ስዊድናዊው ፕሮፌሰር አምሳ ሁለት መጻሕፍትን አበረከቱ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በስዊድን አገር የሉንድ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ የኾኑት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሮቢንሰን በልዩ ልዩ ባለሙያዎችና በተለያዩ አርእስት በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጁ አምሳ ሁለት መጻሕፍትን ለማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል በስጦታ መልክ አበረከቱ፡፡

ፕ/ር ሳሙኤል ሮቢንሰን መጻሕፍታቸውን ሲያስረክቡ

‹TAITU Empress of Ethiopia; Lake Tana and The Blue Nile an Abyssinian Quest; Education in Ethiopia Prospect and Retrospect; The Abyssinian Difficulty the Emperor Tewodross and the Magdala Campaign 1867-68; Slavery, Slave Trade and Abolition Attempts in Egypt and Sudan› የሚሉት ከአምሳ ሁለቱ መጻሕፍት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

ዶ/ር ዮሐንስ አድገህ መጻሕፍቱን ሲረከቡ

ወላጅ አባታቸው ፕሮፌሰር ሮቢንሰን፣ ከሌላ እምነት ወደ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት የተመለሱ የቤተ ክርስቲያን ልጅ እንደ ነበሩና በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) ለበርካታ ዓመታት በመምህርነት አገልግሎት እንደ ሰጡ ያስታወሱት ፕሮፌሰር ሳሙኤል፣ ማኅበሩ የሚያከናውነውን የጥናትና ምርምር ተግባር ለመደገፍና ለማበረታታት በውድ ገንዘብ የገዟቸውን እነዚህን መጻሕፍት በወላጅ አባታቸው ስም ለማእከሉ ማበርከታቸውን ተናግረዋል፡፡

በምጣኔ ሀብት፣ በታሪክ፣ በኅብረተሰብና አካባቢ ሳይንስ፣ በፖለቲካ እና ሌላም የትምህርት መስክ የተዘጋጁት መጻሕፍቱ በተለይ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራን፣ ተመራማሪዎችና ተማሪዎች የጎላ ጠቀሜታ እንዳላቸው ፕሮፌሰሩ ገልጸዋል፡፡

ፕሮፌሰሩ መጻሕፍቶቻቸውን ለማኅበሩ ያበረከቱት በስዊድን አገር የፒኤችዲ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ በሚገኙት የቀድሞው የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዳይሬክተር ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜ አስተባባሪነት መኾኑን የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ሞላ ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡

አቶ ጌታቸው እንዳስታወቁት መጻሕፍቱ በተበረከቱበት ሚያዝያ ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከልዩ ልዩ ዓለማቀፍ የትምህርት ተቋማት የመጡ የውጭ አገር ዜጎች ከፕሮፌሰር ሳሙኤል ጋር በማኅበሩ ሕንጻ ተገኝተዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በከፊል

በዕለቱ በነበረው መርሐ ግብር፣ ፕሮፌሰር ሽፈራው በቀለ (ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) የኢትዮጵያን ታሪክ፤ ዶክተር ዮሐንስ አድገህ (የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዋና ዳይሬክተር) የማኅበረ ቅዱሳንን አመሠራረትና የማእከሉን ተግባር በአጭሩ ለእንግዶቹ አቅርበዋል፡፡ ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜም ማኅበሩ በጥናትና ምርምር ማእከሉ አማካይነት ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጠውን አገልግሎት አስረድተዋል፡፡

ከግራ ወደ ቀኝ፡- ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜ፣ ፕ/ር ሽፈራው በቀለ እና ፕ/ር ሳሙኤል ሮቢንሰን

መጻሕፍቱ አንባብያን ይጠቀሙባቸው ዘንድ በሕጋዊ ደረሰኝ ወደ ማኅበሩ ቤተ መጻሕፍት ገቢ መደረጋቸውን የጠቆሙት አቶ ጌታቸው ሞላ፣ ማኅበረ ቅዱሳን ምሁራንን በማሳተፍ የሚያከናውነውን የጥናትና ምርምር ሥራ የውጭ አገር ዜጎች ለመደገፍ መነሣሣታቸው ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውጩ ዓለም ዘንድ ያላትን ልዩ ቦታ ያመላክታል፡፡ መጻሕፍት ልገሳውም የጥናትና ምርምር ማእከሉን ወደ ተቋም ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ከግብ ለማድረስ ያግዛል›› ብለዋል፡፡

አቶ ጌታቸው ሞላ የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር

በመጨረሻም ፕሮፌሰር ሳሙኤልንና ሌሎች የትምህርት ባልንጀሮቻቸውን በማስተባበር መጻሕፍቱ ለማኅበሩ ቤተ መጻሕፍት ገቢ እንዲኾኑ ያደረጉትን ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜን የማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር በቤተ ክርስቲያን ስም አመስግነው ‹‹ማኅበረ ቅዱሳን የሚሰጠውን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመደገፍ ፈቃደኛ የኾናችሁ አጋሮቻችን! እንደ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሮቢንሰን ልዩ ልዩ መጻሕፍትን ለቤተ መጻሕፍታችን በማበርከት መንፈሳዊ ድርሻችሁን እንድትወጡ ይኹን›› ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በጥናትና ምርምር ማእከሉ ሥር የሚገኘው የማኅበረ ቅዱሳን ቤተ መጻሕፍት ቅዱሳት መጻሕፍትን ብቻ ሳይኾን በልዩ ልዩ የትምህርት መስክና ቋንቋ የተዘጋጁ በርካታ ዓለማቀፍ የጥናትና የምርምር ሥራዎችን ለንባብ እንደሚያቀርብ፤ ዘወትር ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ከጠዋቱ 2፡3 – ምሽቱ 1፡00 ሰዓት (የምሳ ሰዓትን ጨምሮ) አገልግሎት እንደሚሰጥ ያስረዱት የማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር፣ ‹‹መንፈሳዊም ኾነ ዘመናዊ ዕውቀታችሁን ለማዳበር የምትፈልጉ ዅሉ ከማኅበሩ ሕንጻ ስድስተኛ ፎቅ ድረስ በመምጣት በአገልግሎቱ ተጠቃሚ ኹኑ›› ሲሉ መንፈሳዊ ጥሪአቸውን አቅርበዋል፡፡

ትንሣኤ ክርስቶስ በሊቃውንት – ካለፈው የቀጠለ

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹በእርሱ ሞት ከብረናል፡፡ በመለኮቱ ሞት ሳይኖርበት በሥጋ ሞተ፤ ምንጊዜም ቢኾን እርሱ የሕይወት ልጅ ሕይወት ነው፡፡ ይኸውም ከእግዚአብሔር አብ የተወለደው ልደት ነው፡፡ ወደ ሕይወት ሥጋ ደፍሮ በመጣ ጊዜ ሞት እንዲህ ድል ተነሣ፤ መፍረስ መበስበስም በእርሱ (በክርስቶስ) እንዲህ ጠፋ፤ ሞትም ድል ተነሣ፤›› (ቅዱስ ቄርሎስ፣ ሃይ. አበ. ፸፪፥፲፪)፡፡

‹‹ሕማምን፣ ሞትን ገንዘብ አደረ፡፡ በሥጋው የሞተው የእኛን ባሕርይ በመዋሐዱ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ተዋሕዶውን አስረዳ፡፡ ሞት ሰው የመኾን ሥራ ነውና፡፡ ከሙታን ተለይቶ መነሣትም አምላክ የመኾን ሥራ ነውና፡፡ እነዚህ ሁለት ሥራዎችን (ሞትን እና ትንሣኤን) እናውቃለን፤›› (ዝኒ ከማሁ ፸፪፥፴፭)፡፡

‹‹በሥጋ ሞተ እንዳልን ዳግመኛ በሥጋ ተነሣ እንላለን፤ ስለ ትንሣኤም የእርሱ ገንዘብ እንደ ኾነ፤ ሙስና መቃብርም እንዳላገኘው ይነገራል፡፡ ይህ (መሞት፣ መነሣት) ለመለኮት አይነገርም፡፡ የተነሣው ሥጋው ነው እንጂ፤›› (ዝኒ ከማሁ ፸፱፥፱)፡፡

‹‹የሞትን ሥልጣን አጠፋ፤ ዲያብሎስንና ኃይሉን (ኃጢአትን) ሻረ፡፡ የብረት መዝጊያዎችን ሰበረ (ፍዳ፣ መርገምን አጠፋ)፡፡ ሲኦልን በዘበዘ፤ የጣዖት ቤቶችን አፈረሰ፡፡ የምሕረትን በር ከፈተ፡፡ ይህችውም በደሙ የከበረች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ለዅሉ የዘለዓለም ሕይወት መገኛ የሚኾን ልጅነት የተገኘበት ሥጋውን ደሙን ሰጠን፤›› (ቅዱስ ቴዎዶስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፹፫፥፮)፡፡

‹‹ለእኛስ እግዚአብሔር ቃል በባሕርየ መለኮቱ እንደ ታመመ፤ እንደ ሞተ፤ እንደ ተቀበረ ልንናገር አይገባንም፡፡ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ ሞት የሌለበት እንደ ኾነ፣ መድኃኒታችን በሚኾን በሞቱና በሦስተኛው ቀንም በመነሣቱ ትንሣኤን እንደ ሰጠን እናምናለን፡፡ የሞተ እርሱ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና፡፡ ዅሉን የሚችል እርሱ ካልተነሣ፣ የችሎታ ዅሉ ባለቤት እርሱ የሌለ ከኾነ፣ እንኪያስ ትንሣኤም ሐሰት ነዋ! ትንሣኤም ሐሰት ከኾነ ሃይማኖታችን ከንቱ ነው፡፡ እንኪያስ አይሁድንም እንመስላቸዋለን፡፡ ሰው እንደ መኾኑ በሥጋ ባይሞትስ በሞት ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ እንደ መኾኑ ሞትን ባላጠፋ ነበር፡፡ የአዳም የዕዳ ደብዳቤም ከእግዚአብሔርና ከሰው መካከል ባልተደመሰሰም ነበር፤›› (ቅዱስ ሳዊሮስ፣ ሃይ. አበ. ፹፬፥፲፰-፳)፡፡

‹‹ፈጣሪያችን ክርስቶስ ለጌትነቱ እንደሚገባ ሥጋ መለወጥ የሌለበት እስኪኾን ድረስ ድንቅ በሚያሰኝ ትንሣኤ ሙስና መቃብርን አጥፍቷልና፤ በሥጋ በተቀበላቸው በሚያድኑ በእነዚህ ሕማማት ከጽኑ ሞት፣ ከዲያብሎስም ሥልጣን ያድነን ዘንድ፤ ወደ ቀደመ ቦታችንም ያገባን ዘንድ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ ዘአንጾኪያ፣ ሃይ. አበ. ፺፥፴፬)፡፡

‹‹ይታመም ዘንድ በተገባው በሥጋው፣ ነውር የሌለበትን ሕማም በፈቃዱ በእውነት ተቀበለ እንጂ በምትሐት እንዳልታመመ እናገራለሁ፡፡ እንደ ሕማሙ ሞትንም በመስቀል ላይ ተቀበለ፡፡ ለአምላክነቱ በሚገባ፣ ድንቅ በሚያሰኝ ትንሣኤውም የጌትነቱን ሥልጣን ገለጠ፡፡ ሥጋውንም የማይሞት አደረገ፡፡ ከኃጢአት በራቀ በንጹሕ ማኅፀን በተዋሐደው ጊዜ ለመለኮት ገንዘብ ስለኾነ በሥራው ዅሉ አይለወጥም፤›› (ቅዱስ ቴዎዶስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፪፥፲፭)፡፡

‹‹ሕማም የማይስማማው እርሱ በሥጋ ሞትን ታገሠ፤ ብረት ወደ እሳት በገባ ጊዜ ዅለንተናው እሳት እንደኾነ እስኪታሰብ ድረስ በእሳት ዋዕይ እንዲግል፤ በመዶሻ በተመታ ጊዜ በመስፍሕ (መቀጥቀጫ) ላይ እንዲሳብ (እንዲቀጠቀጥ)፤ እሳትም ከብረት ጋር ተዋሕዶ ሳለ ፈጽሞ እርሱ እንዳይመታ፤ ከብረቱም እንዳይለይ፤ ግን የመዶሻ ኃይል ሳያገኘው እንዲመታ፤ ለመዶሻ እንዲሰጥ፤ የሚያድን የጌታ ሕማም እንዲህ እንደ ኾነ ዕወቅ፡፡ በዚህ ትንሽ ምሳሌ፤ በእሳትና በብረት ተዋሕዶ ምልክትነት ፍጹም ተዋሕዶን እንወቅ፤ የእግዚአብሔር ቃል ይህ መከራና ሕማምን የሚቀበል ሥጋን ተዋሕዶ በሞተ ጊዜም ከሦስት ቀን በኋላ አምላክነቱ በተገለጠበት ትንሣኤው ሞትን አጠፋው፡፡ ሥጋው በመቃብር በመቀበሩም በመቃብር ውስጥ የነበረ መፍረስ፣ መበስበስን አጠፋልን፤ ከሥሩም ነቀለው፡፡ ለዚህም ማስረጃ ከቅዱሳን ወገን ብዙ ሰዎች ተነሡ፤›› (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፮፥፶-፶፪)፡፡

‹‹ዳግመኛ እርሱ እንደ ሞተ፤ በሦስተኛውም ቀን እንደ ተነሣ፤ ስለ ተነሣም ሥጋው የማይፈርስ የማይበሰብስ፣ የማይታመም፣ የማይሞት እንደ ኾነ እናምናለን፡፡ ሥጋውም ከእርሱ ጋር አንድ ኾኖ ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአርያም በልዑል ዙፋኑ ተቀመጠ፡፡ ዳግመኛም በሙታንና በሕያዋን ይፈርድ ዘንድ ዅሉ አንድ ኾኖ በሚነሣበት ጊዜ እርሱ በጌትነት ይመጣል፡፡ ለዅሉም እንደ ሥራው ይከፍለዋል፡፡ እኛ በእነዚህ ቃላት ሳናወላውል ጸንተን እንኖራለን፤›› (ቅዱስ ዲዮናስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፱፥፴፪)፡፡

‹‹በፈቃዱ በሥጋው የእኛን ሕማም ታመመ፤ በእውነት የእኛን ሞት ሞተ፡፡ ይኸውም የነፍስ ከሥጋ መለየት ነው፡፡ በፈቃዱ በተለየ አካሉ ሞትን ገንዘብ አደረገ፡፡ በሦስተኛውም ቀን በሥልጣኑ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአባቱ ዕሪና ተቀመጠ፡፡ በኋለኛይቱ ቀንም በሙታንና በሕያዋን ሊፈርድ ይመጣል፤›› (ቅዱስ ፊላታዎስ፣ ሃይ. አበ. ፻፭፥፲፬)፡፡

‹‹በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፤ በሦስተኛው ቀን በመነሣቱም ሲኦልን በዘበዘ፣ ለዅሉም ትንሣኤን ገለጠ፡፡ ፈጽሞ አልተለወጠም፤ ለዅሉ አምላክነቱን አስረዳ፤ ሙስና መቃብርን ከእኛ አጠፋ፤ በቀደመ ሰው በአባታችን በአዳም ትእዛዝ ማፍረስ ምክንያት ሠልጥኖብን ለነበረ ኃጢአት ከመገዛት አዳነን፤›› (ቅዱስ ዲዮናስዮስ ፻፲፩፥፲፫)፡፡

‹‹እሑድ በመንፈቀ ሌሊት ነፍሱን ከሥጋው አዋሕዶ በመለኮታዊ ኃይል ተነሣ፡፡ እርሱ ራሱ ‹ነፍሴን በፈቃዴ አሳልፌ ልሰጥ፣ ሁለተኛም መልሼ ላዋሕዳት ሥልጣን አለኝ፤ ይህን ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ› እንዳለ፡፡ በነጋም ጊዜ ለማርያም መግደላዊት ታያት፤ እጅ ልትነሣው በወደደች ጊዜም ‹ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ› አላት፡፡ ስለዚህም ሥጋዊ አካሉ ከዚያን አስቀድሞ በአብ ቀኝ እንዳልተቀመጠ ዐወቅን፤›› (አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፣ መጽሐፈ ምሥጢር ዘትንሣኤ ፺፭)፡፡

‹‹ዮሴፍ ኒቆዲሞስ ከጲላጦስ ተካሰው፣ ከመስቀል አውርደው፣ በድርብ በፍታ ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት፡፡ በሦስተኛው ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት በዝግ ቤት ገብቶ በጽርሐ ጽዮን ታያቸው፤›› (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ፩፥፳፱-፴፩)፡፡

‹‹ሰውን ስለ መውደድህ ይህን ዅሉ አደረግህ፤ ከሙታን ተለይተህ መቃብር ክፈቱልኝ፤ መግነዝ ፍቱልኝ ሳትል ተነሣህ፡፡ ከእግረ መስቀል ሙታንን አስነሣህ፡፡ ነፍሳትን ከሲኦል ማርከህ ለአባትህ አቀረብህ፤›› (ቅዳሴ ያዕቆብ ዘስሩግ፣ ፩፥፳፬)፡፡

‹‹በታወቀች በተረዳች በሦስተኛይቱ ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት በዝግ ቤት ገባ፡፡ የተወጋውን ጎኑን፣ የተቸነከረውን እጁን፣ እግሩን አሳያቸው፡፡ በዓለመ ነፍስ የኾነውን እያስተማራቸው ዐርባ ቀን ኖረ፤›› (ቅዳሴ ዘሠለስቱ ምዕት ፬፥፳፭-፳፯)፡፡

‹‹ሰማያት (ሰማያውያን መላእክት) የደስታ በዓልን ያደርጋሉ፤ ደመናት (ቅዱሳን) የደስታን በዓል ያደርጋሉ፡፡ ምድር (ምድራውያን ሰዎች) በክርስቶስ ደም ታጥባ (ታጥበው) የፋሲካን በዓል ታደርጋለች (ያደርጋሉ)፤ ያከብራሉ (ታከብራለች)፡፡ ዛሬ በሰማያት (በሰማያውያን መላእክት) ዘንድ ታላቅ ደስታ ኾነ፡፡ ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ የፋሲካን የነጻነት በዓል ታደርጋለች፡፡ የትንሣኤያችን በኩር ክርስቶስ ከሙታን ሰዎች ዅሉ ተለይቶ ቀድሞ ተነሣ፤›› (ቅዱስ ያሬድ፣ ድጓ ዘፋሲካ)፡፡

‹‹ሞትን በሥጋ በቀመሰ ጊዜ መለኮቱ በመቃብር ውስጥ ያለነፍሱ ከበድኑ ጋር ነበር፡፡ በሲኦልም ውስጥ ያለ ሥጋው ከነፍሱ ጋር ህልው ነበር፡፡ በአባቱም ቀኝ ያለ ነፍስና ያለ ሥጋ ህልው ነበር፡፡ በትንሣኤውም ጊዜ ነፍሱን ከሥጋው ጋር አዋሕዶ አስቀድሞ ለአይሁድ ‹ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፤ በሦስተኛው ቀን እሠራዋለሁ› ብሎ እንደ ተናገረ፡፡ አይሁድም ‹ይህ ቤተ መቅደስ ተሠርቶ ያለቀው በዐርባ ሰባት ዓመት ነው፤ አንተ ግን በሦስት ቀን እሠራዋለሁ ትላለህ› አሉት፤ ይህንንም የተናገረው ስለ ራሱ ሰውነት ነው፡፡ በተነሣም ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ስለዚህ ነገር እንደ ተናገረ አሰቡ፡፡ በመጽሐፍና ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም የተናገራቸውን ቃል አመኑ፤ ሁለተኛም ‹ነፍሴን በፈቃዴ አሳልፌ እሰጣለሁ፤ ልለያት መልሼም አዋሕጄ ላስነሣት ሥልጣን አለኝ፤ ይህንንም ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ› ብሏል፡፡ ዳዊትም ‹አቤቱ የመቅደስህን ታቦት ይዘህ ተነሥ› ይላል፡፡ ነቢዩ ‹አቤቱ አንተ የመቅደስህን ታቦት ይዘህ ተነሥ› ለምን አለ? የመቅደሱ ታቦት ከኾነችው ከዳዊት ዘር ከነሣው ሥጋ ጋር በመለኮታዊ ኃይሉ ከሞት እንቅልፍ ከመንቃት በስተቀር የእግዚአብሔር መነሣት ምንድን ነው?›› (አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ መጽ. ምሥጢር ዘትንሣኤ ፸፯-፸፱)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ትንሣኤ ክርስቶስ በሊቃውንት – የመጀመርያ ክፍል

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የድኅነታችን ብሥራት በመኾኑ ለአምሳ ቀናት ያህል በቤተ ክርስቲያን በቅዳሴው፣ በማኅሌቱ፣ በወንጌሉ ወዘተ. ይዘከራል፡፡ በዚህ ሰሙን ‹‹ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን …›› እየተባለ ሞት መደምሰሱ፣ ነጻነት መመለሱ ያታወጃል፡፡ በየጊዜያቱና በየዘመናቱ የተነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ ከዚህ ቀጥሎ የተገለጠውን ትምህርትና ምስክርነት ሰጥተዋል፤

‹‹ከሙታን ተለይቶ ተነሥቶ ሲኦልን ረግጦ፣ በሞቱ ሞትን አጠፋው፤ በሦስተኛው ቀንም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ‹አባት ሆይ፤ አመሰግንሃለሁ› ብሎ ሥግው ቃል አመሰገነ፤›› (እልመስጦአግያ ዘሐዋርያት ፭፥፩)፡፡

‹‹እንደ ሞተ እንዲሁ ተነሣ፤ ሙታንንም አስነሣ፡፡ እንደ ተነሣም እንዲሁ ሕያው ነው፤ አዳኝ ነው፡፡ በዚህ ዓለም እንደ ዘበቱበት፣ እንደ ሰደቡት፣ እንዲሁ በሰማይ ያሉ ዅሉ ያከብሩታል፤ ያመሰግኑታል፡፡ ለሥጋ በሚስማማ ሕማም ተሰቀለ፤ በእግዚአብሔርነቱ ኃይል ተነሣ፤ ይኸውም መለኮቱ ነው፡፡ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ማረከ፤›› (ቅዱስ ሄሬኔዎስ፣ ሃይ. አበ. ፯፥፳፰-፴፩)፡፡

‹‹እንዲህ ሰው ኾኖም ሰውን ፈጽሞ ያድን ዘንድ ታመመ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤›› (ሠለስቱ ምዕት፣ ሃይ. አበ. ፲፱፥፳፬)፡፡

‹‹ሞትን ያጠፋው፣ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ የሞት ሥልጣን የነበረው ዲያብሎስን የሻረው እርሱ ነው፡፡ ሰው የኾነ፣ በሰው ባሕርይ የተገለጠ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔር ያደረበት ዕሩቅ ብእሲ አይደለም፤ ሰው የኾነ አምላክ ነው እንጂ፡፡ ፈጽሞ ለዘለዓለሙ በእውነት ምስጋና ይገባዋል፤›› (ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ሃይ. አበ. ፳፭፥፵)፡፡

‹‹ሥጋው በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡ በዚያም ሰዓት የጌታችን ሥጋው በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሳለ መቃብራት ተከፈቱ፤ ገሃነምን የሚጠብቁ አጋንንትም ባዩት ጊዜ ሸሹ፡፡ የመዳብ ደጆች ተሰበሩ (ሊቃነ አጋንንት፣ ሠራዊተ አጋንንት ድል ተነሡ)፡፡ የብረት ቁልፎቿም ተቀጠቀጡ (ፍዳ፣ መርገም ጠፋ)፡፡ ቅድስት ነፍሱ በሲኦል ተግዘው የነበሩ የጻድቃን ነፍሳትን ፈታች፤›› (ዝኒ ከማሁ ፳፮፥፳-፳፩)፡፡

‹‹ሥጋ ከመለኮቱ ሳይለይ በመቃብር አደረ፤ ነፍሱም ከመለኮት ሳትለይ በገሃነም ተግዘው ለነበሩ ነፍሳት ደኅነትን ታበስር ዘንድ፣ ነጻም ታደርጋቸው ዘንድ ወደ ሲኦል ወረደች፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንደ ተናገረው ቃል ዐፅም፣ ሥጋ ወደ መኾን ፈጽሞ እንደ ተለወጠ የሚናገሩ የመናፍቃንን የአእምሮአቸውን ጉድለት ፈጽመን በዚህ ዐወቅን፡፡ ይህስ እውነት ከኾነ ሥጋ በመቃብር ባልተቀበረም ነበር፡፡ በሲኦል ላሉ ነፍሳት ነጻነትን ያበስር ዘንድ ወደ ሲኦል በወረደ ነበር እንጂ፡፡ ነገር ግን ከነፍስና ከሥጋ ጋር የተዋሐደ ቃል ነው፡፡ እርሱ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ለነፍሳት ነጻነትን ሰበከ፡፡ ሥጋ ግን በበፍታ እየገነዙት በጎልጎታ በዮሴፍ በኒቆዲሞስ ዘንድ ነበረ፤ ቅዱስ ወንጌል እንደ ተናገረ፡፡ አባቶቻችን ሥጋ በባሕርዩ ቃል አይደለም፤ ቃል የነሣውሥጋ ነው እንጂ ብለው አስተማሩን፤ ይህንን ሥጋም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ቶማስ ዳሠሠው፤ በሥጋው ሲቸነከር ቃል ታግሦ የተቀበለውን የችንካሩን እትራትም (ምልክት) በእርሱ አየ፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፥፴፩-፴፮)፡፡

‹‹አሁን እግዚአብሔር ሞተ ሲል ብትሰማ አትፍራ፤ ‹የማይሞተውን ሞተ ሊሉ አይገባም› ከሚሉ፤ ዕውቀት ከሌላቸው፤ ሕማሙን፣ ሞቱን ከሚክዱ መናፍቃን የተነሣ አትደንግጥ፡፡ እኛ ግን በመለኮቱ ሞት እንደ ሌለበት፤ በሥጋ ቢሞትም በመለኮቱ ሥልጣን እንደ ተነሣ እናውቃለን፡፡ ሞት የሌለበት ባይኾንስ ኖሮ በሥጋ በሞተ ጊዜ ሥጋውን ባላስነሣም ነበር፤ ሥጋው እስከ ዓለም ፍጻሜ በመቃብር በኖረ ነበር እንጂ፤›› (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ሃይ. አበ. ፴፬፥፲፯-፲፰)፡፡

‹‹ከመስቀሉ ወደ ሲኦል በመውረዱ አዳነን፤ በአባታቸው በአዳም በደል በሲኦል ተግዘው የነበሩ ጻድቃንን ፈታ፤ ከሙታን ተለይቶ አስቀድሞ በተነሣ በእውነተኛ ትንሣኤውም አስነሣን፡፡ የንስሐንም በር ከፈተልን፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፣ ሃይ. አበ. ፴፮፥፴)፡፡

‹‹በአባታችን በአዳም በደል የተዘጋ የገነት ደጅን የከፈተልን፤ ዕፀ ሕይወትን የሚጠብቅ ኪሩብንም ያስወገደው፤ የእሳት ጦርን ከእጁ ያራቀ፤ ወደ ዕፀ ሕይወት ያደረሰን እርሱ ነው፡፡ ፍሬውንም (ሥጋውን፣ ደሙን) ተቀበልን፡፡ አባታችን አዳም ሊደርስበት ወዳልተቻለው፤ በራሱ ስሕተት ተከልክሎበት ወደ ነበረው መዓርግ ደረስን፡፡ ክፉውንና በጎውን ከሚያስታውቅ፤ ወደ ጥፋት ከሚወስድ፤ በአዳምና በልጆቹም ላይ ኃጢአት ከመጣበት ከዕፀ በለስ ፊታችንን መለስን፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፮፥፴፰-፴፱)፡፡

‹‹የሕይወታችን መገኛ የሚኾን የክርስቶስ ሞት የእኛን ሞት ወደ ትንሣኤ እንደ ለወጠ እናምናለን፤ ክርስቶስም ሞትን አጥፍቶ የማታልፍ ትንሣኤን ገለጠ፤ እንደ ተጻፈ፡፡ ከሰው ወገን ማንም ማን ሞትን ያጠፋ ዘንድ፣ ትንሣኤንም ይገልጣት ዘንድ አይችልም፤ ዳዊት ‹በሕያውነት የሚኖር፤ ሞትንም የማያያት ሰው ማነው? ነፍሱን ከሲኦል፤ ሥጋውን ከመቃብር የሚያድን ማን ነው?› ብሎ እንደ ተናገረ፤›› (ቅዱስ አቡሊዲስ፣ ሃይ. አበ. ፵፪፥፮-፯)፡፡

‹‹በመለኮትህ ሕማም፣ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ በሥጋ መከራ የተቀበልህ አንተ ነህ፡፡ ከአብ ጋር አንድ እንደ መኾንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ ከእኛም ጋር አንድ እንደ መኾንህ በፈቃድህ የሞትህ አንተ ነህ፡፡ በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፡፡ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርህ አንተ ነህ፡፡ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፤ ከሙታን ጋር የተቆጠርህ አንተ ነህ፤ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፡፡ ሦስት መዓልት፤ ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፤ በዘመኑ ዅሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፤ በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምክ አካላዊ እግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፤›› (ቅዱስ ኤራቅሊስ፣ ሃይ. አበ. ፵፰፥፲፪-፲፫)፡፡

‹‹እኛስ ኃጢአታችንን ለማስተሥረይ በሥጋ እንደ ታመመ፤ እንደ ሞተ፤ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ፤ ከሙታንም ተለይቶ በእውነት እንደ ተነሣ፤ ከተነሣም በኋላ በእውነት ወደ ሰማይም እንደ ዐረገ እናምናለን፡፡ በኋላም በሚመጣው ዓለም እርሱ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ይመጣል፡፡ የሰውን ወገኖች ዅሉ በሞቱበት፤ በተቀበሩበት ሥጋ ከሞት ያስነሣቸዋል፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ያለ መለወጥ ዅልጊዜ ይኖራል፡፡ እርሱ በዚህ በሞተበት፤ በተገነዘበት ሥጋ ከሙታን አስቀድሞ እንደ ተነሣ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም፣ ሃይ. አበ. ፶፪፥፲፩-፲፪)፡፡

‹‹የሥጋን ሕማም ለመለኮት ገንዘብ በአደረገ ጊዜ የእግዚአብሔር አካል በባሕርዩ በግድ ሕማምን አልተቀበለም፤ ሕማም በሚስማማው ባሕርዩ ኃይልን እንጂ፡፡ ሞትም በሥጋ ለእግዚአብሔር ቃል ገንዘብ በኾነ ጊዜ ሞትን አጠፋ፡፡ ከሞትም በኋላ ፈርሶ፣ በስብሶ መቅረትን አጠፋ፤›› (ቅዱስ ቴዎዶጦስ ሃይ. አበ. ፶፫፥፳፯)፡፡

‹‹መለኮት በሥጋ አካል በመቃብር ሳለ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በነፍስ አካል ወደ ሲኦል ወረደ፤ እንደዚህ ባለ ተዋሕዶ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ከትንሣኤ በኋላ አይያዝም፤ አይዳሰስም፡፡ በዝግ ቤት ገብቷልና፡፡ ነገር ግን ምትሐት እንዳይሉት ቶማስ ዳሠሠው፡፡ የተባለውን ከፈጸመ በኋላ ቶማስ አመነበት፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፮፥፴፯-፴፰)፡፡

‹‹ክርስቶስ የሙታን በኵር እንደምን ተባለ? እነሆ በናይን ያለች የደሀይቱን ልጅ አስቀድሞ አስነሣው፤ ዳግመኛም አልዓዛርን በሞተ በአራተኛው ቀን አስነሣው፡፡ ኤልያስም አንድ ምውት አስነሣ፡፡ ደቀ መዝሙሩ ኤልሣዕም ሁለት ሙታንን አስነሣ፤ አንዱን ሳይቀበር፣ ሁለተኛውን ከተቀበረ በኋላ ሥጋውን አስነሣ፡፡ እነዚያ ሙታን ቢነሡ ኋላ እንደ ሞቱ፤ እነርሱ ኋላ አንድ ኾነው የሚነሡበትን ትንሣኤ ዛሬ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሙታን ትንሣኤያቸው በኵር ነው፡፡ ‹እንግዲህ ወዲህም ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ የተነሣ እርሱ ነው፤ ዳግመኛም ሞት አያገኘውም› ተብሎ እንደ ተጻፈ፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፯፥፫-፮)፡፡

‹‹ቃል ሥጋውን በመቃብር አልተወም፤ በሲኦልም ካለች ከነፍሱ አልተለየም፡፡ ከነፍስ ከሥጋ በአንድነት ነበረ እንጂ፡፡ ለዘለዓለም ክብር ምስጋና ይግባው፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ሃይ. አበ. ፷፥፳፱)፡፡

‹‹ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ ‹በትንሣኤ ከእናንተ ጋር እስከምመጣበት ቀን ድረስ ከዚያ ወይን ጭማቂ አልጠጣም፤ በሐዲስ ግብር በምነሣበት ጊዜ የምታዩኝ እናንት ምስክሮቼ ናችሁ› ያለውን የማቴዎስን ወንጌል በተረጐመበት አንቀጽ እንዲህ አለ፤ ሐዲስ ያለው ይህ ነገር ምንድን ነው? ይህ ነገር ድንቅ ነው! መዋቲ ሥጋ እንዳለኝ ታያላችሁ፤ ነገር ግን ከትንሣኤ በኋላ የማይሞትነው፤ አይለወጥም፤ ሥጋዊ መብልንም መሻት የለበትም፤ ከትንሣኤ በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ቢበላም ቢጠጣም መብልን ሽቶ አይደለም፤ እርሱ ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሣ ያምኑ ዘንድ በላ ጠጣ እንጂ፡፡ ይህ ድንቅ ሥራ ነው! ያለ መለወጥ ሰው የኾነ ቃል የተቸነከረበትን ምልክት (እትራት) አላጠፋምና፡፡ በሚሞቱ ሰዎች እጅ እንዲዳሠሥ አድርጎታልና፡፡ አምላክ የኾነ ሥጋ የሚታይበት ጊዜ ነውና አላስፈራም፡፡ እርሱ በዝግ ደጅ ገባ፤ ግዙፉ ረቂቅ እንደ ኾነ ሥራውን አስረዳ፡፡ ነገር ግን በትንሣኤው ያምኑ ዘንድ የተሰቀለው እርሱ እንደሆነ የተነሣውም ሌላ እንዳይደለ ያውቁ ዘንድ ይህን ሠራ፡፡ ስለዚህም ተነሣ፤ በሥጋውም የችንካሩን ምልክት (እትራት) አላጠፋም፤ ዳግመኛም ከትንሣኤው አስቀድሞ ደቀ መዛሙርቱ ጧት ማታ ከእርሱ ጋር ይበሉ እንደ ነበረ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በላ፤ ስለዚህም በአራቱ መዓዝነ ዓለም ትንሣኤውን አስረዱ፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ‹ያየነው ከእርሱም ጋር የበላን የጠጣንም እርሱ ነው› ብለው አስረዱ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሃይ. አበ. ፷፮፥፯-፲፪)፡፡

ይቆየን

በዓለ ትንሣኤን በትንሣኤ ልቡና እናክብር

በገብረ እግዚአብሔር ኪደ

ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

 ፋሲካ ማለት መሻገር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር ወልድ እኛን ከወደቅንበት አንሥቶና ተሸክሞ ከዚኽ ምድር ወደ ሰማያት ተሻግሯልና (ተነሥቶ ዐርጓልና)፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹እንግዲኽ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችኁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን ሹበላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም፡፡ ሞታችኋልና ሕይወታችኁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሯልና፡፡ ሕይወታችኁ የኾነ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር ትገለጣላችኁ፤›› እንዳለን /ቈላ.፫÷፩-፬/፣ በጥምቀት ውኃ ሞቱን በሚመስል ሞት ስንሞት፣ አሮጌው ሰውነታችን እንደ ግብጻውያን ተቀብሮ ቀርቷል፡፡ አዲሱ ሰውነታችን ግን እስራኤላውያን ባሕሩ ተከፍሎላቸው እንደ ተሻገሩ ተሻግሯል (ተነሥቷል)፡፡

ብልየት ያለበት የቀዳማዊ አዳም ሰውነታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ ተቀብሮ አዲሱ ሰውነታችን ሕይወትን አግኝቶ ተነሥቷል፡፡ መሬታዊው ሰውነታችን ሞቶ ሰማያዊው ሰውነታችንን ለብሰን መንፈሳውያን ኾነን ተነሥተናል፡፡ ወደ ጥንተ ተፈጥሯችን ተመልሰናል፡፡ አኹን ከእኛ የሚጠበቀው ይኽ ተፈጥሯችንን ሳናቆሽሽ መጠበቅ ነው፤ እንደ ተነሣን መዝለቅ፡፡ ይኽን ለማድረግም ተራራ መውጣት፣ ምድርን መቆፈር፣ የእሳት ባሕርን መሻገር አይጠበቅብንም፡፡ ይኽን ጠብቀን እንድንቈይ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ ፈቃዳችንን፡፡ የሚሠራው እርሱ ራሱ ነውና /ዮሐ.፲፭÷፭/፡፡ መጽንዒ (የሚያጸና) መንፈስ ቅዱስን ያደለንም ስለዚኹ ነው፡፡

የምናመልከውን አምላክ መስለን በሕይወት ሳንሻገር የመሻገርን በዓል (ፋሲካን) የምናከብረው ምን ጥቅም እንዲሰጠን ነው? ከጨለማ ሥራ ወደ ብርሃን ሥራ፣ ከፍቅረ ዓለም ወደ ፍቅረ ክርስቶስ ሳንሻገር ፋሲካን የማክበራችን ትርጕሙ ምንድነው? እኛው ሳንነሣ የመነሣት በዓልን ማክበራችን በፍርድ ላይ ፍርድ በበደል ላይ በደል ከመጨመር ውጪ የሚሰጠን ጥቅም ምንድን ነው? የምንነሣውስ መቼ ነው? በዐይናችን ጉድፍ ብትገባ ስንት ደቂቃ እንታገሣታለን? ታድያ በነፍሳችን ላይ የተጫነውን የኃጢአት ግንድ መቼ ነው የምናስወግደው? መቼ ነው ወደ ላይኛው ቤታችን ቀና የምንለው? ብዙዎቻችን በሕይወታችን ሳንሻገር ነው በዓለ ፋሲካን የምናከብረው፡፡ ክርስቲያን ኾኖ በመብልና በመጠጥ ብቻ ፋሲካን ማክበር ኢ ክርስቲያናዊ ተግባር ነው፡፡

አዲሱን ሰውነታችን ለብሰን ከተነሣን በኋላ እንደ ቀድሞ ምልልስ የምንጓዝ ከኾነ ግን ተመልሰን ወድቀናል፤ አዲሱ ሰውነታችንን አውልቀን አሮጌውን ሰውነታችንን በድጋሜ ለብሰነዋል፡፡ በእኛነታችን ውስጥ ፍቅረ ንዋይ፣ ፍቅረ ሲመት፣ ፍትወት፣ ይኽንንም የመሰሉ ዅሉ ካለ አዲሱ ሰውነታችን ከእኛ ጋር የለም፤ ቢኖርም ታሟል፡፡ በኃጢአት የመቃጠል ስሜት፣ ርኵሰትና ክፉ ምኞት ከእኛ ዘንድ ካለ አሮጌ ሰው ኾነናል፤ ትንሣኤ ልቡናን ገንዘብ አላደረግንም፡፡ ስለዚኽ ከልቡና ሞት እንነሣና ፋሲካን እናክብር፡፡ እስከ አኹን በኃጢአት ውስጥ ካለን ወደ ብርሃን ክርስቶስ እንምጣ (እንሻገርና) የመሻገርን በዓል እናክብር፡፡ ከክፉ ሥራ ወደ ጽድቅ ሥራ እንሻገርና የእውነት ፋሲካን እናክብር፡፡ ከኃይል ወደ ኃይል እንሻገርና ፋሲካን እናክብር፡፡ ከሞት ሥራ ወደ ሕይወት ሥራ እንነሣና የመነሣትን በዓል እናክብር፡፡

እግዚአብሔር የሚወዳችሁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ሆይ! እኛን የሚያሰነካክል ደግሞም የሚጥለን ፈርዖን (ዲያብሎስ) ተሰነካክሎ ወድቋልና ከግብጽ ሕይወታችን እንውጣ፡፡ ተነሥተንም እንሻገር፡፡ ተሻግረንም ሰማያዊውን ፋሲካ እናክብር፡፡ በግብጽ የነበሩት እስራኤላውያን የበጉን ደም በጉበኑና በኹለቱም መቃን ሲቀቡት አጥፊው ከቤታቸው እንዳለፈ አንብበናል /ዘፀ.፲፪÷፲፫/፡፡ ይኸውም በጉ በራሱ ያንን የማድረግ ኃይል ስለ ነበረው አይደለም፤ ደሙ የክርስቶስ ደም አምሳል ስለ ነበር ነው እንጂ፡፡ እኛ ግን የአማናዊውን በግ /ዮሐ.፩፡፳፱/ ደም በልቡናችን፣ በአስተሳሰባችንና በሰውነታችን ዅሉ እንቀባና (እንቀበልና) እንሻገር፡፡

ይኽን ስናደረግ በእባቡና በጊንጡ ይኸውም በዲያብሎስና በሠራዊቱ ላይ ሥልጣን ይኖረናል /ሉቃ.፲÷፲፱/፡፡ የምንበላው በግ ራሱ ሕይወት ስለ ኾነ ሞት በእኛ ላይ አይነግሥም /ዮሐ.፲፬÷፮/፡፡ በዚኽ ዓለም ሳለን ከዚኽ ደስታ ተካፋዮች ከኾንን (የመዠመሪያውን ትንሣኤ ልቡና በንስሐ ከተነሣን) በሚመጣው ዓለምም በክብር ላይ ክብር፣ በሹመት ላይ ሹመት እንቀበላለን (ኹለተኛውን ትንሣኤ እንነሣለን) /ሉቃ.፳፪÷፲፭-፲፮/፡፡ ብንወድቅ እንኳን መልሰን በመነሣት ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር፣ የክብር ክብር፣ ጌትነት የባሕርዩ በሚኾን፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰጭነት በመንግሥተ ሰማያት ጸጋ ክብር እናገኛለንና የጭንቅ ቀን ሳይመጣ በዓለ ትንሣኤን እናክብር፡፡ ለዚህም ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የመከረንን የሚከተለውን ኃይለ ቃል በተግባር ላይ ብናውለው እንጠቀማለን፤

‹‹በምነግራችኁ ነገር እያበሳጨኋችሁና እያሳመምችሁ እንደ ኾነ ይገባኛል? ግን ምን ላድርግ? እኔም እናንተም በምግባር በሃይማኖት የታነጽን እንኾን ዘንድ ብቻ ሳይኾን ከዚያም እናመልጥ ዘንድ ነው፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ከመጨማለቃችን የተነሣ እንዴት አድርጌ ላሳምማችኁ እችላለኁ? ብትሰሙኝና ብትለወጡስ እኔም ማረፍ እንኳን በቻልኩ ነበር፡፡ ስለዚኽ እስካልተለወጣችሁ ድረስ እናንተን መገሠንና መምከሬን አላቆምም፡፡ ስለ ገነመ እሳት ተደጋግሞ ሲነገር የሚበሳጭ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እኔ ግን ከዚኽ የበለጠ ያማረ የተወደደ አስደሳች ትምህርት የለም እለዋለኁ፡፡ እንዴት ይኽ አስደሳች ትምህርት ነው ትለናለህ? ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡ እኔም ወደዚያ መጣል ከደስታ ዅሉ የራቀ ነውናብዬ እመልስላችኋለሁ፡፡ ስለዚኽ ነፍሳችን ከመታሠሯ በፊት የነቃን የተጋን እንኾን ዘንድ ይኽን ደጋግሜ እነግራችኋለሁ፡፡ ስሐ ይግባ እንጂ ማንም እንደ ተወቀሰ አያስብ፤ በንግግሬም የሚቆጣ አይኑር፡፡ ዅላችንም ወደ ጠባቢቱ መንገድ እንግባ፡፡ እስከ መቼስ በስንፍና አልጋ እንተኛለን? ዛሬ ነገ ማለት አይበቃንም ወይ? ሰማያዊ ቪላችንን ቀና ብለን ብንመለከት እኮ በዚኽ ምድር ይኽንን ለመሥራት ባልደከምን ነበር፡፡ እስቲ ንገሩኝ! ሩጫችንን ስንጨርስ ከሬሳ ሳጥንና ከመግነዝ ጨርቅ ውጪ ይዘነው የምንሔድ ነገር ምን አለ? ታድያ ለምን እንከራከራለን?›› (ሰማዕትነት አያምልጣችሁ እና ሌሎች፣ ገጽ ፻፶፮ – ፻፶፯)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሰሙነ ፋሲካ (ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ)

በሊቀ ትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኘ

ሚያዝያ ቀን ፳፻፱ .

ከትንሣኤ እሑድ ቀጥለው ያሉት ዕለታት ‹ሰሙነ ፋሲካ› ወይም ‹ትንሣኤ› እየተባሉ የሚጠሩ ሲኾን፣ የየራሳቸው ምሥጢራዊ ስያሜም አላቸው፡፡ ስያሜአቸውንም በአጭሩ እንደሚከተለው እንመለከታለን፤

ሰኞ

የትንሣኤው ማግሥት ሰኞ ጌታችን በትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ሰትኾን፣ ‹ፀአተ ሲኦል› ወይም ‹ማዕዶት› ትባላለች (ዮሐ. ፲፱፥፲፰፤ ሮሜ. ፭፥፲-፲፯)፡፡

በዳግም ትንሣኤው ማግሥት ያለችው ሰኞ ደግሞ ገበሬው፡- ወንዶቹ እርሻ ቁፋሮውን፣ ንግዱን፣ ተግባረ እዱን ዅሉ፤ ሴቶቹ፡- ወፍጮውን፣ ፈትሉን፣ ስፌቱን የሚጀምሩባት ዕለት ስለ ኾነች ‹እጅ ማሟሻ ሰኞ› ትባላለች፡፡

ማክሰኞ 

የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ሐዋርያው ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት ‹‹እኔ ሳላይ አላምንም›› ብሎ ነበር፡፡ በሳምንቱ ቶማስ በተገኘበት ጌታችን በድጋሜ ለሐዋርያት ተገለጸ፡፡ ስለዚህም ይህቺ ዕለት በሐዋርያው ቶማስ ስም ተሰይማለች (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡ 

ረቡዕ 

ጌታችን ከሞተና ከተቀበረ ከአራት ቀን በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላስነሣው ለአልዓዛር መታሰቢያ ትኾን ዘንድ፤ በክርስቶስ ሥልጣን የአልዓዛርን ከሞት መነሣት አይተው ብዙ ሕዝብ በጌታችን ስለ አመኑ ዕለቲቱ (ረቡዕ) ‹አልዓዛር› ተብላ ትታሰባለች (ዮሐ. ፲፩፥፴፰-፵፮)፡፡ 

ኀሙስ 

ይህቺ ዕለት ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ (አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም) ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ተብሎ ቃል የተገባለት የአዳም ተስፋው ተፈጽሞ ከነልጅ ልጆቹ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ኾና ‹የአዳም ኀሙስ› ወይም ‹አዳም› ተብላ ትከበራለች (ሉቃ. ፳፬፥፳፭-፵፱)፡፡

ዐርብ

ከሆሣዕና ቅዳሜ በፊት ያለችው ዐርብ ደግሞ የጌታችን ዐርባው ጾም የሚፈጸምባት የጾመ ድጓው ቁመትም የሚያበቃባት ዕለት በመኾኗ በቤተ ክርስቲያን ‹ተጽዒኖ› ትባላለች፡፡ የከባድ ሥራ ማቆሚያ (ማብቂያ) ዕለት በመኾኗም በሕዝቡ ዘንድ ‹የወፍጮ መድፊያ፣ የቀንበር መስቀያ› ትባላለች፡፡

ዳግኛም በመጀመርያ የሰው ልጆች አባትና እናት የኾኑት አዳምና ሔዋን ስለተፈጠሩባት፤ በኋላም በሐዲስ ኪዳን ጌታችን ለቤዛ ዓለም ስለ ተሰቀለባትና የማዳን ሥራውን ስለ ፈጸመባት ‹ዕለተ ስቅለት፣ አማናዊቷ ዐርብ› ትባላለች፡፡

የሰሙነ ፋሲካዋ ማለትም የትንሣኤ እሑድ ስድስተኛዋ ዐርብ ደግሞ በክርስቶስ ደም ለተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቤተ ክርስቲያን› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፮፥፳፮-፳፱፤ ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት

በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በስተቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበያይባት ‹የቁራ ገበያ፣ የገበያ ጥፊያ› ስትባል፣ በቤተ ክርስቲያን ግን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጉልበታቸው ላገለገሉት፤ በስቅለቱ ዋይ ዋይ እያሉ እስከ ቀራንዮ ድረስ ለተከተሉት፤ በትንሣኤው ዕለት በሌሊት ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው ለገሰገሱት፤ በትንሣኤውም ጌታችን ከዅሉ ቀድሞ ለተገለጸላቸው ቅዱሳት አንስት መታሰቢያ ኾና ‹ቅዱሳት አንስት› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፭፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፫፥፳፯-፴፫፤ ፳፬፥፩-፲)፡፡

የዋናው ትንሣኤ ሳምንት እሑድ

በዚህች ሰንበት ከላይ እንደ ተጠቆመው ጌታችን በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ «ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!» ብሎ ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡

በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት በደስታ ሲነግሩት «በኋላ እናንተ ‹አየን› ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግንሰምቼአለሁ› ብዬ ልመሰክር፤ ላስተምር? አይኾንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም» በማለቱ የሰውን ዅሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው ወዳጆቹን የልብ ሐሳብ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ «ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!» በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡

ቶማስንም «ያመንህ እንጂ ተጠራጣሪ አትኹን፤ እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ፤» ብሎ አሳየው፡፡ እርሱም ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ «ጌታዬ፣ አምላኬ ብሎ መስክሮ» አመነ፡፡ ስለዚህም ማለትም የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመኾኑ የትንሣኤው ሳምንት እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብሎ ይጠራል፤ ይከበራል (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

በአጠቃላይ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሰሙነ ፋሲካ የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዅሉ ልክ እንደ መጀመሪያው የትንሣኤ ሥርዓት ኾኖ ይከናወናል፡፡ ብርሃነ ትንሣኤውን የገለጸልን አምላካችን ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የትንሣኤ በዓል ትርጕሙና አከባበሩ

በሊቀ ትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኘ

ሚያዝያ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሰን!

«ትንሣኤ» የሚለው ቃል የግእዝ ቃል መገኛው ‹ተንሥአ = ተነሣ› የሚለው ግስ ሲኾን፣ ትርጕሙም መነሣት፣ አነሣሥ፣ አዲስ ሕይወትን ማግኘት ማለት ነው፡፡ ‹ትንሣኤ› በየመልኩ፣ በየዓይነቱ ሲተረጐም አምስት ክፍል አለው፤

የመጀመርያው ትንሣኤ ሕሊና ነው፤ ይህም ማለት ተዘክሮተ እግዚአብሔር (እግዚአብሔርን ማሰብ) ነው፡፡

ሁለተኛውም ትንሣኤ ልቡና ነው፤ የዚህም ምሥጢሩ ቃለ እግዘብሔርን መስማትና በንስሐ እየታደሱ በሕይወት መኖር ነው፡፡

ሦስተኛው ትንሣኤ ለጊዜው (በተአምራት) የሙታን በሥጋ መነሣት ነው፡፡ ነገር ግን በድጋሜ ሌላ ሞት ይከተለዋል፡፡

አራተኛው ትንሣኤ ክርስቶስ በሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ መነሣቱን ያመላክታል፡፡ የርእሰ ትምህርታችን መነሻም ይህ ነው፡፡

አምስተኛውና የመጨረሻው የትንሣኤ ደረጃ የባሕርይ አምላክ የጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ መሠረት ያደረገ ትንሣኤ ዘጉባኤ ሲኾን፣ ይህም ከዓለም ኅልፈት በኋላ ሰው ዅሉ እንደየሥራው ለክብርና ለውርደት፣ ለጽድቅና ለኵነኔ በአንድነት የሚነሣው የዘለዓለም ትንሣኤ ነው፡፡

ወደ ርእሳችን ስንመለስ የትንሣኤ በዓል በምሥጢሩም፣ በይዘቱም ከኦሪቱ በዓለ ፋሲካ ጋር ስለሚመሳሰል ‹ፋሲካ› ተብሎ ይጠራል፡፡ ‹ፋሲካ› ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹ፌሳሕ›፤ በጽርዕ (በግሪክ) ‹ስኻ› ይባላል፡፡ ይህም ወደ እኛው ግእዝና አማርኛ ቋንቋችን ሲመለስ ፍሥሕ (ደስታ)፣ ዕድወት፣ ማዕዶት (መሻገር፣ መሸጋገር)፣ በዓለ ናእት (የቂጣ በዓል፣ እየተቸኮለ የሚበላ መሥዋዕት) ማለት ነው፡፡ የዚህም ታሪካዊ መነሻው በዘመነ ኦሪት ይከበር የነበረው በዓለ ፋሲካ ሲኾን፣ ይህም እስራኤል ዘሥጋ ከግብጽ የባርነት ቀንበር ወደ ነጻነት የተላለፉበት፤ ከከባድ ኀዘን ወደ ፍጹም ደስታ የተሸጋገሩበት በዓል ነው፡፡ በዚህ ኦሪታዊ (ምሳሌ) በዓል አሁን አማናዊው በዓል በዓለ ትንሣኤ ተተክቶበታል፡፡

ፋሲካ (በዓለ ትንሣኤ) በዘመነ ሐዲስ እስራኤል ዘነፍስ የኾንን ምእመናን የክርስቶስን ትንሣኤ የምናከብርበት ዕለት ነው፡፡ ይህ በዓል ከኃጢአት ወደ ጽድቅ፤ ከውርደት ወደ ክብር፤ ከጠላት ሰይጣን አገዛዝ ወደ ዘለዓለማዊ ነጻነት፤ ከአደፈ፣ ከጐሰቆለ አሮጌ ሕይወት ወደ አዲስ ሕይወት የተሻገርንት ከበዓላት ዅሉ የበለጠ የነጻነት በዓል ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና መንፈሳዊ ስሜት በዓሉን እናከብረዋለን፡፡

መድኃኒታችን ሞትን በሞቱ ድል ነስቶ፣ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ፣ በሥልጣኑ የተነሣው መጋቢት ፳፱ ቀን በ፴፬ ዓ.ም እንደ ኾነ ታሪከ ቤተ ከርስቲያን ያስረዳል፡፡ የትንሣኤ በዓል መከበር የጀመረው በቅዱሳን ሐዋርያትና በሰብዐ አርድእት፣ ኋላም በየጊዜው በተነሡ ሊቃውንትና ምእመናን ነው፡፡ ድምቀቱና የአከባበር ሥርዓቱ ይበዛ፣ ይቀነስ እንደ ኾነ እንጂ በዓሉ መከበሩ ተቋርጦ አያውቅም፡፡

በቅብብሎሽ ከዚህ በደረሰው ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰሙነ ሕማማት ግብረ ሕማማቱን ስታነብ ሰንብታ ለትንሣኤ እሑድ አጥቢያ ማታ በ፪ ሰዓት «ለጸሎት ተሰብሰቡ» ስትል የደወል ድምፅ ታሰማለች፡፡ ካህናቱም በቤተ ክርስቲያን ተሰብስበው ሥርዓቱን በጸሎት ይጀምራሉ፡፡ ሕዝቡም በቤተ ክርስቲያን ይሰባሰባል፡፡ ካህናቱ መዝሙረ ዳዊት፣ ነቢያት፣ ሰሎሞንና ውዳሴ ማርያም ከተደረሰ በኋላ «ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ» የሚለውን ግጥማዊ የደስታ መዝሙር ይዘምራሉ፡፡

ምንባቡ፣ ጸሎቱና ሌላውም ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ ጸሎተ አኰቴት ተደርሶ ዲያቆኑ ነጭ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ፣ አክሊል ደፍቶ፣ መስቀል ይዞ፣ በጌታችን መቃብር በራስጌና በግርጌ በታዩት መላእክት ምሳሌ እንደ እርሱው ነጭ ልብሰ ተክህኖ በለበሱ፣ ድባብ ጃንጥላ በያዙ፣ መብራት በሚያበሩ ሁለት ዲያቆናት ታጅቦ በቅድስት ቆሞ፡- «ወተንሥአ እግዚአብሔር ከመ ዘንቃህ እምንዋም፣ ወከመ ኀያል ወኅዳገ ወይን፣ ወቀተለ ፀሮ በድኅሬሁ፤ እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፤ የወይን ስካር እንደ ተወው ኃያል ሰውም ጠላቱን በኋላው ገደለ፤» የሚለውን የዳዊት መዝሙር በረጅም ያሬዳዊ ዜማ ይሰብካል (መዝ. ፸፯፥፷፭)፡፡

ካህናቱም ከበሮ እየመቱና በእርጋታ እያጨበጨቡ ተቀብለው ይዘምራሉ፡፡ ሕዝቡም በጭብጨባና በዕልልታ የደስታ ዝማሬው ተሳታፊ ይኾናል፡፡ ይህ ምስባክ በዲያቆኑና በመላው ካህናት ሁለት ሁለት ጊዜ፤ በዲያቆኑና በመላው ካህናት አንድ ጊዜ (በጋራ) ይዘመራል፡፡ ይህም በድምሩ አምስት መኾኑ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም በጌታችን ሞትና ትንሣኤ ዓለም ለመዳኑ ምሳሌያዊ ማስረጃ ነው፡፡ በመቀጠል ካህኑ ትንሣኤውን የሚያበሥር ትምህርት ከማቴዎስ፣ ከማርቆስና ከሉቃስ ወንጌል አውጥቶ ያነባል፡፡ የዮሐንስ ወንጌል በቅዳሴ ጊዜ ይነበባል (ዮሐ. ፳፥፩-፱)፡፡

በማስከተል ከሊቃውንቱ መካከል ሥራው የሚመለከተው ወይም የተመደበው ባለሙያ (መዘምር) መስቀል ይዞ «ትንሣኤከ ለእለ አመነ» የሚለውን እስመ ለዓለም ከቃኘ በኋላ ለበዓሉ ተስማሚ የኾነው አርያም ተመርቶ በመቋሚያ ይዘመማል፡፡ ከዚያም «ዮም ፍሥሐ ኮነ በሰንበተ ክርስቲያን፣ እስመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና በሰንበተ ክርስቲያን ዛሬ ደስታ ኾነ …፤» የሚለው አንገርጋሪ በመሪና በተመሪ ይመለጠናል፤ በግራ በቀኝ እየተነሣ ይዘመማል፤ ይጸፋል፡፡

በዚህ ጊዜ «በጨለማ የነበራችሁ ሕዝቦች የትንሣኤውን ብርሃን እዩ፤ ብርሃኑንም ወስዳችሁ የብርሃኑ ተካፋይ ኹኑ፤» እያለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጀችውን ጧፍ እያበራች ታድላቸዋለች፡፡ ወዲያውኑም ‹‹ትንሣኤከ ለእለ አመነ ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ = ለአመነው ለእኛ ብርሃንህን ላክልን፤›› የሚለውን እስመ ለዓለም እየዘመሩ፣ መብራት እያበሩ ካህናቱና ሕዝቡ ዑደት ያደርጋሉ (ቤተ ክርስቲያኑን ይዞራሉ)፡፡

መዘምራኑና ካህናቱ ከዑደት ሲመለሱ «ይእቲ ማርያም» የተባለው የኪዳን ሰላም ይጸፋና ኪዳን ተደርሶ ሲያበቃ እንደ ቦታው ደረጃ ፓትርያርክ ወይም ሊቀ ጳጳስ ወይም ቆሞስ ወይም ቄስ ዘለግ ባለ ድምፅ በንባብ «ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ» ሲሉ ካህናቱና መዘምራኑ ‹‹በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን = በታላቅ ኃይልና ሥልጣን» ብለው ይቀበላሉ፡፡ አሁንም ካህኑ «አሰሮ ለሰይጣን = ሰይጣንን አሰረው» ባለ ጊዜ መላው ካህናት «አግዐዞ ለአዳም = አዳምን አርነት ነጻ አወጣው» ይላሉ፡፡

በመቀጠል «ሰላም = ሰላም፣ አንድነት፣ ፍቅር» ሲሉ ዅሉም «እምይእዜሰ = ከዛሬ ጀምሮ» ብለው ይቀበላሉ፡፡ ካህኑም «ኮነ ፍሥሐ ወሰላም = ሰላምና ደስታ» ብለው ሦስት ጊዜ አውጀው «ነዋ መስቀለ ሰላም» እያሉ መስቀል ሲያሳልሙ ካህናቱና ሕዝቡም «ዘተሰቅለ ቦቱ መድኃኔ ዓለም» እያሉ ይሳለማሉ፡፡ ካህኑም «እግዚአብሔር ይፍታ» ይላሉ፡፡ ግብረ ሕማማት ሲነበብበት ከሰነበተው ጠበልም ይረጫል፡፡ የተረፈውንም ጠበል ሕዝቡ ለበረከት ወደየቤቱ ይወስደዋል፡፡

ከዚያም ልኡካኑ ለቅዳሴ እየተዘጋጁ መዘምራኑ ምስባክ መወድሱን ካዜሙ በኋላ በመቋሚያ ይዘሙታል፡፡ አያይዞም ይትፌሣሕ› የተባለውን መዝሙር ቃኝተው ከዘመሙ በኋላ «… ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤ ተኀፂባ በደመ ክርስቶስ = … ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካውን ታደርጋለች፤» እያሉ ይጸነጽላሉ፡፡ አያይዘውም የመዝሙሩን ሰላም ይጸፋሉ፡፡ መንፈቀ ሌሊት ሲኾንም ቅዳሴ ተቀድሶ ሥርዓተ ቍርባን ይፈጸማል፡፡ ከዚያም ሠርሖተ ሕዝብ = የሕዝብ ስንብት ከኾነ በኋላ ካህናቱም ሕዝቡ ወደየቤታቸው ሔደው እንደየባህላቸው ይፈስካሉ (ይገድፋሉ)፡፡

የመግደፊያ ዝግጅት ለሌላቸው ነዳያንም በየመንደሩ እየተዞረ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ» እየተባለ ከሥጋውም፣ ከአይቡም፣ ከቅቤውም ከመጣጣሙም፣ ከእርጐውም ይታደላል፡፡ ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ዳግም ትንሣኤ ድረስ ሕዝበ ክርስቲያኑ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ» እየተባባለ በዚህ መልኩ አብሮ እየበላ፣ እየጠጣ፣ እየተደሰተ እግዚአብሔርን ሲያመሰግን ይሰነብታል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የ፳፻፱ ዓ.ም በዓለ ትንሣኤን አስመልክቶ ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የተበረከተ ቃለ ምዕዳን

img_0028

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

ሚያዝያ ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በእንተ በዓለ ትንሣኤ ቅድስት ዘእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ሎቱ ስብሐት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

  • በአገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
  • ከአገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
  • የአገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
  • በሕመም ምክንያት በየጠበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
  • እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ኾናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

በትንሣኤው ኃይል በመቃብር ውስጥ በስብሶ መቅረትን ሽሮ ትንሣኤ ሙታንን ያበሠረ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት በዓለ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ!!

‹‹ወሰበረ ኆኃተ ብርት ወቀጥቀጠ መናሥግተ ዘሐፂን፤ የናስ ደጆችን ሰባበረ፡፡ የብረት መወርወሪያዎችንም ቀጥቅጦ ቈራረጠ፤›› (መዝ. ፻፯፥፲፮)፡፡

ይህ አምላካዊ ኃይለ ቃል ወልደ እግዚአብሔር የኾነ ኢየሱስ ክርስቶስ በመሥዋዕትነቱ ብቃት እንደ ናስ የጠነከሩትን የኃጢአት ደጆች እንደሚሰባብር፤ እንደ ብረት የጸኑትን የሞት ብረቶች ቀጥቅጦ በመቈራረጥ እንሚያስወግድ መንፈስ ቅዱስ በዳዊት አንደበት የተናገረው ቃለ ብሥራት ነው፡፡ የኃይለ ቃሉ ምሥጢራዊ ይዘት በጠንካራ ነገር የተገዙና በጽኑ መወርወሪያዎች ክርችም ብለው የተዘጉ ደጆች መኖራቸውን ጠቁሞ እነዚህን ሰባብሮና ቀጥቅጦ በሩን የሚከፍት አንድ ኃያል መሢሕ እንደሚመጣ የሚያመለክት ነው፡፡

በመጀመሪያው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል እንደምናነበው የሰው መኖሪያ የነበረው ገነተ ኤዶም በኃጢአተ ሰብእ ምክንያት በፍትሐ እግዚአብሔር ሲዘጋ፣ በሰይፈ ነበልባል እንደ ተከረቸመ፤ ኪሩባውያን ኃይላትም በጥበቃ እንደ ተመደቡበት በግልጽ ተመዝግቦአል፡፡ ይህ የጽድቅ የክብርና የሕይወት ደጅ በዚህ ኹኔታ ሲዘጋ፣ ለሰው ልጅ የቀረለት መኖሪያ ለሰይጣንና ለሠራዊቱ የተዘጋጀው፤ እሳቱ የማይጠፋ፣ ትሉ የማያንቀላፋ የእቶነ እሳት ከተማ ነበረ፡፡

ለመለኮታዊ ሱታፌና ለዘለዓለማዊ ሕይወት ታድሎ የነበረው የሰው ልጅ ለእግዚአብሔር ባለመታዘዙ ምክንያት ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመታት ያህል የተጋዘው ከላይ በተጠቀሰው የዲያብሎስ ከተማ ነበር፡፡ የዚህ ከተማ ደጆችና በሮች፣ መዝጊያዎችና መወርወሪያዎች ኃጢአት፣ ፍትሐ ኵነኔ እና ሞተ ነፍስ ወሥጋ ነበሩ፡፡ የሰው ልጅ ኃጢአትን ስለ ሠራ እግዚአብሔር የቅጣት ፍርድን ፈረደበት፤ ቅጣቱም የነፍስና የሥጋ ሞት ነበረ፡፡ እነዚህ ነገሮች እርስበርስ እንደ ሰንሰለት ተያይዘው የዲያብሎስን ከተማ የናስና የብረት ያህል ጠንካራ ደጅ እንዲኾን አድርገውታል፡፡

ይህንን በር ሰብሮና ፈልቅቆ የሰዎችን ነፍሳት ከዲያብሎስ ከተማ መዞ ለማውጣት ለፍጡር ፈጽሞ የማይቻል ነበረ፤ ሦስቱም ነገሮች ከፍጡራን ዓቅም በላይ በመኾናቸው አምላካዊ ኃይል የግድ አስፈላጊ ኾነ፡፡ በዚህም ምክንያት ጌታችን ሥጋችንን ተዋሕዶ በዚህ ዓለም በመገለጥ እኛ ከኃጢአት፣ ከፍትሐ ኵነኔ እና ከሞት ነፍስ የምንድንበት መንገድ እርሱ ብቻ መኾኑን በአጽንዖት አስተማረ፡፡

በመጨረሻም እንደ ትምህርቱና እንደ ቃሉ በመስቀሉ ኃይል ወይም በመሥዋዕትነቱ  ብቃት ሦስቱ ነገሮች ማለትም ኃጢአት ፍትሐ ኵነኔ እና ሞተ ነፍስ ከሰው ጫንቃ ላይ እንዲወገዱ አደረገ፡፡ ለሰው የማይቻል የነበረ ይህ ግብረ አድኅኖ፣ በተዋሕዶ አምላክም ሰውም ለኾነ ለጌታችን ለአምላካችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የሚቻል ነበርና በእርሱ መሥዋዕትነት እውን ኾነ፡፡

ጥንቱንም ለሰው ልጅ ሕይወትና ክብር ጠንቆች የነበሩ እነዚህ ሦስቱ ነበሩና እነርሱ ተሰባብረውና ተቀጥቅጠው ሲወገዱ በሲኦል ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ነፍሳት በአጠቃላይ ዓለም ከመፈጠሩ በፊት ወደ ተዘጋጀላቸው ወደ መንግሥተ እግዚአብሔር ተመልሰው ገቡ፡፡ ከክርስቶስ ሞት በኋላ የነፍሳተ ሰብእ ጉዞ ወደ ዲያብሎስ ከተማ ወደ ሲኦል መኾኑ ቀርቶ ወደ እግዚአብሔር ከተማ ወደ ጽዮን መንግሥተ ሰማያት ኾነ፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች በዓለ ትንሣኤን ከምንም በላይ በላቀ ኹኔታ የምናከብርበት ምክንያት ኃጢአት፣ ፍትሐ ኵነኔ እና ሞተ ነፍስ ወዲያ ተሽቀንጥረው በምትካቸው በክርስቶስ ቤዛነት ጽድቅን፣ ይቅርታንና ሕይወተ ነፍስን የተቀዳጀንበትና ከድል ዅሉ የበለጠ የድል ቀን በመኾኑ ነው፡፡ ዅላችንም መገንዘብ ያለብን ዓቢይ ነገር የክርስቶስ ድርጊቶች በሙሉ ለሰው ድኅነት ሲባል ብቻ የተደረጉ እንጂ ለእግዚአብሔር የሚፈይዱት አንዳች ምክንያት የሌላቸው መኾኑን ነው፤ ይህም ማለት በክርስቶስ የተፈጸሙ ድርጊቶች በሙሉ ለእኛ ሲባል የተደረጉ መኾናቸውን መገንዘብ አለብን ማለት ነው፡፡

ክርስቶስ ተሰቀለ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፤ ተነሣ ሲባል፣ እኛ ተሰቀልን፤ ሞትን፤ ተቀበርን፤ ተነሣን ማለት እንደ ኾነ ልብ ብለን ልናስተውል ይገባል፡፡ እኛ ተሰቅለን ሞተንና ተቀብረን የኃጢአታችንን ዕዳ የመክፈል ዓቅም ስላጣን ለእኛ ያልተቻለውን ጌታችን ስለ እኛ ብሎ፣ በእኛ ምትክ ኾኖ ለኃጢአታችን መከፈል የነበረበትን ዋጋ ዅሉ ከፍሎ አድኖናልና ነው፡፡ እኛ በክርስቶስ ቤዛነት ነጻነታችንን ተቀዳጅተን ወደ እግዚአብሔ መንግሥት ዳግመኛ መግባት የቻልነው ክርስቶስ የከፈለው መሥዋዕትነት ለእኛ ተብሎ፣ ስለ እኛ የተደረገ በመኾኑ ነው፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ የእርሱ ትንሣኤ ብቻ እንደ ኾነ አድርገን የምንገነዘብ ከኾነ ታላቅ ስሕተትም ነው፤ ኃጢአት፣ ኵነኔ እና ሞተ ነፍስ የሌለበት እርሱማ ምን ትንሣኤ ያስፈልገዋል? ትንሣኤ ለሚያስፈልገን ለእኛ ተነሣልን እንጂ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን አስመልክቶ ሲያስተምር፣ ‹‹እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጸጋ ስለ ኾነ በኢየሱስ ክርስቶስ አስነሣን፡፡ ከእርሱ ጋርም በሰማያዊ ሥፍራ አስቀመጠን፤›› ብሎአል (ኤፌ. ፪፥፬-፯)፡፡ ከዚህ አኳያ የቀን ጉዳይ ካልኾነ በቀር የትንሣኤያችን ጉዳይ በክርስቶስ ትንሣኤ የተረጋገጠና ያለቀለት ነገር እንደ ኾነ ማስተዋል፣ መገንዘብ፣ መረዳትና ማመን ይገባናል፡፡

የጌታችን ትንሣኤ ለሰው ልጅ ተብሎ የተደረገ በመኾኑ የእኛ ትንሣኤ ነው ብለን ዅሌም መውሰድና መቀበል አለብን፤ ምክንያቱም የክርስቶስ ትንሣኤ የመጨረሻ ግቡ የሰው ልጆች ትንሣኤን ማረጋገጥ ነውና፡፡ የትንሣኤ ዕድል በክርስቶስ ቤዛነት ለዅሉም ተሰጥቶአል፤ አዋጁም ሕጉም በክርስቶስ ትንሣኤ ጸድቆአል፡፡ የቀረ ነገር ቢኖር የመጨረሻው ተግባራዊ ፍጻሜ ነው፤ እርሱም ቀነ ቀጠሮ የተያዘለት ስለ ኾነ ወደዚያው በእምነትና በሥነ ምግባር መገስገስ ነው፡፡ ሰውን ለዚህ ዐቢይ ጸጋና ዕድል ላበቃ ለእግዚአብሔር አምላካችን ክብርና ምስጋና ለእርሱ ይኹን፡፡

      የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሠራውና ያስተማረው ዅሉ ምን ለማግኘት ነበረ? ተብሎ ቢጠየቅ በአጭር ዐረፍተ ነገር ‹‹ሰውን ለማዳን ነዋ!›› ብሎ መመለስ ይቻላል፡፡ እውነቱም ሐቁም ይህና ይህ ብቻ ነው፡፡ ይህን ያህል ውጣ ውረድ፣ ይህን ያህል ዋጋ ያስከፈለ የሰው መዳን በእግዚአብሔር ዘንድ ምን ያህል ተፈላጊ እንደ ኾነ በአድናቆት መመልከትና መቀበል ታላቅ አስተዋይነት ነው፡፡

በዚህ ሰውን የማዳን የእግዚአብሔር ክንውን እኛ ሰዎች የእግዚአብሔር ልጆች ለመኾን በቅተናል፤ ልጆቹም ኾነናል፡፡ ታድያ ልጅ በጠባይም፣ በመልክም፣ በሥራም አባቱን ቢመስል ጌጥም የክብር ክብርም ነውና በዅሉም ነገር አባታችንን መከተልና መምሰል ከእኛ ይጠበቃል፡፡ እግዚአብሔር አባታችን እንደ መኾኑ፣ እኛም ልጆቹ እንደ መኾናችን መጠን የአባታችንን ተቀዳሚ፣ መደበኛና ቀዋሚ ሥራ የኾነውን ሰውን የማዳን ሥራ ሳናቋርጥ የማስቀጠል ግዴታ አለብን፡፡

ዛሬም ዓለማችን የሚያድናት፣ እስከ ሞት ድረስም ደርሶ ቤዛ የሚኾናት፣ ሰላምንና ነጻነትን የሚያቀዳጃት የእግዚአብሔርን ልጅ ትፈልጋለች፡፡ የጌታችን ትንሣኤ ከመቃብር በመነሣትና ሙታንን በማስነሣት ብቻ የሚገለጽ አይደለም፡፡ ጌታችን ከመሞቱና ከመነሣቱ በፊት ብዙ ሰዎችን ከረኃብ፣ ከበሽታ፣ ከሥነ ልቡና እና ውድቀት አስነሥቷል፤ ከተሳሳተ አመለካከት፣ ከጭካኔ ከመለያየት አባዜም በተአምራትም በትምህርትም አድኗል፡፡ ጌታችን ሰውን ለማዳን ሥራ በእርሱ ብቻ ተሠርቶ እንዲቀር አላደረገም፤ እኛም እንድንሠራውና እንድንፈጽመው አዘዘን እንጂ፡፡

ከዚህ አንጻር በክርስቶስ ዘመን እንደ ነበረው ዅሉ ዛሬም ብዙ በሽተኞች የሚያድናቸው አጥተው በየጎዳናው፣ በየሰፈሩ፣ በየመንገዱ ወድቀው ይሰቃያሉ፤ እነዚህን ማን ያድናቸው? የተመጣጠነና በቂ ምግብ አጥተው ብዙ ሕፃናት፣ እናቶችና አረጋውያን በረኃብ አለንጋ ይገረፋሉ፤ ኅብስቱን አበርክቶ እነሱን ማን ይመግባቸው? በተሳሳተ አመለካከት ለሥነ ልቡና ውድቀት፣ ለቀቢፀ ተስፋ እንደዚሁም ለስሑት ትምህርተ ሃይማኖት ተጋልጠው ሃይማኖታቸውንና ታሪካቸውን በመፃረር የሚገኙ ብዙ ናቸው፤ እነዚህን ማን አስተምሮ ወደ እውነቱ ይመልሳቸው? በእግዚአብሔር ዘንድ እነዚህን ሥራዎች መሥራትና ማስተካከል የሕዝበ ክርስቲያኑና የመምህራነ ወንጌል ግዴታዎች ናቸው፡፡

በማኅበረሰቡ ሥር ሰደውና ተስፋፍተው የሚታዩትን እነዚህን መሰል ሃይማኖታዊና ማኅበራዊ ችግሮች በወሳኝነት ለመቋቋም ትምህርትና ልማት መተኪያ የሌለውን ሚና ይጫወታሉ፤ ለአገራችን ደህንነት መወገድ ቍልፍ መፍትሔ ሃይማኖትና ልማትን አጣምሮ ለመያዝና በእነርሱ ጸንቶ መኖር አማራጭ የሌለው ነው፡፡ ከእነዚህ ውጭ የኾነ ኑሮ ምንም ቢኾን ምሉእ አይደለም፤ ጣዕምም የለውም፡፡ የሰውን ዅለንተናዊ ሕይወት ለማዳን ሁለቱንም በተግባር መተርጐም ያስፈልጋል፡፡

አገራችን ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ በእነዚህ ነገሮች የታደለች እንደ ነበረችና እነዚህን አጣምራ በመያዝ የት ደርሳ እንደ ነበር በአገሪቱ ውስጥ ያሉ የሚታዩና የማይታዩ መረጃዎች ምስክርነታቸውን በመስጠት ዛሬም አልተገቱም፡፡ በአሁኑ ጊዜ አገራችን የተያያዘችውን የልማትና የሰላም ጉዞ አጠናክራ እስከ ቀጠለች ድረስ ሕሙማን የሚፈወሱባት፣ ሩኁባን ጠግበው የሚኖሩባት፣ በመንፈሳዊና በዘመናዊ ዕውቀት የበለጸጉ ዜጎች የሚታዩባት አገር የማትኾንበት ምክንያት ምንም የለም፡፡

መላው የአገራችን ሕዝቦች በኑሮአቸውና በሕይወታቸው መሠረታዊ ለውጥ ማምጣት የሚችሉት በሌላ ሳይኾን፣ እነርሱ ራሳቸው እንደ ቀድሞ አባቶቻቸው በራስ በመተማመንና በልበ ሙሉነት፣ በትጋትና በቅንነት፣ በፍቅርና በስምምነት፣ በእኩልነትና በወንድማማችነት፣ በሰላምና በአንድነት፣ በመቻቻልና በአብሮነት ኾነው በሚያስመዘግቡት የልማት ውጤት እንደ ኾነ መርሳት የለባቸውም፡፡ አገርን ለማልማትና የጠላትን ጥቃት በብቃት ለመመከት በአንድነት ኾኖ ከመታገል የተሻለ አማራጭ የለም፤ ስለዚህ ሕዝባችን እነዚህን እስከ መቼውም ቢኾን በንቃት ሊከታተላቸውና ሊጠብቃቸው ይገባል፡፡ በአእምሮ የላቁ ኾኖ መገኘት በራሱ እውነተኛ ትንሣኤ ነውና፡፡

በመጨረሻም

የጌታችን ትንሣኤ ሰውን የማዳን የእግዚአብሔር ዓላማን ያሳካ ፍጻሜ እንደ ኾነ ዅሉ የትንሣኤ ልጆች የኾንን እኛም ሰውን ለማዳን በሚደረገው መንፈሳዊና ልማታዊ ርብርቦሽ ተሳትፏችንን አጠናክረን እንድንቀጥል መንፈሳዊና አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

መልካም በዓለ ትንሣኤ ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ዘሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሚያዚያ ፰ ቀን ፳፻ወ፱ ዓ.ም

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ቀዳም ሥዑር

ሚያዝያ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የሰሙነ ሕማማቷ ቅዳሜ ‹ቀዳም ሥዑር› ወይም ‹ቀዳሚት ሥዑር› ትባላለች፡፡ ትርጕሙም ‹የተሻረች ቅዳሜ› ማለት ነው፡፡ የማትጾመዋ ቅዳሜ ከቀድሞው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል ‹የተሻረችው ቅዳሜ› ተብላ ተጠርታለች፡፡ ነገር ግን ቃሉ ጾምን እንጂ በዓል መሻርን አያመለክትም፡፡ በቀዳም ሥዑር  ሌሊት ሥርዓቱ የሚጀመረው በመኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ምንባብ ነው፡፡ ማኅሌቱም እዝሉ እየተቃኘ፣ እየተመጠነ፣ እየተዘመመ፣ እየተመረገደ፣ እየተጸፋ ያድራል፡፡ ጠዋት አቡን፣ መዋሥዕት፣ ውዳሴ ማርያም ዜማ ተደርሶ ‹‹ወለመልአከ ሕይወትሰ ሰቀልዎ›› በሚለው ሰላም ሥርዓተ ማኅሌቱ ይጠናቀቃል፡፡

ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት ስለ ኾነ ዕለተ ቅዳሜ ‹ለምለም ቅዳሜ› ተብላም ትጠራለች፡፡ በቀዳም ሥዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል (ቃለ ዓዋዲ) እየመቱ ‹‹ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ›› የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደ ሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደ ገለጠልን በማብሠር፤ ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲያቆናት ቄጠማ ተሸክመው ቃጭል ሲያቃጨሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሣኤውን ለሚናፍቅ ምእመን ትልቅ ብሥራት ነው፡፡

ቀጤማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤ ሌሊት ድረስ በራሳቸው ላይ አሥረውት ይቆያሉ፡፡ ይህም አይሁድ በጌታችን ራስ ላይ የእሾኽ አክሊል ማሠራቸውን የሚያስታውስ ነው፡፡ የቀጤማው አመጣጥና ምሥጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ (በጥፋት ውኃ) በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሠረችው ቀጤማ ይዛ በመግባት ነው፡፡ ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ‹‹የኃጢአት ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ፤ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ፤ ታወጀ፤›› በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበሥሩበታል፡፡

ዕለተ ቅዳሜ ‹ቅዱስ ቅዳሜ› እየተባለችም ትጠራለች፡፡ ቅዱስ መባሏም ቅዱስ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን ከሥራው ዅሉ ስላረፈባት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ሥራውን ዅሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ፤ በነፍሱ ሲኦልን በርብሮ ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለ ኾነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየች ዕለት መኾኗን ለማመላከት ‹ቅዱስ› (ቅድስት) ተብላለች፡፡

ምእመናን ሆይ! በአጠቃላይ የጌታችንን የመከራ ሳምንት ‹ሰሙነ ሕማማት› ብለው ሰይመው፣ ሥርዓት አውጥተው አባቶቻችን ያቆዩልንን ትውፊት ልንጠብቀውም፣ ልንጠቀምበትም ይገባል፡፡ የዕለታቱን ክብርና ስያሜ ከማወቅና ከመረዳት ጋር በዕለታቱ የታዘዙትን ሃይማኖታዊ ግዴታዎችን መወጣት ይኖርብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ተዋሕዶ (ልዩ ዕትም ዘሰሙነ ሕማማት)፣ ማኅበረ ቅዱሳን፤ ከሚያዝያ ፩ -፲፭ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም፣ ማኅበረ ቅዱሳን፤ አዲስ አበባ፡፡

ቀዳሚት ሥዑር

በመምህር ቸሬ አበበ

ሚያዝያ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ዕለተ ቅዳሜ እግዚአብሔር አምላካችን የሚታዩትንና የማይታዩትን፣ በእግር የሚሔዱትን፣ በክንፍ የሚበሩትን እና በባሕር የሚዋኙትን እንስሳትን፣ በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ያረፈባት ዕለት ነች፡፡ የመጀመሪያዋ ቅዳሜ ለእግዚአብሔር የዕረፍት ዕለት ናት፡፡ እግዚአብሔርን ፍጥረታትን ፈጥሮ ከፈጸመ በኋላ ስላረፈባት ‹ሰንበት ዐባይ› (ታላቋ ሰንበት) ትባላለች፡፡ ይህቺን ዕለት እስራኤላውያን እንዲያከብሯት ታዟል፡፡ ዕለተ ቀዳሚት (ሰንበት ዐባይ) በዘመነ ሐዲስም የተለየ የደኅነት ሥራ ተከናውኖባታል፡፡ እግዚአብሔር ጥንት ሥነ ፈጥረትን በመፍጠር ዕረፍት እንዳደረገባት ዅሉ፣ የፍጥረት ርእስ የኾነውን አዳምን ለማዳን ሕማምና ሞት የተቀበለው አምላካችን ክርስቶስ በመቃብር አርፎባታል (ማቴ. ፳፯፥፷፩)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ መቃብር አርፎ የዋለባት ዕለት በመኾኗ ‹ቀዳሚት ሥዑር› ወይም ‹ቀዳም ሥዑር› ትሰኛለች፡፡ ‹ሥዑር› የተባለችበት ምክንያትም በዓመት አንድ ቀን ስለምትጾም (የጾም ቀን በመኾኗ) ነው፡፡ የጌታችን እናት ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታችን ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት ጀምሮ ብርሃነ ትንሣኤውን እስኪያዩ ድረስ እኽል ውኃ በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ ያደረጉት የነበረ አምላካቸው በመቃብር ስላረፈ ዕለቷን ሞቱን በማሰብና ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡

እመቤታችንና ቅዱሳን ሐዋርያት በማዘን፣ በመጾምና በመጸለይ ዕለቷን እንዳከበሯት ዅሉ የተዋሕዶ ልጆችም የተቻላቸው ከሐሙስ ጀምረው በማክፈል (በመጾም) እኽል ውኃ ሳይቀምሱ ለሁለት ቀናት ያድራሉ፡፡ ያልተቻላቸው ደግሞ ዓርብ ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡ በዚህ ዕለት ከሰኞ ከሆሣዕና ማግሥት ጀምረው እስከ ስቅለተ ዓርብ ድረስ በስግደት እና በጾም ያሳለፉ ምእመናን በዕለተ ቅዳሜ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ይሰበሰባሉ፡፡ የጠዋቱ ጸሎት ሲፈጸምም ካህናቱ ‹‹ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፤ በመስቀሉ ሰላምን መሠረተ» እያሉ በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰቡ ምእመናን የምሥራች ቄጠማ ያድላሉ፡፡

ቄጠማው የምሥራች ምልክት ነው፡፡ ቄጠማው የምሥራች ምልክት ተደርጐ የተወሰደው በኖኅ ዘመን ከተፈጸመው ታሪክ ጋር በማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሕዝቦች ከሕገ እግዚአብሔር ውጪ ኾነው እጅግ የሚያሳዝን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ በንፍር ውኃ ተጥለቅልቀዋል፡፡ በወቅቱ ጻድቁ ኖኅ ወደ መርከብ ይዞአቸው ከገባው እንስሳት መካከል የውኃውን መጉደል ለመረዳት ርግብን በመርከብ መስኮት አሾልኮ ይለቃታል፤ እርሷም ቄጠማ በአፍዋ ይዛ ትመልሳለች፡፡ ኖኅም በዚህ ቄጠማ የውኃውን መድረቅ ተረድቶ ተደስቷል (ዘፍ. ፱፥፩-፳፱)፡፡

ቄጠማ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች መንገሪያ እንደ ኾነ ዅሉ፣ አሁንም ‹‹በክርስቶስ ሞት ሞተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ፤›› ስትል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡ ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የኾነውን ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፡፡ የክርስቶስ ተከታዮች ዅሉ ከጨለማ ወደ ብርሃን፤ ከዋዕየ ሲኦል (የሲኦል ቃጠሎ) ወደ ጥንተ ማኅደራቸው ገነት መመለሳቸውን በዚህ አኳኋን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

መስቀል የድኅነት ዓርማ (ምልክት)

በዲያቆን ዘላለም ቻላቸው

ሚያዝያ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እግዚአብሔር አምላካችን በቸርነቱ አዳምንና ሔዋንን ከፍጥረቱ ዅሉ አልቆ በራሱ አርአያና አምሳል ፈጥሮ ገነትን ያህል ቦታ አዘጋጅቶ በተድላ በደስታ እንዲኖሩ፣ ሌሎችንም ፍጥረታት ዅሉ እንዲገዙ ሥልጣንንም ጭምር ሰጣቸው (ዘፍ. ፩፥፳፭)፡፡ አዳምና ሔዋንም በገነት በነበሩባቸው ዓመታት ከእግዚአብሔር ጋር እየተነጋገሩ በፍጥረታት ላይ ነግሠው በደስታ ይኖሩ ነበር፡፡ በኋላ ግን ‹‹አትብሉ›› የተባሉትን ዕፅ በልተው የእግዚአብሔርን ሕግ በማፍረስ በደሉ፡፡

ከፈጣሪያቸው ጋር ራሳቸውን ለማስተካከል (አምላክ ለመኾን) በማሰብና በመመኘታቸው ይቅርታ የማይገባውን ዐመፅ  ፈጸሙ፡፡ በዚህ ጊዜ አዳም፡- ‹‹… ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትኹን፣ በሕይወት ዘመንህ ዅሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ፤ እሾኽና አሜከላ ታበቅልብሃለች …››፤ ሔዋን ደግሞ፡- ‹‹… በፀነስሽ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛዋለሁ፤ በጭንቅ ትወልጃለሽ …» ተብለው ተረገሙ (ዘፍ. ፫፥፲፭-፲፱)፡፡ «ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህ» (ዘፍ. ፪፥፲፰) ተብሎ አስቀድሞ በተነገራቸው ሕግ መሠረት ከእግዚአብሔር ጋር ተጣሉ፤ ከገነት ተባረሩ፤ የሞት ሞት ተፈረደባቸው፡፡

አዳምና ሔዋንም ኾኑ ልጆቻቸው ከዚህ ውድቀት ራሳቸውን ለማዳን አልቻሉም፤ ከተፈረደባው የሞት ሞት እንዲድኑ የበደሉን ካሣ በሞት የሚከፍል ሰው ያስፈልግ ነበር፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሔር ፍርዱ እውነተኛና ትክክለኛ ነውና ካሣ ሳይከፈል ፍርዱ አይሻርምና፡፡ ከአቤል ጀምሮ የፈሰሰው የነቢያት ደምም ካሣ ሊኾን አልተቻለውም፤ እነዚህ ሰዎች ራሳቸው የአዳምና ሔዋን በደል ስለ ነበረባው ለመሥዋዕትነት አልበቁም፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ርኅሩኅ አምላክ ነውና የፍጡሩ የሰው ልጅ ሥቃይ ስላሳዘነው ከራሱ ጋር የሚታረቅበትን መንገድ አዘጋጀ፡፡ ስለዚህም ሥጋ ለብሶ (ሰው ኾኖ)፣ መከራ ተቀብሎ፣ ሙቶ እንደሚያድናቸው ቃል ኪዳን ገባላቸው፡፡

የዘመኑ ፍጻሜ (የቀጠሮው ቀን) በደረሰ ጊዜም ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል እግዚአብሔር ቃል (ወልድ) ከነፍሷ ነፍስ፣ ከሥጋዋ ሥጋ ነሥቶ (ተዋሕዶ) ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ ነቢዩ አሳይያስ «በሰዎች ዘንድ የተናቀና የተጠላ የሕማም ሰውና ሥቃይ ያልተለየው ነበር፤ በእርግጥ እርሱ ደዌአችንን ወሰደ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ …፤›› እንዳለው ከልደቱ እስከ ስቅለቱ ድረስ መከራን በመቀበል የበደላችንን ዋጋ ከፈለ (ኢሳ. ፶፫፥፫-፬)፡፡ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ በከፈለው የሕይወት መሥዋዕትነትም የሰው ልጆችን ከራሱ፣ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አስታረቃቸው፡፡ በመስቀሉም መለኮታዊ ሥልጣኑን ገልጦ፣ ዲያሎስንና ሠራዊቱን ቀጥቅጦ ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን በሲኦል የነበሩ ነፍሳትን ነጻ አወጣቸው፡፡ «ወሪዶ እመስቀሉ ቀጥቀጠ ኃይሎ ለፀላኢ አርአየ ሥልጣኖ ለዕለ ሞትከመስቀሉ ወርዶ የጠላትን ኃይል ቀጠቀጠ፤ በሞትም ላይ ሥልጣኑን ገለጠ፤» እንዳለ ቅዱስ ያሬድ፡፡

መስቀል ክርስቶስ መከራ የተቀበለበት እና የማዳኑን ሥራ የገለጠበት የድኅነታችን ዓርማ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰፊ አገር በሰንደቅ ዓላማ (ባንዲራ) ይወከላል፡፡ ሰንደቅ ዓላማ ጨርቅ ቢኾንም ትርጕሙ ግን አገር ማለት ነው፡፡ ባንዲራን መውደድ፣ ለባንዲራ መሞት ስንልም አገርን መውደድ፣ ለአገር መሞት ማለታችን ነው፡፡ ተቋማትና ድርጅቶችም እንዲሁ የራሳቸው መገለጫ የኾነ ዓርማ አላቸው፡፡ መስቀልም የክርስቶስ የማዳኑ ሥራ የመከራውና የሞቱ ወካይ ዓርማ (ምልክት) ነው፡፡ መስቀሉን ስናይ፣ ስናማትብ፣ ስሙን ስንጠራ (ስንሰማ) በእነዚህ ዅሉ የክርስቶስን መከራና የማዳን ሥራውን እናስታውሳለን፡፡ ‹‹በመስቀሉ አዳነን›› ስንልም ጌታችን በመስቀል ላይ በፈጸመው ቤዛነት ድነናል ማለታችን ነው፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን በብሉይ ኪዳን የነበሩትን የመሥዋዕት ሥርዓቶች ያዘጋጀው፤ በሕዝቡ መካከል ለመገኘቱ ምልክት የኾነውን ታቦት የሰጠው ሰዎች አምልኮታቸውን ለመፈጸም የሚታይ የሚዳሰስ ነገር በመፈለጋቸው ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳንም በቤተ ክርስቲያን ያሉት ልዩ ልዩ ሥርዓቶች፣ ንዋያተ ቅዱሳት፣ ከዚሁ አንጻር የተዘጋጁ ናቸው፡፡ በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የሚገኘው የማይታይ ጸጋ በሚታይ አገልግሎት የሚፈጸመውም ስለዚህ ነው፡፡ መስቀልም እግዚአብሔር አምላካችን ለእኛ ሲል የተቀበለውን መከራ የምናስታውስበት፤ ከሞት ሞት መዳናችንን በማሰብ አምልኮታችንን የምንገልጥበት የድኅነታችን ዓርማ ነው፡፡ የጌታችንን መከራ፣ ስቅለት እና ሞት ክርስቲያኖች ዅል ጊዜ ማሰብ አለብን፡፡ ይህንን እንድናደርግ የሚያስችለን፤ ስለ ክርስቶስ ሕማም ስናስብም ሕሊናችንን ሰብስቦ የተከፈለልንን ዋጋ እንድናስታውስ የሚያደርገን መስቀል ነውና፡፡

ጌታችን «መስቀሌን ተሸክማቸሁ ተከተሉኝ» ሲልም መከራዬን፣ ስቃዬን፣ ሞቴን ተጋሩ ማለቱ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «ጥልን በመስቀሉ ገደለ» ሲል እንደ ገለጸው (ኤፌ. ፪፥፲፮)፣ እኛም «መስቀል ኃይልነ መስቀል ጽንዕነ መስቀል ቤዛነ መስቀል መድኃኒተ ነፍስነ አይሁድ ክህዱ ንሕነሰ አመነ ወእለ አመነ በኀይለ መስቀለ ድኅነ፤ መስቀል ኃይላችን ነው፤ መስቀል የምንጸናበት ነው፤ መስቀል ቤዛችን ነው፤ መስቀል የነፍሳችን መዳኛ ነው፡፡ አይሁድ ይክዱታል፤ እኛ ግን እናምነዋለን፡፡ ያመነውም እኛ በመስቀሉ ኃይል እንድናለን፤ ድነናልም» እያልን የክርስቶስን መከራውን፣ መስቀሉን፣ ሞቱን፣ በሞቱም እኛ መዳናችንን እንመሰክራለን፡፡

‹‹… በመስቀልህ …›› ስንልም ‹‹መከራ በመቀበልህ፣ በመሰቀልህ፣ በሞትህ፣ …›› ወዘተ ማለታችን ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም «መስቀል ብርሃን ለኵሉ ዓለም መሠረተ ቤተ ክርስቲያን፤ መስቀል የዓለሙ ዅሉ ብርሃን፤ የቤተ ክርስቲያንም መሠረት ነው፤ … » ዳግመኛም ‹‹በመስቀሉ አርኀወ ገነተ ወተሞዐ ኃይለ ሥልጣኑ ለሞት፤ በመስቀሉ ገነትን ከፈተ፤ የሞተ ኃይልም ድል ተደረገ፤›› በማለት ክርስቶስ በመስቀሉ ገነት መከፈቷን፤ ሞትም ድል መደረጉን ያብራራል፡፡

ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ መስቀል ያገኘችውን ጸጋና ለክርስቶስ ያላትን ክብር ራሷ መመስከሯን ሲገልጽም ቅዱስ ያሬድ እንዲህ ሲል ይዘምራል፤ ‹‹ትዌድሶ መርዓት ቤተ ክርስቲያን እንዘ ትብል ‹በመስቀልከ አብራህከ ሊተ እንዘ ግድፍት ወኅድግት አነ ምራቀ ርኩሳን ተዐገሥከ በእንቲአየ ሕይወተከብኩ በትንሣኤከ ጸጋ ነሣዕኩ ወደቂቅየኒ ገብኡ ውስተ ሕጽንየ በመስቀልከ አብራህከ ሊተ በመስቀልከ አድኀንከ ኵሎ ዓለመ›፤ ሙሽሪት ቤተ ክርስቲያን (ጌታን) እንዲህ እያለች ታመሰግነዋለች፤ ‹የተተውሁና የተጣልሁ ኾኜ ሳለ አብርተህልኛል፤ ስለ እኔ ብለህ የርኩሳንን ምራቅ ታግሠሃል፡፡ በትንሣኤህጋን አገኘሁ፤ ልጆቼም ወደ እቅፌ ገቡ፡፡ በመስቀልህ አበራህልኝ፤ በመስቀልህም ዓለምን ዅሉ አዳንህ›፤»

መስቀል ምንን ያስታውሰናል?

መስቀልን ስናይ፣ መስቀልን ሰናስብ፣ ስሙንም ስንጠራ የሚከተሉትን ምሥጢራት እናስታውሳለን፤

ሀ. እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር

ነቢዩ ኢሳይያስ «እኛ ዅላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ እያንዳንዳችንም በየመንገዳችን ነጎድን፤» እንዳለው (ኢሳ. ፶፫፥፮)፣ እኛ የሰው ልጆች በኃጢአታችን ምክንያት ከእግዚአብሔር ተለይተን፣ በሞት ጥላ ሥር በመከራና በችግር እንኖር ነበር፡፡ አምላካችን እኛን ለማዳን አንድያ ልጁን ወደዚህ ምድር ልኮና የሞት መሥዋዕትነት ከፍሎ አድኖናል፡፡ «በእርሱ የሚያምን ዅሉ የዘለዓለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን ወዷል፤» ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፫፥፲፮)፡፡ ይህም እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር ያሳያል፡፡ ምክንያቱም ስለ ወዳጆቹ ሕይወትን አሳልፎ ከመስጠት የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውምና (ዮሐ. ፲፭፥፫፤ ሮሜ. ፭፥፰)፡፡ ስለዚህ መስቀል ስለ እኛ ሲል በመስቀል ላይ የሞትን ጽዋ የተቀበለው መድኃኒታችን ክርስቶስ ለእኛ ያለውን ፍቅር የሚያስታውሰን ምልክት ነው፡፡

ለ. ኃጢአታችንንና የኃጢአት ደመወዝ ሞት መኾኑን

መስቀል ኃጢአታችንን የሚያስታውሰን ምልክት ነው፡፡ ጌታችን በመስቀል የተሰቀለው ኃጢአተኞች በመኾናችን፣ እኛን ለማዳን ነውና፡፡ «በበደላችን ሙታንነን ሳለ በክርስቶስ ሕያዋንንን» እንደ ተባለው (ኤፌ. ፪፥፭)፣ ጌታችን እኛን ከሞት ለማዳን በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ለመሞት ያበቃው እኛ መበደላችን፤ የበደል (የኃጢአት) ደመወዝ ደግሞ ሞት መኾኑ ነው፡፡ መስቀል ይህንን ያስታውሰናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «በዋጋ ተገዝታችኋልና የራሳችሁ አይደላችሁም፤» እንዳለው (፩ኛ ቆሮ. ፮፥፳)፣ ከኃጢአት ባርነት ነጻ የወጣነው ዋጋ ተከፍሎብን እንደ ኾነ በመረዳት እግዚአብሔርን ማመስገን፤ ለእርሱም በትሕትና መገዛት ይኖርብናል፡፡

ሐ. የእግዚአብሔርን ቅን ፈራጅነት

መስቀል የእግዚአብሔር ፍቅር እና ቅን ፍርድ በአንድ ላይ የተደረጉበት አደባባይ ነው፡፡ አዳም በበደለ ጊዜ አስቀድሞ በተነገረው መሠረት ሞት ተፈረደበት፤ እግዚአብሔር የሰው ልጆች ወዳጅ በመኾኑ ሊያድነው ቢወድም፣ ስለ በደሉ ካሣ ሳይከፈል አላዳነውም፡፡ ስለዚህ ራሱ መጥቶ መሥዋዕት በመኾን የበደሉን ካሣ በመስቀል ላይ ከፈለ፤ በዚህም የእግዚአብሔር ፍቅሩና ቅን ፍርዱ በአንድ ላይ ተገለጠ፡፡

መ. የጌታችንን ሕማማትና ሞት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የበደላችንን ዋጋ የከፈለው ሊነገሩ የማይችሉ ሕማማትን ተቀብሎ፣ ተሰዶ፣ ተሰድቦ፣ ተዋርዶ፣ ተገርፎ፣ የኃጢአተኞች ምራቅ ተተፍቶበት፣ መስቀል ተሸክሞ ተራራ ወጥቶ፣ እጆቹና እግሮቹ ተቸንክረው፣ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ፣ የሞትን ጽዋ ቀምሶ ነው፡፡ መስቀል እነዚህን ዅሉ የጌታችንን ሕማማትና ሞት የሚያስታውሰን ምልክት ነው፡፡

ሠ. ይቅር መባላችንን እና ድኅነታችንን

መስቀልን ስንመለከት እግዚአብሔር ኃጢአታችንን እንዴት ይቅር እንዳለንና በመስቀል ላይ ሳለ «አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁም ይቅር በላቸው» ማለቱን እናስታውሳለን (ሉቃ. ፲፫፥፴፬)፡፡ ዳግመኛም ጌታችን በነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዶ በዲያብሎስ አገዛዝ ሥር የነበሩ ነፍሳትን ነጻ እንዳወጣቸው፤ እኛንም በአዳም በደል ምክንያት ከመጣብን የባሕርይ ድካም እንዳዳነን እናስባለን፡፡ አሁንም መስቀልን ስንመለከት በጌታ ቀኝ ተሰቅሎ የነበረው ወንበዴ ድኅነትን እንዳገኘ፤ ጌታችን በቸርነቱ በደሉን ዅሉ ይቅር ብሎ በፍቅሩ ወደ እርሱ እንደ ሳበውና ወደ ገነት እንዳስገባው እናስባለን፡፡ እኛም በተስፋ እንሞላለን፡፡

ረ. ትንሣኤንና ዳግም ምጽአትን

የጌታችንን መስቀልና ሞት ስናስታውስ አብረን ትንሣኤውንም እናስባለን፤ በእርሱ ትንሣኤ ደግሞ የእኛን ትንሣኤ ተስፋ እናደርጋለን፡፡ በተመሳሳይ መልኩ መስቀል ዳግም ምጽአትንም ያስታውሰናል፡፡ ዳግም ምጽአትን ስናስብም ለፍርድ በፊቱ እንደምንቆም እናስታውሳለን፡፡ ጌታችን ስለ ኅልፈተ ዓለምና ዳግም ምጽአት ሲያስተምር እንዲህ ብሏልና፤ «የዚያን ጊዜ የሰው ልጅ ምልክት (መስቀል) በሰማይ ይታያል …. የሰው ልጅም በሰማይ ደመና ኾኖ በኃይልና በታላቅ ክብር ሲመጣ ያዩታል፤» (ማቴ. ፳፬፥፴)፡፡

ሰ. መስቀልን እንድንሸከም መታዘዛችንን

መስቀል ጌታችን «ሊከተለኝ የሚወድ ራሱን ይካድ፤ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ … የራሱንም መስቀል ተሸክሞ የማይከተለኝ ደቀ መዝሙሬ ሊኾን አይችልም፤» በማለት ያስተማረንን ትምህርት ያስታውሰናል » (ማቴ. ፲፮፥፳፬፤ ሉቃ. ፲፬፥፳፯)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡