ብዙ ከተሰጠው ከእርሱ ብዙ ይፈለግበታል
ሐምሌ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ቤተ ክርስቲያናችን ካሏት አህጉረ ስብከት ሁሉ ለየት የሚልበት ባሕርያት አሉት፡፡ ሀገረ ስብከቱ የሀገሪቱ ዋና ከተማ እንደመሆኑ በተለያዩ ምክንያቶች ከሁሉም አህጉረ ስብከት የሚመጡ ክርስቲያኖች አገልግሎት የሚያገኙባቸው ገዳማትና አድባራት ያሉበት ሀገረ ስብከት ነው፡፡ በተለያዩ ቋንቋዎች የሚናገሩ የተለያዩ ባህሎች ያሏቸው የቤተ ክርስቲያን ቤተሰቦች ተገናኝተው በአንድነት መንፈስ አገልግሎት የሚያገኙበትና የሚቀበሉበት ሀገረ ስብከትም ነው፡፡
ሀገረ ስብከቱ በርካታ የቤተ ክርስቲያናችን መምህራን ሊቃውንት የሚገኙበትም ሀገረ ስብከት ነው፡፡ በመንፈሳዊው ትምህርት ብቻ ሳይሆን በዓለሙ የሚሰጠውን ማኅበራዊና የተፈጥሮ ሳይንስ፣ የሙያና የቀለም ትምህርቶች የተማሩ አንቱ የተባሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆችም የሚገኙበት ሀገረ ስብከት ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን በታላቅ ፍቅር የሚጠብቃት፣ አገልግሎቷን ዕለት ዕለት የሚሻ ቸርና የዋህ ሕዝበ ክርስቲያን ያለበት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቤተ ክርስቲያን የምትተዳደርበትን ብዙ የገንዘብ የቁሳቁስና የሰው ኃይል ሀብት ይዞ የሚገኝ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ አርአያነት ያለው አግልግሎትን ሊሰጥም እንደሚችል የሚታሰብ ነው፡፡