በግብጽ አብያተ ክርስቲያናት በደረሰ የቦምብ ጥቃት ከዐርባ አራት በላይ ክርስቲያኖች ዐረፉ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ቀን ፳፻፱ .

egypt10

በግብጽ አገር የቅዱስ ማርቆስ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናት

በግብጽ አገር በአሌክሳንደርያ እና ታንታ ከተሞች በቅዱስ ማርቆስ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ የግብጽ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ሚያዝያ ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በደረሰ ከፍተኛ የቦምብ ጥቃት ከዐርባ አራት በላይ ክርስቲያኖች ሲያርፉ፣  ከአንድ መቶ በላይ የሚኾኑት ደግሞ ለአካል ጉዳት ተዳረጉ፡፡

egypt11

ጥቃቱ የተፈጸመባቸው አብያተ ክርስቲያናት ውስጣዊ ክፍል እና ጥቃቱ በሕንጻዎቹ ላይ ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ጥቃቱ የደረሰው በርካታ የግብጽ ምእመናን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተሰባስበው በዓለ ሆሣዕናን ሲያከብሩ በነበሩበት በዕለተ ሰንበት ረፋድ ላይ ሲኾን፣ በሁለቱም አብያተ ክርስቲያናት በምእመናን በምእመናን ላይ ለደረሰው አሰቃቂ ጥቃትም ‹አይ ኤስ አይ ኤስ› ተብሎ የሚጠራው የጥፋት ቡድን ‹‹ሓላፊነቱን እወስዳለሁ›› ማለቱን፤ የሟቾች ቍጥርም ከተጠቀሰው አኃዝ በላይ እየጨመረ መምጣቱን ልዩ ልዩ የብዙኃን መገናኛዎች ዘግበዋል፡፡

bishop-angaelos

ብፁዕ አቡነ አንጌሎስ – በእንግሊዝ አገር የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ

በእንግሊዝ አገር የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አንጌሎስ የደረሰውን ጥቃት በማስመልከት በሰጡት ቃለ ምዕዳን፡- ‹‹… በዛሬው ዕለት በዓለ ሆሣዕናን እና የክርስቶስን ወደ ኢየሩሳሌም መግባት እንዳከበርን ዅሉ፣ በዚህች ዕለት ያለፉ ወገኖቻችንም ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም መግባታቸውን እናጠይቃለን፡፡ የመድኃኒታችንን ቅዱስ ሳምንት (ሰሙነ ሕማማት) ስናከብርም የቤተሰቦቻቸውን ሐዘን እና በዚህ ጥቃት ጉዳት የደረሰባቸውን  ወገኖቻችንን ሕመም እንጋራለን፡፡ በዚህ ሳምንት መጨረሻ ታላቁን በዓለ ትንሣኤ በምናከብርበት ወቀትም ምድራዊ ሕይወታችን ብዙ ጊዜ በመከራ የተመላ የሕይወት ጉዞ እንደ ኾነና ይህ መከራም በመጨረሻው ዘመን ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔር መንግሥት ለመውረስ እንደሚያበቃን እናስተውላለን›› የሚል መልእክት አስተላፈልዋል፡፡

egypt12

‹‹ስለ እርሱ ዅልጊዜ ይገድሉናል፤ እንደሚታረዱ በጎች ኾነናል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ በመላው ዓለም የሚገኙ ክርስቲያኖች በተለይ ግብጻውያን በተደጋጋሚ በአፅራረ ቤተ ክርስቲያን ጥቃት እየደረሰባቸው ነው፡፡ በዚህ ዓመት በግብጽ ከደረሱ አሰቃቂ ጥቃቶች መካከል ታኅሣሥ ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በካይሮ ከተማ የደረሰው የቦምብ ፍንዳታ ከሃያ አምስት በላይ ግብጻውያን ክርስቲያኖችን መቅሠፉና ከአምሳ በላይ የሚኾኑትን ማቍሰሉ የሚታወስ ነው፡፡ በትናንትናው ዕለት የደረሰው ከፍተኛ ጥቃትም መላው የግብጽ ሕዝብን አስጨንቋል፡፡ የግብጽ መንግሥትም ለሦስት ወራት የሚቆይ የአስኳይ ጊዜ አዋጅ አውጥቷል፡፡

ምንጮች፡

  • Alahram /Daily News Egypt
  • Aljazeera
  • BBC
  • Christian Today
  • CNN
  • Orthodoxy Cognate Page
  • Reuters

ሆሣዕና (ለሕፃናት)

በቤካ ፋንታ

መጋቢት ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢየሩሳሌም በምትገኝ በአንድ ትንሽ መንደር ውስጥ ነው የምኖረው፡፡ ከተወለድኩ አምስት ዓመት ሞልቶኛል፡፡ በዕለተ ሰንበት በቤት ውስጥ እየተጫወትሁ፣ እናቴም በጓዳ ሥራ እየሠራች ሳለን በድንገት የብዙ ሰዎች የዕልልታ ድምፅ በሰፈሩ ውስጥ ሰማን፡፡ እናቴም በፍጥነት ከጓዳ ሮጣ ወጥታ ‹‹ልጄ! ልጄ! ነይ እንሒድ!›› ብላ አዝላኝ እየሮጠች ከቤት ወጣች፡፡ በኹኔታው ተገርሜአለሁ፡፡

በሰፈር ውስጥ ያሉ ጓደኞቼ ዅሉ በእናቶቻቸው ጀርባና በአባቶቻቸው ትከሻ ላይ ኾነው ከወላጆቻቸው ጋር በደስታ ዕልል ይላሉ፡፡ የሕፃናቶቹን ብዛት ሳይ ይበልጥ ተደሰትሁ፡፡ የሚያለቅስ አንድም ልጅ የለም፡፡ ‹‹ዛሬ የሕፃናት የደስታ እና የዝማሬ ቀን ነው›› ብሎ ልቤ በደስታ ፈነደቀ፡፡ ወላጆቻችን ዅሉ የዘንባባ ዝንጣፊ እየቈረጡ ያዙ፤ ለእኛም ሰጡን፡፡ ከዚያ ዕልል እያልን በደስታ ወደ ቤተ መቅደስ ሮጥን፡፡

በመንገድ ላይ በጣም ብዙ ሕዝብ አየሁ፤ እነርሱም ዘንባባ ይዘው ደስ ብሏቸው እንደኛ ወደ ቤተ መቅደስ ይሮጣሉ፡፡ በመካከላቸው አንድ ትልቅ አህያ አየሁኝ፣ ከአህያይቱም ጋር ውርንጫዋ (ልጇ) አለች፡፡ የሚያማምር ልብስ በአህያዎቹ ጀርባ ላይ ተነጥፏል፡፡ በውርንጫዋም ላይ የዅላችን ፈጣሪ፣ ንጉሣችን፣ አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተቀምጦ ስመለከት በደስታ ዘለልሁኝ፡፡

ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መኾን በጣም ያስደስታል፡፡ ምክንያቱም እርሱ እኛ ሕፃናትን እቅፍ አድርጎ ስሞን በጉልበቱ ላይ ቁጭ አድርጎ ያስተምረናል፣ ይመክረናል፡፡ በዙሪያውም ላሉት ሰዎች ‹‹እንደነዚህ ሕፃናት ንጹሓንኑ፤ ኃጢአት አትሥሩ፤›› እያለ ይመክራቸዋል፡፡

ከዚያ ዕልል እያለ የሚያመሰግነው ሕዝብ፣ እንደዚሁም በእናትና በአባቶቻችን እቅፍ ውስጥ ያለን ሕፃናት በአንድነት ኾነን ጮክ ብለን የዘንባባውን ቅጠል እያውለበለብን መዝሙር መዘመር ጀመርን፡፡ መዝሙሩም እንዲህ የሚል ነው፤ ‹‹ሆሣዕና በአርያም ለዳዊት ልጅ፤ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፡፡ ሆሣዕና በአርያም፤ ሆሣዕና በአርያም፤ ሆሣዕና በአርያም፡፡›› የመዝሙሩ ድምፅ በኢየሩሳሌም ከተማ ከጫፍ እስከ ጫፍ ተሰማ፡፡ በጣም ደስ ያለኝ ደግሞ የእኛ የሕፃናቱ ድምፅ ከትልልቆቹ በልጦ መሰማቱ ነው፡፡

ጌታችንን በአህያዋ ላይ ተቀምጦ ባየሁት ጊዜ ትዝ ያለኝን አባዬ መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበ ያስተማረኝን ታሪክ ልንገራችሁ፤ ታሪኩም፡- ‹‹አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፣ እጅግ ደስ ይበልሽ! አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፣ ዕልል በዪ! እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም በአህያ፣ በአህያይቱም ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፤›› የሚል ነው (ትንቢተ ዘካርያስ ፱፥፱)፡፡

የዝማሬውን ድምፅ ሲሰሙ አምላካችንን ኢየሱስ ክርስቶስን የማይወዱት በከተማው ውስጥ ያሉ ጨካኝ ሰዎች ወደ እኛ መጡ፡፡ ሰዎቹም ሕዝቡ ዅሉ ደስ ብሏቸው እየዘመሩ፣ ዕልል እያሉ፣ የዘንባባውን ቅጠል እያውለበለቡ፣ ኢየሱስ ክርስቶስን እያመሰገኑ ወደ ቤተ መቅደስ ሲሔዱ በተመለከቱ ጊዜ ተናደው ሕዝቡን ‹‹ዝም በሉ!›› ብለው ተቈጧቸው፡፡ ሕዝቡም ፈርትው ዝም አሉ፡፡

እኔና ጓደኞቼ ግን በእናታችን ጀርባ ላይ ካሉት ሕፃናት ጋር አብረን ኾነን ጮክ ብለን ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› የሚለውን መዝሙር ሳናቋርጥ እንዘምር ነበር፡፡ የገረመኝ ደግሞ ከእኔ የሚያንሱ ሕፃናትም መዝሙሩን ጮክ ብለው ሲዘምሩት መስማቴ ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሔር ሆይ መናገር የማንችለውን እኛን እንድንዘምርልህ ስለፈቀድህልን ተመስገን!›› ብዬ አምላኬን አመስግኜ መዝሙሩን መዘመር ቀጠልሁኝ፤ ‹‹ሆሣዕና፣ ሆሣዕና፣ ሆሣዕና በአርያም …፡፡››

በኋላ ግን እነዚያ ጨካኞቹ ሰዎች ስላስፈራሯቸው ወላጆቻችን ዝም አስባሉን፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በአህያዋ ውርንጫ (በትንሿ አህያ) ላይ ቁጭ ብሎ ለጨካኞቹ ሰዎች ‹‹ከሕፃናት ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን ለራሴ አዘጋጅቻለሁ፡፡ የእነርሱንም አፍ ይዛችሁ ዝም ብታስብሏቸው በዙሪያዬ ያሉት ድንጋዮች ያመሰግኑኛል፤›› አላቸው፡፡

ከዚያም ጌታችን፡- ‹‹የፈጠርኋችሁ ድንጋዮች ሆይ! ሕፃናት እንደ ዘመሩ እናንተም በመዝሙር አመስግኑኝ፤›› በማለት በታላቅ ድምፅ ሲናገር ግዙፍ ድንጋዮች ከመሬት ወደ ላይ እየተነሡ ‹‹ሆሣዕና በአርያም ለዳዊት ልጅ ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና እናቀርባለን …›› እያሉ በሚያስደስት ድምፅ እየመዘመሩ እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ በዚህ ጊዜ ጨካኞቹ ሰዎች አፍረውና ፈርትው ተመለሱ፡፡

እኛ ሕፃናት፣ ወላጆቻችንና በዙሪያችን የነበሩ ድንጋዮችም አምላካችንን ከበን በዕልልታ እየዘመርን፤ ለአህያዎቹ መርገጫ ልብሳችንንና የዘንባባውን ዝንጣፊ እያነጠፍን ወደ ቤተ መቅደስ ገባን፡፡ በዚያም ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደስ የሚል ትምህርት አስተማረን፡፡

በመጨረሻም ‹‹ሆሣዕና›› ብለን ምስጋና ላቀረብነውና በቤተ መቅደስ ተገኝተን ቃሉን ለምንሰማው ሕፃናት ጌታችን እንዲህ ብሎ መከረን፤ ‹‹ልጆቼ በመዝሙራችሁ ተደስቻለሁ፡፡ ዅል ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን እየመጣችሁ ዘምሩልኝ፡፡አንደበታችሁ በመዝሙር አግዚአብሔርን አመስግኑበት እንጂ ዘፈን እንዳትዘፍኑበት፡፡ ዘፈንጢአት ነው፡፡››

ትምህርቱን ተከታትለን ከእናቴ ጋር ደስ እያለን ወደ ቤታችን ተመለስን፡፡ ታዲያ ዅል ጊዜ ይህችን የሆሣዕናን በዓል በውስጤ አስባታለሁ፤ መዝሙሩን መዘመር በጣም ያስደስተኛል፡፡ አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻ የመከረኝንም ምክር ጠብቄ ዘፈን የሚባል በአፌ ሳልዘፍን በመዝሙር እግዚአብሔርን እያመሰገንሁ አደጌአለሁ፡፡

ልጆችዬ! ዛሬ የምታነቡት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፩ ከቍጥር ፩ እስከ ፲፮ እና የማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ ፲፩ ከቍጥር ፩ እስከ ፲፯ ያለው ትምህርት ነው፡፡

‹‹ሆሣዕና በአርያም›› ብለን እንድናመሰግነው የፈቀደልን፤ ኃይሉን ጥበቡን የሰጠን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይኹን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – የመጨረሻ ክፍል

፰. ሆሣዕና

በልደት አስፋው

መጋቢት ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ልጆች ደኅና ሰነበታችሁ? እግዚአብሔር ይመስገን! ባለፈው ዝግጅት ሰለ ሰባተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት (ስለ ኒቆዲሞስ) ተምራችሁ ነበር፡፡ መልካም ልጆች! በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ስለ ስምንተኛውና የመጨረሻው የዐቢይ ጾም ሳምንት ማለትም ስለ ሆሣዕና አጭር ትምህርት እንደሚከተለው ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ስምንተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ሆሣዕና› ይባላል፡፡ ትርጕሙም ‹መድኃኒት፣ አሁን አድን› ማለት ነው፡፡ ሆሣዕና ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ በክብር፣ በምስጋና ወደ ኢየሩሳሌም የገባበት ዕለት ነው፡፡

በዚህ ዕለት ሕፃናትና አረጋውያን በአንድነት ኾነው፣ የዘንባባ ቅጠል ይዘው፡- ‹‹ለዳዊት ልጅ በሰማይ መድኒት መባል ይገባዋል፤ በእግዚአብሔር ስም የመጣ የዳዊት ልጅ ዳዊት አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ቡሩክ ነው!›› እያሉ በአንድነት ጌታችንን አመስግነዋል፡፡

ስለዚህም ሆሣዕና በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በመንፈሳዊ ሥርዓት ይከበራል፡፡ እኛ ክርስቲያኖችም ለመታሰቢያ ይኾን ዘንድ በራሳችን ላይ የዘንባባ ቅጠል በመስቀል ምልክት እናስራለን፡፡

ልጆች! የዐቢይ ጾም ሳምንታትን ስያሜና ታሪክ በሚመለከት በተከታታይ ክፍል ያቀረብንላችሁን ትምህርት በዚሁ ፈጸምን፡፡ በሉ ደኅና ኹኑ ልጆች! ለበዓለ ትንሣኤው በሰላም ያድርሰን፡፡ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችን ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሆሣዕና በአርያም

በዲያቆን ሚክያስ አስረስ

መጋቢት ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ሰውን ከወደቀበት የበደል ጉድጓድ ያወጣው ዘንድ እግዚአብሔር ክንዱን ወደ ዓለም ላከ፡፡ ሰው ኾኖ የተገለጠው የእግዚአብሔር ክንድ በትሕትና ሁለተኛ አዳም ኾኖ በለበሰው ሥጋ በጉድጓድ ተጥሎ፤ በሥጋ፣ በነፍስ፣ በውስጥ፣ በአፍአ ቈስሎ የነበረ አዳምን ከሞተ ነፍስ አድኖታል፡፡ ከእርሱ አስቀድሞ ሰውን ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከባርነት ወደ ነጻነት የሚያመጣ ባለመኖሩ ዅሉን የፈጠረ፣ ዅሉን የሚያኖር እግዚአብሔር በለበሰው ሥጋ ሞቶ ለሰው ልጅ መድኃኒት ኾነ፡፡ በዚህም ‹‹መድኃኒተ ፈነወ እግዚአብሔር ለሕዝቡ፤ እግዚአብሔር ለሕዝቡ መድኃኒትን ላከ፤›› ተብሎ በነቢዩ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ (መዝ. ፻፲፥፱)፡፡

ክርስቶስ ባለ መድኃኒት ኾኖ በኃጢአት ለታመሙ ደቂቀ አዳም ዅሉ ሕይወትን ይሰጥ ዘንድ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ በምድራዊ ሥርዓት እንደምናየው መድኃኒትና ባለ መድኃኒት እንደሚለያዩት አይደለም፡፡ እርሱ በመምጣቱ (ሰው በመኾኑ) ሁለቱንም ፈጸመ እንጂ፡፡ መድኃኒት አድርጎ ሥጋውን ደሙን የሰጠ እርሱ ነው፡፡ በካህናት አድሮ ሰው በንስሐ ሲመለስ መድኃኒት ወደ ኾነው ወደ ራሱ የሚመራም እርሱ ነው፡፡ በእመቤታችን ማኅፀን የተጀመረው የክርስቶስ መድኃኒትነት እና ፍቅሩ ፍጻሜውን ያገኘው በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ መሐሪ ንጉሥ እርሱ መኾኑን ይገልጥ ዘንድም በፈቃዱ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ከመግባቱ አስቀድሞ ከኢየሩሳሌም ፲፮ ያህል ምዕራፍ በምትርቀው በቤተ ፋጌ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ነበር፡፡ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለቱን ማለትም ጴጥሮስን እና ዮሐንስን ‹‹በፊታችሁ ወዳለችው መንደርዱ፤ ወደ እርሷ ገብታችሁ ከሰው ማንም ገና ያልተቀመጠበትን ውርንጫ ታስሮ ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ፤›› በማለት አዘዛቸው (ማር. ፲፩፥፪)፡፡ ሰው ወዳልገባባት የተዘጋች የምሥራቅ ደጅ ወደ ምትባል ወደ ድንግል መጥቶ ዘጠኝ ወር ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ እንደ ኖረ፤ ማኅየዊት ከምትኾን ሕማሙ በኋላም ሰው ባልተቀበረበት መቃብር እንደ ተቀበረ፤ አሁንም ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት ማንም ሰው ያልተቀመጠባቸውን፣ አህያንና ውርንጫን እንዲያመጡ ደቀ መዛሙርቱን አዘዘ፡፡

የፍጥረት ዅሉ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በልደቱ እስትንፋሷን የገበረችለትን አህያ አሁን ደግሞ በፈቃዱ ስለ ሰው ዅሉ ሊሞት ሲል ንጉሥነቱን ሊያስመሰክርባት ወደደ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ካለው ፲፮ ምዕራፍ ዐሥራ አራቱን በአህያ ላይ ሳይቀመጥ በእግሩ ተጓዘ፡፡ ከዚያም ሁለቱን ምዕራፍ በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ከሔደ በኋላ የኢየሩሳሌምን መቅደስ ሦስት ጊዜ በውርጫዋ ላይ ኾኖ ዞረ፡፡ በዚህም ሕግ በተሰጣቸው አይሁድ እና ሕግ ባልተሰጣቸው አሕዛብ ላይ እኩል ቀንበርን መጫን እንዳይገባ አጠየቀ፡፡

ወደ ኢየሩሳሌም ሲሔድም እርሱን የሚከተሉት ሰዎች ሆሣዕና በአርያም› እያሉ ያመሰግኑት ነበር፡፡ ይኸውም በሰማይ በልዕልና ያለ፤ ከሰማይ የመጣ መድኃኒት› ማለት ነው፡፡ ብዙ ሰዎችም ልብሳቸውን እና ቅጠሎችን በመንገድ ላይ አነጠፉ፡፡ ‹‹ሆሣዕና በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው›› እያሉም ጌታችንን አመሰገኑ (ማር. ፲፩፥፰-፲)፡፡ ዛሬም እኛ ክርስቲያኖች ‹‹ቡሩክ ስሙ ለእግዚብሔር ወቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ስሙ ምስጉን ነው፡፡እግዚአብሔር ነኝ› ብሎ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ እርሱ ክርስቶስም ምስጉን ነው፤›› በማለት የአብ እና የወልድ መለኮታዊ አንድነትን ገልጸን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡

በክርስቶስ ሕማም እና ሞት የእግዚአብሔር ፍቅሩ እና መሓሪነቱ ተገልጧል፡፡ ክርስቶስ የተቀበለው መከራም የእርሱን አምላክነት እና ንጉሥነት አልሸሸገውም፡፡ እንዳውም ዙፋኑን መስቀል በማድረግ ንጉሥነቱን በመድኃኒትነቱ ገልጿል እንጂ፡፡ በማእከለ ምድር ተሰቅሎ በመድኃኒትነቱ ንጉሥነቱን መግለጡንም ነቢዩ፡- ‹‹እግዚአብሔርሰ ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማእከለ ምድር፤ እግዚአብሔር ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድር መካከልም መድኃኒትን አደረገ፤›› በማለት የተናገረው ቃል ያመለክታል (መዝ. ፸፫፥፲፪)፡፡ በሌላ የመዝሙር ክፍልም፡- ‹‹አንሰ ተሰየምኩ ንጉሠ በላዕሌሆሙ በጽዮን በደብረ መቅደሱ፤ እኔ በተቀደሰው ተራራ ላይ ንጉሥ ኾኜ ተሾምኹ፤›› በማለት ነቢዩ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መንገሡን ተናግሯል (መዝ. ፪፥፮)፡፡ ይህንም ‹‹እነርሱ (አይሁድ) ‹ሰቀልነው፤ ገደልነው፤ በኋላ ፈርሶበስብሶ ይቀራል፤› ይሉኛል እንጂ እኔስ ደብረ መቅደስ በሚባል መስቀል ላይ ነግሻለሁ›› ብለው ኦርቶዶክሳውያን አበው ይተረጕሙታል፡፡

የጌታችን ሕማሙ እና ሞቱ ንግሥናው፣ ክብሩ የተገለጠበት ምሥጢር እንጂ ክብሩን የሚሸሽግ ውርደት አይደለም፡፡ ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ፡- ‹‹ይትባረክ እግዚአብሔር ዘሰመየ ሕማማተ ወልዱ ክብረ ወስብሐተ፤ የልጁን ሕማማት ክብርና ምስጋና አድርጎ የሰየመ እግዚአብሔር ይመስገን!›› ያለውም ስለዚህ ነው፡፡ የክርስቶስ ሕማሙ እኛን ያከበረበት በመኾኑ ክብርና ምስጋና እንደ ተባለ እናስተውል፡፡

ከጌታችን በስተቀኝ በኩል ተሰቅሎ የነበረው ወንበዴም፡- ‹‹አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ?›› በማለት ንጉሥነቱን መስክሮለታል (ሉቃ. ፳፫፥፵፪)፡፡ ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም በምስጋና መግባቱ መድኃኒትነቱን እና ንጉሥነቱን ያሳያል ማለታችንም ስለዚህ ነው፡፡ ዳግመኛም ዅሉን የያዘ ጌታ በአህያ ላይ መቀመጡ ትሕትናውን ያስረዳል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ፡- ‹‹ዘይነብር ዲበ ኪሩቤል ዲበ ዕዋለ አድግ ነበረ›› በማለት ሰማያዊው አምላክ ልዑል እግዚአብሔር በትሕትና በአህያ ጀርባ እንደ ተቀመጠ ተናገረ፡፡

ጌታችን በመድኃኒትነቱ ድንቅ የኾኑ ተአምራትን ለሰዎች አሳየ (ገለጠ)፡፡ ‹‹እምሆሣዕናሁ አርአየ ተአምረ ወመንክረ›› እንዳለ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ በቅዳሴው፡፡ ይህም ክርስቶስ በአህያ ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም በገባ ጊዜ አእምሮ፣ ጠባይዕ ያልቀናላቸው ሕፃናት ዕውቀት ተገልጾላቸው ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› እያሉ ማመስገናቸውን ያጠይቃል፡፡ መናገር የማይችሉ ድንጋዮች እርሱ በከሃሊነቱ ዕውቀት ሰጥቷቸው መናገር ችለው ጌታችንን አመስግነዋልና፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መኾኑን፤ ቀድሞ በአዳም በደል ምክንያት ለሰው ከመገዛት ውጪ የነበሩ ፍጥረታት የሰውን ሥጋ ለብሶ በተገለጠው በክርስቶስ አማካይነት ዳግመኛ ለሰው መገዛታቸውን ከዚህ ምሥጢር እንረዳለን፡፡

ዳግመኛም ጌታችን በመድኃኒትነቱ የሥላሴ ልጅነት ማግኘትን እና ተአምራት ማድረግን ገለጠ፡፡ ‹‹እምሆሣዕናሁ አርአየ ጸጋ ወኃይለ›› እንዲል (ቅዳ. ጎርጎ. ዘኑሲስ)፡፡ የእርሱ የማዳን ሥራ ከሰው ተወስዶ የነበረውን የጸጋ ልጅነት እንዲመለስ ከማድረጉ ባሻገር በልጅነት ላይ ተአምራትን ለማድረግ አስችሏል፡፡ ይኸውም እርሱ በረድኤት አድሮባቸው ድንቅ ተአምራትን ለሚያደርጉ ቅዱሳን መሠረት ነው፡፡ በተጨማሪም የበደሉትን ያከብራቸው ዘንድ፤ ኃጥአንን ከኃጢአታቸው ያነጻቸው ዘንድ፤ እንደዚሁም የሳቱትን ይመልሳቸው ዘንድ ለንስሐ የሚኾን ዕንባን ሰጠ፡፡ ‹‹እምሆሣዕናሁ ወሀበ ፈልፈለ አንብዕ ለኃጥአን›› እንዲል (ቅዳ. ጎርጎ. ዘኑሲስ)፡፡

በተመሳሳይ ምሥጢር ጌታችን በመድኃኒትነቱ ለዕውራን ብርሃንን ሰጥቷል፡፡ ይኸውም ለጊዜው በዐይነ ሥጋ የታወሩትን በመፈወስ ዐይናቸውን እንዳበራላቸው፤ ለፍጻሜው ግን ዕውቀትን ከማጣት የተነሣ ታውረው ለነበሩ ዅሉ ዕውቀትን፣ ጥበብን ማለትም አንድነቱን፣ ሦስትነቱን፣ አምላክነቱንና የዓለም መድኃኒት መኾኑን የሚረዱበትን ጥበብ እንደ ገለጠላቸው የሚያመለክት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሆሣዕና

በመ/ር ኃይለ ማርያም ላቀው

መጋቢት ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹ሆሣዕና› የሚለው ቃል ‹ሆሼዕናህ› ከሚለው የዕብራይስጥ  ቃል የተወሰደ ሲኾን፣ ትርጕሙም እባክህ አሁን አድን› ማለት ነው፡፡ ‹‹አቤቱ እባክህ አሁን አድን፤ አቤቱ እባክህ አሁን አቅና፡፡ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩከ ነው፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፻፲፯፥፳፭-፳፮)፡፡ የሆሣዕና በዓል ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ አዕሩግም ሕፃናትም ‹‹ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ፣ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፣ ሆሣዕና በአርያም›› እያሉ ጌታችንን በክብር መቀበላቸው የሚታወስበት በዓል ነው፡፡

በሌላ አገላለጽ ይህ በዓል ‹የጸበርት እሑድ› (Palm Sunday) ይባላል፡፡ ታሪኩም የመልካም ምኞትና የድል አድራጊነት መገለጫ ኾኖ ከደገኛው አባታችን ይስሐቅ ልደት ጋር ተያይዞ የመጣ ነው፡፡ ሣራ ልማደ እንስት ከተቋረጠባት በኋላ ዅሉን ቻይ አምላክ ይስሐቅን በሰጣት ጊዜ ዘመዶችዋ የተሰማቸውን ደስታ ለመግለጽ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ እስራኤል ከአስከፊው የግብጻውያን አገዛዝ ተላቀው ባሕረ ኤርትራን በደረቅ ሲሻገሩ የተሰማቸውን እጥፍ ድርብ ደስታ በገለጡ፣ እንደዚሁም ዮዲት የተባለች ንግሥተ እስራኤል ሆሎፎርኒስ የተባለ አላዊ ንጉሥን ድል ባደረገች ጊዜ ቤተ እስራኤል እንደ ሰንደቅ ዓለማ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ ወደ አደባባይ ወጥተው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡

በዘመነ ሐዲስም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ከዲያብሎስ ቁራኝነት፣ ከሲኦል ባርነት ነጻ ለማውጣት ወደ ዙፋን መስቀሉ በተጓዘ ጊዜ ሕፃናት እና አዕሩግ ነጻ የሚወጡበት ቀን መድረሱን እግዚአብሔር አመላክቷቸው ዘንባባ በመያዝ ዘምረዋል (ሉቃ. ፳፪፥፲፰)፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ ክርስቲያን ዘንባባ እየተባረከ ለሕዝቡ ይታደላል፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ዘንባባ በመያዝ እግዚአብሔርን እንዳመሰገኑ እኛ እስራኤል ዘነፍስም ዘንባባ (ጸበርት) በግንባራችን በማሰር በዓሉን እናከብራለን፡፡ በዕለተ ሆሣዕና አዕሩግና ሕፃናት ‹‹ለዳዊት ልጅ መድኃኒት መባል ይገባዋል›› እያሉ ዘምረዋል፡፡

ይህ ዅሉ በአንድ ወገን የነበረው የአቀባበል ሥነ ሥርዓት ሲኾን፣ በሌላ በኩል የነበረው አቀባበል ደግሞ እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ሥርዓተ ኦሪትን፣ ትንቢተ ነቢያትን በሚገባ እንከተላለን ይሉ የነበሩ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ጌታችንን ‹‹ደቀ መዛሙርትህን ገሥፃቸው›› ነበር ያሉት፡፡ ጌታችንም መልሶ፡- ‹‹እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ›› በማለት ሕያዋን ሰዎች ብቻ ሳይኾኑ ግዑዛን ፍጥረታትም እርሱን እንደሚያመሰግኑ አስረድቷቸዋል፡፡ ቅናት አቅላቸውን ያሳታቸው ፈሪሳውያን የሕዝቡን ምስጋና ወደ ጥላቻ እንዲለወጥ በማድረጋቸው በዕለተ ሆሣዕና ዘንባባ ይዘው ይዘምሩ የነበሩ ጭምር በዕለተ ዓርብ ‹‹ይሰቀል!›› እያሉ በጌታችን ላይ ጮኸዋል፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ በነቢዩ ዘካርያስ፡- ‹‹እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ኾኖ በአህያም፣ በአህያዪቱ ግልገል በውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፤›› ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጽሟል (ዘካ. ፱፥፱፤ ማቴ. ፳፩፥፬፤ ማር. ፲፩፥፩-፲፤ ሉቃ. ፲፱፥፳፰-፵፤ ዮሐ. ፲፪፥፲፭)፡፡ ጌታችን በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱ የሰላም ንጉሥ መኾኑን ያመለክታል፡፡ እስራኤል ዘመነ ምሕረት ሲኾንላቸው አባቶቻቸው በአህያ ጀርባ ተቀምጠው ይታዩ ነበር፡፡ ጌታም እውነተኛ ሰላም ይዤላችሁ መጣሁ ሲለን በአህያ ጀርባ ወደ ቤተ መቅደስ ሕይወታችን ተጉዟል፡፡

መድኃኒታችን ክርስቶስ መላእክት በዕለተ ልደቱ ‹‹በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይገባዋል፤ በምድርም ሰላም ለሰዉ ዅሉ ይሁን›› እያሉ የዘመሩለት የሰላም ባለቤት ነው (ሉቃ. ፪፥፲፫)፡፡ በመዋዕለ ትምህርቱም ‹‹ሰላሜን እሰጣችኋለሁ›› ብሎ አስተምሮናል (ዮሐ. ፲፬፥፳፯)፡፡ ሰላሙን የሚሰጥበት ዕለት መቃረቡን ለማመልከት ጌታችን በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ቤተ መቅደስ መጣ፡፡ በሌላ በኩል በአህያ ጀርባ መቀመጡ ኅቡዕ ምሥጢር አለው፡፡ በአህያ ጀርባ የተቀመጠ ሰው ሌላውን አሳድዶ አይዝም፤ እርሱም ሮጦ አያመልጥም፡፡ በዚህም ጌታችን በእምነት ለሚፈልጉት የሚገኝ፣ ለማይፈልጉት ግን የማይገኝ አምላክ መኾኑን አስተምሯል፡፡

ለታሰሩት መፈታትን ሊሰብክ ሰው የኾነው ጌታችን ከማሰሪያዋ በተፈታች አህያ እንደ ተቀመጠ ዅሉ ዛሬም ከኃጢአት እስራት በተፈታ ሕይወት አድሮ የሕሊና ሰላምን ይሰጣል፡፡ የአህያን ጀርባ ያልናቀ ጌታችን ትሑት ሰብእና እና የተሰበረ ልቡና ወዳለው ሰው ዘወትር ይጓዛል፡፡ እርሱ የተዋረደውንና የተሰበረውን ልብ አይንቅምና (መዝ. ፶፥፲፯፤ ኢሳ. ፷፮፥፪)፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ፀሐይ ዕድሜአችን ሳትጠልቅ በእምነት እግዚአብሔርን እንፈልገው፡፡ ሰላሙን ይሰጠን ዘንድም ንስሐ ገብተን ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› እያልን እናመስግነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡- ሐመር ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፣ መጋቢት/ሚያዝያ ፲፱፻፺፮ ዓ.ም፡፡

ኒቆዲሞስ – የክርስቲያኖች ፊደል  

መጋቢት ፳፮ ቀን ፳፻፱ .

ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ የምሥራቹን ቃል ሲያውጅ እስራኤላውያን የተቀበሉት በተደበላለቀ ስሜት ነበር፡፡ በአንድ በኩል ለብዙ ዘመናት በባርነት ሲገዙ ስለ ነበር ከሮማውያን ቅኝ ግዛት ነጻ የሚያወጣቸው መሲሕ ይፈልጋሉ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለብዙ ዘመናት በባርነት ቀንበር ስለ ደከሙ ተስፋ በመቁረጥ ተዳክመው ነበር፡፡ መሲሕ ቢመጣ እንኳ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት ጦር ይዞ፣ ሠራዊት አስከትሎ ነው ብለው ያምኑ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው የክርስቶስን መሲሕነት ያልተቀበሉት፡፡ አብዛኛው እስራኤላዊ የክርስቶስን መሲሕነት ቢጠራጠርና ባይቀበለውም፣ በፍጹም እምነት እስከ መጨረሻው  የተከተሉትም  ነበሩ፡፡ ለዚህም  ትልቅ ማሳያ የሚኾነን ከፈሪሳውያን ወገን የኾነው ኒቆዲሞስ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህን  ታላቅ ሰው ለማዘከር የዐቢይን ጾም ሰባተኛ እሑድ በስሙ ሰይማ ታከብረዋለች፡፡ ተከታዮቿ ምእመናንም የእርሱን አሠረ ፍኖት እንዲከተሉ ትመክራለች፤ ታስተምራለችም፡፡

ኒቆዲሞስ ማነው?

ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ ነው (ዮሐ. ፫፥፩)

የእስራኤላውያን ለብዙ ዘመን በባርነት መኖር የሕዝቡን የአኗኗር ኹኔታ ቀይሮታል፡፡ በግዞት ጊዜ ከአሕዛብ የቀሰሟቸው አጉል ትምህርቶች በእምነትም በአስተሳሰብም እጅግ እንዲለያዩና እንዲራራቁ ምክንያት ኾነዋል፡፡ አይሁዳውያን፣ ሳምራውያን፤ ከአይሁዳውያንም ሰዱቃውያን፣ ጸሐፍት፣ ፈሪሳውያን፣ ወዘተ. ተብለው እንዲከፋፈሉ ከዚህም እጅግ ወርደው ገሊላዊ፣ ናዝራዊ እንዲባባሉ ያበቃቸው ከአሕዛብ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ፈር አለማስያዛቸው ነበር፡፡

ከአይሁድ ቡድኖች መካከል ፈሪሳውያን ሕግን በማጥበቅ ሕዝቡን የሚያስመርሩ፤ ቀሚሳቸውን በማስረዘም እነርሱ የማይፈጽሙትን ሕግ በሕዝብ ላይ የሚጭኑ፤ ራሳቸውን ከሌሎች በላይ ከፍ ከፍ የሚያደርጉ ‹‹አባታችን አብርሃም ነው›› እያሉ የሚመጻደቁ፤ የአባታቸው የአብርሃምን ሥራ ግን የማይፈጽሙ የአይሁድ ቡድን ክፍሎች ናቸው (ዮሐ. ፰፥፴፱)፡፡ ኒቆዲሞስም ራሱን ከዚህ ሕዝብ ለይቶ በፍጹም ልቡ ክርስቶስን ፍለጋ የመጣ ፈሪሳዊ ነው፡፡ ቀድሞ አባታችን አብርሃምን ‹‹ከቤተሰብህ ተለይተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሒድ›› ያለው አምላክ ኒቆዲሞስን ከፈሪሳውያን ለይቶ ጠራው (ዘፍ. ፲፪)፡፡

ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ ነው (ዮሐ. ፫፥፩)

ሮማውያን ሕዝቡን የሚያስተዳድሩት ከላይ ያለውን ሥልጣን ተቆናጠው ታች ያለውን ሕዝብ ባህላቸውን በሚያውቅ፣ ቋንቋቸውን በሚጠነቅቅ አይሁዳዊ ምስለኔ ያስገዙ ነበር፡፡ አውሮፓውያንም አፍሪካን ለመቀራመት የተጠቀሙበት ስልት ይህን ዓይነት ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ምንም እንኳ ፈሪሳዊ ቢኾን አለቃ እንዲኾን በሮማውያን የተሾመ ባለ ሥልጣን ነው፡፡

ኒቆዲሞስ መምህረ እስራኤል ነው (ዮሐ. ፫፥፭)

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ምሥጢረ ጥምቀትን በገለጸለት ጊዜ ሲደናገር አይቶ «አንተ የእስራኤል መምህር ስትኾን ይህን አታውቅምንብሎታል፡፡ ይህ ጥያቄ የሚጠቁመን ኒቆዲሞስ አለቅነትን ከመምህርነት የያዘ፤ በአይሁዳውያን ዘንድ የታፈረና የተከበረ ሰው እንደ ነበረ ነው፡፡ መምህር ቢኾንም ‹‹የሚቀረኝ ያላወቅሁትያልጠነቀቅሁት ብዙ ነገር አለ›› በማለት የመምህርነቱን ካባ አውልቆ፣ የተማሪነትን ዳባ ለብሶ ከክርስቶስ ሊማር መጣ፡፡

ኒቆዲሞስ ምሁረ ኦሪት ነው (ዮሐ. ፫፥፯)

አንዳንዴ ሳያውቁ አወቅን ሳይማሩ እናስተምር የሚሉ ደፋር መምህራን አይጠፉም፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ከዚህ በተለየ አለቅነትን ከመምህርነት፣ መምህርነትን ከምሁርነት አስተባብሮ የያዘ፤ ዕውቀትን ከትሕትና፣ ምሁርነትን ከመንፈሳዊነት ጋር አስማምቶ የኖረ ሰው ነበር፡፡ የኦሪት ምሁር መኾኑን የሚጠቁመን ደግሞ ከካህናት አለቆች ጋር ያደረገው ክርክር ነው፡፡

ኒቆዲሞስ ምን አደረገ?

ለምሥጢረ ጥምቀት መገለጥ ምክንያት

የአይሁድ የፋሲካ በዓል እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀኑ እንደ ደረሰ ለሐዋርያቱ ተናግሮ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡ እንደ ሰውነቱ ሰለቸኝ ደከመኝ ሳይል ሕዝቡን ቀንና ሌሊት በትምህርትና በተአምራት ያገለግል ነበር፡፡ በዚህ ሰዓት ነው ኒቆዲሞስ በሌሊት ገስግሶ ወደ ጌታችን የመጣው፡፡ በፊቱ ቀርቦም «መምህር ሆይ» ብሎ የእርሱን አላዋቂነት፣ የክርስቶስን ማእምረ ኅቡዓትነት (የተሰወረን አዋቂነት) መሰከረ፡፡ ጌታችንም አመጣጡ ከልብ መኾኑን አውቆ ምሥጢረ ጥምቀትን (ዳግም ልደትን) ገለጸለት፡፡ ምሥጢሩም የኦሪት ምሁር ለነበረው ኒቆዲሞስ ለጆሮ የከበደ፣ ለመቀበል የሚቸግር ኾነበት፡፡ የከበደውን የሚያቀል፣ የጠበበውን የሚያሰፋ አምላክ ምሥጢሩ ለኒቆዲሞስ  እንደ ከበደው ስላወቀ ቀለል አደረገለት፡፡ ዳግም ልደት ከእናት ማኅፀን ሳይኾን ከውኃ እና ከመንፈስ ቅዱስ እንደ ኾነ አብራራለት፡፡

 አዋቂ ነን የሚሉትን አሳፈራቸው

ወቅቱ የአይሁድ የፋሲካ በዓል የቀረበበት፤ ጻፎችና የካህናት አለቆች ጌታን ለመያዝ፣ እንደ ሙሴም ሕግም ሊያስፈርዱበት የተቻኮሉበት ጊዜ ነበር፡፡ ጌታችን የሙሴ ፈጣሪ መኾኑን አላወቁምና፡፡ የካህናት አለቆች ተሰብስበው ክርስቶስን ለመያዝ በሚመካከሩበት ጊዜ ከሙሴ መጽሐፍ ሕግ ጠቅሶ ሊቃውንተ ኦሪትን አፍ ያስያዛቸው ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ ሳይስማሙ ወደየቤታቸው እንዲበታተኑ ምክንያት የኾነ ታላቅ ሰው ነው – ኒቆዲሞስ፡፡

ጌታን ለመገነዝ በቃ (ዮሐ. ፲፱፥፴፰)

ጌታችን በቀራንዮ አደባባይ ራሱን ለዓለሙ ቤዛ አድርጎ ሲሰጥ እስከ ሞት ከአንተ አንለይህም ያሉት ደቀ መዛሙርቱ ከዮሐንስ በቀር ሲበታተኑ፣ በዘጠኝ ሰዓት ቀራንዮ ላይ የነበረው ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ኾኖ የክርስቶስን  ስጋ ከአለቆች ለምኖ የገነዘው፤ ወደ ሐዲስ መቃብር ያወረደውም ኒቆዲሞስ ነበር፡፡

ከኒቆዲሞስ ምን እንማር?

አትሕቶ ርእስ (ራስን ዝቅ ማድረግ)

ብዙዎቻችን ባለን የኑሮ፣ የዕውቀት እና የሥልጣን ደረጃ ራሳችንን ከፍ ከፍ አድርገን የመማር አቅም ያጣን፤ ቁጭ ብሎ መማር ለደረጃችን የማይመጥን የሚመስለን ስንቶቻችን እንኾን? በአንድ ወቅት አባ መቃርስ ከሕፃናት እንቆቅልሽ ለመማር ቁጭ እንዳሉ፣ በእንቆቅልሹም ልባቸው ተነክቶ እያነቡ ወደ በዐታቸው እንደ ተመለሱ እያወቅን እኛ ግን ከአባቶች የመማር አቅም አጣን፡፡ ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ፣ የአይሁድ አለቃ፣ መምህረ እስራኤል፣ ምሁረ ኦሪት ቢኾንም ራሱን ዝቅ አድርጎ ከጌታ እግር ሥር ቁጭ አለ፡፡ ሕዝብን ከመምራትና ከማስተማር ይልቅ ቁጭ ብሎ መማር ምንኛ መታደል ነው!

ጌታችንም በትምህርቱ «ማርያምም  መልካም ዕድልን መርጣለችከእርሷም አይወሰድባትም» ያለው ስለዚህ አይደል? (ሉቃ. ፲፥፵፪)፡፡ በቅዱስ ወንጌል ላይ በተደጋጋሚ የምናገኘው የፈሪሳውያንን ግብዝነትና የጌታችንን ተግሣፅ ነው፡፡ ትሑት የሚያሰኘው ሳያውቁ አውቃለሁ ማለት ሳይኾን፣ እያወቁ አላውቅም ማለት ነው፡፡ ሳይማሩ ተምሬያለሁ ማለት ሳይኾን ተምረውም ልክ እንደ ኒቆዲሞስ ለመማር ራስን ዝቅ ማድረግ ነው፡፡ ከፈሪሳዊው ይልቅ የቀራጩ ጸሎት ተቀባይነትን ማግኘቱም ለዚህ አንዱ ማስረጃ ነው (ሉቃ. ፲፰፥፲፩-፲፮)፡፡

 ጎደሎን ማወቅ

በአብዛኞቻችን ዘንድ የሚታየውና ክርስትናችንን፣ አገልግሎታችንን እና ቤተ ክርስትያናችንን እየተፈታተነ ያለው ችግር ጎደሎዎቻችንን አለማወቃችንና ምሉዕ እንደ ኾነን ማሰባችን ነው፡፡ ነገር ግን ምንም  እንዳልኾኑ አውቆ ራስን ለክርስቶስ እና ለቤተ ክርስቲያኑ አሳልፎ መስጠት ምንኛ መታደል ነው! ኒቆዲሞስ ያለውን ሳይኾን ያጣውን፤ የሞላለትን ሳይኾን የጎደለውን ፍለጋ ወደ ክርስቶስ መጣ፡፡ ዕውቀት ብቻውን ምሉዕ አያደርግም፡፡ አለቅነትም ቢኾን ገደብ አለው፡፡ ኒቆዲሞስ ምሁረ ኦሪት እንጅ ምሁረ ሐዲስ አይደለም፤ መምህረ እስራኤል ዘሥጋ እንጅ መምህረ እስራኤል ዘነፍስ አይደለም፡፡ የሕይወቱን ክፍተት ሊሞላ የሚችል አንድ ክርስቶስ ብቻ ነውና ኒቆዲሞስ ጉድለቱን አምኖ ጎደሎውን ሊያስሞላ ወደ ክርስቶስ መጣ፡፡ ‹‹የሚጎድለኝ ምንድን ነው?›› ብሎ እንደ ጠየቀው እንደዚያ ሰው ጎደሎን ማመን ምንኛ ታላቅ ነገር ነው!

አልዕሎ ልቡና (ልቡናንን ከፍ ማድረግ)

ኒቆዲሞስ ይዞ የመጣው ሥጋዊ ሕዋሳቱን ነበር፡፡ ጌታችን ግን አመጣጡ ለመልካም እንደ ኾነ አውቆ ለሥጋዊ ዕውቀት እጅግ የሚከብደውን ምሥጢረ ጥምቀትን ገለጸለት፡፡ መጀመሪያ ይህን ምሥጢር ለመቀበል አልተቻለውም ነበር፡፡ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ምሥጢሩን ፍንትው አድርጎ ሲያብራራለት ግን ልቡናው ምሥጢሩን ለመቀበል ተዘጋጀ፡፡ ምሥጢራትን ለመቀበል ልቡናን ከፍ ከፍ ማድረግ ይገባል፡፡ የእምነታች መሠረት በሥጋ ዓይን ማየት፣ በሥጋ ጆሮ መስማት፣ በሥጋ እጅ መዳሰስ ብቻ ከኾነ እምነታችን ልክ እንደ እንቧይ ካብ ኾነ ማለት ነው፡፡ ትቂት የፈተና ነፋስ ሲነፍስበት፣ ጠቂት የመከራ ተፅዕኖ ሲደርስበት መፈራረስ፣ መናድ ይጀምራል፡፡ ኒቆዲሞስም ምሥጢሩ መጀመሪያ ቢከብደውም ቅሉ በኋላ ልቡናውን ወደ ሰማያዊው ምሥጢር ከፍ ስላደረገ ምሥጢሩን በቀላሉ ተረዳ፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ሲፈታተኗትና እየተፈታተኗት ያሉ አካላት በሙሉ የስሕተታቸው ምንጭ እንደ ግያዝ ከአካባቢያቸውና ከምናየው አካል (ቁሳዊ ዓለም) ውጭ መመልከት አለመቻል ነው (፪ኛ ነገ. ፮፥፲፯)፡፡ ለዚህም ነው ካህኑ በሥርዓተ ቅዳሴ ጊዜ የቍርባኑ ምሥጢር እንዲገለጽልን «አልዕሉ አልባቢክሙልቦናችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ» የሚሉን፡፡

ስምዐ ጽድቅ (የእውነት ምስክር) መኾን

ቅዱስ ጳውሎስ፡- «ለእውነት እንጅ በእውነት ላይ ምንም ማድረግ አንችልም» በማለት እንደ ተናገረው (፪ኛ ቆሮ. ፲፫፥፰)፣ ቤተ ክርስቲያን በሰማዕትነት የምትዘክራቸው ቅዱሳን በሙሉ ለእውነት ብለው ራሳቸውን ለክርስቶስ አሳልፈው የሰጡትን አባቶች እና እናቶችን ነው፡፡ በፍርኀትና በሐፍረት፣ በይሉኝታና በሐዘኔታ እውነትን አለመመስከር በክርስቶስ ፊት ያስጠይቃል እንጅ አያስመሰግንም፡፡ ኒቆዲሞስ ያለ ፍርኀትና ያለ ሐፍረት በካህናቱ ፊት እውነትን መስክሯል፡፡ ካህናቱን መጽሐፍ ጠቅሶ እውነትን ተናግሮ አሳፍሯቸዋል፡፡ እውነትንና ፀሐይን ፈርቶ የትም መድረስ አይቻልም፡፡ በመሪዎችና በታላላቅ ባለ ሥልጣናት ፊት እውነትን መመስከር ክርስትናችን የሚያስገድደን ዐቢይ ቁም ነገር ነው (ሉቃ. ፲፪፥፫-፭)፡፡

ትግሃ ሌሊት (በሌሊት ለአገልግሎት መትጋት)

እንደ ሌሊት ለመንፈሳዊ ሕሊና፣ ለተመስጦ የሚመች ጊዜ የለም፡፡ ቀን ለሥጋ ሲራወጥ የነበረ አካልና መንፈስ ሌሊቱን ለነፍስ በመገዛት ሥጋውን ማድከም አለበት፡፡ ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቀኑን በቅዳሴ፤ ሌሊቱን ደግሞ በማኅሌት፣ በሰዓታት፣ በኪዳን እግዚአብሔርን ስታምሰግን  የምታድረው፡፡ ‹‹ሌሊትስ ጌታን ለማመስገን የተፈጠረ ድንቅ ጊዜ ነው›› እንዳለ ቅዱስ ማር ይስሐቅ፡፡ ጌታችንም ሐዋርያቱን ‹‹ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ›› ብሏቸዋል (ማቴ. ፳፮፥፵፩)፡፡ አሁንም ቤተ ክርስቲያን እንደ ኒቆዲሞስ ለኪዳን፣ ለማኅሌት፣ ለጸሎት በሌሊት የሚገሰግስ ምእመንን ትፈልጋለች፡፡

እስከ መጨረሻ መጽናት

ክርስትና ለጀመሩት ሳይኾን ለጨረሱት፤ ለወጠኑት ሳይኾን ለፈጸሙት የድል አክሊል የምትሰጥ መንገድ ናት፡፡ ስለዚህም የመሮጫ መሙ ጠበበን፤ ሩጫው ረዘመብን ብለው ከመስመሯ ለሚወጡ ዴማሶች ቦታ የላትም (፪ኛ ጢሞ. ፬፥፲)፡፡ ጌታችንን በመዋዕለ ስብከቱ ብዙ ሺሕ ሕዝብ ቢከተለውም እስከ መስቀሉ አብረውት የነበሩ ጥቂቶች ናቸው፡፡ የተወሰነው ሕዝብ ቀድሞም የተከተለው ለምግበ ሥጋ ነበርና ቀራንዮ ላይ አልተገኘም፡፡ ቀራንዮ ላይ ምግበ ነፍስ እንጅ ምግበ ሥጋ የለምና፡፡ ሌሎችም አይሁድን ከመፍራታቸው የተነሣ ከመስቀሉ ሥር አልተገኙም፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ክርስቶስ በፈቃዱ ነፍሱን ከሥጋው በለየበት ሰዓት ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ኾኖ የክርስቶስን ክቡር ሥጋ ከመስቀል አውርዶ፣ ገነዞ በሐዲስ መቃብር ለመቅበር ታድሏል፡፡

በዚህ የመከራ ሰዓት ከዮሐንስና ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ውጭ ማንም በሥፍራው አልነበረም፡፡ በመጨረሻው ሰዓት ከመስቀሉ ሥር የተገኙት የቁርጥ ቀን ልጆች ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ናቸው፡፡ ይህም ኒቆዲሞስ ፈተናውን ዅሉ ተቋቁሞ እስከ መጨረሻው ለመጽናቱ ምስክር ነው፡፡ በክርስትና ሕይወታችን በምቹ ጊዜ የምናገለግል፣ ፈተና ሲመጣ ግን ጨርቃችን (አገልግሎታችንን) ጥለን የምንሮጥ፣ ሰበብ አስባብ ፈልገን የምናፈገፍግ ብዙዎች ነን (ማር. ፲፬፥፲፭)፡፡ ዕውቀት፣ ሀብት እና ጊዜ ጣኦት ኾኖበት ከመሃል መንገድ የቀረውን፤ ሩጫውን ያቋረጠውን፤ ከቤተ ክርስቲያ አገልግሎት የራቀውን ክርስቲያን ቈጥረን አንጨርሰውም፡፡ ጌታችን በትምህርቱ «ወዘአዝለፈ ትዕግሥቶ ውእቱ ይድኅን፤ እስከ መጨረሻው የሚጸና እርሱ ይድናል» (ማቴ.፳፬፥፲፫) በማለት የድኅነት ተስፋ ሰጥቶናልና ዅላችንም እንደ ኒቆዲሞስ እስከ መጨረሻው በሃይማኖታችን ልንጸና ይገባናል፡፡

በአጠቃላይ ከኒቆዲሞስ ሕይወት ብዙ ቁም ነገሮችን እንማራለን፡፡ የኒቆዲሞስ በሌሊት ገስግሶ መምጣት ለምሥጢረ ጥምቀት ትምህርት መገለጥ ምክንያት እንደ ኾነ ዅሉ፣ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን በቅዳሴው፣ በኪዳኑ፣ በሰዓታቱ፣ በማኅሌቱ ብንሳተፍ ረቂቅ የኾነው ሰማያዊ ምሥጢር ፍንትው ብሎ ይገለጥልናል፡፡ እንደ ኒቆዲሞስ ራሳችንን ዝቅ አድርገን በምሥጢራት በመሳተፍ ለታላቅ ክብር እንበቃ ዘንድ የአምላካችን የልዑል እግዚአብሔር መልካም ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም

በአያሌው ዘኢየሱስ

መጋቢት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፤›› (ዮሐ.፫፥፫)፡፡

ይህ ቃል ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ካስተማረው ትምህርት የተወሰደ ኃይለ ቃል ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ብዙ የተማረ፤ ብዙ ያወቀ የሃይማኖት ሊቅ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ሊቅ፣ ምሁር፣ አለቃ ተብሎ ተጠርቶአል፡፡ በጊዜው ከነበሩ ሰዎች ከፍ ያለና የላቀ ዕውቀት የነበረው ሰው ነበር፡፡ በሌሊት ወደ ጌታ እየመጣ ይማር ነበር፡፡ የማታ ተማሪ ነበር፡፡ ቀን፣ ቀን የምኵራብ አስተማሪ ኾኖ ብዙ ሰዎችን ያስተምር ስለ ነበረና እርሱ የሚያስተምራቸው አይሁድ ጌታችንን ስላልተቀበሉ በቀን ለመማር አመቺ ጊዜ አልነበረውም፡፡

በአይሁድ ሕግ ጌታን የሚከተልና የሚቀበል ሰው ከምኵራብ ይባረር ስለ ነበረ እነርሱን ላላማስቀየም ኒቆዲሞስ ማታ፣ ማታ ነበር የሚማረው፡፡ ኒቆዲሞስ፡- ‹‹ከሰው ችሎታ በላይ የኾኑ ተአምራትን ስለምትሠራ እኛን ለማስተማርና ለመምከር ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልከህ የመጣህ ነህ›› ብሎ ለጌታችን መስክሮለታል፡፡ ጌታችንም፡- ‹‹እናንተን ለማስተማር እንደ መጣሁ ከተረዳህ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገባም›› አለው፡፡

ኒቆዲሞስ ስላልገባው ‹‹እኔ አርጅቼአለሁ፤ እንዴት ነው ወደ እናቴ ማኅፀን ተመልሼ የምገባውና ዳግም የምወለደው?›› ብሎ ኢየሱስ ክርስቶስን ጠየቀው፡፡ ጌታችንም፡- ‹‹ሰው ከሰው ከተወለደ ሥጋዊ ነው፤ የሰው ልጅ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ለመኾን በመንፈስ መወለድ አለበት፡፡ ከእግዚአብሔር መወለድ ነፋስ ከየት ተነሥቶ ወዴት እንደሚነፍስ እንደማይታወቅ ያለ ረቂቅ ምሥጢር ነው›› አለው፡፡ አሁንም ያ ሊቅ፤ ያ አዋቂ ‹‹አልገባኝም›› አለ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- ‹‹አንተ የእስራኤል መምህር እና ሊቅ ኾነህ እንዴት ይህን አታውቅም?›› አለው፡፡ ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደ ሰማይ የሚወጣ የለም፤ የምናውቀውንም እንናገራለን ካለው በኋላ ጥያቄውን በዚህ ገታ፡፡

ኒቆዲሞስ  ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ መማሩ የሚያስመሰግነው ተግባር ነው፡፡ አይሁድ ወገኖቹ ጌታን ሳይከተሉት እርሱ ግን ጌታን መውደዱ የሚያስደንቅ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የሚያመሸው ከጌታ ጋር ነበር፡፡ ባለችው ትርፍ ጊዜው ዅሉ ወደ ፈጣሪው ይሔድ ነበር፡፡ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ ቀን ሲያስተምርና ሲደክም ስለሚውል ማታ፣ ማታ ማረፍ ይገባው ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ቤቴ ገብቼ ልረፍ አላለም፡፡ ባለ ሥልጣንና ባለጠጋ ስለ ነበር ደጅ የሚጠናው ሕዝብና መሰል ባልንጀሮቹ ይፈልጉት ነበር፡፡ ይኹን እንጂ ከእነርሱ ጋር አላመሸም፡፡

ከዚህ አባት ታላቅ ትምህርት ልንማር ያስፈልጋል፡፡ እኛ ዛሬ የምናመሸው የት ነው? የምናመሸውስ ከማን ጋር ነው? ምን ስናደርግ ነው የምናመሸው? ኒቆዲሞስ ቤቱ አልነበረም የሚያመሸው፤  ከእውነተኛው መምህር ጋር እንጂ፡፡ ኒቆዲሞስ ጽድቁንና በረከቱን እየያዘ ነበር ወደ ቤቱ ይገባ የነበረው፡፡ እኛ ወደ ቤታችን የምንገባው እየከበርን ነው ወይ? ጸድቀን ነው የምንገባው ወይስ ጐስቁለን?

የዛሬ ዘመን ሰው እየሰከረ፣ እየጨፈረ፣ እየደማ፣ እየቆሰለ አእምሮውን ስቶ ነው ወደ ቤቱ የሚመለሰው፡፡ የሚሞትም አለ፡፡ በቤት ያሉት ወገኖቹም ‹‹እንቅፋት ያገኘው ይኾን? ይሞት ይኾን?›› እያሉ እየተሳቀቁ ነው የሚያመሹት፡፡ ማምሸት እንደ ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ነው እንጂ! ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በማምሸቱ ፈጣሪውን አወቀ፡፡ ጌታን ማወቅ ብቻ ደግሞ አይበቃም፡፡ ማወቅማ አጋንንትም ያውቁታል፡፡ ከመንፈስ መወለድ ያስፈልጋል፡፡

የሰው ልጅ ዕፀ በለስን በበላ ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅነቱን ተነጥቆ ነበር፡፡ ጌታችን መጥቶ ዳግም ሰው እስከሚያደርገን ድረስ የሰይጣን ልጆች ኾነን ነበር፡፡ ከዚያም በዐርባና በሰማንያ ቀን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ተወልደናል፡፡ እግዚአብሔርን አባታችን የምንለውም ስለዚህ ነው፡፡ ከእርሱ ከተወለድንና ልጅነትን ካገኘን፣ እንደ ገና ልጅነታችንን እንዳናጣ አክብረን እንያዘው፡፡ መጀመሪያም አላወቅንበትም ነበር፡፡ አዳም ከገነት የሚወጣ አልመሰለውም ነበር፡፡ ሰይጣን አታሎታል፡፡ እኛም እንደ ገና እንዳንታለል ልጅነታችን እንዳይሰረዝ እንጠንቀቅ፡፡

የብዙዎቻችን ልጅነት ዛሬ እየተወሰደ ነው፡፡ ልጅነታችንን እያስነጠቅነው ነው፡፡ እነኤሳው እየነጠቁን ነው፡፡ ብዙዎች እንደ ያዕቆብ ልጅነታችንን ሊወስዱብን አሰፍስፈዋል፡፡ ሰይጣን እንደ አዳም ሊነጥቀን አሰፍስፏል፡፡ ኒቆዲሞስ አርጅቶ ነበር፡፡ በጥምቀትና በንስሐ ግን አዲስ ሕይወትን አግኝቶአል፤ ታድሷል፡፡ ያረጀው ሕይወቱ ለምልሟል፡፡ እኛም ዛሬ በጣም አርጅተናል፡፡ ያረጀው ሰውነታችንን በሥጋውና በደሙ በንስሐ እናድሰው፡፡ ይህ ከኾነ ነው የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርሰው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

  • ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የከምባታ፣ ሀድያ፣ ጉራጌና ሥልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በአዲስ አበባ የደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ደብር የበላይ ሓላፊ፤ በዚሁ ደብር በአስተዳዳሪነት ባገለገሉባቸው ዓመታት ካስተማሩት ትምህርተ ወንጌል የተወሰደ (መጋቢት ፳፩ ቀን ፲፱፻፹፭ .ም)፡፡

የ፲፪ኛው ሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በፎቶ

መጋቢት ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን ለ፲፪ኛ ጊዜ ያዘጋጀው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በቾ ወረዳ ቤተ ክህነት ከአዲስ አበባ ከተማ በሰባ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ቱሉ ጉጂ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዛሬው ዕለት ተካሒዷል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም ከዐሥራ ሦስት ሺሕ ሁለት መቶ አምሳ በላይ ምእመናን መሳተፋቸው ታውቋል፡፡ መርሐ ግብሩ ከሰዓታት በፊት በጸሎት የተፈጸመ ሲኾን፣ የጉባኤውን አጠቃላይ ኹኔታም በሚከተሉት ፎቶዎች ትመለከቱ ዘንድ ጋበዝናችሁ፤

img_0137

ቱሉ ጉጂ ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን

img_0275

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0348

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ

img_0317

ብፁዕ አቡነ ዳንኤል ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ

img_0092

img_0097

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

img_0103

img_0098

የጉባኤው ተሳታፊዎች ቆመው ጸሎተ ወንጌል ሲያስደርሱ

img_0290

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0237

ምክረ አበው አቅራቢ መምህራን

img_0243

img_0227

img_0271

የማኅበረ ቅዱሳን ዘማርያን የበገና ዝማሬ ሲያቀርቡ

img_0113

የመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ሰ/ት/ቤት የጎልማሶች መዘምራን መዝሙር ሲያቀርቡ

img_0213

መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ የበገና ዝማሬ ሲያቀርቡ

img_0121

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0110

img_0160

img_0326

img_0329

img_0153

img_0180

img_0169

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0216

በጉባኤው የተገኙ የቱሉ ጉጂና የአካባቢው ምእመናን በከፊል

img_0005

የጉዞው ቅድመ ዝግጅት

img_0018

img_0021

img_0012

img_0047

ጉዞ ወደ ቱሉ ጉጂ

img_0076

የቱሉ ጉጂ አካባቢ ወጣቶች መንገድ ሲያስተካክሉ

img_0078

img_0081

የመኪኖች መቆሚያ እና የጉባኤው ቦታ በከፊል ከርቀት ሲታይ

img_0122

img_0087

ምእመናን ከመኪና ወርደው ወደ ጉባኤው ሲያመሩ

img_0083

img_0132

የጉባኤው ሥፍራ በከፊል

img_0350

ጉባኤው በጸሎት ከተፈጸመ በኋላ ምእመናን ወደ ተዘጋጁላቸው መኪኖች ሲመለሱ

img_0355

img_0352

img_0353

img_0360

ኒቆዲሞስ

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

መጋቢት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም ዐውጁ፡፡ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ዅሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ሰብስቡ፤ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ፡፡ በጽዮን መለከት ንፉጾምንም ቀድሱ፤›› በማለት የዐዋጅ አጽዋማትን እንድንጾም እግዚአብሔር አምላካችን በነቢዩ ኢዩኤል ላይ አድሮ ነግሮናል (ኢዩ. ፩፥፲፬፤ ፪፥፲፭)፡፡ ከእነዚህ አጽዋማት መካከልም ዐቢይ ጾም አንዱ ነው፡፡

ይህ ጾም የጠፋውን የሰውን ልጅ ለመፈለግ፣ የሞተውን አዳምን ለማስነሣት ሰው ኾኖ ወደዚህ ዓለም የመጣው፣ ወልደ አብ ወልደ ማርያም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመብል የተጀመረውን የሞት መንገድ ለማጥፋት ሲል የጾመው ጾም ነው፡፡ እኛም አባቶቻችን በሠሩልን ሥርዓት መሠረት በዐቢይ ጾም ወራት ‹ዘወረደ› ብለን ጀምረን በዓለ ትንሣኤን እስከምናከብርበት ዕለት ድረስ ያሉትን ሰንበታት በልዩ ልዩ ስያሜ በመጥራት የተከፈለልንን ዋጋ እያሰብን ቃለ እግዚአብሔር እንማራለን፤ እንዘምራለን፤ እንጸልያለን፡፡ ከእነዚህ ሰንበታት መካከል በሰባተኛው ሳምንት የሚገኘው ወቅት ‹ኒቆዲሞስ› ይባላል፡፡

ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የነበረው ሰው ነው፡፡ የአይሁድ አለቆች አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን ‹‹ምልክት አሳየን›› እያሉ ይፈታተኑት ነበር፡፡ ጌታችን ስለ ሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ እያስረዳ ቢያስተምራቸውም እነርሱ ግን አልገባቸውም ነበር፡፡ ከዚህም አልፎ ጌታችን በተአምራቱ የታመሙትን ሲፈውስ ‹‹ሕጋችን ተሻረ›› ይሉ ነበር፡፡ በዚህ ዅሉ ተአምራትና ትምህርት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ወቅት ከአይሁድ አለቆች አንዱ ኒቆዲሞስ በቀን እንዳያደርገው አይሁድን ቢፈራ፣ አንድም ጊዜ ባያደርሰው እንደ ባልንጀሮቹ ክርስቶስን ሳይቃወም በሌሊት ወደ ጌታችን ዘንድ እየሔደ ወንጌልን ይማር ነበር፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍስ የታመሙትን በቃሉ፣ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ ኒቆዲሞስ ሰምቶ፣ ተመልክቶ በመምህርነቱ ሳይኮራ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ በልቦናው የተሳለውን እውነትን የመፈለግ ስሜት አንግቦ ከጌታው፣ ከመምህሩ ከክርስቶስ ዘንድ በሌሊት ይገሰግስ ነበር (ዮሐ. ፫፥፩)፡፡ ምስክርነቱንም እንዲህ ሲል መስጠት ጀመረ፤ ‹‹መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከኾነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና፤›› (ዮሐ. ፱፥፳፬፤ ሐዋ. ፲፥፴፰)፡፡

ይህን ምስክርነቱን በሚሰጥበት ጊዜም ጎዶሎን የሚሞላ፤ አላዋቂነት በአዋቂነት የሚለውጥ፤ ከምድራዊ ዕውቀት ወደ ሰማያዊው ምሥጢር የሚያሸጋግር አምላክ ‹‹ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም፤›› በማለት የአይሁድ መምህር ለኾነው ኒቆዲሞስ ቢያስተምረው ምሥጢሩ አልተገለጠለትም ነበርና ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?›› በማለት ጥያቄ አቅርቧል (ዮሐ. ፫፥፮፤ ፩ኛጴጥ. ፩፥፳፫)፡፡ ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፤›› (ኤፌ. ፭፥፳፮) በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ቢያስረዳውም ምሥጢሩ ከአቅሙ በላይ ስለ ኾነበት እንደምን ይቻላል? በማለት ጠይቋል፡፡

አበ ብዙኃን አብርሃም ከአምላኩ ሞገስን አግኝቶ የሰዶምና ገሞራ ጥፋት እንዳይደርስ ለመማለድ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር እንደ ነበረ፤ ኒቆዲሞስም አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምሥጢር ከአምላኩ በጠየቀ ጊዜ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- ‹‹አንተ የእስራኤል መምህራቸው ኾነህ ሳለ ይህን ነገር አታውቅምን? በምድር ያለውን ስንነግራችሁ ካላመናችሁ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለምሙሴምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀላል፡፡ ያመነበት ዅሉ ለዘለዓለም ሕያው እንዲኖር እንጂ እንዲጠፋ አይደለም ...፤›› እያለ ሰው በመብል ምክንያት የአምላኩን ትእዛዝ አፍርሶ ከእግዚአብሔር ቢለይም የሰው ልጅ ያጣውን ልጅነት ለመመለስ፣ ስመ ክርስትናን፣ ሀብተ ወልድን ለመስጠት ጌታችን መምጣቱን አስረዳው (ዮሐ. ፫፥፲፬)፡፡ ይህን የክርስቶስን የማዳን ሥራና በሥጋ መገለጥም ‹‹ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ አመከርከኒ ወኢተረከ ዐመፃ በላዕሌየ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው፤ ልቤን ፈተንኸው፡፡ በሌሊትም ጐበኘኸኝ፤ ፈተንከኝም፡፡ ምንም አላገኘህብኝም፡፡ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው፤›› (መዝ. ፲፮፥፫) በማለት ቅዱስ ዳዊት ከኒቆዲሞስ ሕይወት ጋር በማዛመድ አመሥጥሮታል፡፡

በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምሥጢሩ የተገለጸለት ኒቆዲሞስ ቀድሞ በአደባባይ ሔዶ መማርን ይፈራ እንዳልነበረ ምሥጢሩ ሲገለጽለት ግን አይሁድ ጌታችንን በሰቀሉት ዕለት ፍርኃት ርቆለት ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበር በቃ፡፡ ‹‹ወአልቦ ፍርኃት ውስተ ተፋቅሮትነ፤ ፍጹም ፍቅር ፍርኃትን አውጥቶ ይጥላል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፳፯፥፶፰፤ ፩ኛዮሐ. ፬፥፲፰)፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ያመነየተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ፣ ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል›› (ማር. ፲፮፥፮) በማለት በሰጠን ቃል ኪዳን መሠረት በአምላክነቱ አምነን የመንግሥቱ ወራሾች እንኾን ዘንድ ለኒቆዲሞስ ምሥጢሩን እንደ ገለጸ ለእኛም ይግለጽልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል አምስት  

በቴዎድሮስ እሸቱ

መጋቢት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

፯. ኒቆዲሞስ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደኅና ናችሁ? መልካም! ይኸው ዘወረደ ብለን በመጀመሪያው ሳምንት የጀመርነው ጾም ዛሬ ኒቆዲሞስ ላይ ደርሷል፡፡ ኒቆዲሞስ የሰባተኛው ሳምንት መጠሪያ ነው፡፡ ልጆች! የአይሁድ መምህር የኾነ አንድ ኒቆዲሞስ የሚባል ሰው ነበር፡፡ ይህ የአይሁድ መምህር ማታ ማታ እየመጣ ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ትምህርት ይማር ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ማታ ማታ የሚማረው ለምን መሰላችሁ ልጆች?

አንደኛ የአይሁድ መምህር ስለ ኾነ አይሁድ ሲማር እንዳያዩት ነው፡፡ እነርሱ ሲማር ካዩት ገና ሳይማር ነው እንዴ እኛን የሚያስተምረን እንዳይሉት፤ ሁለተኛ አይሁድ በክርስቶስ የሚያምኑ ሰዎችን ከአገራቸው ያባርሩ ስለ ነበር እንዳይባረር በመፍራቱ፤ ሦስተኛ ሌሊት ምንም የሚረብሽና ዐሳብን የሚሰርቅ ጫጫታ ስለሌለ ትምህርቱ እንዲገባው ነበር፡፡ እናንተስ በሌሊት ትምህርታችሁን የምታጠኑት እንዲገባችሁ አይደል ልጆች? በሌሊት ዐሳባችሁ አይበተንም፡፡

ታዲያ አንድ ቀን ማታ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔር መንግሥት ሊወርስ አይችልም›› ብሎ ለኒቆዲሞስ ስለ ጥምቀት አስተማረው፡፡ ኒቆዲሞስም ‹‹ሰው ከሸመገለ ካረጀ በኋላ እንዴት ድጋሜ ሊወለድ ይችላል?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ጌታችንም ዳግም ልደት ማለት ሰው በጥምቀት የሚያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት እንደ ኾነ፣ ሰው ተጠምቆ የእግዚአብሔር ልጅ ካልኾነ መንግሥተ ሰማያትን እንደማይወርስ አስተማረው፡፡ ኒቆዲሞስም ስለ ጥምቀት በሚገባ ተረዳ፡፡

ልጆች! በዚህ ሳምንት ከሚነገረው ከዚህ ታሪክ ዅል ጊዜ የእግዚአብሔርን ቃል መማር እንዳለብን፤ ያልገባን ነገር ካለ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ጠይቀን መረዳት እንደሚገባን እንማራለን፡፡ እናንተም እንደ ኒቆዲሞስ ቃለ እግዚአብሔር በመማር እና ስለ እምነታችሁ ያልገባሁን በመጠየቅ በቂ ዕውቀት ልትቀስሙ ይገባችኋል፡፡ ልጆች! ለዛሬ በዚህ ይበቃናል፤ ደኅና ሰንብቱ፡፡