አመልካች /Demonstratives/

 ነሐሴ 8 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመ/ር ደሴ ቀለብ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ መምህር

1. መራሕያን ያልናቸው ሁሉ አመልካቾች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የሚታወቁት ግን እንደሚከተለው በምሳሌ ቀርበዋል፤

ተክለ ማርያም ሖረ ኀበ ደብረ መንክራት

ውእቱ ሖረ ኀበ ደብረ ሊባኖስ

ውእቱ ብእሲ ሖረ ኀበ ደማስቆ

ይእቲ ወለት በልዐት ኅብስተ

ውእቶሙ ሙሉድ አእመሩ ትርጓሜ መጻሕፍት

ውእቶን አንስት ሰገዳ ለእግዚአብሔር አምላከ ኢትዮጵያ

ውእቶን አዋልድ በልዓ ኅብስተ

እሙንቱ ውሉድ አንበቡ ወንጌለ ዮሐንስ

እማንቱ አንስት ሰገዳ ለእግዚአብሔር አምላከ ኢትዮጵያ

ነጠላ                         ብዙ
ውእቱ ያ (that)          ውእቶሙ (ሙንቱ) እነዚያ (those)

ይእቲ ያቺ                  ውእቶን (ማንቱ)

  • እነዚህ ሁሉ የሩቅ ወይም በኅሊና ያለን ነገር ያመለክታሉ፡፡

2. ዝንቲ ብእሲ ሖረ ኀበ ኢየሩሳሌም፣ ይህ ሰው ወደ ኢየሩሳሌም ሔደ፡፡

ዝ ብእሲ ሖረ ኀበ ኢየሩሳሌም፣
ዛቲ ብእሲት መጽአት እምደብረ ታቦር፣ የቺ ሴትዮ ከደብረ ታቦር መጣች፡፡
ዛቲ ብእሲት መጽአት እምደብረ ታቦር፣
እሉ ሰብዕ ሖሩ ኀበ ደብረ ከርቤ ግሸን፣ እነዚህ ሰዎች ወደ ደብረ ከርቤ ሔዱ
እላ ደናግል ቅዱሳት እማንቱ፣ እነዚህ ደናግል ቅዱሳት ናቸው

ነጠላ                            ብዙ
ዝ፣ ዝንቱ ይህ (This)        እሉ እነዚህ (These)

ዛ፣ ዛቲ ይች                   እላ እነዚህ

  • እነዚህ ሁሉ የቅርብን ነገር ያመለክታሉ፡፡

3. ዝኩ መምህረ ቅኔ ውእቱ = ያ ሰው የቅኔ መምህር ነው፡፡

እንትኩ ወለት እኀተ ሙሴ ይእቲ ያቺ ልጅ የሙሴ እኅት ናት

እንታክቲ አስካለ ማርያም ይእቲ

እልኩ ሰብእ ኢትዮጵያዊያን ውእቶሙ = እነዚያ ሰዎች ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡

እልክቱ

እልክቶን ደናግል መጽኣ እምገዳም = እነዚያ ደናግል ከገዳም መጡ፡፡

ነጠላ                                           ብዙ

ዝኩ፣ ዝክቱ (ዝለኩ) = ያ (that)        እልኩ፣ እልክቱ = እነዚያ (those)

እንትኩ፣ እንታክቲ = ያቺ                  እልኮን፣ እልክቶን = እነዚያ

  • እነዚህ ደግሞ እንደ ተራ ቁጥር አንድ የሩቅ ነገርን ያመለክታሉ፡፡

መልመጃ

አዛምድ (አስተፃምር፣ አስተዛምድ)

  1.  ዝኩ           አ. ሖረት

  2. ውእቱ          በ.ቀደስኪ

  3. አንታክቲ        ረ. መጽኣ

  4. እልክቱ         ደ. ነበሩ

  5. ይእቲ          ሀ. ሰገድኪ

  6. እሉ            ለ. ሖርነ

  7. እላ            ሐ. አንበብክሙ

  8. ዝክቱ          መ. ቀደሰ

  9. ዝንቱ          ሠ. ሐርክን

  10. እልኮን

  11. እልኩ

  12. እሙንቱ

የሚከተሉትን ወደ ግእዝ ተርጉም፤ ፈክር (ተርጉም) ኀበ ልሳነ ግእዝ

  1. ያች ልጅ ቆንጆ ናት፡፡

  2. እነዚያ ኤልሳቤጥና ማርያም ናቸው፡፡

  3. ያ የወንጌል ተማሪ ነው፡፡

  4. ይህ መጽሐፍ አዲስ ነው፡፡

  5. እነዚህ የክርስቶስ አገልጋዮች ናቸው፡፡

              ሰላምታ

እፎ ኀደርከ ኁየ = እግዚአብሔር ይሰባሕ

(እንዴት አደርክ ወንድሜ) = (እግዚአብሔር ይመስገን)

ትምህርት እፎ ውእቱ = ሠናይ ውእቱ

(ትምህርት እንዴት ነው) = (ጥሩ ነው)

ማእዜ ውእቱ ዘፈጸምክሙ ፈተናክሙ = ዘዮም ወርኅ

(መቼ ነው ፈተናችሁን የጨረሳችሁት) = (የዛሬ ወር)

በጽባሕ አይቴ ሐዊረከ ውእቱ ዘኢረክብኩከ =ኀበ ከኒሣ /ቤተክርስቲያን/

(በማለዳው ያላገኘሁህ የት ሄደህ ነው) =ወደ ቤተክርስቲያን

በየነ ምንት =በይነ ነገረ ማርያም

(ስለምን) = (ስለ ነገረ ማርያም)

ኩሉ ሰብአ ቤትከ፣ እምከ፣ አቡከ፣ አኁከ፣ ደኅና ወእቶሙ = ወሎቱ ስብሐት

(ሁሉም ቤተሰቦችህ ደህና ናቸው) = (አዎ ምስጋና ለሱ ይሁን)

በል ሠናይ ምሴት ጌሰም ንትራከብ = ኦሆ ለኩልነ

( በል መልካም ምሽት ነገ እንገናኝ) = (እሺ ለሁላችን) 

 

ክረምት

ነሐሴ 7 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዕጉለ ቋዓት፥ ደስያት

ይህ ወቅት ከነሐሴ 10 እስከ ነሐሴ 27 ቀን ድረስ ያሉት 17 ዕለታት የሚጠሩበት ነው፡፡ ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች የሚታወሱበት ጊዜ ሲሆን ወቅቱም ዕጓለ ቋዓት ደስያት ዐይነ ኩሉ ይባላል፡፡ ዕጓለ ቋዓት የሚለው ቃል ቁራን ሲያመለክት፣ ቁራ ሲወለድ ያለ ፀጉር በሥጋው ብቻ ይወለዳል፡፡

 

እናትና አባቱም እነርሱን ባለመምሰሉ ደንግጠው ይሸሻሉ፤ በዚህ ጊዜ የሚንከባከበው ሲያጣ እግዚአብሔር በረድኤት አፉን ከፍቶ ምግብ ሲሻ ተሐዋስያንን ብር ብር እየደረገ ከአፉ ያስገባለታል፡፡ “ልጆቹ ወደ እግዚአብሔር ሲጮኹ፥ የሚበሉትም አጥተው ሲቅበዘብዙ፥ ለቁራ መብልን የሚሰጠው ማን ነው? ” (ኢዮ.38፥41) ተብሎ እንደ ተገለጠው እግዚአብሔር የሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናትና አባቱ ያለ ፀጉር ያወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ እናትና አባቱ ቀርበው ይንከባከቡታል፡፡ በሥነ ፍጥረት አቆጣጠር ግን በክንፍ የሚበሩ አዕዋፍን ሁሉ ይወክላል፡፡

 

ይህም አምላካችን እግዚአብሔር ለፍጥረቱ ሁሉ የሚያስብ በመሆኑ ይህን ዘመን ርኅርሔ ለተመላው አምላክነቱ ሥራው መታሰቢያ እንዲሆን ቤተ ክርስቲያን ዕጓለ ቋዓት በማለት ታስታውሰዋለች፡፡

ደስያት ማለት በውኃ የተከበቡ ቦታዎች ማለት ነው፡፡ እነዚህን ቦታዎች በውኃ እንዲሸፈኑ አድርጎ በውስጣቸው ያሉትን ሰዎች እንስሳት አራዊት አዕዋፍ ሁሉ የሚጠብቃቸው፣ በተስፋና በእምነት አበርትቶ የሚያኖራቸው እግዚአብሔር ነው፡፡ ይህን ድንቅ ሥራ ያዩ በውስጥ በውጭ ያሉት ሰዎች እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል፡፡ በደሴት (በቤተ ክርስቲያን) የተጠጉ ሁሉ ከሞተ ሥጋና ከሞተ ነፍስ ይጠበቃሉ፡፡

በዚህ ወቅት፡- ክፍለ ክረምቱ እንደተገባደደ፥ ውኃው እየጠራ፣ መሬቱ እየረጋ፣ ደመናውና ጉሙ እየተቃለለ፣ የወንዞች ሙላት እየቀነሰ፣ የክረምት ምግባቸውን ይዘው በየዋሻው የከረሙ ጭልፊቶችን አሞራዎች ድምፃቸውን እየሰሙ ምግብ ፍለጋ ሲወጡ የሚታዩበት ወቅት ነው፡፡

በተጨማሪም ከነሐሴ 27-29 ያለው ጊዜን “ሞተ አበው” በመባል ይታወቃል፡፡ ከ22ቱ አርእስተ አበው የአብርሃም ይስሐቅና ያዕቆብ ቤተሰቦቻቸው ዕረፍት ይታሰባል፡፡ ቅዱስ መጽሐፋችንም “አብርሃም ልጁን ይስሐቅን ሊሰዋ ወጣ፤ እግዚአብሔር ቤዛ አድርጎ ቀንዱ በዕፀ ሳቤቅ የተያዘ በግ አወረደለት” በማለት የአብርሃምን ታዛዥነት የይስሐቅን ቤዛነት ያወሳል፡፡ የተቀበሉትም ቃል ኪዳን “ወተዘከረ ሣህሎ ዘለዓለም ዘሠርዓ ለአብርሃም ወመሐለ ለይስሐቅ ወዐቀመ ስምዐ ለያዕቆብ ያርኁ ክረምተ ይገብር ምሕረተ እም ሰማይ ይሁብ ወእምድር በረከተ ያጸግብ ነፍስ ርኅብት” በማለት ይዘመራል፡፡

 

ፍልሰታና ሻደይ

ነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም.

ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በኋላ በመላው ዓለም የክርስትና እምነት በሐዋርያቱ መሰበክ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በኢትዮጵያ ሀገራችን የክርስትና እምነት ተሰብኳል፡፡  በተለይም ሀገራችን የሰሜኑ ክፍል  ህዝበ ክርስቲያኑ ለረጅም ዘመናት ሥርዓተ አምልኮ ሲፈጽምባቸው እንደነበሩና አሁንም አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነ በአካባቢው የሚገኙ በርካታ ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናትና መንፈሳዊ ቁሶች ያስረዳሉ። እነዚህም የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ መንፈሳዊ ቅርሶች ናቸው። ከማይዳሰሱ መንፈሳዊ ቅርሶች መካከል የተለያዩ መንፈሳዊ በዓላት የሚከበሩበት ሥርዓት አንዱ ነው።

asendya 01በዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ከሚከበሩ በዓላት መካከል የሻደይ ምስጋና / ጨዋታ አንዱ ሲሆን ልጃገረዶች በአማረ ልብስ ደምቀው አሸንድዬ በሚባል ቄጠማ ጉንጉን ወገባቸውን አስረው የሚያከብሩት ነው። በዓሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃማኖታዊ ይዘት አለው። በዓሉ ከነሐሴ 16 ጀምሮ እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ ይከበራል። ይህ በዓል በዋግ ኽምራ ሻደይ፣ በላስታ አሸንድዬ፣ በትግራይ አሸንዳ፣ በቆቦ አካባቢ ሶለል፣ በአክሱም አካባቢ ደግሞ ዓይነ ዋሪ እየተባለ ይጠራል።

የሻደይ በዓል ከኦርቶዶክስ ተዋሐዶ እምነት ጋር እየተያያዘ የመጣ ሲሆን አጀማመሩ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መነሻ አለው፡፡ ከነዚህም መካከል የአዳም ከገነት መባረር፣ የኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ፣ ከዘመን መለወጫ፣ ከመጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አንገት መቆረጥ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ (ፍልስታ) እና ከመስፍኑ ዮፍታሔ ልጅ ታሪክ ጋር በማስተሳሰር የሚያስቀምጡት ሲሆን በማኅበረስቡ አባቶችና ሊቃውንቱ ዘንድ ጎልቶ የሚነገረውና የሚተረከው ግን የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ (ፍልስታ) በዓልን መሠረት ያደረገ ነው።

አባታችን አዳም በገነት ሳለ ሕግ በመተላለፉ ጸጋ እግዚአብሔር ርቆት እርቃኑን በሆነ ጊዜ አካሉን ለመሸፈን ቅጠል መጠቀሙን ለማሰብ ያች አዳምና ሔዋን ክብራቸውን ተገፈው ከገነት የተባረሩባትን ዕለት በማሰብ በወቅቱ ያገለደሙትን ቅጠል በምልክትነት በመውሰድ የሻደይ ቅጠልን በገመድ ላይ ጎንጉነው በወገባቸው አገልድመው/አስረው/ አዳምና ሔዋን ከገነት ከመውጣታቸው በፊት ግብረ ሥጋ ግንኙነት ያልጀመሩ ደናግላን ስለነበሩ ያንን በመከተልና በምሳሌነት በመውሰድ ያላገቡ የአገው ልጃገረዶች ተሰባስበው ያችን ዕለት ወይም ቀን በመታሰቢያነት ለመቁጠር ወይም ለመዘከር የሻደይ ጨዋታን መጫወት ወይም ማክበር እንደጀመሩ ይናገራሉ።

ከኖኅ ዘመን ታሪክ ጋር ያለው ግንኙነት ደግሞ ከጥፋት ውኃ በኋላ ውኃው የመጉደሉን ምልክት ርግብ ለኖኅ የለመለመ የወይራ ቅጠል ይዛ በመምጣት በምድር ሰላም እነደሆነ የምሥራች አብሥራለች። ከዚሁ ጋር በተገናኘ በዓሉን ያንን ለምለም ቅጠል ወገባቸው ላይ በማሰር ከጨለማ ወደ ብርሃን ተሸጋገርን ሲሉ ማክበር እንደጀመሩ ከታሪኩ ጋር አያይዘው ያስቀምጡታል።

ከመስፍኑ ዮፍታሔ ታሪክ ጋርም ቢሆን የሻደይ በዓል እንዴት ግንኙነት እንዳለው ሲያስቀምጡ ዮፍታሔ ወደ ጦርነት በሔደ ጊዜ በድል ከተመለስ ለአምላኩ መሥዋዕትን ለማቅረብ ስዕለት ገበቶ ነበር። ይህም ከቤቱ ሲመለስ መጀመሪያ የሚቀበለውን እንደሚሠዋ ሲሆን በዚህ ጊዜ ያለ ወትሮዋ ልጁ እየዘፈነች ልትቀበለው ወጣች በዚህም በጣም አዘነ። ልጁም ለአምላኩ የገባውን ስዕለት እንዳያስቀር ሁለት ወር ስለ ድንግልናዋ አልቅሳ ስዕለቱን እንዲፈጽም ጠይቃው ከሁለት ወር በኋላ ስዕለቱን የፈጸመ ሲሆን አባቷ የገባውን ቃል ኪዳን እንዳያጥፍ ያበረታታችውንና መሥዋዕትነትን ለሀገር፣ ለህዝብ፣ ለአባትና ለፈጣሪዋ የከፈለችውን የዮፍታሔን ልጅ በየዓመቱ ለአራት ቀናት ሙሾ በማውጣት አስበው ይውላሉ፡፡ በዚህ መሠረት በበዓሉ ላይ ከሚፈጸሙ ተግበራት ጋር አዛምደው መነሻው ከዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ እንደሆነ ይናገራሉ። “ጽዮንን ክበቡዋት በዙሪያዋም ተመላለሱ…በብርታትዋ ልባችሁን አኑሩ፣ ለሚመጣው ትውልድ ትነግሩ ዘንድ” መዝ 48፥12

 

የሻደይ በዓል አጀማመርን በተመለክተ ከላይ ከተቀመጡት ታሪኮች በተጨማሪ በአካባቢው ሕዝብና በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንቶች ዘንድ ተደጋግሞ የሚነሣው ታሪክ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ በዓል ሲሆን ይኸውም እግዚአብሔር አምላክ ለአዳምና ሔዋን ከ5500 ዘመን በኋላ ወደዚህ ዓለም አንድያ ልጁን ልኮ ከኃጢያት እሥራት ነጻ እንደሚያወጣቸው በገበላቸው ቃልኪዳን መሠረት አምላክ የተወለደባት እና ትንቢቱ የተፈጸመባት፣ በሔዋን ስህተት ከገነት የተባረረው የሰው ልጅ በእርሷ ምክንያት ከኃጢያት ባርነት ነጻ የወጣባትና ወደ ቀድሞ ቤቱ ገነት እንዲመለስ ምክንያት የሆነችው የሰው ልጅ መመኪያ የተባለች እመቤት፣ እንደማንኛውም ሰው የተፈቀደላትን እድሜ በምድር ከኖረች በኋላ ሞተ ሥጋን እንደ ሞተች ከመጽሐፍት እንረዳለን፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከዚህ በኋላ ሞትን ድል አድርጋ ከመቃብር ተነሥታ ወደ ሰማይ አረገች፡፡

በፍልሰታ ወቅት በዓሉ መከበሩም ለሻደይ ተጨዋቾች ተምሳሌትና የድንግልናቸው አርዓያ የሚያደርጓት ድንግል ማርያም አካላዊ ሥጋዋ ከጌቴሰማኔ ወደ ገነት መፍለሱን እንዲሁም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ከነበረበት መነሣቱን ምክንያት በማድረግ እንደሆነ የዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ስብከተ ወንጌል መምሪያ ሓላፊ የሆኑት መጋቢ ምስጢር ገብረ ሕይወት ኪዳነ ማርያም “በዓሉ በልጃገረዶች ዘንድ ተወዳጅ የሆነው በሄዋን ምክንያት የተዘጋው ገነት በእመቤታችን አማካኝነት በመከፈቱ ነው። መመኪያቸው ስለሆነች ልጃገረዶች በዓሉን ያከብሩታል ድንግልናቸውንም አደራ የሚሉት በእርሷ ነው” ሲሉ ይናገራሉ።

ዕርገቷን መላዕክት በእልልታ፣ በሽብሸባና በዝማሬ ነጫጭ ልብስ ለብሰው አጅበዋት ነበር፡፡ ዕለቱን ፍስለታ ብለን የምንጠራውም ማርያም ከሞት ተነሥታ ማረጓን፣ ሙስና መቃብር አፍልሳ መነሣትዋን ወይም ዕርገቷን በማሰብ ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችን በነሐሴ 16 ቀን እንደ አዲስ በመላዕክት ሽብሸባ፣ እልልታ፣ ዝማሬና ዝማሜ ታጅባ ከምድር ወደ ሰማይ ስታርግ እንዳዩ፡፡ በታላቅ ፍስሃ ይመለከቱና በታዓምራቱ ይደነቁም ነበር፡፡ ከዛን ዕለት ጀምሮ ደናግል ቅዱሳን ከመላእክቱ በተመለከቱት ሥርዓት መነሻነት ባህላዊ ነጫጭ ልብሶችን ለብሰው፣ አምረውና አጊጠው፣ የወቅቱ መታሰቢየ የሆነውን ለምለሟን ከምድር ሳሮች ሁሉ ረዘም ያለችውን የሻደይ ቅጠል በወገባቸው አስረው እንደ መላአክቱ አክናፍ ወገባቸውን ከግራ ወደ ቀኝ እያመላለሱ በማሽከርከር እያሸበሸቡ፣ በአንደበታቸው እየዘመሩና በእጆቻቸው እያጨበጨቡ በአንድነት ተሰባሰባስበው በፍቅርና በሐሴት ከነሐሴ 1 ቀን ጀምሮ በመጾም ጾሙ ከሚፈታበት ከዳግም ዕርገቷ ነሐሴ 16 ጸሎታቸው ተሰምቶላቸው የፈለጉትን ማየታቸውን ምክንያት በማድረግ እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ በየዓመቱ ማክበር እንደተጀመረ ይነገራል፡፡

እናቶችና እኅቶች በአደባባይ ወጥተው የድንግል ማርያምን ሞትን ድል አርጎ መነሣት ትንሣኤዋንና ዕርገቷን እንደ ነጻነታቸው ቀን ቆጥረው የተለያዩ አልባሳትን በማድረግና ለበዓሉ ክብር በመስጠት ከበሮ አዘጋጅተው አሸነድዬ የተባለውን ቄጠማ በወገባቸው ታጥቀው ምስጋና በማቅረብ በዓሉን ይዘክራሉ፡፡ በዚህም መሠረት የሻደይ ጨዋታ የፍስልታ በዓል መከበር ከጀመረበት ጊዜ አንሥቶ እንደተጀመረና በምእመኑ ለረጅም ጊዜ እየተከበረ የኖረ ሃይማኖታዊ በዓል እንደሆነ ይታመናል፡፡

የሻደይ ልጃገረዶች የቡድን አመሠራረት ደብርን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ የሻደይ ጨዋታ በዓል በሚያከብሩበት ጊዜ ልጃገረዶች የተለያዩ ባህላዊ አልባሳትን ለብሰው ከበሮ እና ለምስጋናው የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላት ተጠራርተው በመጀመሪያ ወደ አጥቢያቸው በመሄድ የቤተ ክርስቲያኑን ደጁን አልፈው ይዘልቃሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኑን ደጅ ከተሳለሙ በኋላ የተለያዩ ጣዕመ ዝማሬ እያሰሙ ሦስት ጊዜ ይዞሩና ደጃፉን ተሳልመው በቅጥር ግቢው አመቺ ቦታ ፈልገው ምስጋናቸውን ይጀምራሉ፡፡ ከበሮአቸውን እየመቱ፣ የታቦቱን ስም እየጠሩ በሚያምር ድምፃቸው፣ ሽብሻቦ፣ ውዝዋዜ፣ ጥልቅ መልእክትን በያዙ ግጥሞች፣ ለዚህ ያደረሳቸውን አምላክና ታቦት ያወድሳሉ፣ ያሞግሳሉ፣ ያከብራሉ፣ ይለማመናሉ፡፡ ምስጋናው ለዚህ ዓመት ያደረሳቸውን አምላክ የሚያመስግኑበት እና ቀጣዩ ዓመትም እንደዚሁ የሰላም፣ የጤና የተድላ እንዲሆን የሚማጸኑበት፣ ተስፋቸውን የሚገልጹበትና ስለት የሚሳሉበት በመሆኑ ምስጋናውን ሞቅ፣ ደመቅ አድርገው ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ በፍቅር፣ በደስታ፣ በመተሳሰብና በሰላም ይጫወታሉ፡፡ እያንዳንዱ አባል ለእግዚአብሔርና ለደብራቸን ታቦት ያልሆነ እያሉ ጉልበታቸውን፣ ችሎታውንና ልምዳቸውን ሳይቆጥቡ በምስጋናው ይሳተፋሉ።

ከቤተ ክርስቲያን መልስ በአካባቢው ወዳሉት ትልልቅ አባቶች ዘንድ ሄደው በመዘመር ምርቃን ይቀበላሉ። ከዚያ መልስ ወደ ተራራማ ስፍራ በመውጣት ክብ ሠርተው ይዘምራሉ፡፡ ከዝማሬያቸው ውስጥ ግጥሞቹ መንፈሳዊ ይዘት ያላቸው ግጥሞች ከግለሰባዊ ስሜት ወይም ከግለሰብ ውዳሴ የራቁ ናቸው፡፡ የቡድን አመሠራረታቸው ደብርን መሠረት ያደረገ በመሆኑ አንዱ ቡድን ከሌላው ቡድን የተሻለ መሆኑን ለማሳየት ፣ የደብሩን ኃያልነት፣ ደብራቸውን እንደማያስደፍሩና እንደሚጠብቁ በምስጋናቸው ይገልጻሉ፡፡

የወከሉትን ደብር ታቦት ስም እየጠሩ ለአባት እናት፣ ለቤተሰብ ጤና፣ ጸጋ፣ ሀብት፣ ሰላም በአጠቃላይ መልካሙን ሁሉ እንዲያድላቸው ይማጸናሉ፡፡ አደራውን ለታቦቱ ይሰጣሉ፡፡ ለዚህም ዜማውና ግጥሙ ተመሳሳይ ቢሆንም የወከሉትን ደብር ስም ብቻ በማቀያየር በተመሳሳይ ዜማና መወደስ እና መማጸን በሁሉም የሻደይ ተጨዋች ቡድኖች ይታይል፡፡ ልጃገረዶቹ በዚህ የምስጋና ጊዜ የሚሰበሰቡትን ሥጦታዎች ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን ይሰጣሉ።

የሻደይ ምስጋና/ጨዋታ በዚህ መልኩ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በማመስገን ከፍከፍ በማድረግ ዕርገቷን በማሰብ የአምላክ እናት አማልጅን እያሉ ስሟን በመጥራትና በማክበር የሚከናወን በመሆኑ ይህንን ሃይማኖታዊ መሠረትነት ያለውን ትውፊት የመጠበቅና የማስጠበቅ ሓላፊነት ከሁላችን ይጠበቃል። የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን፡፡

  • ምንጭ፡-ሰቆጣ ማእከል ሚዲያ ክፍል

 

ደብረ ታቦርና ቡሄ

 ነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

የኢትየጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው ዘጠኝ ዓበይት በዓላት አንዱ የደብረ ታቦር በዓል ነው። በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን የሚከበረው ይህ በዓል መሠረቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ደብረ ታቦር ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስት ደቀመዛሙርቱን ይዞ ወደ ተራራው የወጣበትና ፊቱ እንደ ፀሐይ የበራበት፣ ልብሱም እንደብርሃን ነጭ የሆነበት፣ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ተራራ ነው።

ከስድስት ቀንም በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው። በፊታቸውም ተለወጠ፥ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፥ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ። እነሆም፥ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው። ጴጥሮስም መልሶ ኢየሱስን ጌታ ሆይ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ፥ በዚህ ሦስት ዳስ አንዱን ለአንተ አንዱንም ለሙሴ አንዱንም ለኤልያስ እንሥራ አለ። እርሱም ገና ሲናገር፥ እነሆ፥ ብሩህ ደመና ጋረዳቸው፥ እነሆም፥ ከደመናው። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት የሚል ድምፅ መጣ። ደቀ መዛሙርቱም ሰምተው በፊታቸው ወደቁ እጅግም ፈርተው ነበር።

 

ኢየሱስም ቀርቦ ዳሰሳቸውና፡ ተነሡ አትፍሩም አላቸው። ማቴ. ፲፯፡፩-፭ በቤተ ክርስቲያን ደብረታቦር ከቤተክርስቲያን ውጭ አከባበሩ ቡሄ እየተባለ የሚከበረው በዓል በሀገራችን በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡ ቡሄ ማለት ብራ፣ ብርሃን፣ ደማቅ ገላጣ፣ የተገለጠ ማለት ነው፡፡ ቡሄ ሲመጣ የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ወደ ብርሃን፣ ወደ ጥቢ የሚያመራበት፣ ወደ መፀው የሚዘለቅበት ወገግታ ፣ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚለወጥበት፣ የሚሸጋገርበት ወቅት በመሆኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ በዚህ መሰረት የክረምቱ አፈና ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታየውም በዚህ በዓል አካባቢ ስለሆነ ይቺ ዕለት ‘ቡሄ’ የሚለውን ስያሜ አገኘ። ቡሄ ማለት ገላጣ፣ የተገለጠ ማለት ነው፡፡ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት፣ ብረሃን የታየበት ድምጸ መለኮት የተሰማበት ስለሆነ፤ ችቦ ስለሚበራ የብርሃን በዓል በማለት የቡሄ በዓልም ይባላል፡፡

 

በገጠርም ሆነ በየከተማው ልጆች ጅራፋቸውን ገምደው ሲያጮሁ ይሰነብታሉ። እናቶችም ለበዓሉ ዝግጅት ስንዴ ሲለቅሙ፣ ሲፈትጉ፣ ሲፈጩ ይሰነብታሉ። መነሻ የሆናቸው ትውፊት ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ዕለት ጊዜው ምሽት ነበር፡፡ እረኞችም ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል ፡፡ያንን ለማስታወስ «ቡሄ» ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና ችቦ በማብራት በዓሉን የሚከበረው ከዚህ በመነሣት ነው፡፡ የንጋት ወጋገን ሲፈናጠቅ ልጆች በከባድ ድምጽና በጅራፍ ጩኸት የሚታጀብ፣ በገደላገደል ስር እንዲያስተጋባ ተደርጎ ብዛት ባላቸው ህጻናት በከፍተኛ ድምጽ የሚዘመር ነው ቡሄ ። የጅራፉ ጩኸትም እግዚአብሔር አብ “የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት” ሲል ሐዋርያት ራሳቸውን ስተው የወደቁበትን የመለኮት ድምፅ ለማስታወስ ነው፡፡

 

ደብረታቦር ወይም ቡሄ በአብነት ተማሪዎች “ስለ ደብረ ታቦር” እያሉ እህል፣ ፣ ጌሾ ለምነው ጠላውን ጠምቀው፣ ዳቦውን ጋግረው፣ ቆሎውን ቆልተው ለደብረ ታቦር ዕለት ሊያስቀድሱ የመጡትን ምዕመናን በመጋበዝ በታላቅ ድምቀት ያከብራሉ፡፡ ይህ ትውፊት መምህረ ሐዋርያት የነበረው ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን ተማሪዎቹን ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ደብረ ታቦር ይዞ ሄዶ የተገለጠ ምስጢር ስለሆነ ከመምህራቸው ጋር በመሆን በዓለ ደብረ ታቦርን /ቡሄን ያከብራሉ፡፡ ስሙን ይጠራሉ፡፡

የደብረ ታቦር ወይም የቡሄ ግጥሞች

ድምጽህን ሰማና በብሩህ ደመና
የቡሄው ብርሃን ለኛ መጣና

ያዕቆብ ዮሃንስ ሆ! እንዲሁም ጴጥሮስ
አምላክን አዩት ሆ! ሙሴ ኤልያስ
አባቱም አለ ሆ! ልጄን ስሙት
ቃሌ ነውና ሆ! የወለለድኩት

ድምጽህን ሰማና በብሩህ ደመና
የቡሄው ብርሃን ለኛ መጣና።
መጣና መጣና ደጅ ልንጥና

መጣና ባመቱ እንዴት ሰነበቱ፣
ክፈት በለዉ በሩን የጌታዪን
ክፈት በለዉ ተነሳ ያንን አንበሳ፣

የመሳሰሉት

 

awa mer 2006 1

በሐዋሳ በተለያዩ ቋንቋዎች የሚያስተምሩ ሰባኪያነ ወንጌል ተመረቁ

ነሐሴ 2 ቀን 2006 ዓ.ም.

በዲ/ን ያለው ታምራት ከሐዋሳ ማእከል

awa mer 2006 1በማኅበረ ቅዳሳን ሐዋሳ ማዕከል በተለያዩ አምስት ቋንቋዎች የሚያስተምሩ 33  ሰባኪያነ ወንጌል በሐዋሳ ካህናት ማሠልጠኛ ለአንድ ወር በቀንና በማታ ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ትምህርቶችን እና ሥልጠናዎችን ሲከታተሉ ቆይተው ብፁዕ አቡነ ገብርኤል  የሲዳማ፣ የጌዲኦ፣ የአማሮና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት  ሐምሌ 27 ቀን 2006 ዓ.ም በሐዋሳ ደብረ ምጥማቅ  መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በድምቀት አስመረቀ፡፡

awa mer 2006 2ተመራቂ ሰልጣኞቹ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ባልተስፋፋባቸው የገጠር አብያተ ክርስቲያናት መካከል ከሲዳማ፣ ከጌዲኦ፣ ከአማሮና ከቡርጂ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ ሲሆን፤ በሲዳምኛ፤ በጌዲኦኛ፤በኩየርኛ፤በቡርጂኛና በኦሮምኛ ቋንቋዎች የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ በአንድ ወር ቆይታቸውም ከሚሰጣቸው መንፈሳዊ ትምህርት በተጨማሪ በስብከት ዘዴ ላይ ያተኮረ የልምምድ ልውውጥ አድርገዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ለተመራቂዎቹ የምስክር ወረቀት፤ ለአገልግሎት የሚጠቀሙበት መጽሐፍ ቅዱስ እና ማጣቀሻ መጸሕፍትን ከሰጡ በኋላ ባስተላለፉት መልእክት “ከአማርኛ እና ግዕዝ በተጨማሪ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ማስተማር ግዴታችን ነው፤ ሥልጠናውም ወደፊት ተጠናክሮ በመቀጠል አለበት” ብለዋል፡፡

 

በዕለቱ ተመራቂ ሠልጣኞች በደብረ ምጥማቅ መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን ለተገኘኙ ምእመናን በቋንቋቸው በማስተማር ያገለገሉ ሲሆን፤ ምዕመናንም ይህን ላደረገ እግዚአብሔር በእልልታ እና በጭብጨባ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

 

የሐዋሳ ማእከል ሰብሳቢ ቀሲስ ደረጀ ሚደቅሶ በበኩላቸው ማኅበረ ቅዱሳን የሐዋሳ ማእከል በተከታታይ ለስድስት ዓመታት በተመሳሳይ መልኩ በተለያዩ ቋንቋዎች ያሰለጠናቸው ሰባኪያነ ወንጌል ቁጥር 274 ማድረሱን ገልጸዋል፡፡ ሠልጣኞችም ወደ መጡበት የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ተመልሰው ምእመናን በሚገባቸው ቋንቋ እያስተማሩ በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ፤ ወደ ሌላ እምነት የተቀየሩትንም አስተምረው ወደ እናት ቤተክርስቲያናቸው እንዲመልሱ የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ከሀገረ ሰብከቱ ሊቀ ጳጳስ በተጨማሪ የሀገረ ሰብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ የደብር አለቆች፣ ካህናትና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

 

adama 2006 1

የአዳማ አቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤትን ለመገንባት የመሠረት ድንጋይ ተቀመጠ

ነሐሴ 2 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

adama 2006 1በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ለሚያስገነባው የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የአጸደ ሕፃናትና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳይ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የበላይ ሓላፊ ሐምሌ 27 ቀን 2006 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ አኖሩ፡፡

adama 2006 2በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳይ መሪነት፤ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፤ የናዝሬት ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ካህናትና አገልጋዮች፤ የማእከሉ አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው ምእመናን በተገኙበት ጸሎተ ወንጌል በማድረስ ብፁዕነታቸው የመሠረት ድንጋይ ባኖሩበት ወቅት በሰጡት ቃለ ምእዳን “ከሁሉም ነገር በፊት የሰው ሀብት ዕውቀት ነው፡፡ ዕውቀት ደግሞ የማይሠረቅ ሀብት በመሆኑ የማይሠረቀውን፤ የማይዘረፈውን ሀብተ እግዚአብሔርን መያዝ መልካም ነው፤ የመሠረት ድንጋይ የምናኖረውም ድንቁርናን ለማጥፋት ነው” ብለዋል፡፡

ማኅበሩ የሚያከናውናቸው ዘርፈ ብዙ ተግባራትና ለቤተ ክርስቲያን እያበረከተ ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት ብፁዕነታቸው “ሁላችንም የምንሠራው የቤተ ክርስቲያናችንን ሥራ በመሆኑ፤ መሠረቱም፤ ጣሪያውም አንድ ነው፡፡ የማኅበሩ አባላት ቤተ ክርስቲያናችሁን እንደምትወዱ፤ እንደምታከብሩም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታውቃለች፤ ሁላችንም እንመሠክራለን፡፡ ትውልድን በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ኮትኩቶ ማሳደግ ተገቢ በመሆኑ ከጎናችሁ ነን፤ በርቱ” በማለት የትምህርት ቤቱ ሕንፃ ግንባታ በፍጥነት ተጀምሮ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት እንዲበቃ ተመኝተዋል፡፡

adama 2006 3ቀሲስ እሸቱ ታደሰ የማኅበሩን መልእክት ሲያስተላልፉ “ማኅበረ ቅዱሳን የተማረ ትውልድን ለመቅረጽ፤ ትምህርት ለማስፋፋት እንደ አንድ ዓላማ አድርጎ በመያዝ በየአኅጉረ ስብከቱ ዐሥር ትምህርት ቤቶችን በመክፈት ቤተ ክርስቲያንን የሚያውቅና በዕውቀት የበለጸገ ትውልድ ለማፍራት በመሥራት ላይ ነው፡፡ የአዳማ ማእከል ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ቤት ተከራይቶ የዐፀደ ሕፃናትና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በመክፈት አገልግሎት እየሠጠ ቢሆንም፤ የተማሪዎቹ ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከተ በመምጣቱ ሰፋ ያለ ቦታ ማግኘት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ሆነ፡፡ በዚህም መሠረት የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን በማስፈቀድ በአንድ ሚሊዮን ብር ከአባላት በማሰባሰብ በአዳማ ከተማ መሬት በመግዛት በዛሬው እለት በብፁዕነታቸው የመሠረት ድንጋይ ለማኖር በቅተናል” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ሕፃናትን በቃለ እግዚአብሔር ኮትኩቶ ማሣደግን ከፍተኛ ትኩረት ይሰጡ እንደነበር የገለጹት ቀሲስ እሸቱ ከብፁዕነታቸው ኅልፈት በኋላም በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሣይ ቀጣይነት ኖሮት በዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የካህናት ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት፤ እንዲሁም በሀገረ ስብከታቸው የሚያከናውኗቸው የትምህርትና የልማት ሥራዎች ለሁሉም አርአያ እንደሚሆኑ ተናግረዋል፡፡

የአዳማ አቡነ ጎርጎርዮስ የአጸደ ሕፃናትና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በ2004 ዓ.ም. ቤት ተከራይቶ 32 ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር የጀመረ ሲሆን፤ የማእከሉ አባላት የቤት ኪራይ በመክፈል፤ የጽዳት ሥራውን በማሰራት፤ እንዲሁም ጊዜያቸውን መሥዋዕት በማድረግ በነጻ ያስተምሩ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታቸው እንደሆነ አባላቱ ይገልጻሉ፡፡

በ2300 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የሚገነባው ባለ4 ፎቅ የተማሪዎች መማሪያ ሕንፃ 12 ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅም ከማእከሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

የጎንደር መካነ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን

 ነሐሴ 1 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

ክፍል ሦስት

የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርና ሰበካ ጉባኤ እንቅስቃሴ

በጎንደር በአራት ቦታዎች ላይ የትርጓሜ መጻሕፍት ጉባኤ ቤቶች ይገኛሉ፤ ትምህርትም በተጠናከረ ሁኔታ ይሰጥባቸዋል፡፡ ነገር ግን ለቤተ ክርስቲያን ባለውለታ የሆኑት የመምህር ኤስድሮስ ወንበር በልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ታጥፏል፡፡ ይህንን ገጽታ ለመቀየርና የመምህር ኤስድሮስን ወንበር ወደነበረበት ለመመለስ የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርና ሰበካ ጉባኤው ሰፊ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡

ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ጉባኤ ቤቶቹን ዳግም ወደነበሩበት ለመመለስ ጥረት ሲያደርጉ የነበረ ቢሆንም ለፍጻሜ ሳይበቃ ወደ ደቡብ ጎንደር ተቀይረው ሄዱ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ ተግባራዊ ባይሆንም በቅርቡ አንድ ውጤት ላይ ለመድረስ ጠንክረው እንደሚሰሩ አስተዳደሩና ሰበካ ጉባኤው ይገልጻሉ፡፡ ወደፊት ሊሰሩ ከታቀዱ ሥራዎች መካከል አንዱ የጉባኤ ቤቱን ጥንት ወደነበረበት መመለስ ይገኝበታል፡፡

ከታቀዱት የልማትና የአገልግሎት ሥራዎች መካከል ቅድሚያ የሚያደርጉት ቤተ ክርስቲያኗ ሙሉ አገልግሎት መስጠት የምትችልበትን ሁኔታ ማመቻቸት በመሆኑ፤ ካህናቱ የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲሰጡ በትምህርት ብቃታቸውን ማሳደግ ላይ ትኩረት ተሰጥቶበት እንደሚሠራ ይገልጻሉ፡፡ ለዚህም ብቃት ያላቸው መምህራንን በማዘጋጀት፤ ከማኅበረ ቅዱሳን ጎንደር ማእከል ጋር በመተባበር በወንጌል ትምህርት በቂ ልምድ እንዲኖራቸው በመሥራት ላይ እንደሚገኙ ይናገራሉ፡፡

“በልደታ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ጥላ ዘቅዝቆ መለመን አይቻልም፡፡ ምእመናን ሳይሳቀቁ ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው በነፃነት ጸሎት አድርሰው፤ ቡራኬ ተቀብለው እንዲሄዱ ምቹ ሁኔታዎችን ፈጥረናል ለማለት እንችላለን፡፡ ምእመናንን በልመና ማሳቀቅ አይገባም፤ አስበውና ደስ ብሏቸው ነው መሥጠት የሚኖርባቸው” በማለት የሰበካ ጉባኤው ምክትል ሰብሳቢ ዲያቆን ሙሉቀን ብርሃኑ ይገልጻሉ፡፡

በቤተ ክርስቲያኗ አገልገሎት አይቋረጥም፤ ሊቃውንቱም የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት ጠብቀው ያገለግላሉ፡፡ ለአብነት ተማሪዎች ቤት ተሰጥቷቸው፤ የመብራትና ውኃ ተከፍሎላቸው በመማር ላይ ይገኛሉ፡፡ በእንተ ስማ ለማርያም በሚሰማሩበትም ወቅት ምእመናን ስለሚያውቋቸው ያላቸውን ሰጥተው ይሸኗቸዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያኗ ጽ/ቤት በእያንዳንዱ አገልጋይ ካህን ስም ፋይል ከፍቶ የንስሐ ልጆቻቸውን ስም ዝርዝር እንዲያስመዘግቡ ተደርጓል፡፡ እያንዳንዳቸው የንስሐ ልጆቻቸውን በአግባቡ በመያዝና በመምከር፤ ቢያንስ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ከንስሐ ልጆቻቸው ጋር እንዲገናኙ በማድረግ፤ በየቤታቸው እየተገኙ ጸሎት አድርስው፤ ጠበል ረጭተውና አስተምረው የመመለስ ግዴታ እንዳለባቸው በመረዳት ይህንኑ በተግባር ላይ እያዋሉት ይገኛሉ፡፡ አስተዳደሩም ይከታተላል፡፡ የንስሐ አባቶቻቸው የሚፈለግባቸውን ሓላፊነት ካልተወጡና የሥነ ምግባር ችግር እንዳለባቸው ካረጋገጡ ምእመናን ወደ ጽ/ቤት በመምጣት ሪፖርት ያደርጋሉ፡፡ አስተዳደሩም ችግሩን ለመፍታት ጥረት ከማድረግ አንስቶ አስተዳደራዊ እርምጃ ይወስዳል፡፡

ምእመናን ሓላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ በማድረግ ረገድ ለካህናት ብቻ የተተወ ባለመሆኑ የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደር መምህራንን በመመደብ፤ ትምህርተ ወንጌል የሚያገኙበትን ሁኔታ በማመቻቸት አንድ ክርስቲያን በክርስትና ሕይወት ውስጥ እስካለ ተገቢውን አገልግሎት እንዲያገኝ ይደረጋል፡፡ ምእመናን ሓላፊነታቸውን ለመወጣት የሚያደርጉት ጥረት የሚበረታታ ነው፡፡ አሥራት በኩራት ከማውጣት አንስቶ ንስሐ በመግባት ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን በመቀበል በሕይወታቸው ለሌሎች አርአያ የሚሆኑ ምእመናን ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥራቸው በመጨመር እየፈሩ ነው፡፡

የልማት እቀዶች፡-

የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደር የልማት ሥራዎችን በመሥራት ላይ የሚገኝ ሲሆን፤ በ400 ሺህ ብር የዳቦ መጋገሪያ ማሽን አስገብቷል፤ ሦስት ቋት ያለው ወፍጮና አንድ ማበጠሪያ በመትከል አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ በቤተ ክርስቲያኗ ዙሪያ ሰፊ ቦታ ስላለ ባለ አራት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃ በመሥራትና በማከራየት ራሷን የምትችልበት ሁኔታ ለማመቻቸት ጥረት እየተደረገ ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያኗን በአዲስ መልክ በጥሩ ዲዛይን ለማነጽ በብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የመሠረት ድንጋይ ተጥሏል፡፡ ለታቦቱ ማረፊያ የሚሆን ባለ አንድ ፎቅ ሕንፃም በመጠናቀቅ ላይ ይገኛል፡፡ ምእመናን ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርጉም ይጠበቃል፡፡ የጎንደር መምህራን ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች አዳራሽ ለመገንባት ለቤተ ክርስቲያኗ ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ተፈቅዶላቸው ግንባታውን በማጠናቀቅ አገልግሎት ላይ ውሏል፡፡

የጠበሉ ቦታን በማስተካከል ምእመናን ሳይቸገሩ አገልግሎት የሚያገኙበት ሁኔታ በማመቻቸት የግንባታ ሥራው ይከናወናል፡፡

የልደታ ለማርያም የጥምቀተ ባሕር ቦታ ለሙስሊሞች ተሰጥቶ ስለነበር ከፍተኛ ችግር ተከስቶ ቆይቷል፡፡ በተለይም በ2001 ዓ.ም. የተፈጠሩት ግጭቶች አስቸጋሪ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ የችግሩ አሳሳቢነት ቀጥሎም ጥምቀተ ባሕሩ ከሙስሊሞች ተወስዶ ለአንድ ጀርመናዊ ባለ ሀብት ተሰጠ፡፡ ነገር ግን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ እና በከተማው ወጣቶችና ምእመናን ብርቱ ጥረት ሳይሳከላቸው ቀርቷል፡፡

ቦታው የቤተ ክርስቲያን ሃብት በመሆኑ የልማት ሥራዎችን መሥራት እንደሚገባ በማመን ፕሮፖዛል በማዘጋጀት ለአማራ ክልላዊ መንግሥት ኢንዱስትሪና ከተማ ልማት ቢሮ ቀርቦ ውሳኔ እንዲሰጥበት ወደ ጎንደር ከተማ አስተዳደር አስተላልፎት በመታየት ላይ ይገኛል፡፡

ቦታው 46 ሺህ ካሬ ሜትር የሚገመት ሲሆን፤ የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርና ሰበካ ጉባኤው ይህን ሥፍራ ለጥምቀተ ባሕርና ለልማት ለማዋል ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ በቦታውም የግእዝ ቋንቋ ትምህርት ቤት፤ ሁለገብ ሕንፃ፤ የአረንጓዴ መናፈሻ፤ የኪነ ጥበብ ማእከል፤ መዋኛ ገንዳ፤ ሁለገብ የመሰብሰቢያ አዳራሽና ሌሎችንም ያቀፈ እንዲሆን ተደርጎ ዲዛይኑን በማዘጋጀት ለከተማ አስተዳደሩ ገብቷል፡፡ የሚመለከተው አካል ያጸድቀዋል ተብሎም ይጠበቃል፡፡  

መራሕያን ምድብ ተውላጠ ስሞች /Pronoun/

 ሐሴ 1 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመ/ር ደሴ ቀለብ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ መምህር

መራሕያን ማለት “መሪዎች” ማለት ሲሆን በግእዝ ቋንቋ አስር /10/ የሚሆኑ ተውላጠ ስሞች /መራሕያን/ አሉ፡፡ እነርሱም፡-

  1. አነ …………………..እኔ

  2. አንተ…………………. አንተ

  3. አንቲ ………………… አንቺ

  4. ውእቱ ………………. እርሱ

  5. ይእቲ ……………….  እርሷ

  6. ንሕነ ………………… እኛ

  7. አንትሙ………………. እናንተ /ለቅርብ ወንዶች/

  8. አንትን ………………. እናንተ /ለቅርብ ሴቶች/

  9. ወእቶሙ ……………… እነዚያ /ለወንዶች/

  10. ውእቶን …………….. እነዚያ /ለሴቶች/

መራሕያን በዐረፍተ ነገር

ቀደሰ (ቀዳማይ አንቀጽ Past tense) = አመሰገነ

 

  1. አነ ቀደስኩ                     6. ንሕነ ቀደስነ

  2. አንተ ቀደስከ                    7. አንትሙ ቀደስክሙ

  3. አንቲ ቀደስኪ                    8. አንትን ቀደስክን

  4. ውእቱ ቀደሰ                     9. ወእቶሙ ቀደሱ

  5. ይእቲ ቀደሰት                   10. ወእቶን ቀደሳ

የግሱ የመጨረሻ ፊደል “ከ” ከሆነ ያንኑ መለየት አለብን፡፡ ምሳሌ ሰበከ ብሎ አነ ሰበኩ (“ኩ” ይጠብቃል) ይላል እንጂ ሰበክኩ አይልም ስለዚህ ማጥበቅ አለብን ማለት ነው፡፡

1.1. ነባር አንቀጽ (Verb to be)

ውእቱ , ነው፣ ነበር፣ ነሽ፣ ነህ፣ ናችሁ

ይእቲ , ናት፣ ነበረች

ውእቶሙ (ሙንቱ) , ናቸው፣ ነበሩ (ለወንዶች)

ወእቶን (እማንቱ), ናቸው፣ ነበሩ (ለሴቶች )

ምሳሌ፡- አነ ውእቱ ፍኖተ ጽድቅ

        አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም

        አንተ ውእቱ ቤዛ ኩሉ ዓለም

       ማርያም ይእቲ መሠረተ ሕይወት

       ጳውሎስ ወጴጥሮስ መምህራን ውእቶሙ

       ሰሎሜ ወኤልሳቤጥ ቅዱሳት ውእቶን

1.2. ሥርዓተ ዐረፍተ ነገር በምሳሌ

ሕዝቅኤል ነቢይ

  • ሕዝቅኤል ነቢይ ውእቱ

  • ነቢይ ውእቱ ሕዝቅኤል

  • አኮ /አይደለም/ ነቢይ ሕዝቅኤል

“ውእቱ” ለሚለው አዎን አለው “አኮ” ነው፡፡

የሚከተሉት ከመራሕያን ከግሶች ጋር አዛምድ/አስተፃምር/

 

  1. አንትን                         ሀ ነበርኩ
  2. ውእቱ                         ለ በላዕነ
  3. አነ                             ሐ ሖርኪ
  4. ውእቶን                       መ ጸለዩ
  5. ይእቲ                          ሠ ቀተልክን

ረ መጽአት

ሰ ኖምክሙ

ሸ ሖራ

ቀ በልዐ 

ወልጥ ኀበ ልሳነ አምሃራ (ወደ አማርኛ መልስ)

  1. ንሕነ ሖርነ ኀበ አክሱም ወላስታ

  2. አንቲ ውእቱ እመ ብርሃን

  3. ማርያም ወለደት ወልደ ዘበኩራ

  4. አንተ ወአነ ሰማእነ ቃለ እግዚአብሔር

  5. እለ መኑ /አነማን/ ውእቶሙ ዘሖሩ ኀበ ገዳመ ሲና

ወደ ግእዝ መልስ /ወልጥ ኀበ ልሳነ ግእዝ/

  1. ወደ ጸሎት ቤት ሄድን

  2. እኔ ነኝ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሄድኩ፡፡ (ዘ=የ)

  3. እነርሱ በኅብረት ተቀመጠ (ኅቡረ = በኅብረት)

  4. ቶማስ እና ጴጥሮስ መምህራን ናቸው፡፡

  5. ማርያም ድንግል የአሮን በትር (በትር = ብትር) ናት፡፡

  6. አንተ የክርስቶስ ወንጌል ሰበክህ፡፡

  7. አንተ ሰባኪ አይደለህም፡፡

አስተካክለህ ጻፍ (ጹሑፍ በሥርዓተ ሰዋሰው)

ምሳሌ /ሐዘነ/ ማርያም አመ ተሰቅለ ክርስቶስ/ ኀዘነት ማርያም /አመተሰቅለ ክርስቶስ/

  1. /ኖመ/ አንተ ላዕለ አራት /አልጋ/

  2. /ሖረ/ አንትን ኀበ ደብረ ጽጌ

  3. /ቆመ/ ማርያ ወማርያም ቅድመ ቤተ መቅደስ

  4. /ኀደረ/ ፍሬ ጽድቅ ውስተ ቤተ አርድእት /ተማሪዎች/

  5. /አርመመ/ ሚካኤል አመ ተሰቅለ አምላክ

  6. /ተፈሥሑ/ ጻድቃን በእግዚአብሔር

 

 

abnet 2006 2

ለአብነት ተማሪዎች የአልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ድጋፍ በመደረግ ላይ ነው

 ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

  • በ150 አብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለሚገኙ ለ10 ሺህ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች ለማዳረስ ሥርጭቱ ይቀጥላል፡፡

  • “ያለኝ አንድ የተቀደደ ሱሪና አንድ ሸሚዝ ብቻ ነበር ፤ ቅያሪ ስለሌለኝ በመጨነቅ ላይ ሳለሁ በመድረሳችሁ እግዚአብሔር ይስጥልኝ” ከአብነት ተማሪዎች አንዱ::

abnet 2006 2
በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት “ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል ከምእመናን አልባሳትና ቁሳቁሶችን በማሰባሰብ በየአኅጉረ ስብከቱ ለሚገኙ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች የአልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁስ ድጋፍ በመደረግ ላይ ይገኛል፡፡

“ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል ለሁለተኛ ጊዜ ከሐምሌ 18 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በመካሔድ ላይ ባለው የሥርጭት መርሐ ግብር የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ውስጥ በሚገኙ አገልጋዮችና በየማእከላቱ ተወካዮች አማካይነት በየአኅጉረ ስብከቱ በመንቀሳቀስ በማሰራጨት ላይ ይገኛሉ፡፡

abnet 2006 1በዚህም መሠረት በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት /ለሐይቅ እስጠፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ አንድነት ገዳም፤ ለቦሩ ደብረ ብርሃን ሥላሴ፤ ለከሚሴ ደብረ ገነት ቅዱስ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት/፤ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት /ለመርሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን፤ ለራማ ደብረ ሲና ኪዳነ ምሕረት አንድነት ገዳም/፤ በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት /ለደብረ ብርሃን ሥላሴ፤ ለአቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል፤ ለአበራ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ለመንበረ መንግስት መድኃኔዓለም፤ ለግምጃ ቤት ቅድስት ማርያም አብያተ ክርስቲያናት/ ውስጥ ለሚገኙ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች የአልባሳትና የሳሙና ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡

በደቡብ ጎንደር /ለመንበረ ልዑል አስቻ ቅዱስ ሚካኤል፤ ለጽርሐ አርያም ዙር አባ አቡነ አረጋዊ ገዳም፤ ለቅድስት ቤተልሔም፤ ለደብረ ልዑላን መድኃኔዓለም፤ ለእስቴ ደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ፤ መሸለሚያ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፤ አባይ ማዶ ቅዱስ ገብርኤል፤ ለማቢ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፤ ለቆማ ፋሲለደስ፤ ለእስቴ ቅዱስ ሚካኤል ወቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናት/፤ በምዕራብ ጎጃም /ለናዳ ቅድስት ማርያም ገዳም፤ ለብጡላ ኢየሱስ፤ ለቆጋ ቅዱስ ጊዮርጊስ/፤ እንዲሁ ተመሳሳይ ድጋፍ የተደረገላቸው ሲሆን፤ በአራቱ ጉባኤያትና በማስመስከሪያ ትምህርት ቤቶች ከአልባሳትና ከሳሙና በተጨማሪ የጫማ፤ የክብሪት፤ የውኃ አጋርና ልብስ መስፊያ ክሮች አሠራጭቷል፡፡

የአብነት ትምህርት ተማሪዎች የሚያጋጥማቸውን የአልባሳት እጥረት ለመቅረፍ ከምእመናን አልባሳትን “ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል በማሰባበስብ እየተሠራጨ በሚገኝበት ወቅት ከየማእከላቱ በተውጣጡ የጤና ባለሙያዎች የአብነት ተማሪዎች እንዴት የአካባቢና የግል ንጽሕናቸውን መጠበቅ እንደሚገባቸው ትምህርት እየተሰጣቸውም ይገኛል፡፡

በ150 አብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለሚገኙ 10 ሺህ ተማሪዎች የአልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁስ ለማሠራጨት ታቅዶ እየተሠራ ሲሆን፤ በዚህ ሥርጭት እስካሁን በ23 አድባራትና ገዳማት ውስጥ ለሚገኙ 4110 /አራት ሺህ አንድ መቶ አሥር/ በላይ ለሚሆኑ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች ለማዳረስ ተችሏል፡፡ ሥርጭቱ በየአኅጉረ ስብከቱ የሚገኙ አብነት ትምህርት ቤቶችን ያካተተ በመሆኑ እንቅስቃሴው ቀጥሏል፡፡

የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ በደብረ ልዑላን መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ለአብነት ተማሪዎቹ አልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁስ ሲሰጥ ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክት “ሥጦታው መልካም ነው፤ መሆንም የሚገባው ነው፡፡ ንቃትና ትጋት ከተማሪዎች የሚጠበቅ ሲሆን፤ ጤናቸው ተጠብቆ ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ ማስተማርም ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡

በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት በመርሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር የሆኑት መጋቤ ምሥጢር መምህር ፍሬ ስብሐት ምሥጋናው በበኩላቸው “በችግር ምክንያት ትምህርታቸውን ሳይጨርሱ በሚወጡትና ወደ ከተማ ኮብልለው በሚቀሩት ተማሪዎች ባዝንም፤ አንድ ገበሬ አርሶ ፍሬውን ሲሰበስብ እንደሚደሰተው ሁሉ ተማሪዎቼ ለጥሩ ውጤት ሲበቁ ነፍሴ ይደሰታል፡፡ ያሳደገኝም፤ ያስተማረኝም ማኅበረ ቅዱሳን ነው፡፡ እንድማር፤ እዚህ ደረጃ እንድደርስ ድጎማ እያደረገልኝ ለዚህ አብቅቶኛል፡፡ የተዘረጋው ወንበር በችግር ምክንያት እንዳይታጠፍ ማኅበሩ ለተማሪዎች ባደረገው ድጋፍ በጣም ተደስቻለሁ” ብለዋል፡፡

“መምህራኖቻችን በችግር ውስጥ ይገኛሉ፡፡ እኛም ተምረን የእነሱ እጣ እንዳይደርሰን እንሠጋለን፡፡ ችግሩን መቋቋም የተሳናቸው ወደ ከተማ እየኮበለሉ በጥበቃ ወይም በቀን ሠራተኛነት እየተቀጠሩ ነው፡፡ እኛ ግን የልብሳችንና የቀለባችን መሸፈን ተስኖናል፡፡ እኔን እንደ ምሳሌ መውሰድ ይቻላል፤ ያለኝ አንድ የተቀደደ ሱሪና አንድ ሸሚዝ ብቻ ነበር፤ ቅያሪ ስለሌለኝ በመጨነቅ ላይ ሳለሁ በመድረሳችሁ እግዚአብሔር ይስጥልኝ” ሲል በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት በራማ ደብረ ሲና ኪዳነ ምሕረት abenet 2006 4አንድነት ገዳም ከሚገኙ የቅዳሴ ተማሪዎች አንዱ ይገልጻል፡፡

በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት የመጀመሪያው ዙር “ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በ2003 ዓ.ም. በማካሔድ ለበርካታ አብነት ትምህርት ተማሪዎች ማዳረስ መቻሉ ይታወሳል፡፡

ይህ መርሐ ግብር ወደፊትም እንደሚቀጥል ከዋና ክፍሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

meg 28 2006 01

ቅዱስ ፓትርያርኩ ጾመ ፍለሰታን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጡ

 ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ፍቃዱ ዓለሙ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት በየዓመቱ ከነሐሴ 1 እስከ 16 የሚጾመው የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ጾም ዘንድሮም የፊታችን ሐሙስ ይጀምራል፡፡

meg 28 2006 01 ይህን አስመልክቶ በቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ጽሕፈት ቤት በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅትብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ “የቅድስት ድንግል ማርያምን በዓለ ትንሣኤ ምክንያት አድርገን የምንጾመው ይህ ጾም ለሀገራችን፤ ለሕዝባችንና ለዓለሙ ሁሉ መዳንን፤ ምሕረትንና ይቅርታን ለማስገኘት ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ቅዱስነታቸው፣ በጾሙ ወቅት ሁሉም ክርስቲያን የተራቡትን በማጉረስ፣ የታረዙትን በማልበስና የተቸገሩትን በመርዳት ጾሙን ለመጾም ከወዲሁ ቅድመ ዝግጅት ማድረግ እደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊትና ጥንታዊት እንደመሆኗ መጠን ከጥንት ጀምሮ ይህንን ክብረ ቅድስት ድንግል ማርያም ጠብቃ እስካሁን አቆይታለች፤ ለወደፊትም እስከ ዕለተ ምጽአት በዚሁ ትቀጥላለች ብለዋል፡፡ ጾመ ፍልሰታ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያን በአዋጅ ከሚጾሙ ሰባቱ አጽዋማት መካከል አንዱ ሲሆን ከሕጻናት ጀምሮ ሁሉም ሕዝበ ክርስቲያን በፍጹም ትጋት የሚጾሙት የበረከት ጾም ነው፡፡