝብን የሚያስተዳድር ዮሴፍ፣ እግዚአብሔርን በንጹሕ ልቡና የሚያመሰግን ዳዊት፣ ከሐዲዎችን የሚበቀል ቄርሎስ፣……………..

‹‹እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?››

ከነገደ ብንያም የተወለደው ነቢዩ ሚክያስ የስሙ ትርጓሜ ‹‹እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?›› ነው። እንደ ስሙ ትርጕምም የእግዚአብሔር ቸርነት ከየትኛውም ኃጢአትና ከየትኞቹም በቊጥር የበዙ ኃጢአተኞች ይልቅ ታላቅ መሆኑን፣ ይልቁንም እግዚአብሔር ኃጢአትን እንጂ ኃጢአተኞችን የማይጸየፍ እንደሆነ አስተምሯል። በሰባት ምዕራፎች በተጠቃለለ ነገረ ድኅነትንና ንስሐን ማዕከል ያደረገ ትምህርቱና ትንቢቱ መሲሑ የሚወለደበትን ስፍራ ሳይቀር ‘ደረቅ ትንቢት’ በግልጽ እንዲህ ሲል “አንቺ ቤተልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘለዓለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል” ተናግሯል።

ወርኃ ነሐሴ

ነሐሴ የሚለውን ቃል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ላይ “ናሴ” ማለት መጨረሻ የመስከረም ዐሥራ ሁለተኛ በማለት ይፈቱታል፡፡ (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝመበ ቃላት ገጽ ፮፻፴፯)

ጽኑ እምነት

እለእስክንድሮስ የተባለው መፍቀሬ ጣዖት፣ ጸላዬ እግዚአብሔር፣ የዲያቢሎስ ምርኮኛ የሆነው በሰው እጅ ከድንጋይ ተጠርቦ ለተሠራው ጣዖት ሕዝቡን እንዲሰግዱ ሲያስገድድ፣ ስቶ ሲያስት፣ ሲያስፈራራ ኖሯል፡፡ አብዛኛው ለሥጋው ሳስቶ፣ መከራውን ተሰቆ ለጣዖት ሲሰግድ ሕፃን ቂርቆስ ግን እምቢ አለ፤ የቀደሙ አባቶቹን የተጋድሎ ታሪክ ያውቃልና ልቡን አጸና፤ ለመከራው ተዘጋጀ፤ እናቱ ለልጇ ሳስታ፣ ለጣዖት ልትንበረከክ፣ ልትክድ ሲዳዳት ሕፃኑ ግን ጸና፤ መከራውን ሳይሰቀቅ እለ እስከንድሮስ ላቆመው ጣዖት አልሰግድም አለ፡፡

‹‹አትጨነቁ…›› (ማቴ.፮፥፴፬)

ሰዎች  መልካምና ክፋ ነገርን ለማሳካት ይጨነቃሉ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹አትጨነቁ›› ያለን ለክፋትና ለኃላፊው ዓለም ተጨንቀን መፍትሔ ለማናመጣለት ነገር ነው፡፡ (ማቴ.፮፥፴፬) ፈጣሪያችን ለእኛ ለልጆቹ በዚህ ምድር በእንግድነት ስንኖር ምን እንደሚያስፈልገን ያውቃል፤ የሚያሻንንም ይሰጠናል፤ እናስብ ዘንድ አስተዋይ አእምሮ ሰጥቶናል፤ ማሰብ ከሚገባን በላይ ደግሞ ልንጨነቅ ስለማይገባ ‹‹አትጨነቁ›› አለ፡፡ አበው በብሂላቸው ‹‹…አስብ እንጂ አትጨነቅ..›› የሚሉን ለዚህ ነው፡፡ በምድር ስንኖር በማሰብ በመጠንቀቅ፣ በመጠበቅ እንደ ርግብ የዋህ እንደ እባብ ደግሞ ብልህ ሆነን ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ልንፈራና ልንጨነቅ እንደማይገባ ግን ክርስትናችን ያስተምረናል፡፡ ጌታችን ለአባቶቻችንን ቅዱሳን ሐዋርያት ስለሚቀበለው መከራ፣ ስለሞቱ ሲነግራቸው ባዘኑ ጊዜ ‹‹…ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ በእኔም ደግሞ እመኑ…›› በማለት በአንዳች ነገር እንዳይጨነቁ ልባቸው እንዳይታወክ ነገራቸው፡፡ (ዮሐ. ፲፬፥፩)