‹‹ለእግዚአብሔርም የመዓዛ ሽታ የሚሆንን መባንና መሥዋዕትን አድርጎ ስለ እናንተ ራሱን አሳልፎ እንደሰጠ ክርስቶስ በፍቅር ተመላለሱ›› (ኤፌ. ፭፥፪)
የእግዚአብሔር ልጆች እንሆን ዘንድ አምላኮተ እግዚአብሔርን መፈጸም ይጠበቅብናል፡፡ በመጽሐፍም አባቶቻችን በብሉይ ኪዳን ፍየል፣ በግ፣ ወይፈን፣ ርግብን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር ሲያቀርቡ እሳት ከሰማይ ወርዳ መሥዋዕቱን ትበላላቸው እንደነበር ይገልጻል፡፡ መሥዋዕታቸውንም እሳት መብላቱ እግዚአብሔር ለመቀበሉ ማረጋገጫ ነበረች፡፡ እነርሱም በዚህ ከእግዚአብሔር ጋር ታርቀው ይኖሩ ነበር፡፡ ቅዱስ አባታችን ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን ሲተረጉም ‹‹መሥዋዕት ማለት አንተ ሰው ዛሬ በግ፣ ፍየል፣ ወይፈን ወይም ርግብ የምታርድ አይምሰልህ፤ ራሱን ሠውቷልና፡፡ ከአንተ የሚፈልገው መሥዋዕት ምንድነው ካልከኝ ራስህን መሥዋዕት አድርገህ ማቀረብ ነው፤ ክህነት የማያስፈልጋት መሥዋዕት ማለት ይህች ናት›› ብሏል፡፡ መሥዋዕት የሚቀርብበት መረብረቢያው፣ መጸፍጸፊያው፣ ድንጋዩ፣ ጉልቻው፣ እንጨቱ፣ እና ማገዶው ደግሞ ምሕረትና ርኅራኄ ነው፡፡ ፍቅር፣ ትዕግሥት፣ ትሕትና፣ የዋህነት እና ንጽሕና የመሥዋዕት መረብረቢያዎች ናቸው፡፡ ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት እና ቸርነት መሥዋዕት ሲሆኑ የሚቀርቡበት ምድጃ ትዕግሥትና ትሕትና ነው፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)