ማቴዎስ ወንጌል

ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ 7 ካለፈው የቀጠለ

ሠ. ሰፊ ደጅ የተባለች ባለጸጋን መጽውት ድኃን ጹም ማለት ነው፡፡

ሰፊ ደጅ የተባለች ፈቃደ ሥጋ ናት ወደ ሰፊው ደጅ የሚገቡ ብዙዎች ወደ ጠባቧ ደጅ የሚገቡ ደግሞ ጥቂቶች መሆናቸው ጌታን አያስቀናውም፡፡ ምክንያቱም ጥቂት ዕንቁ ያለው ደግሞ ብዙ ወርቅ ባለው፤ ጥቂት ወርቅ ያለው ብዙ ብር ባለው፤ ጥቂት ብር ያለው ብዙ ብረት ባለው፤ ጥቂት ብረት ያለው ብዙ ሸክላ ባለው አይቀናም፡፡

6. ስለ ሐሰተኞች ነቢያት

የበግ ለምድ ለብሰው ይመጣሉ የተባሉት ነጣቂ ተኩላዎች መንፈሳውያን መስለው የሚመጡ ሥጋውያን፤ ሃይማኖታውያን መስለው የሚመጡ መናፍቃን ናቸው፡፡ ጌታችን “በውስጣቸው ግን ነጣቂዎች ተኩላዎች ናቸው፡፡” ማለቱ ቢመረምሯቸው ሰውን ከመንጋው/ ከማኅበረ ምእመናን/ መካከል እየነጠቁ ወደ ገሃነም የሚያወርዱ መሆናቸውን ሲያጠይቅ ነው፡፡ እነዚህም ወይንና በለስ የማይገኝባቸው እሾሆችና ኩርንችቶች በመሆናቸው ከፍሬያቸው እንደሚታወቁ ተናግሯል፡፡ ይህም “ሥራቸውን አንሠራም ትምህርታቸውን ግን ብንማር ምን ዕዳ ይሆናል? ትሉኝ እንደሆነ ከመናፍቅ መምህር ሃይማኖት፣ ከሐሰተኛ መምህር እውነተኛ ትምህርት ቃል አይገኝም ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ወይን ወይንን ኮሶ ደግሞ ኮሶን ያፈራል እንጂ ወይን ኮሶን፣ ኮሶ ደግሞ ወይንን አያፈራም፡፡ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ተቆርጦ ወደ እሳት እንዲጣል መናፍቃንንም ሥላሴ በገሃነም እሳት ፍዳ ያጸኑባቸዋል፡፡

ጌታችን ከዚህ አያይዞ “ሁሉ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ ይሉሃል፤ ታዲያ ወደ መንግሥትህ የሚገባውንና የማይገባውን በምን እናውቃለን? ትሉኝ እንደሆነ የሰማይ አባቴን ፈቃድ የሠራ ይገባል እንጂ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ የሚለኝ ሁሉ ወደ መንግሥተ ሰማያት አይገባም፡፡ በዚያን ጊዜም ከቶ አላውቃችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ” ብሏል፡፡ ትንቢት መናገርማ በለዓምም ትንቢት ተናግሯል፡፡ ዘኁ.20፡4፣17፡፡ አጋንንትን ለማውጣት ደቂቀ አስቄዋ አጋንንትን አውጥተዋል የሐዋ.19፡14፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ስለእነዚህ ሰዎች ሲናገር “እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኰለኞች ሠራተኞች ናቸውና፡፡

 

ይህም ድንቅ አይደለም፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና፡፡ እንግዲህ አገልጋዮቹ ደግሞ የጸድቅን አገልጋዮች እንዲመስሉ ራሳቸውን ቢለውጡ ታላቅ ነገር አይደለም፤ ፍጻሜአቸውም እንደ ሥራቸው ይሆናል፡፡” ሲል አስጠንቅቋል 2ኛ ቆሮ.11፡13-15፡፡ በኦሪቱም “በመካከልህም ነቢይ ወይም ሕልም አላሚ ቢነሣ ምልክትም ተአምራትም ቢሰጥህ እንደነገረህም ምልክቱ ተአምራቱም ቢፈጸም እርሱም ሄደን የማታውቃቸውን ሌሎች አማልክት እንከተል እናምልካቸውም ቢልህ፣ አምላካችሁን እግዚአብሔርን በፍጹም ልባችሁ በፍቡጸምም ነፍሳችሁ ትወድዱት እንደሆነ አምላካችሁ እግዚአብሔር ሊፈትናችሁ ነውና የዚያን ነቢይ ቃል ወይም ያን ሕልም አላሚ አትስሙ” ተብሏል ዘዳ.13፡1-3፡፡

7. በዓለት ላይ ስለተመሠረተውና በአሸዋ ላይ ስለተሠራው ቤት፡፡

ጌታችን በዚህ በመጨረሻው አንቀጽ ላይ ቃሉን ሰምቶ እንደ ቃሉ የሚኖረውን ልባም ሰው በዓለት ላይ በተመሠረተ ቤት መስሎታል፡፡ በዓለት ላይ የተመሠረተውም ቤት ዝናብ ወርዶ በጐርፍ፣ ነፋስ ነፍሶ በነፋስ ተገፈቶ አልወደቀም ብሏል፡-

ዓለት ለኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወልድ ዋሕድ ብለው ለሚታመንበት ሁሉ መንፈሳዊ መጠን የሚገኝበትና መንፈሳዊ መሠረት የሚቆምበት ዓለት ነው 1ኛ.ቆሮ.10፡4፡፡ ለማያምኑት ግን የማሰናከያ ዓለት ተብሎአል ኢሳ.8፡14፣ 1ኛ.ጴጥ.2፡8፡፡ ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስንም ዓለት ነህ ብሎታል ማቴ.16፡16-18፡፡ ዝናም ነፋስ የባለ መከራ ነው፡፡

ከምሳሌው የምንረዳው ዋነኛው ምሥጢር እንደሚከተለው ነው፡፡

  1. ሃይማኖትን በበጎ ልቡና ይዘው እንደ ቃሉ የሚኖሩ ሰዎች ዓላውያን መኳንንት መከራ ቢያጸኑባቸው፣ ቤተሰቦቻቸውም ንጉሥ የወደደውን ዘመን የወለደውን ይዛችሁ ኑሩ ብለው ቢገፋፏቸው ምንም ይሁን ምን በክህደት አይወድቁም፡፡ እነዚህ ሃይማኖታቸውንና ምግባራቸውን እንደ ኢዮብ ባለ ሰውነት ይዘው የሚኖሩ ሰዎች የልጅ ሞት፣ የሀብት ውድመት እና የአልጋ ቁራኛ የሚያደርግ ደዌ ቢያጋጥማቸውም በምስጋና ይኖራሉ እንጂ ሃይማኖታቸውን አይለውጡም፡፡

  2. ሃይማኖትን በበጎ ልቡና ይዘው እንደቃሉ የሚኖሩ ሰዎች በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን ስለሚኖሩ አጋንንት በጎ አስመስለው ገፋፍተው ከክፉ ወጥመድ አይጥሏቸውም፡፡ እንዲህ ዓይነቶቹን ሰዎች አጋንንት በአሳብ ይዋጓቸዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች እንደ እንጦንስ እንደ መቃርስ ንጽሕ ጠብቀን ከሴት ርቀን እንኖራለን የሚል አሳብ ሲመጣባቸው ቸኩለው አይወስኑም፡፡ ፈጥነው ለመምህረ ንስሐቸው ይነግራሉ፡፡ እነርሱም ቆዩ ይሏቸዋል፡፡ ደግሞም እንደ እንጦንስ እንደ መቃርስ ንጽሕ ጠብቀን ከሴት ርቀን መኖር አይቻለንም፤ እንደ ኢዮብ እንደ አብርሃም በሕግ ጸንተን እንኖራለን የሚል አሳብም ሲመጣባቸው ለመምህረ ንስሐቸው ይነግሩታል፡፡ እርሱም የሰይጣን ፆር እንደሆነ ዐውቆ ቆዩ ይላቸዋል፡፡ በመጨረሻም አጋንንት ሁሉም አይሆንልንም አሰኝተው ሃይማኖቱን ለማስለቀቅ ይገፋፏቸዋል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህ ሰዎች በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን በእግዚአብሔር ቃል ላይ ተመሥርተው ስለሚኖሩ አይወድቁም፡፡

ጌታችን ቃሉን ሰምቶ እንደቃሉ የማይኖረውን ሰው ደግሞ በአሸዋ ላይ በተሠራ ቤት መስሎታል፡፡ ይህንንም ቤት ጐርፍ ነፋስ በገፉት ጊዜ አወዳደቁ የከፋ ሆኗል፡፡ እነዚህም ሃይማኖታቸውን በበጎ ልቡና ያልያዙ ሰዎች ናቸው፡፡ እንደ ቃሉ ይኖሩ መከራውን ተሰቅቀውና በወሬ ተፈትነው በክህደት ይወድቃሉ፡፡ ለጊዜው በጌታ ዐፀደ ወይን በቤተ ክርስቲያን ቢበቅሉም ፀሐይ ሲወጣ ግን ይጠወልጋሉ ማቴ.13፡5-6፣20፡፡

ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን አስተምህሮ ከፈጸመ በኋላ ሕዝቡ ትምህርቱን አደነቁ፡፡ ምክንያቱም እንደ ጻፎቻቸው ሳይሆን እንደ ባለሥልጣን ያስተምራቸው ነበረ፡፡ ይህም ማለት ንጉሥ እንዲህ ይላችኋል እንደሚሉ ሹማምንት ያይደለ እኔስ እላችኋለሁ እያለ አስተምሯቸዋልና ነው፡፡

“ከመዝ ይቤ እግዚአብሔር” እንደሚሉ ዐበይት ነቢያት ያይደለ ሠራዔ ሕግ እንደ መሆኑ እኔስ አላችኋለሁ እያለ አስተምሯቸዋል፡፡ “ከመዝ ይቤ ሙሴ፤ ከመዝ ይቤ ሳሙኤል፣” እንደሚሉ ደቂቀ ነቢያት ያይደለ ፈጻሜ ሕግ እንደመሆኑ አስተምሯቸዋል፡፡

“ከባድና አስቸጋሪ ሸክም ተብትበው በሰው ትከሻ ይጭናሉ እነርሱ ግን በጣታቸው ስንኳ ሊነኩት አይወዱም፡፡” እንዳላቸው ጸሐፍት ፈሪሳውያን ያይደለ እንደ ጌትነቱ በርኅራኄ አስተምሯቸዋል፡፡ ከወርቁ የጠራውን፣ ከግምጃ ያማረውን፣ ከላሙ የሰባውን እንደሚሉ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ያይደለ የቸርነቱን ሥራ እየሠራ አስተምሯቸዋል፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ሰኔ 1989 ዓ.ም.

dn tolosa 2

የ2006 ዓ.ም. የግቢ ጉባኤያት ፍሬዎች ዋንጫና ሜዳልያቸውን ለማኅበረ ቅዱሳን አስረከቡ

ነሐሴ 28 ቀን 2006 ዓ.ም

እንዳለ ደምስስ

  • ለኔ ይህ ዋንጫ ትልቁ ሀብቴ ነው፤ ሰው ሀብቱ ባለበት ልቡ ይኖራልና ዋንጫውን ሳስብ ማኅበሬን አስባለሁ፤ ተግቼም እንዳገለግል ያደርገኛል፡፡ የማልተካውን ሀብቴ ለማይተካው የማኅበሬ አገልግሎት መሥጠት ለኔ ታላቅ ደስታ ነው፡፡ /ዲያቆን ቶሎሳ ታዬ/

dn tolosa 2ማኅበረ ቅዱሳን በ2006 ዓ.ም. ከዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ግቢ ጉባኤያት በርካታ ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡ በዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ቆይታቸው ያስመዘገቡት ውጤት ከፍተኛ በመሆኑም በርካቶች የተሸለሙትን ዋንጫና ሜዳልያ በሥጦታ ለማኅበሩ በማበርከት ላይ ይገኛሉ፡፡

ከእነዚህ ተመራቂዎች መካከል በወሎ ዩኒቨርስቲ ደሴ ካምፓስ በእንስሳት ሳይንስ ትምህርት የተመረቀው ዲያቆን ቶሎሳ ታዬ አንዱ ነው፡፡ በዩኒቨርስቲ ቆይታው የግቢ ጉባኤው ሰብሳቢ የነበረ ሲሆን፤ በርካታ ውጣ ውረዶችን ተቋቁሞ 4 ነጥብ እና 18A+ በማምጣት የዩኒቨርስቲው አጠቃላይ አሸናፊ በመሆን ዋንጫና ሜዳልያ ለመሸለም በቅቷል፡፡

የተሸለመውን ዋንጫ በማኅበረ ቅዱሳን ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በመገኘት ለማኅበሩ ሲያስረክብ፤ ሜዳልያውን ደግሞ ከሕፃንነት ጀምሮ ሲያገለግልበት ለነበረው ለምእራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት በለስ ወረዳ ዳቡስ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጥለት በጉባኤው ላይ ለተገኘው የወረዳ ማእከሉ ተወካይ እንዲያደርስለት አስረክቧል፡፡dn tolosa 3

ዲያቆን ቶሎሳ ዋንጫና ሜዳልያውን ካበረከተ በኋላ ባስተላለፈው መልእክት “ወሎ ዩኒቨርስቲ ስገባ ማኅበሩ ባዘጋጀው የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል መርሐ ግብር ላይ ተገኝቼ የጉባኤ ቃና ጋዜጣን ገዝቼ ዶክተር እንግዳ በጅማ ዩኒቨርስቲ ሲመረቁ ያገኙትን ሜዳልያ ለማኅበሩ እንደሰጡ አነበብኩ፡፡ ወዲያውኑ እኔም ለዚህ ክብር እግዚአብሔር ቢያበቃኝ ያገኘሁትን ሽልማት ለማኅበሩ ለመሥጠት ቃል ገባሁ፡፡ እግዚአብሔርም ምኞቴን አሳካልኝ፡፡ ለኔ ይህ ዋንጫ ትልቁ ሀብቴ ነው፤ ሰው ሀብቱ ባለበት ልቡ ይኖራልና ዋንጫውን ሳስብ ማኅበሬን አስባለሁ፤ ተግቼም እንዳገለግል ያደርገኛል፡፡ የማልተካውንና በሕይወቴ አንድ ጊዜ ብቻ የማገኘውን ሀብቴ ለማይተካው የማኅበሬ አገልግሎት መሥጠት ለኔ ታላቅ ደስታ ነው” ብሏል፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ላይ የተገኙት ፕሮፌሰር ጥላሁን ተሾመ ዋንጫውንና ሜዳልያውን ከዲያቆን ቶሎሳ በመረከብ ለማኅበሩ ሰብሳቢና ለወረዳ ማእከሉ ከሠጡ በኋላ የተሰማቸውንdn tolosa 4 ደስታ ሲገልጹ “ይህ ውጤት በሀገራችን በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ታሪክ በጥቂቶች ብቻ ሊመዘገብ የሚችል ከፍተኛ ውጤት ነው፡፡ ካስመዘገበው ውጤት ይልቅ ደግሞ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ በሕይወቱ አንድ ጊዜ ብቻ ሊገጥመው የሚችለውን እድል ውድ ሥጦታ ለማኅበሩ መሥጠቱ አስደንቆኛል፡፡ ብዙዎቻችንንም ያስተማረ ነው፡፡ ወደፊትም በሕይወቱ የተሳካ ጊዜ አሳልፎ ለሌሎች አርአያ እንዲሆን እመኛለሁ” ብለዋል፡፡

የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ሰሙ ሥጦታውን ከተቀበሉ በኋላ የተሰማቸውን ሲገልጹም “ይህ ሥጦታ ጠቅላላ ጉባኤውንና ማኅበራችንን ወክዬ ነው የተቀበልኩት፡፡ እኛም ይህንን ታሪክና ሀብት ለመጠበቅ፤ አገልግሎቱንም ለማገዝ አብሮንም በአገልግሎት እንዲዘልቅ የምንችለውን ሁሉ እናደርጋለን፤ አደራውንም ተቀብለናል” ብለዋል፡፡

የደሴ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን ጸሐፊ ዲያቆን ሰሎሞን ወልዴ በሠጠው ምሥክርነትም ዲያቆን ቶሎሳ የግቢ ጉባኤው ሰብሳቢ ሆኖ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች መሠብሠቢያ አዳራሽ በማሠራት፤ በአቅራቢያው ቤተ ክርስቲያን በማሳነጽና በመምራት፤ የሥራ አስፈጻሚና በዩኒቨርስቲው የሚካሔዱ አገልግሎቶችን በማስተባበር ተጠምዶ ስለሚውል ለዚህ ክብር ይበቃል የሚል ግምት አልነበረንም፡፡ ሆኖም ለግቢ ጉባኤውና ማኅበሩ ለሚያከናወነው አገልግሎት አርአያ እንዲሆን ስናበረታታው ቆይተናል፡፡ እግዚአብሔር መልካም ነገር አደረገልን፡፡ በወረዳ ማእከላችን ከሚገኙ 8 ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውሰጥ ከተዘጋጁት ሜዳልያዎች ሰባቱን የወሰዱት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ናቸው ብሏል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ በወልዲያ ዩኒቨርስቲ በደሴ ካምፓስ በትምህርትና እቅድ አስተዳደር ከፍተኛ ውጤት በማምጣት ሜዳልያ ተሸላሚ የሆነው አሰፋ አደፍርስ፤ በደብረ ታቦርdn tolosa 5 ማእከል የፈቃደ እግዚእ ኮሌጅ ተመራቂዎቹ ዘውዴ ደሴና ከፍያለው ስመኝ ለማኅበሩ ማእከላት ሜዳልያቸውን አስረክበዋል፡፡ እንዲሁም ከሐረር የሜንሽን አግሮ ቴክኒካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ የሆነው ቃል ኪዳን ዓለሙ ሜዳልያውን በማእከሉ በኩል ለኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጥለት አበርክቷል፡፡

guba 2006 24 1

ማኅበረ ቅዱሳን 11ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሔደ

ነሐሴ 27 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

guba 2006 24  1የማኅበረ ቅዱሳን 11ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ነሐሴ 24 እና 25 ቀን 2006 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕንፃ መሰብሰቢያ አዳራሽ የሀገር ውስጥና የውጭ ማእከላት፤ የወረዳ ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች፤ የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አሥፈፃሚ አባላት፤ የማኅበሩ ልዩ ልዩ ክፍል ተጠሪዎች፤ ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት አካሄደ፡፡

guba 2006 24  2የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፈዎች ከነሐሴ 23 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል የተደረገላቸው ሲሆን፤ የጸሎት፤ የመርሐ ግብር ትውውቅና ማስገንዘቢያ በጠቅላላ ጉባኤው አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ በዶክተር ዳኝነት ይመኑ ቀርቧል፡፡ የእጽበተ እግር መርሐ ግብርም ተከናውኗል፡፡

ነሐሴ 24 ቀን 2006 ዓ.ም. ጠዋት ጉባኤው በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክትና የማኅበሩ የሁለት ዓመታት የዕቅድ ክንውን ዘገባ በማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ ቀርቧል፡፡ በቀረበው ዘገባም የስብከተ ወንጌል guba 2006 24  3አገልግሎት ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማትን በማጠናከር ረገድ፤ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት ለማጠናከር ከአህጉረ ስብከቶች ጋር እየተሠሩ ስለሚገኙ በርካታ ተግባራት ፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያትን በማጠናከር ረገድ፤ የማኅበሩን ተቋማዊ አቅም ለማሳደግ እየተሠሩና በመሠራት ላይ የሚገኙ ሥራዎች፤ ያጋጠሙ ችግሮችና የተወሰዱ መፍትሔዎችን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

የ2005 ዓ.ም. የማኅበሩ የሒሳብ ሪፖርት በማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፤ እንዲሁም የኦዲትና ኢንስፔክሽን ሪፖርት በአቶ የሺዋስ ማሞ የቀረቡ ሲሆን፤ የ2004 ዓ.ም. እና የ2005 ዓ.ም. የሁለቱን ዓመታት የኦዲት ሪፖርት ዓለም አቀፍ እውቅና ባለው የውጭ ኦዲተር በማስመርመር በድርጅቱ ሓላፊ የኦዲት ሪፖርቱ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም በቀረቡት ሪፖርቶች ላይ ውይይት በማካሔድ አጽድቋቸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ከ1996 ዓ.ም. በማኅበሩ ሥራ አመራር ጉባኤ ጸድቆ ሲሠራበት የቆየው የማኅበረ ቅዱሳን ጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅትና የምርጫ ሥነ ሥርዓት መመሪያ በአሁኑ ወቅት ማኅበሩ ከደረሰበት የእድገት ደረጃና የአገልግሎት ስፋት አንጻር ሊጣጣም ባለመቻሉ መመሪያውን ማሻሻል በማስፈለጉ በሥራ አመራር ጉባኤው የተሰየመው ኮሚቴ የጥናቱን ረቂቅ ለጠቅላላ ጉባኤው አቅርቧል፡፡ በቀረበው የጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅትና የምርጫ ሥነ ሥርዓት መመሪያ ማሻሻያ ረቂቅ ላይ በተሳታፊዎች ውይይት ተካሒዶበት ለማሻሻያ የሚጠቅሙ በርካታ ሃሳቦች ተነስተዋል፡፡ አጥኚ ኮሚቴውም የቀረቡለትን ገንቢ ሃሳቦች በማካተት ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ እንዲያቀርብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤውም የቀረበለትን ማሻሻያውን መርምሮ ውሳኔ እንዲያሳልፍ ጠቅላላ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፡፡

guba 2006 24  5ጠቅላላ ጉባኤው በሁለተኛ ቀን ውሎው ብፁዕ አቡነ ሰላማ የምሥራቅ ሐረርጌ ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን፤ በሰጡት ቃለ ምእዳን “ያሰባሰባችሁ እግዚአብሔር ነው፤ በእናንተ ኃይል አልተሰባሰባችሁም፡፡ ፈቃደ እግዚአብሔር አስነስቷችኋልና በጉዟችሁ ፈተና ሊገጥማችሁ ይችላል፡፡ ፈተና ደግሞ ያለ ነው፤ ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም፡፡ ከሚወድህ ይልቅ የሚጠላህ ይጠቅምሃል እንዲሉ አባቶቻችን ካልተፈተኑ ክብር አይገኝም፡፡ በአገልግሎታችሁ እንደጸናችሁ ሳትበሳጩ ልትጓዙ ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ማኅበሩን ይባርክ” ብለዋል፡፡

በቀጣይነትም ጠቅላላ ጉባኤው የግቢ ጉባኤያት የእድገትና ውጤታማነት መርሐ ግብር ስልታዊ አቅጣጫና እቅድ በሚቀጥሉት ዐሥር ዓመታት /ከ2007 – 2017/፤ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ እቅድ አጋማሽ ዘመን ግምገማ በሚሉ ሁለት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ተወያይቷል፡፡

የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት እድገትና ውጤታማነት ስልታዊ አቅጣጫና እቅድ ለሚቀጥሉት ዐሥር ዓመታት ተግባራዊ ለማድረግ በቀረበው ጥናት ላይ ተሳታፊዎችን በ23 ቡድን በመከፋፈል ውይይት ተደርጓል፡፡ በቡድን ውይይቱ የተነሱ በርካታ ነጥቦችን በግብአትነት በመያዝ በዋናነት በተያዙ የጥናቱ ክፍሎች ተከፋፍለዋል፡፡ በዚህም መሠረት የተነደፉት ግቦች፤ ዓላማዎች፤ ስልቶችና ተግባራት ስልታዊ እቅዱን ከማሳካት አንጻር፤ የግቢ ጉባኤያትን ስልታዊ እቅድ ከማስፈጸም አንጻር መዋቅራዊ አደረጃጀቱ ምን መምሠል እንዳለበት፤ በቀረበው ሰነድ ላይ የተጠቀሰው ገንዘብ ማግኛ ስልትና ምንጭ ተገቢ መሆኑን መመልከት፤ የግቢ ጉባኤያት ሁኔታ በአገልግሎት ክፍሎች በዋና ጉዳይነት አካቶ መሥራት በሚሉት ነጥቦች ሥር ለይቶ በመያዝ ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ ለውሳኔ በማቅረብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤው የቀረበለትን ሠነድ መርምሮ በማጽደቅ ተግባራዊ እንዲሆን ጠቅላላ ጉባኤው ወስኗል፡፡

guba 2006 24  4የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ እቅድ አጋማሽ ዘመን ግምገማ በማስመልከት ከጥር 2005 ዓ.ም. እስከ ግንቦት 2006 ዓ.ም. የተከናወኑትን ሥራዎች ተገምግመው ሓላፊነት በወሰደው አጥኒ ቡድን ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርበዋል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም ውይይት በማድረግ አቅጣጫ ሰጥቷል፡፡ በዚህም መሠረት ቀጣይ አፈጻጸማችን ምን መምሰል እንደሚገባው ለማሳየት ቢሞከር፤ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ከስትራቴጂክ እቅዱ አንጻር አስታርቆ ማስኬድ፤ የክብደት አሥራር ሥርዓቱን ግልጽ ማድረግ፤ ግምገማው ከስልታዊ እቅዱ ጋር በደንብ ቢታይ የሚሉና ሌሎችም ጠቃሚ ነጥቦች ከተካተቱት ውስጥ ይገኙበታል፡፡ የጥናት ቡድኑ ከጠቅላላ ጉባኤው በተሰጡት ሃሳቦች መሠረት የግምገማውን ውጤት በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ እንዲያቀርብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤውም አጽድቆ በሚመለከታቸው አካላት ተግባራዊ እንዲደረግ እንዲያስተላልፍ ውሳኔ ላይ ተደርሷል፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ማጠቃለያ ላይም የዝግጅቱ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዶክተር ዳኝነት ይመኑ ለጉባኤው መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉ ድርጅቶችንና በጎ አድራጊ ምእመናንን በዝርዝር በመጥቀስ በጠቅላላ ጉባኤው ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ እንዲሁም የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፊዎች ጉባኤው እሰኪጠናቀቅ ድረስ ላሳዩት አርአያነት ላለው ሥነ ምግባር የተላበሰ ታዛዥነትና ተሳትፎ አመስግነዋል፡፡

በጉባኤው ማጠቃለያም ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፊዎች ለሦስት ቀናት በትዕግስት፤ በታዛዥነትና በንቁ ተሳታፊነት ለአገልግሎት ጠቃሚ የሆኑ ሃሳቦችን በማምንጨት ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ከ650 በላይ ተወካዮች ተሳትፈዋል፡፡

 

ማቴዎስ ወንጌል

ነሐሴ 22 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ 7

በማቴዎስ ወንጌል በምዕራፍ ሰባት ውስጥ የሰውን ነውር ከማጋነን ይልቅ የራስን ባሕርይ መቆጣጠር አስፈላጊ መሆኑን በሰፊው እንማራለን፡፡ ዋና ዋና አሳቦቹም የሚከተሉት ናቸው፡፡

  1. ስለ ፍርድ

  2. የተቀደሰውን ለውሾች መስጠት እንደማይገባ

  3. ዕንቁን በእሪያዎች ፊት ማስቀመጥ እንደማይገባ

  4. ስለ ልመና

  5. ስለ ጠባቧ ደጅ እና ስለ ሰፊው ደጅ

  6. ስለ ሐሰተኞች ነቢያት

  7. በዐለት ላይ ስለተመሠረተውና በአሸዋ ላይ ስለተመሠረተው ቤት

1. ስለ ፍርድ፡-

ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሌላው ላይ መፍረድ እንደማይገባ አስተምሯል፡፡ በዚህ ትምህርቱም “እንዳይፈረድባችሁ አትፍረዱ፤ በምትፈርዱበት ፍርድ ይፈረድባችኋልና፡፡” ብሏል፡፡ ይህም ንጹሕ ሳትሆኑ ወይም ሳትሾሙ ብትፈርዱ ይፈረድባችኋል ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ተሾመው የፈረዱ አሉና፡፡ ለምሳሌ፡- ሙሴ በስለጰዓድ፣ ኢያሱ በአካን፣ ቅዱስ ጴጥሮስ በሐናንያና ሰጲራ፣ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ በበርያሱስ ፈርደዋል ዘኁ.27፡1-15፣ 36፡2-12፣ ኢያ.7፡1-26፣ የሐዋ.5፡1-11፣ 13፡4-12፡፡ አንድ ሰው ንጹሕ ሳይሆን በፈረደው ፍርድ እንደሚፈረድበት ከንጉሡ ከዳዊት ሕይወት መማር ይቻላል 2ኛ ሳሙ.12፡1-15፡፡

ቅዱስ ጳውሎስም በመልእክቱ “ስለዚህ አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ የምታመካኘው የለህም፤ በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኰንናለህና፤ አንተው ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህና፡፡ እንደዚህም የሚያደርጉት ላይ የእግዚአብሔር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ አንተም እንደዚህ በሚያደርጉ የምትፈርድን ያንን የምታደርግ ሰው ሆይ አንተ ከእግዚአብሔር ፍርድ የምታመልጥ ይመስልሃልን?” ብሏል፡፡

ለዚህም ነው ጌታችን በወንድምህ ዓይን ያለውን ጉድፍ ከማውጣትህ በፊት በዓይንህ የተጋረድውን ምሰሶ አስወግድ ያለው፡፡ ጉድፍ የተባሉት ጥቃቅን ኃጢአቶች ሲሆኑ ምሰሶ የተባሉት ደግሞ ታላላቅ ኃጢአቶች ናቸው፡፡ ይህም ጥቃቅኗን ኃጢአቶች እየተቆጣጠርክ በባልንጀራህ ከመፍረድህ በፊት አንተው ራስህ ታላላቆቹን ኃጢአቶችህን በንስሐ አስወግደህ እንዳይፈረድብህ ሁን ማለት ነው፡፡

እዚህ ላይ የባልንጀራ ኃጢአት ትንሽ የራስ ኃጢአት ደግሞ ትልቅ የተባለበት ምክንያት ሰው የባልንጀራውን ኃጢአት የሚያውቀው በከፊል የራሱን ግን የሚያውቀው ሙሉ በሙሉ በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ ከዚህ ተላልፎ እገሌ እንዴት ኃጢአት ይሠራል ብሎ በሌላው መፍረድ ፈሪሳውያንን መሆን ነው ማቴ.23፡1-39፡፡

2. የተቀደሰውን ለውሾች መስጠት እንደማይገባ፡-

ጌታችን “በእግራቸው እንዳይረግጡት፣ ተመልሰውም እንዳይነክሱአችሁ፣ የተቀደሰውን ለውሾች አትስጡ” ብሏል፡፡ ለመሆኑ ውሾች የተባሉት ሥራይን የሚያደርጉ፣ ሴሰኞች፣ ነፍሰ ገዳዮች ጣዖትን የሚያመልኩና የሐሰትን ሥራ ሁሉ የሚወዱ ናቸው ራእ.22፡15፡፡ እነዚህም ከቶ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገቡም፡፡ ዕድል ፈንታቸው ጽዋ ተርታቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፡፡ ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው ራእ.21፡8፣ 27፡ 1ኛ.ቆሮ.6፡9-10፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀደሰውን ለውሾች አትስጡ ማለቱ የተቀደሰውን ሥጋዬንና የከበረውን ደሜን ለእነዚህ አታቀብሉ ማለቱ ነው፡፡ አንድም ቋንቋችን ከቋንቋችሁ፣ መጽሐፋችን ከመጽሐፋችሁ አንድ ነው፡፡ እያሉ እንዳይከራከሯችሁና እንዳይነቅፏችሁ ሃይማኖታችሁን ለመናፍቅ አትንገሩ ማለቱ ነው፡፡ መናፍቃንም ውሾች ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ውሾች የተባሉ ወደ ቀደመ ግብራቸው የሚመለሱ በደለኞች ናቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችንን እና መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ከማወቅ ጋራ ከዚህ ዓለም ኃጢአት ከተለዩ በኋላ ዳግመኛ በእርስዋ ተጠላልፈው የሚሸነፉ ከሆነ ከቀደመ በደላቸው ይልቅ የኋላው በደላቸው የጸና የከፋ ይሆናል፡፡ አውቀዋት ከተሰጠቻቸው ከቅድስት ትእዛዝ ከሚመለሱ ጥንቱኑ የጽድቅን መንገድ ባላወቋት ይሻላቸው ነበር፡፡

 

ምክንያቱም እንደ ውሻ ወደ ትፋት መመለስ ነውና ብሏል 2ኛ.ጴጥ.2፡20-22፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሰላም የሚያውኩ ሰዎችም ውሾች ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ሰዎች ጺፍላቸው በኒያ ለከፍካፎች መናፍቃን እወቁባቸው ብሏቸዋል ፊል3፡2፡፡ አንድም የተቀደሰ የተባለ ሥጋውና ደሙ ነው፡፡ ስለሆነም ከኃጢአት ለመመለስ ላልወሰኑ በደለኞችና በክህደት ለጸኑ መናፍቃን ሥጋውንና ደሙን ማቀበል አይገባም፡፡

3. ዕንቁን በእሪያዎች ፊት ማስቀመጥ እንደማይገባ፤

ጌታችን “ዕንቁዎቻችሁን በእሪያዎች ፊት አትጣሉ” ያለበትም ምክንያት አለው፡፡ ከአገራቸው ቀን ዋዕየ ፀሐይ ይጸናል፡፡ ሌሊት ዕንቁ ከተራራ ላይ አኑረው የሚጽፍ ሲጽፍ፣ አውሬ የሚያድንም ሲያድን ያድራል፡፡ እሪያ /አሳማ/ መልከ ጥፉ ነው፡፡ በዕንቁው አጠገብ ሲሄድ የገዛ መልኩን አይቶ ደንግጦ ሲሄድ ሰብሮት ይሄዳል፡፡

ዕንቁ የጌታ እሪያ የአይሁድ ምሳሌ ናቸው፡፡ በገዛ ኃጢአታቸው ቢዘልፋቸው የዕንቁ መስተዋት ሆኖ መልከ ጥፉ ኃጢአታቸውን ቢያሳያቸው ጠልተው ተመቅኝተው ገድለውታል፡፡ አንድም እሪያ የተባሉ ወደ ቀደመ ኃጢአታቸው የሚመለሱ ሰዎች ናቸው፡፡ “የታጠበች እሪያ በጭቃ ለመንከባለል ትመለሳለች እንደሚባል እውነተኞች ምሳሌዎች ሆኖባቸዋል” 2ኛ.ጴጥ.2፡22፡፡

አንድም እሪያዎች የአጋንንት ማደሪያዎች ሆነው ወደ እሳት ባሕር ለሚገቡ ሰዎች ምሳሌዎች ናቸው ማቴ.8፡32፡፡ አንድም እሪያዎች የተባሉ መናፍቃን ናቸው፡፡ ስለሆነም ዕንቁ የሆነ ሃይማኖታችንን፣ ሥርዓታችንን፣ ታሪካችንን እና ትውፊታችንን በእነርሱ ፊት ልናቀርብ አይገባንም፡፡

4. ስለ ልመና፡-

“ለምኑ ይሰጣችሁማል፡፡” ጌታችን እንዲህ ማለቱ የበቃውንና ያልበቃውን በምን እናውቀዋለን ትሉኝ እንደሆነ “ለምኑ ይሰጣችኋል” ማለቱ ነው፡፡ ለምነው ያገኙ ዮሐንስ ዘደማስቆና ድሜጥሮስ የበቃና ያልበቃ ለይተው ያቀብሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም መንፈሳዊ ሰው ሁሉን ይመረምራልና 1ኛ.ቆሮ.2፡15፡፡ ፈልገው ያገኙና አንኳኩተው የተከፈተላቸው ሰዎች ብዙዎች በመሆናቸውም “የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፣ የሚፈልገውም ያገኛል፣ መዝጊያንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል” አለ፡፡ ከቀደሙ ሰዎች አብርሃም ከኳላ ሰዎች ደግሞ ሙሴ ጸሊም በፀሐይ በሥነ ፍጥረት ተመራምረው አምነዋል፡፡ በክርስቶስ ቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ በመለመኑ በመፈለጉ እና በማንኳኳቱ የገነት በር ተከፍቶለታል፡፡ “ጌታ ሆይ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ አለው፡፡ ኢየሱስም እውነት እልሃለሁ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ አለው” ሉቃ.23፡42፡፡

በተጨማሪም፡- ለባሕርያችሁ ክፋት ጥመት የሚስማማችሁ ስትሆኑ እናንተ ለልጆቻችሁ በጎ ነገርን የምታደርጉላቸው ከሆነ ቸርነት የባሕርይ የሚሆን ሰማያዊ አባታችሁማ በጎ ነገርን ለሚለምኑት እንደምን በጎ ነገርን ያደርግላቸው ይሆን አላቸው፡፡

5. ስለ ጠባቧ ደጅ እና ሰፊው ደጅ፡-

ሀ/ ወደ ሕይወት የምትወስድ ጠባብ ደጅ እና ቀጭን መንገድ የተባለች ሕገ ወንጌል ናት፡፡ ምክንያቱም “ቀኝ ጉንጭህን በጥፊ ለሚመታህ ሁሉ ሁለተኛውን ደግሞ አዙርለት፤ እንዲከስህም እጀ ጠባብህንም እንዲወስድ ለሚወድ መጐናጸፊያህን ደግሞ ተውለት፤ ማንም ሰው አንድ ምዕራፍ ትሔድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሒድ፡፡ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፣ የሚረግሙአችሁንም መርቁ፣ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፣ ስለሚያሳድዱአችሁም ጸልዩ፤ ትላለችና፡፡

ለ/ ጠባብ ደጅና ቀጭን መንገድ የተባለች ባለጸጋን ጹም ድኃን መጽውት ማለት ነው፡፡

ሐ/ ጠባብ በር የተባለች ፈቃደ ነፍስ ናት

መ/ ወደ ጥፋት የሚወስድ ሰፊ ደጅና ትልቅ መንገድ የተባለች ኦሪት ናት፡፡ ምክንያቱም የገደለ ይገደል፣ ዓይን ያጠፋ ዓይኑ ይጥፋ ጥርስ የሰበረ ጥርሱ ይሰበር፣ እጅ የቆረጠ እጁ ይቆረጥ፣ እግር የሰበረ እግሩ ይሰበር፣ ያቃጠለ ይቃጠል፣ ያቆሰለ ይቁሰል፣ የገረፈ ይገረፍ ትላለችና ዘጸ.21፡23፣ ማቴ.5፡38፡፡

ይቀጥላል

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ሚያዚያ 1989 ዓ.ም. 

atens 01

በግሪክ አቴንስ ዐውደ ርእይ ተካሔደ

ነሐሴ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

አውሮፓ ማእከል

atens 01በግሪክ አቴንስ ምክሓ ደናግል ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤና ሰንበት ትምህርት ቤት ከማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል ጋር በመተባበር ከነሐሴ 9 እስከ 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ዐውደ ርእይ ተካሔደ፡፡

ለተከታታይ ሦስት ቀናት የቆየው ዐውደ ርእይ በበርካት ምእመናን የተጎበኘ ሲሆን፤ የቤተ ክርስቲያን ጥንታዊ ታሪክ፣ የገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅታዊ ሁኔታ፣ የማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረትና መንፈሳዊ አገልግሎት በተመለከተ ገለጻ ተደርጓል፡፡ ዐውደ ርእዩን የተመለከቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ምእመናንም አስተያየታቸውን በቃልና በጽሑፍ ሰጥተዋል፡፡

atens 04በተለይም ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ነባራዊ ሁኔታ ከቀረበው ገለጻ መረዳታቸውንና ማዘናቸውን የገለጹት ምእመናን፤ በገዳማትና በአብነት ትምህርት ቤቶች ላይ የሚታየው ችግር ለመፍታት ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመሆን አቅማቸው የፈቀደውን ድጋፍ ለማድረግ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡

በዚህም መሠረት ማኅበረ ቅዱሳን አብነት ትምህርት ቤቶችን ለመርዳት የቀረጸውን የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የነጻ ትምህርት እድል ፕሮጀክት ለመርዳት የገንዘብ ድጋፍ አድርገዋል፡፡ ፕሮጀክቱም በተያዘለት እቅድ መሠት እስኪፈጸም ድረስ ድጋፋቸውን አጠናክረው ለመቀጠል ቃል ገብተዋል፡፡

በተጨማሪም ገዳማትንና አብነት ትምህርት ቤቶችን በጋሪ ለመርዳት እንዲያስችል ማኅበረ ቅዱሳን በግሪክ አቴንስ ከተማ ማእከል እንዲያቋቁምላቸው ምእመናን ጥያቄ አቅርበዋል፡፡atens 03

ማኅበረ ቅዱሳን በቅርቡ በጀርመን ካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም እና በኮሎኝ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል አብያተ ክርስቲያናት ዐውደ ርእይ አዘጋጅቶ እንደነበር መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን፤ ዐውደ ርእዩ በቤልጂየም ብራስልስ አብያተ ክርስቲያናትም ይቀጥላል፡፡

 

የግእዝ ሥርዓተ ንባብ (pronounciation)

ነሐሴ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመ/ር ደሴ ቀለብ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ መምህር

የግእዝ ሥርዓተ ንባብ ስምንት ናቸው፡፡ እነርሱም፡- 

  1. ማንሳት                       5. ማናበብ

  2. መጣል                       6. አለማናበብ

  3. ማጥበቅ                      7. መዋጥ

  4. ማላላት                      8. መቁጠር ናቸው፡፡

1. ማንሳት፡- ይህ ሥርዓተ ንባብ የቃሉ መጨረሻ ፊደል ሳድስ ከመሆን የተለየ ሆኖ ቃሉ በከፈተኛ ድምፅ የሚነገር ወይም የሚነበብ ማለት ነው፡፡ ለዚህም ነው ሁሉም የግስ ዓይነቶች በከፍተኛ ድምፅ የተነበቡ ተነሽ ናቸው የሚባሉት፡፡

ምሳሌ፡- ነበረ = ተቀመጠ

ሐበነ = ስጠን

ተዘከረኒ = አስታውሰኝ

ውእቱ = ነው፣ ነበር፣ እሱ፣ ናቸው ወዘተርፈ፡፡

አንስት ሖራ = ሴቶች ሔዱ

ይግበሮ = ይሥራው

ያጥምቆ = ያጥምቀው

2. መጣል (ተጣይ)፡- ይህ ሥርዓተ ንባብ መጨረሻው ሳድስ ሆኖ የማይነሳ ማለት ነው፡፡

ምሳሌ፡- ማርያም፣ ሚካኤል፣ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ቤተ መንግሥት፣ ቅድስት፣ መቅደስ ወዘተርፈ፡፡

3. ማጥበቅ፡- ይህ ሥርዓተ ንባብ ከቃሉ ውስጥ የሚጠብቅ ፊደል ኖሮ ቃሉ ጠብቆ እንዲነበብ የሚያደርግ ነው፡፡

ምሳሌ፡- ቀደሰ = አመሰገነ

ሰብሐ = አመሠገነ

ተዘከሮ = አስታውሰው

ነጸረ = ተመለከተ

4. ማላላት፡- ይህ ሥርዐተ ንባብ በቃሉ ውስጥ የሚጠብቅ ፊደል ሳይኖርና ንባቡም ላልቶ ሲነበብ ነው፡፡

ምሳሌ፡- ቀተለ = ገደለ

ነበረ = ተቀመጠ (ኖረ)

አምለከ = አመለከ

ገብረ = ፈጠረ (ሠራ)

ፈጠረ = ፈጠረ (በአማርኛው ይጠብቃል)

5. ማናበብ፡- ይህ ሥርዓተ ንባብ ሁለት ወይም ከዚያ በላይ የሆኑ ቃላት እንደ አንድ ሆነው ሲናበቡና ን፣ በን ወይም የን ሲያመጡ ነው፡፡

ምሳሌ፡- ቤተ ክርስቲያን = የክርስቲያን ቤት

ቤተ መቅደስ = የማመስገኛ ቤት

ትምህርተ ሃይማኖት = የሃይማኖት ትምህርት

ድንግለ ሙሴ

ብሥራተ ገብርኤል

ዜና ሥላሴ

ውዳሴ ማርያም

ጥዑመ ልሳን

ወልደ ኢየሱስ

ተዋሕዶ ቃል

ዜና ቤተ ክርስቲያን

6. አለማናበብ፡- ይህ ሥርዓተ ንባብ ሁለት ወይም ከዚያ በላይ የሆኑ ቃላት ራሳቸውን ችለው ሲነበቡ ወይም አንዱ ላንዱ አጎላማሽ ሲሆን ነው፡፡

ምሳሌ፡- ቅዱስ አምላክ ይባላል እንጂ ቅዱስ አምላክ አይባልም፡፡

ድንግል ማርያም

መጽአ ወልድ – ወልድ መጣ

ጳውሎስ ሐዋርያ

7. መዋጥ፡- መዋጥ ማለት ከቃሉ ውስጥ ያለ ፊደል እንዲሁ ሳይጎላ በውስጠ ታዋቂነት የሚነበብ ነው፡፡ ከዚህ ላይ ማስተዋል ያለብን ፊደሉ በጽሑፍ ጊዜ ግን ሥርዓቱን ጠብቆ ይጻፋል፡፡

ምሳሌ፡- ወይን (wan) ተብሎ እንጂ ወይን (wayyin) ተብሎ አይነበብም፡፡

ድንግል – ከዚህ ላይ ን ተውጣለች

ገብር – ከዚህ ላይ ደግሞ ብ ተውጣለች፡፡ ስለዚህ ገብር ባለሁለት ቀለም ነው፡፡

ኤልሳዕ ከዚህ ላይ ደግሞ ዕ ትዋጣለች፡፡

ርኩስ ኩ ተውጣለች፡፡

ከዚህ ላይ ብዙውን ጊዜ የሚዋጡት ቀለሞች ሲሆኑ መዋጥና አለመዋጣቸው ግን እንደ ንባቡና እንደትርጓመው ይለያያል፡፡

8. መቁጠር፡- ይህ ሥርዓተ ንባብ በአንድ ቃል ውስጥ የሚገኙ ፊደላትን ያለምንም መዋጥ ማንበብ ማለት ነው፡፡

ምሳሌ፡– ውእቱ ከሚለው ቃል ሁሉም ፊደላት ይነበባሉ እንጂ ሳድስ ስለሆነች ብቻ የምትዋጥ አይደለችሙ፡፡

ይእቲ፣ መላእክት፣ ማርያም፣ ማእከል፣ እኅት፣ ትማልም፣ ዮሐንስ፣ አጽፋር (ጥፍሮች) ስእርት (ፀጉር)፣ ኤልያስ፣ ብሔር (ሀገር) እሙንቱ፣ ስብሐት፣ ሐዋርያት፣ መጻሕፍት (ህ ትቆጠራለች)

ከእነዚህ ሥርዓተ ንባቦች በተጨማሪ ሌሎችም አሉ፡፡

 

ለምሳሌ፡- ወዳቂና ሰያፍ

ሀ. ወዳቂ፡- የምንለው ሥርዓተ ንባብ የቃሉ መጨረሻ ፊደል ካዕብ፣ ሳልስ፣ ራብዕ ኀምስና ሳብዕ ሆኖ የማይነሳ እና ቃሉ ሲነበብ የመጨረሻውን ፊደል በመያዝ እንዲወድቅ የሚያደርግ የሥርዓተ ንባብ ዓይነት ነው፡፡

ምሳሌ፡- ኀቤሁ ወደሱ የዚህ ቃል የመጨረሻ ፊደል ሁ ካዕብ ሲሆን ወዳቂ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ልዩነቶች እንዳሉ ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ ለምሳሌ ውእቱ የሚለው ነባር አንቀጽ ተነሽ እንጂ ወዳቂ አይደለም፡፡ እንዲሁም ግሶች በትዕዛዝም ሆነ በሓላፊ ሲመጡ ወዳቂ ናቸው ማለት አንችልም፡፡

 

ለምሳሌ፡- ሖሩ = ሔዱ ወይም ሑሩ = ሒዱ ብንልም ተነሽ እንጂ ወዳቂ አይደለም፡፡ ለሣልስ ምሳሌ ከይሲ ብእሲ መዋቲ መሃሪ ወዘተርፈ ሲሆኑ ግስ ከሆነ ግን አይወድቅም፡፡

 

ምሳሌ፡- ሰአሊ ለነ ቅድስት ከዚህ ላይ ሰአሊ የሚለው ቃል ወዳቂ አይደለም ለራብዕ ምሳሌ አንበሳ፣ ዜና፣ ወዘተረፈ ከዚህ ላይም በግስ የሚነገር ከሆነ አይወድቅም፡፡

 

ለምሳሌ፡- እላ አንስት ሖራ /እነዚያ ሴቶች ሔዱ/ ከዚህ ላይ « ሖራ » የሚለው ይነሳል እንጂ አይወድቅም፡፡

ለኀምስ ምሳሌ ውዳሴ፣ ቅዳሴ፣ ይባቤ፣ ወዘተረፈ

ለሳብዕ ምሳሌ ዶርሆ/ዶሮ/፣ መንበሮ፣ ቀቲሎት/

ንዑስ አንቀጽ የሆኑት ሁሉ ወዳቂ ናቸው፡፡ በተጨማሪ ቦዝ አንቀጽ የሆኑ ወዳቂዎች እንዳሉም ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን በግስ ትአዛዝ ወይም ዘንድ አንቀጽ የሆኑት ሊነሱ እንደሚችሉ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ 

Emebetachin-Eriget

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፥8/

ነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

Emebetachin-Erigetሰላም ለፍልሰተ ሥጋኪ መካነ ፍሥሐ ምጡቀ ፤ በአእባነ ባህርይ ዘተነድቀ ፤ማርያም ደብተራ እንተ ኢትትከደኒሠቀ፤እመቤቴ ማርያም ሆይ ምጡቅና ሩቅ ወደሚሆን የደስታ ቦታ ላረገ ሥጋሽ ሰላምታ ይገባል ፡፡ ይኸውም ኅብሩ ሊመረምሩት በማይቻል ዕንቊ የታነፀ ሕንፃ ይገኝበታል፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አዳም አባታችን እግዚአብሔርን በድሎ፣ ክብሩን አጥቶ፣ ሞተ ሥጋ ሞተ ነብስ ተፈርዶበት፣ ከገነት ሲባረር ፤ ምህረትና ቸርነት የባህሪው የሆነው አምላክ ይቅር ይለው፣ ወደ ቀደመ ክብሩ ይመልሰው ዘንድ ተማጽኗል፡፡ እግዚአብሔር አምላክም የአዳምን ማዘን፣ መጸጸት ፣ ንስሀ መግባት ተመልክቶ 5500 ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ስደትህን በስደቴ፣ ሞትህን በሞቴ አጥፍቼ የቀደመ ክብርህን መልሼ ያጣኸውን ርስት ገነት መንግስተ ሰማያት አወርስሃለሁ፡፡ገላ4፡4 በማለት ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡

አዳም አባታችን ቃል ኪዳን በተገባለት መሠረት የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያነት የተመረጠች፣ ለአዳም እና ዘሩ መዳን ምክንያት የሆነች የልጅ ልጅ የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዳ 15 ዓመት ሲሆናት በቅዱስ ገብርኤል ብስራት የእግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ማደሪያ ሆነች፡፡ ልጇን በወለደች ወቅት የሰብዓ ሰገልን “የተወለደው የአይሁድ ንጉስ ወዴት አለ” የሚለውን ዜና የሰማ ሄሮድስ የተወለደውን ህጻን ለመግደል አዋጅ አወጀ ፡፡ እመቤታችንም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማዳን ወደ ግብጽ ይዛው ተሰደደች ማቴ.2፡12፡፡

የስደት ዘመኑ አልቆ ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱ በኋላ ኢየሱስ ክርስቶስ 30 ዘመን ሲሆነው ስለመንግስተ እግዚአብሔር ስለ ሰው ልጆች ነጻነት ይሰብክ ጀመር፡፡ ኃላም የአዳም ዘር ሞት ለማጥፋት ፣ባርነትን አጥፍቶ ነጻነትን ለማወጅ በመስቀል ተሰቅሎ ሞተ ፡፡ በሦስተኛው ቀን ተነስቶ ነጻነትን አወጀ፡፡ በዚህ ሁሉ የድኅነት ጉዞ ውስጥ ያልተለየችና ምክንያተ ድኂን የሆነችው እመቤታችን የሰው ልጆች ድኅነት ሲረጋገጥ በተወለደች በ64 ዓመቷ ጥር 21 ቀን አረፈች፡፡

a ergete mariam 2006 1ሐዋርያት መጽናኛቸው እናታቸው ቅድስት ድንግል ማርያም ብታርፍባቸው ሥጋዋን ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡

ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡ዮሐንስ ከገነት ሲመለስ ለሐዋርያት “ የእመቤታችንን ሥጋ ወደ ገነት መወሰድ ነገራቸው፡፡ “ዮሐንስ የእመቤታችንን ሥጋ ገነት ማረፍ አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው፤ ከነሐሴ 1 ቀን – ነሐሴ 14 ቀን ጾመዋል፡፡ “ሰላም ለፍልሰተ ሥጋኪ መካነ ፍሥሓ ወኑዛዜ፡ ኀበ ኢይሬእይዎ ለላህ ወኢይሔይልዎ ለትካዜ፡ ማርያም ህሉት ዉስተ ልበ ኣምላክ እምቅድመ ግዜ፡ ትፍሥሕትሰ ተፈሣሕኩ ብፍልሰትኪ ይእዜ፣ ገጸ ዚኣኪ እሬኢ ማዕዜ”ይላል መልክዓ ፍልሰታ፡፡

እግዚአብሔር ሀዘናቸውን ተመልክቶ መጽናናትን ይሰጣቸው ዘንድ ከነሐሴ 1 ቀን -ነሐሴ 14 ቀን ሐዋርያት በአንድ ልብ ሆነው ሱባኤ ያዙ (በጾም በጸሎት ተወስነው ) እግዚአብሔርም የልብ መሻታቸውን አይቶ ነሐሴ 14 ቀን ጌታ የእመቤታችንን ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሩዋት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው፡፡ እነርሱም ትወጪ ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል አሏት፡፡ ያን ጊዜም ከዕፅ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን የማርያም ሥጋዋ ወጣ፡፡ ሐዋርያት ገንዘው በክብር ቀብረዋታል፡፡ ስለ ግንዘቷም “ሰላም ለግንዘተ ሥጋኪ ብእደ ሓዋርያት ኣርጋብ፤ ብአፈወ ዕፍረት ቅዱው ዘሐሳብ ሴቱ ዕጹብ፤ ማርያም ድንግል ውለተ ህሩያን ሕዝብ፤ ረሰይኩኪ እግዝእትየ ህየንተ እም ወኣብ፤ ይኅጽነኒ ከመ ጥብ ፍቅርኪ ሓሊብ።” ያለው ለዚህ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ በዝማሬ ድርሰቱ “በስብሐት ውስተ ሰማያት መላእክት ወሊቃነ መላእክት ወረዱ ለተቀብሎታ፣ እብለኪ ወእሙ ለእግዚእየ እብለኪ ዳዊት አቡሃ ምስለ መሰንቆሁ ሙሴኒ እንዘ ይፀውር ኤፉደ መጽኡ ሃቤሃ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ሐዋርያት አጠኑ ሥጋሃ በማዕጠንተ ወርቅ፣ ሱራፌል ወኪሩቤል ሰፍሑ ከነፊሆሙ ላዕሌሃ፣ ወረደ ብርሃን እምሰማያት ወመብረቀ ስብሐት እምውስተ ደመናት፣ ተለዓለት እምድር ውስተ አርያም በስብሐት ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ” ብሏል፡፡

ጌታችንም ዘላለማዊ ወደሆነ መንግሥተ ሰማያት መላእክት እና ሰማዕታት እየሰገዱላት አሳረጓት፡፡ ንጉሥ ዳዊት “በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋ ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” እንዳለ /መዝ 44¸9/፡፡ ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ተመልሶ ከሰማይ ወረደ፡፡ ሐዋርያት ተሰብስበው ስለ እመቤታችን ሥጋ ፈጽሞ ሲያዝኑና ሲተክዙ አገኛቸው፡፡ እርሱም እንዳየ እንደሰማ ሥጋዋም በታላቅ ክብር ማረጉን ነገራቸው፡፡

መላእክትና ሊቃነ መላእክት ቅዱስ ሥጋዋን ለማሳረግ በታላቅ ምሥጋና ከሰማይ ወረዱ፤ አባቷ ዳዊት ከመሰንቆው ጋር ሙሴም የአገልግሎት ልብሱን ለብሶ፣ ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስም ወደ እርሷ መጡ ሥጋዋንም በወርቅ ማዕጠንት አጠኑ፡፡ ሱራፌልና ኪሩቤልም በላይዋ ክንፎቻቸውን ዘረጉ /ጋረዱ/፡፡ ከሰማያት ብርሃን የምስጋና መብረቅም ከደመናት ውስጥ ወጣ፡፡ ከምድር ወደ ሰማያት በምስጋና ከፍ ከፍ አለች ከልጇ ጋርም በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች” ማለት ነው፡፡ ይህም “በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች፡፡” መዝ.44፥9 ተብሎ የተነገረላትን ቃለ ትንቢት የተፈጸመላት መሆኑን ያመለክታል፡፡

ከሐዋርያት ወገን የሆነው ቅዱስ ቶማስ ለወንጌል አገልግሎት ሄዶ በወቅቱ አልነበረም፡፡ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ሕንድ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” ይላል፤ ተበሳጨ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁኝ” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የልቡናን ሐዘን የምታቀል እመቤታችን፡- አይዞህ አትዘን እኒያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም፡፡ አንተ አይተሃል፡፡ ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው፡፡” ብላ የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡

ከዚህ በኋላ ሄዶ፤ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ እንጂ ልማድህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም፤ አንተ እየተጠራጠርህ ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” አለው፡፡ እርሱም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ይሰማቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ ሂዶ መቃብሩን ቢከፍተው የእመቤታችን ሥጋዋን አጥቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንግጦ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ቶማስ “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች” አላቸው፡፡

a ergete mariam 2006 2ቅዱስ ቶማስ የያዘውንም ሰበን እያሳያቸው፡- “ቅዱስ ሥጋዋን የገነዛችሁበት ጨርቅ /ሰበን/ ይህ አይደለምን” ብሎ ሰበኑን ሰጣቸው፡፡ ይህንንም ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ከዚህ በኋላ በዓመቱ “ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ በማለት ጾም ጀመሩ፡፡

በ16ኛው ቀን አምልካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ እመቤታችንን መንበር ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ራሱ ቀድሶ አቁርቧቸዋል፡፡ሐዋርያት ከዚህ በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን በብቃት ለመወጣት ቻሉ፡፡ ይህንን ዐቢይ ምሥጢር አስመልክቶ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ተንሥአ እግዚኦ” ውስተ ዕረፍትከ፡፡ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፡8/፡፡

“ወትቀውም ንግሥት በየማንከ በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኁብርት፤ በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” /መዝ.44፡9/ ሲል በ ቅዱስ ዳዊት የተናገረው ቃለ ትንቢት በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና የጸናች የቅድስት ድንግል እመቤታችንን ዕረፍትና ትንሣኤ እንዲሁም ፍለሰት /ዕርገት/ በምሥጢር ከማሳየቱም ሌላ ወላዲተ አምላክ በልጇ በወዳጇ በኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት በክብርመኖሯንም ያስረዳል /ራእ.11፡19/፡፡

 

a kassel 1

ማኅበረ ቅዱሳን በጀርመን ዐውደ ርእይ አካሔደ።

ነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም.

በጀርመን ቀጠና ማእክል

a kassel 1በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ሐምሌ 26 እና 27 2006 ዓ.ም በጀርመን ካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ፣ የማኅበረ ቅዱሳንን ታሪክ፣ አገልግሎትና በየጊዜው ያጋጠሙትን ችግሮች እንዲሁም የቤተክርስቲያን አገልግሎት በአውሮፓ በተለይም በጀርመን ያለበትን ሁኔታ፣ የአመሠራረት ታሪከ እና መንፈሳዊ እንቅስቃሴ የሚያስቃኝ ዐውደ ርእይ ተካሔደ።

ዐውደ ርእዩ በካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ በመጋቤ ምሥጢር ኅሩይ ኤርምያስ ተከፍቷል። ምእመናን ዐውደ ርእዩን ከተመለከቱ በኋላ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረት፣ ገዳማትና የአብነት ትምህር ቤቶችን ለመደገፍ እያደረገ ስላለው እንቅስቃሴ በቂ መረጃ ማግኘታቸውን ገልጠው የማኅበሩን አገልግሎት ለመደገፍ ፍላጎት እንደላቸው ገልጸዋል። መጋቤ ምሥጢር ኅሩይ ኤርምያስ በበኩላቸው ራሳቸው ያለፉበት የአብነት ትምህርት ቤት ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለሀገር ያበረከቱት አስተዋጽኦ ተመልካች ሊረዳው በሚችል መልኩ መቅረቡን አድንቀው ማእከሉ ዐውደ ርእዩን በደብሩ ስላካሔደ በስበካ ጉባኤው ስም ምሥጋና አቅርበዋል፤ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት የቤተክርስቲያን አገልግሎት በመሆኑ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል::

a koeln 1ዐውደ ርእዩ ነሐሴ 3 እና 4 ቀን 2006 ዓ.ም በኮሎኝ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ላይ በአጥቢያው ሰበካ ጉባኤና በሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ በጀርመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሓላፊ ፈቃድ ለምእመናን ለመታየት በቅቷል። ዐውደ ርእዩን የከፈቱት ሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ ሲሆኑ በዕለቱ የቀረበው ዐውደ ርእይ ጥንታዊ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ ምእመናን እንዲረዱት የሚያደርግ በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእዩን በዚህ ቤተክርስቲያን ማካሔዱ ያስደሰታቸው መሆኑን ተናግረዋል። በመቀጠልም የድጓ እና የአቋቋም መምህር የሆኑት እና ከካርል ስሩህ አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን የመጡት ሊቀ ጠበብት ተክሌ ሲራክ ስለአብነት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት እና በአሁኑ ወቀት ተማሪዎች ስላሉባቸው ቸግሮች ሰፊ ገለጻ አድርገዋል፡፡ ችግሮቹን ለመፍታት አባቶች፣ ምእመናንና ማኅበራት ሊያደርጓቸው ይገባል ያሏቸውን የመፍትሔ ሐሳቦች ጠቁመዋል::

በኮሎኝ ደ/ሰ/ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የሚገኙ ምእመናን ዐውደ ርእዩን ከተከታተሉ በኋላ ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ላይ ከፍተኛ ሥራ መሥራቱን የሚያሳይ መረጃ ሳያገኙ የቆዩ መሆናቸውን ገልጸው ወደ ፊት ግን ከማኅበሩ ጋር በመተባበር በጋራ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶችን ለመርዳት ቃል ገብተዋል። ዐውደ ርእዩ ለሁለት ቀናት ክፍት ሆኖ በምእመናን የተጎበኘ ሲሆን ከ150 በላይ የሚሆኑ የአጥቢያው ምእመናን እንደጎበኙት የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ በነበሩ አንዳንድ ክፍተቶች ማኅበረ ቅዱሳን በአጥቢያው ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ሳያደርግ የቆየ ቢሆንም ከዚህ በኋላ ግን በአዲስ መልክ ከደብሩ አስተዳዳሪ፣ ከሰበካ ጉባኤው እንዲሁም ከምእመናን ጋር ለመሥራት ከስምምነት ላይ ተደርሷል። ከዚህ በፊት በማኅበሩ ላይ ቅሬታ የነበራቸው ምእመናንም ከዐውደ ርእዩ በኋላ ጥያቄና አስተያየት አቅርበው በቂ ማብራሪያና ምላሽ በማግኘታቸው በቀጣይ ከማኅበሩ ጋር ለመሥራት በጎ ፍላጎት ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል።

ተመሳሳይ የዐውደ ርእይ ዝግጅቶች በግሪክ አቴንስና በቤልጂየም ብራስልስ አብያተ ክርስቲያናት የሚካሔድ መሆኑ ተጠቅሷል።

 

a ledeta mariam 2006 01

አድርሺኝ

ነሐሴ 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

a ledeta mariam 2006 01በጎንደር ከተማ በፍልሰታ ለማርያም ጾም ወቅት በካህናቱ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና በምእመናን አማካይነት በየዓመቱ የሚከናወን የተለመደ ሥርዓት አለ፡፡ ይህም ሥርዓት “አድርሺኝ” በመባል ይታወቃል፡፡

በጎንደር ከነገሡት ነገሥታት መካከል ከ1703-1708 ዓ.ም. ለአምስት አመታት በንግሥና የቆዩት ዐፄ ዮስጦስ የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያንን በመትከል የሚታወቁ ሲሆን፤ አድርሽኝ የተሠኘውንም ሥርዓት በእርሳቸው እንደተጀመረ ይነገራል፡፡

ስለ ሥርዓቱ አጀማመር አባቶች ሲናገሩ፣ ዐፄ ዮስጦስ ተቀናቃኞቻቸው የከፈቱባቸውን ጦርነት ለመመከት ወደ ጦርነት ሲዘምቱ “ልደታ ለማርያም ሳትለዪኝ በድል ብትመልሺኝ፤ ለዚህም ታላቅ ክብር ብታደርሺኝ በየዓመቱ በፍልሰታ ለማርያም ሱባኤ ካህናቱን፤ መኳንንቱንና ምእመናንን ሰብስቤ ግብዣ አደርጋለሁ” በማለት ብፅዐት ይገባሉ፡፡ እርሳቸውም ድል አድርገው በመመለሳቸው በቃላቸው መሠረት በጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ደጀ ሰላም ሕዝቡን ሰብስበው ግብዣ ማድረጋቸውን ቀጠሉ፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑም እርሳቸውን ተከትሎ በየዓመቱ በጾመ ፍልሰታ ወቅት ይህንን ሥርዓት ይተገብሩት ጀመር፤ ስያሜውም “አድርሺኝ” ተባለ፡፡

አድርሺኝ በመላው ጎንደር በየአብያተ ክርስቲያናቱና በየአካባቢው በፍልሰታ ጾም ወቅት ይከናወናል፡፡ ምእመናን ከቅዳሴ መልስ ሱባኤው እስኪጠናቀቅ በመረጡት አንድ ቤት ውስጥ ተሰብስበው ቆሎና ጠላ አዘጋጅተው በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ጽዋ ይጠጣሉ። በተለይም መነኮሳይያት እናቶች በሚታደሙበት ጽዋ ላይ “ኦ! ማርያም” የሚለውን የተማጽኖ መዝሙር ይዘምራሉ። ይህ መዝሙር በሚዘመርበት ጊዜ ያለ ምንም ጥርጥር እመቤታችን ፊት ለፊት ትቆማለች ተብሎ ስለሚታሰብ በፍጹም ተመሥጦና በመንበርከክ ያከናውኑታል።

የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ-ኤስድሮስ ሰንበት ት/ቤት ወጥነት እንዲኖረው በማሰብ ይህንን የእናቶች የምሕላ ዝማሬ ለተተኪ ትውልድ ለማስተላለፍ እንዲቻል አሰባስቦ አዘጋጅቶታል፡-

ኦ! ማርያም

ኦ! ማርያም እለምንሻለሁ ባሪያሽ፤

እስኪ አንድ ጊዜ ስሚኝ ቀርበሽ፤ ከአጠገቤ ቆመሽ፤

ፅኑ ጉዳይ አለኝ ላንቺ የምነግርሽ፤

የዓለሙን መከራ ያየሽ፤

በእናትሽ በአባችሽ ሀገር፤

በምድረ ግብፅ ዞረሽ ውሃ የለመንሽ፡፡

ከሁሉ ሁሉ ጤፍ ታንሳለች፤

ከጭቃ ወድቃ ትነሳለች፤

ስትነሳ /2/ የአዳም ልጅ ሁሉ ሞትን ረሳ፤

የአዳም ልጅ ሁሉ ሰነፈና የኑሮ ቤቱን ረሳና፤

ተው አትርሳ /2/ ተሠርቶልሃል የእሳት ሳንቃ፡፡

ያን የእሳት ሳንቃ፤ የእሳት በር፤

እንደምን ብዬ ልሻገር፤

ተሻገሩት አሉ የሠሩ ምግባር፤

እኔ ባሪያሽ እንዴት ልሁን? ሰላም ሰጊድ /2/

በመሥቀሉ ሥር ያያትን ተሰናበታት እናቱን፤

እናትዬ ለምን ታለቅሻለሽ ተሰቅዬ፤

ይስቀሉኝ ሐሰት በቃሌ ሣይገኝ፡፡

ንፅሕት የወልደ እግዚአብሔር እናት፤

ንፅህት በፍቅሯ ወዳጆቿን ስትመራ፤

ንፅሕት በቀኝ ወዳጆቿን ስትጎበኝ፤

የእኛስ እመቤት ያች ሩኅሩኅ፤

ከለላችን ናት እንደ ጎጆ፤

እርሷን ብለው ጤዛ ልሰው ኖሩ ትቢያ ለብሰው /2/

ኪዳነ ምሕረት ሩኅሩኅ ተይ አታቁሚኝ ከበሩ፤

የገነሃም እሣት መራራ ነው አሉ፤

እኔ ባሪያሽ እንዴት ልሁን? ሰላም ሰጊድ /2/

ድንግል ማርያም ንፅሕት፤

የምክንያት ድኅነት መሠረት፤

እንለምንሻለን ወደ አንቺ አንጋጠን፤

ከፈጣሪ በይ አማልጅን ሰላም ሰጊድ /2/

ኃያል /2/ ቅዱስ ሚካኤል ኃያል፤

የለበሰው ልብሱ የወርቅ ሐመልማል፤

ይህም ተጽፏል በቅዱስ ቃል ሰላም ሰጊድ /2/

ጊዮርጊስ ስልህ ዘንዶ ሰገደ ከእግርህ፤

እፁብ ድንቅ ይላሉ ገድልህን የሰሙ፤

አንተ አማልደኝ ከሥልጣኑ ሰላም ሰጊድ /2/

አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ደግ አባት፤

መጥቼልሃለሁ ከደጋ፤

ስንቄንም አድርጌ አጋምና ቀጋ፤

አንተ አማልደኝ ከፈጣሪ ሰላም ሰጊድ /2/

ፃድቅስ ባያችሁ ተክለ ሃይማኖት፤

በአንድ እግር ቆመው ሰባት ዓመት፤

በተአምኖ ሰባት ባቄላ ምግብ ሆኖት /2/

ተክለ ሃይማኖት አባቴ፤

መሠላሌ ነህ ለሕይወቴ፤

የዓለሙን ኑሮ መጥፎነቱን፤

የፈጣሪያችን ቤዛነቱን፤

አስተውለኸው አጥንተኸው፤

ደብረ ሊባኖስ የተሰዋኸው፡፡

ክርስቶስ ሠምራ እናታችን፤

ከአምላካችን ፊት መቅረቢያችን፤

ሣጥናኤልን አሸንፈሽ፤

ከግዛቱ ውስጥ ነፍስን ማረክሽ፡፡

ክርስቶስ ሠምራ ቅድስቷ፤

ለጽድቅ ሕይወት አማላጇ፤

እንለምንሻለን ወደ አንቺ አንጋጠን፤

ከፈጣሪ በይ አማልጅን ሰላም ሰጊድ /2/

ኦ! አባቴ አንተ ረኃቤ ነህ ጥማቴ፤

የኔ መድኃኒት ኃያል ተመልከተን ዝቅ በል፤

የነገሩህን የማትረሳ፤

የለመኑህን የማትነሳ፤

አምላኬ አንተ ነህ አምባዬ፤

የሕይወት ብርሃን ጋሻዬ፡፡

ማርያም ስሚን ወደ ሕይወት መንገድ ምሪን፤

ከአጠገባችን ቁጭ ብለሽ አድምጭን፤

ይደረግልን ልመናሽ ስትመጪ /2/

አንቺ እናቴ ሆይ /2/ የሔድሽበትን ትቢያ ቅሜ፤

ያረፍሽበትን ተሳልሜ፤

በሞትኩኝ /2/ የኋላ ኋላ ላይቀር ሞት፡፡ /2/

 

በፍልሰታ ለማርያም ጾም ወቅት ዘወትር ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በቤተ-ኤስድሮስ ሰንበት ት/ቤት ካለፉት 21 ዓመታት ጀምሮ ጸሎት ዘዘወትር፣ ውዳሴ ማርያም፣ ይዌድስዋ መላእክት፣ መዝሙረ ዳዊት 50 እና 135፣ ጸሎተ ምናሴ፣ መሐረነ አብ ጸሎት በዜማ ከተጸለየ በኋላ ኦ! ማርያም የምሕላ መዝሙር ይዘመራል፡፡

  • ማስታወሻ፡- መረጃውን በመስጠት የተባበሩንን ዲያቆን ሙሉቀን ብርሃኑ እና የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ- ኤስድሮስ ሰንበት ትምህርት ቤትን በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

 

የማቴዎስ ወንጌል

 ነሐሴ 9 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ ስድስት

በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የሚከተሉት አሳቦች ተጠቃልለው ይገኛሉ፡፡

  1. የምጽዋት ሥርዓት

  2. ጠቅላላ የጸሎት ሥርዓት

  3. የአባታችን ሆይ ጸሎት

  4. ስለ ይቅርታ

  5. የጾም ሥርዓት

  6. ስለ ሰማያዊ መዝገብ

  7. የሰውነት መብራት

  8. ስለ ሁለት ጌቶች

  9. የዕለት ጉርስና የዓመት ልብስ

1. የምጽዋት ሥርዓት፡- ጌታችን በዚህ ትምህርቱ እንደ ግብዞች መመጽወት እንደማይገባ ተናግሯል፡፡ ግብዞች የሚመጸውቱት ሰው ሰብስበው፣ ቀን ቀጥረው በተመሳቀለ ጉዳና በአደባባይ ነው፡፡ የሚመጸዉቱትም ለመጽደቅ ሳይሆን ለውዳሴ ከንቱ ስለሆነ፤ ስለዚህም አንተ በምትመጸውትበት ጊዜ ቀኝ እጅህ የምትሠራውን ግራ እጅህ አትወቀው ብሏል፡፡ እንዲህም ያለበት ምክንያት፡-

ሀ. በቀኝ አጅህ የያዝኸውን በግራ እጅህ አትያዘው ማለቱ ነው፡፡ ምክንያቱም ግራ ደካማ ስለሆነ ጥቂቱን ብዙ አስመስሎ ልቀንስለት ይሆን ያሰኛል፡፡ ቀኝ ግን ኃያል ስለሆነ ብዙውን ጥቂት አስመስሎ አንሷል ልጨምርበት ያሰኛል፡፡

 

ለ. ግራ እጅ የተባለች ሚስት ናት፤ ሚስት በክርስትና ሕይወት ካልበሰለች ሀብቱ እኮ የጋራችን ነው፣ ለምን እንዲህ ታበዛዋለህ? እያለች ታደክማለች፡፡ ከሰጠ በኋላ ግን ከሚስት የሚሰወር ነገር ስለሌለ ይነግራት ዘንድ ይገባል፡፡ ብትስማማ እሰየው፤ ባትስማማ ግን መለየት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ጥንቱን የተጋቡት እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ሰጥተው መጽውተው ለመጽደቅ ነውና፡፡ 

 

ሐ. ግራ እጅ የተባሉት ልጆች ናቸው፤ የአባታችን “የቁም ወራሽ የሙት አልቃሽ” እያሉ ያደክማሉና፡፡

 

መ. ግራ እጅ የተባሉት ቤተሰቦች ናቸው፤ የጌታችን ወርቁ ለዝና፣ ልብሱ ለእርዝና እህሉ ለቀጠና እያሉ ያዳክማሉና፡፡

 

ይህን ሁሉ አውቀን ተጠንቅቀን የምንመጸውት ከሆነ በስውር ስንመጸውት የሚያየን ሰማያዊ አባታችን በጻድቃን፣ በሰማዕታትና በመላአክት ፊት ዋጋችንን በግልጥ ይሰጠናል፡፡

 

2. የጸሎት ሥርዓት፡- ግብዞች የሚጸልዩት ለታይታ ነው፤ አንተ ግን ከቤትህ ገብተህ ደጅህን ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ፡፡ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ያስረክብሃል፡፡ ብሏል፡፡ ይህም ማለት የምትጸልይበት ጊዜ ሕዋሳትህን ሰብስበህ፣ በሰቂለ ልቡና ሆነህ ወደ ሰማያዊ ወደ እግዚአብሔር አመልክት፤ ተሰውረህም ስትጸልይ የሚያይ አባትህ ዋጋህን ይሰጥሃል ማለት ነው፡፡ ይህ የግል ጸሎትን የተመለከተ ነው እንጂ በቤተ ክርስቲያን የሚደረግ የማኅበር ጸሎትን አይመለከትም፡፡

 

3. የአባታችን ሆይ ጸሎት፡- ጌታችን ማንም ቢሆን ሲቆምና ሲቀመጥ፣ ሲተኛና ሲነሣ ሊጸልይ የሚችለውን አጭር የኅሊና ጸሎት አስተማረ፡፡ ይህንንም በዝርዝር እንመለከተዋለን፡-

ሀ. አባታችን ሆይ፡- ጌታችን ከግብርናተ ዲያብሎስ /ከዲያብሎስ ባርነት/ ነጻ እንዳወጣን፣ አጥተነው የነበረውን ልጅነት እንዳገኘን ሲያጠይቅ አቡነ /አባታችን/ በሉኝ አለ፡፡ ጌታ ሎሌውን መምህር ደቀመዝሙሩን ምን ቢወደው ያበላዋል፣ ያጠጣዋል፣ የልቡናውን ምሥጢር ያጫውተዋል እንጂ ርስቱን አያወርሰውም፡፡ ርስቱን የሚያወርሰው ለልጁ ነው፡፡ እርሱ ግን ጌታችን እና አምላካችን ሲሆን የማታልፍ ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያወርሰን ስለሆነ አቡነ በሉኝ አለ፡፡ አባት ለወለደው ልጁ እንዲራራ የሚራራልን ስለሆነ አቡነ በሉኝ አለ፡፡

ለ. በሰማያት የምትኖር፡- እንዲህ ማለቱ ራሱ ከምድራዊ አባት ሲለይ ነው፡፡ ምድራዊ አባት ሲወልድ በግዘፍ ሲያሳድግ በግዘፍ ነው፡፡ ኋላም ሓላፊ ርስቱን ያወርሳል፡፡ ጌታችን ግን ሲወልደን በረቂቅ፣ ሲያሳድገንም በረቂቅ ነው፡፡ ኋላም የማታልፍ ርስቱን መንግሥተ ሰማይን ያወርሰናል፡፡ በተጨማሪም ጌታ በሁሉ ምሉዕ ሲሆን ስለ ልዕልናው በሰማይ የምትኖር ይባላል፡፡

ሐ. ስምህ ይቀደስ፡- ይህም “ስምየሰ መሐሪ ወመስተሠፀል” ስሜ መሐሪና ይቅር ባይ ነው፡፡” ያልኸው ይድናልና፤ መላእክት ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ብለው ስምህን አመስግነው ቅድስናህን ተሳትፈው እንዲኖሩ፣ እኛም ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ብለን አመሰግነንህ ቅድስናህን ተሳትፈን እንድንኖር አድርገን በሉ ሲለን ነው፡፡

መ. መንግሥትህ ትምጣ፡- መንግሥተ ሰማይ ትምጣልን ልጅነት ትሰጠን በሉ ሲል ነው፡፡ እንዲህም ማለቱ መንግሠተ ሰማይ ከወዲያ ወዲህ የምትመጣ፣ ከወዲህም ወዲያ የምትሔድ ሆና ሳይሆን ትገለጽልን በሉ ማለቱ ነው፡፡

ሠ. ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነ እንዲሁም በምድር ይሁን፡- መላእክት በሰማይ ሊያመሰግኑህ ፈቃድህ እንደሆነ እኛም በምድር ያለን ደቂቀ አዳም እናመሰግንህ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን፡፡ ኋላ ሙተን ተነሥተን እንድናመሰግንህ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን በሉ ሲል ነው፡፡

 

ረ. የዕለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬ፡- በዚህ ዓለም ሳለን ለዕለት የሚሆነን ምግባችንን ስጠን በሉ ሲል ነው፡፡

 

ሰ. በደላችንን ይቅር በለን እኛም የበደሉንን ይቅር እንደምንል፡- ማረን፣ ይቅር በለን፣ ኃጢአታችንን አስተስርይልን፣ በደላችንን ደምስስልን መተላለፋችንን ሁሉ ይቅር በለን፤ ይቅርታን እናገኝ ዘንድ እኛም የበደሉንን ሁሉ ይቅር እንላለን ሲል ነው፡፡

 

ሸ. አቤቱ ወደ ፈተናም አታግባን፡- ከክፉ ሁሉ አድነን እንጂ ወደ ኃጢአት፣ ወደ ክህደት፣ ወደ መከራ፣ ወደ ገሃነም አታግባን ከዚህ ሁሉ አድነን እንጂ በሉኝ ሲል ነው፡፡

 

ቀ. መንግሥት ያንተ ናትና፡- መንግሥተ ሰማያት ያንተ ገንዘብህ ናትና በሉኝ ሲል ነው፡፡

 

በ. ኃይል ምስጋናም ለዘላለሙ፡- ከሃሊነት፣ ጌትነት፣ ለዘላለሙ ገንዘብህ ናትና፤ አሜን በእውነት በሉኝ ሲል ነው፡፡

 

4. ስለ ይቅርታ የሰውን ኃጢአት ይቅር ባትሉ የሰማይ አባታችሁ እናንተንም ይቅር አይላችሁም፡፡ የሰውን ኃጢአት ይቅር ብትሉ ግን እናንተም የሰማይ አባታችሁ ይቅር ይላችኋል ብሏል፡፡

 

5. የጾም ሥርዓት፡- ግብዞች በሚጾሙበት ጊዜ ሰው እንዲያውቅላቸው ፊታቸውን አጠውልገው፣ ግንባራቸውን ቋጥረው፣ ሰውነታቸውን ለውጠው የታያሉ፡፡ እነዚህም በዚህ ዓለም የሚቀረውን ውዳሴ ከንቱ በማግኘታቸው የወዲያኛውን ዓለም ዋጋ ያጡታል፡፡ እናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ ራሳችሁን ተቀቡ፣ ፊታችሁንም ታጠቡ፡፡ የተቀባ የታጠበ እንዳይታወቅበት አይታወቅባችሁ አለ፡፡ ይህስ በአዋጅ ጾም ነው ወይስ በፈቃድ ጾም ነው ቢሉ በፈቃድ ጾም ነው እንጂ በዓዋጅ ጾምስ ምንም ውዳሴ ከንቱ የለበትም ምክንያቱም ሁሉ ይጾመዋልና፡፡ አንድም በገዳም ነው ወይስ በከተማ ቢሉ በከተማ ነው እንጂ በገዳምስ ምንም ውዳሴ ከንቱ የለበትም፡፡ የምሥጢራዊ መልእክቱም ታጠቡ ንጽሕናን ያዙ፣ ተቀቡ ደግሞ ፍቅርን ገንዘብ አድርጉ ማለት ነው፡፡ እንዲህም በማድረጋችሁ ማለት ጾመ ፈቃድን ተሰውራችሁ በመጾማችሁ ተሰውሮ የሚያያችሁ አባታችሁ በቅዱሳን መካከለ ዋጋችሁን ይሰጣችኋል አለ፡፡

 

6. ሰማያዊ መዝገብ፡- ጌታችን ሰማያዊ መዝገብ ያለው አንቀጸ ምጽዋትን ነው፡፡ ኅልፈት፣ ጥፋት ያለበትን፣ ብል የሚበላውን ነቀዝ የሚያበላሸውን ምድራዊ ድልብ፤ ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው የሚወስዱትን ቦታ አታደልቡ አለ፡፡ ይህም ስለ ሦስት ነገር ተናግሮታል፡፡

 

ሀ. እህሉን፡- ነዳያን ከሚበሉት ብለው ብለው፣ ልብሱንም ነዳያን ከሚለብሱት ብለው አኑረውት ብል ቢበላው ወይም ነቀዝ ቢያበላሸው ምቀኝነት ነውና፡፡

 

ለ.ለክፉ ጊዜ ይሆነኛል ብሎ ሰስቶ ነፍጎ ማኖር በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የሚመግበውን ለጋስ አምላክ እግዚአብሔርን ከዳተኛ ማድረግ ነውና፡፡

 

ሐ. ምንም እጅ እግር ባያወጡለት ገንዘብን ማኖር ጣዖትን ማኖር ነውና ስለሆነም ኅልፈት ጥፋት የሌለበትን፣ ሰማያዊ ድልብ ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው ከማይወስዱት ቦታ አደልቡ፤ ገንዘባችሁ ካለበት ዘንድ ልባችሁ በዚያ ይኖራልና አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም ውዳሴ ከንቱ ያለበትን ውዳሴ ከንቱ የሚያስቀርባችሁን፣ ሌቦች /አጋንንት/ በውዳሴ ከንቱ የሚያስቀሩባችሁን ምጽዋት አትመጽውቱ፤ ውዳሴ ከንቱ የማያስቀርባችሁን፣ ውዳሴ ከንቱ የሌለበትን ሌቦች /አጋንንት/ በውዳሴ ከንቱ የማያስቀሩባችሁን ምጽዋት መጽውቱ፤ መጽውታችሁ ባለበት ልባችሁ ከዚያ ይኖራልና ማለት ነው፡፡

7. የሰውነት መብራት፡- የሥጋህ ፋና ዓይንህ ነው፤ ዓይንህ ነው፤ ዓይንህ ብሩህ ይሆናል፤ ዓይንህ የቀና እንደሆነ ሥራህ ሁሉ የቀና ይሆናል፡፡ ዓይንህ የታመመ ከሆነ ጨለማ እንደምን ይጸናብህ? የታመመው ዓይንህ የታመመ ከሆነ ጨለማ እንደምን ይጸናብህ የታመመው ዓይንህ እንደምን ያይልሃል አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም እንደሚከተለው ነው፡፡

 

ሀ. ብርሃን የተባለው አእምሮ ጠባይዕ ነው፤ እዕምሮ ጠባይህ ያልቀና እንደሆነ ሥራህ ያለቀና ይሆናል፤ በተፈጥሮ የተሰጠህ አእምሮ ጠባይህ እንደምን መክበሪያ መጽደቂያ ይሆንሃል ማለት ነው፡፡

 

ለ. ብርሃን የተባለው ምጽዋት ነው፤ ምጽዋትህ ውዳሴ ከንቱ የሌለበት እንደሆነ ሥራህ ሁሉ የቀና ይሆናል፡፡ ምጽዋትህ ግን ውዳሴ ከንቱ ያለበት እንደሆነ ሥራህ ሁሉ ያልቀና ይሆናል፤ ከአንተ የሚሰጥ ምጽዋትህ ውዳሴ ከንቱ ያለበት ከሆነ ፍዳ እንደምን ይጸናብህ ይሆን እንዴትስ መክበሪያ መጽደቂያ ይሆንልሃል ማለት ነው፡፡

 

8. ስለ ሁለት ጌቶች፡- ለሁለት ጌታ መገዛት አይቻለውም፤ ይህም ባይሆን ማለት እገዛለሁም ቢል አንዱን ይጠላል ሌላውን ይወዳል፤ ለአንዱ ይታዘዛል ለሌላው አይታዘዝም ምክንያቱም አንዱ ቆላ ውረድ ሲለው ሌላው ደግሞ ደጋ ውጣ ቢለው ከሁለት ለመሆን ስለማይችል ነው፡፡ እንደዚህም ሁሉ ለእናንተም ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አይቻላችሁም አለ፡፡

 

9. የዕለት ጉርስና የዓመት ልብስ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን ምግብ ከመስጠትማ ነፍስን እም ኀበ አልቦ አምጥቶ መፍጠር አይበልጥምን ልብስ ከመስጠትማ ሥጋን ከአራቱ ባሕርያት አዋሕዶ መፍጠር አይበልጥምን ነፍስንና ሥጋን አዋሕጄ የፈጠርኳችሁ እኔ ትንሹን ነገር ምግብና ልብስን እንዴት እነሳችኋለሁ አለ ምሥጢራዊ መልእክቱም እንደሚከተለው ነው፡፡

 

ሀ. ምግብ ከመስጠትማ ነፍስን ካለችበት ማምጣት አይበልጥምን ልብስ አይበልጥምን ታዲያ ነፍስን ካለችበት አምጥቼ ሥጋን ከመቃብር አስነሥቼ አዋሕጄ በመንግሥተ ሰማይ በክብር የማኖራችሁ እንዴት ምግብና ልብስ እነሳችኋለሁ ማለት ነው፡፡

 

ለ. ሥጋዬን ደሜን ከመስጠትማ ነፍስንና ሥጋን ማዋሐድ አይበልጥምን ታዲያ ነፍስንና ሥጋን ተዋሕጄ ሰው የሆንኩላቸው እኔ እንዴት ሥጋዬንና ደሜን እነሳችኋለሁ ማለት ነው፡፡

 

ስለሆነም ዘር መከር የሌላቸውን፣ በጎታ በጎተራ በሪቅ የማይሰበስቡትን፣ ሰማያዊ አባታችሁ የሚመግባቸውን አዕዋፉን አብነት አድርጉ፡፡ እናንተ ከእነርሱ አትበልጡምን ከተፈጥሮ አዕዋፍ ተፈጠሮተ ሰብእ አይበልጥምን ለኒያ ምግብ የሰጠ ለእናንተ ይነሣችኋልን አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም እግዚአብሔር በምድረ በዳ የመገባቸውን እሥራኤል ዘሥጋን አስቡ፤ በዘመነ ብሉይ ከነበሩት ከእነርሱ በዘመነ ሐዲስ ያላችሁት እናንተ እስራኤል ዘነፍስ የተባላችሁት አትበልጡም ለእኒያ የሰጠሁ ለእናንተ እነሳችኋለሁን ማለት ነው፡፡

ስለ ልብስስ ለምን ትጨነቃላችሁ የሜዳ አበቦች እንዴት እንዲያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ፤አይደክሙም አይፈትሉም ነገር ግን እላችኋለሁ ሰሎሞንስ እንኳ በክብሩ ሁሉ ከነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም፡፡ እግዚአብሔር ግን ዛሬ ያለውን ነገርም ወደ ዕቶን የሚጣለውን የሜዳን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከሆነ እናንተ ሃይማኖት የጎደላችሁ ለእናንተማ እንዴት ልብስ ይነሳችኋል ስለሆነም ምን እንበላለን ምን እንጠጣለን ምን እንለብሳለን ብላችሁ አትጨነቁ፡፡ ይህንንስ ሁሉ ሃይማኖትና ምግባር የሌላቸው አሕዛብ ይፈልጉታል፡፡ እናንተስ አስቀድማችሁ መንግሥቱንና ጽድቁን እሹ፡፡ አስቀድማችሁ ሃይማኖት ምግባርን፣ ልጅነትንና መንግሥተ ሰማያትን ፈለጉ የዚህ ዓለምስ ነገር ሁሉ በራት ላይ ዳራጐት እንዲጨመር ይጨመርላችኋል፡፡ ነገ ለራሱ ይጨነቃልና አትጨነቁ፤ ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል አለ ይህም ለነገ ያጸናናል ብላችሁ አብዝታችሁ አትመገቡ የነገውን ነገ ትመገቡታላችሁና አንድም ነገ እንናዘዘዋለን ብላችሁ ኃጢአታችሁን አታሳድሩ የነገውን ነገ ትናገራላችሁ ማለት ነው፡፡

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ታኅሣሥ 1989 ዓ.ም.