“የሚሰማኝ ግን በተስፋ ይኖራል” (ምሳ.፩፥፴፫)
በብዙ ኅብረ አምሳል አምላካችን እግዚአብሔር የሰውን ልጅ አስተምሯል። ነቢያቱን በብዙ ቋንቋና ምሳሌ አናግሯል። የሰው ልጅ በልቡናው መርምሮ የተወደደ ሕይወት መኖር ሲሳነው በሊቀ ነቢያት ሙሴ በኩል ሕገ ኦሪትን ሰጥቶታል። በሕገ ልቡና “እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን” እንደሚል ቀደምት አበው የተጻፈ ነገር ሳይኖር እንደ እግዚአብሔር አሳብ መኖር ችለዋል። (ሮሜ.፰፥፳፰) እንደ አሳቡ መኖር ላልቻሉት ደሞ ጽሕፈቱን እያዩ በንጽሕና እንዲኖሩ ኦሪት ተጽፋ በሙሴ በኩል ተሰጠች። በኋላም ራሱ ጌታችን ሰው ሁኖ ፻፳ ቤተሰብ መርጦ በቃልና በገቢር አስተምሯል። ይህን ትምህርትም ወንጌላውያን ጽፈው ደጉሰው እንዲያስቀምጡት የጌታችን ፈቃድ ሁኖ ለትውልድ ተላልፏል።