የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በአፋን ኦሮሞ
ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን ሓላፊነትና የአባቶችን አደራ ተቀብሎ ወንጌለ መንግሥትን በመላው ዓለም ለማዳረስ የሚተጋው ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሥር ያለ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሮና መሠረተ እምነት የሚጠብቅና የሚያስጠብቅ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀ ደንብ የተሰጠውና በደንቡ መሠረት ብቻ የሚመራ ማኅበር እንጂ ራሱን የቻለ የእምነት ተቋም አይደለም፡፡ አባላቱም ለአንድ መንፈሳዊ ዓላማ ከመላው ኢትዮጵያ የተሰባሰቡ የተዋሕዶ ልጆች እንጂ የአንድ አካባቢ ተወላጆችና አንድ ብቻ ቋንቋ ተናጋሪዎች አይደሉም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናን በሚሰሙት ቋንቋ ዅሉ ቃለ እግዚአብሔርን ተምረው ለመንግሥተ ሰማይ ይበቁ ዘንድ የሚጠበቅበትን መንፈሳዊና አገራዊ ድርሻ በአግባቡ ለመወጣት የሚሠራ፤ በአጠቃላይ ለመንፈሳዊ ተልእኮ የሚፋጠን ማኅበር ነው፡፡