በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውን ተሳታፊዎች ተናገሩ

በዝግጅት ክፍሉ

ታኅሣሥ ፳፯ ቀን ፳፻፱ .

img_0298

ዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ማርያም ገዳም

img_0351

፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት በዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ድንግል ማርያም ገዳም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን፣ አባቶች ካህናትና ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በተገኙበት ታኅሣሥ ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም መካሔዱ የሚታወስ ነው፡፡

img_0325

በሐዊረ ሕይወቱ ጠዋትና ከሰዓት በኋላ በተከናወነው መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ በማኅበሩ ሰባክያነ ወንጌል መ/ር ምትኩ አበራና መ/ር ያረጋል አበጋዝ ልቡናን የሚገዛና ድካመ ነፍስን የሚጠግን ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

img_0296

ምክረ አበው አቅራቢ አባቶች

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ለ ‹‹ምክረ አበው›› በተጋበዙት በቆሞስ አባ ሳሙኤል በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የብሉያትና ሐዲሳት ትርጓሜ መምህር፤ በአባ ገብረ ኪዳን በደቡብ ጎንደር እስቴ መካነ ኢየሱስ ደብር የአባ ኤስድሮስ ጉባኤ ቤት የሐዲሳት ትርጓሜ መምህርና የብሉያት ደቀ መዝሙር፤ በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ በአዲስ አበባ የምሥራቀ ፀሐይ ቀበና መድኀኔ ዓለም ደብር የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር እና የስብከተ ወንጌል ክፍል ሓላፊ የብዙ ምእመናንን ጥያቄ የሚመልስ ትምህርት ቀርቧል፡፡

img_0333

የማኅበሩ መዘምራን ወረብና መዝሙር ሲያቀርቡ

በማኅበሩ ዘማርያንና በሊቀ መዘምራን ዲ/ን ቴዎድሮስ ዮሴፍ የቀረበው ያሬዳዊ ወረብና መዝሙርም የጉባኤው ክፍል ነበር፡፡

የሐዊረ ሕይወቱ ዐቢይ ኰሚቴ ሰብሳቢ አቶ ኤርምያስ ዓለሙ ለዝግጅት ክፍላችን እንዳስታወቁት ትኬት በመግዛት የመጡ ስምንት ሺሕ፤ ለልዩ ልዩ አገልግሎት ለመስጠት የተመደቡ አንድ ሺሕ፤ ከዓለም ገና እና ከአካባቢው የመጡ ደግሞ በግምት ሁለት ሺሕ፤ በድምሩ ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ የታደሙ ሲኾን በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውንም ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ቃለ ምዕዳን በሰጡበት ወቅት ‹‹ይህ ጉባኤ በዚህ ቦታ መዘጋጀቱ ለገዳሙ ብቻ ሳይኾን አጠቃላይ ለሀገረ ስብከታችን ትልቅ ዕድል ነው፤ በዚህ አካባቢ የሚገኙ ምእመናንም በመርሐ ግብሩ ትልቅ ተስፋ አግኝተዋል፤›› ካሉ በኋላ ‹‹ይህንን ጉባኤ በዚህ ቦታ በማካሔድ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስደሰቱ ማኅበሩን አመስግነዋለሁ፤›› በማለት የማኅበሩን አገልግሎት አበረታተዋል፡፡

ብ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ከከፊል የጉባኤው ተሳታፊዎች ጋር

ከመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች መካከል አንዳንዶቹ በሐዊረ ሕይወቱ በመሳተፋቸው በርካታ መንፈሳዊ ቁም ነገር ማግኘታቸውን፣ በትምህርቱ ነፍሳቸው መርካቷንና አእምሯቸውም መደሰቱን ጠቅሰው ይህን ዅሉ ምእመን በአንድ ድንኳን ሥር አሰባስቦ፤ ቍርስ እና ምሳ መግቦ ቃለ እግዚአብሔር እንዲማር በማድረጉ ማኅበረ ቅዱሳንን አድንቀዋል፡፡ አያይዘውም ‹‹መርሐ ግብሩ ከዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየወሩ ቢካሔድልን?›› የሚል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ed

የጉባኤው ተሳታፊ አባቶችና ወንድሞች በከፊል

የዓለም ገና እና የአካባቢው ማኅበረ ካህናትና ምእመናንም ሐዊረ ሕይወቱ በአካባቢያቸው በመካሔዱ ካገኙት መንፈሳዊ ትምህርት ባሻገር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መንፈሳዊ ጉባኤ የማዘጋጀት ልምድን ከማኅበረ ቅዱሳን መማራቸውንም ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በማኅበሩ ሰብሳቢ በአቶ ታምሩ ለጋ የማኅበሩ መልእክት የቀረበ ሲኾን በመልእክቱም ማኅበሩ በሚያበረክተው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በመሳተፍ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በጋራ ለመደገፍና አገልግሎቷን በሚፈለገው ደረጃ ለማሳደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን የበኩሉን እገዛ ያደርግ ዘንድ ሰብሳቢው ጥሪያቸውን በቤተ ክርስቲያን ስም አስተላልፈዋል፡፡

wo

የጉባኤው ተሳታፊ እናቶችና እኅቶች በከፊል

እንደዚሁም የማኅበሩ የስድስት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ የትኩረት አቅጣጫዎችን የስልታዊ ዕቅዱ ክንውንና ትግበራ ጽ/ቤት ሓላፊ አቶ ፋንታኹን ዋቄ አቅርበው ለዕቅዱ መሳካትም ምእመናን በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ የድርሻቸውን አስተዋፅዖ እንዲያበርክቱ አሳስበዋል፡፡

በመቀጠልም ሐዊረ ሕይወቱ በተሳካ ኹኔታ እንዲከናወን ድጋፍና ትብብር ያደረጉ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስንና የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችን፤ የሰበታ አዋስ ወረዳ ቤተ ክህነትና ወረዳ ማእከሉን፤ የደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስና ቅድስት ማርያም ገዳም ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤትን፣ ማኅበረ ካናትንና ምእመናንን፤ ከፌዴራል መንግሥት ጀምሮ በየደረጃው እስከ ከተማ አስተዳደሩ ድረስ የሚገኙ የመንግሥት አካላትን ማኅበሩ በእግዚአብሔር ስም አመስግኗል፡፡

11

መርሐ ግብሩ በጸሎት ሲፈጸም

በመጨረሻም ፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ተፈጽሟል፡፡