ዓለም አቀፍ ሙቀትን በመከላከል ረገድ የገዳማትና አድባራት ብዝኀ ሕይወት እንክብካቤ ይሻል

የካቲት 22/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሙቀት መጨመርን ለመቀነስ ያሏት ብዝኀ ሕይወት አስተዋጽኦቸው ከፍተኛ መሆኑን በማኅበረ ቅዱሳን ሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል ሓላፊ ዶ/ር ሳሙኤል ኀይለ ማርያም አስታወቁ፡፡

ሓላፊው እንደገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን በእቅድ ሊሠራቸው ካቀዳቸው መካከል የብዝኀ ሕይወት ጥበቃ  በታላቁ ደብረ ሊባኖስ ገዳም  እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በርካታ ገዳማትና አድባራት ያሏት መሆኑን የገለጹት ዶ/ር ሳሙኤል የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ለጥናት መመረጡ ለጥናቱ መከናወን አመቺነት ካለው የቦታ ቅርበትና ከገዳሙ የብዝኀ ሕይወት ይዘትና ጥራት አንጻር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በደብረ ሊባኖስ ገዳም በጀመረው በዚህ ጥናት ላይ የግብርና ባለሞያዎች፣ የግብርና ምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች፣ የአካባቢ ጥበቃ ባለሞያዎች እና በካርበን ልቀት ዙሪያ ልምድና ምርምር ያደርጉ ባለሞያዎች ያሉት ቡድን አቋቁሟል፡፡ ቡድኑ ከገዳሙ አመራር አካላትና ከማኅበረ ቅዱሳን ፍቼ ማእከል ጋር በመሆን ጥናቱን እያከናወነ መሆኑን ዶ/ር ሳሙኤል ጠቅሰው በጥናቱ ውጤትም ላይ መሠረት ያደረገ  ፕሮጀክት በገዳሙ ላይ የሚተገበር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ጥናቱም የገዳሙን የብዝኀ ሕይወት ያለበትን ደረጃ  እንዲሁም በብዝኀ ሕይወቱ ላይ ተጽዕኖ የሚያደርሱትን ነገሮች መለየት፣ የዚህ ጥናት በመነሣት በቀጣይ መሠራት የሚገባቸውን ጉዳዮች ጭምር መሠረት ያደረገ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

የደብረ ሊባኖስ ገዳም የብዝኀ ሕይወት ጥናት ቡድን ፕሮጀክቱን ሲተገብር የገዳሙ የአካባቢ ልማት እቅድ የሚወጣለት ሲሆን በገዳሙ ያሉት ብዝኀ ሕይወት ያለባቸው ቦታዎች ተለይተው ልዩ እንክብካቤ የሚደረግላቸው ይሆናል፡፡ የገዳሙም አኗኗር ብዝኀ ሕይወቱን ከመጠበቅ አንጻር መሆኑን ነው የተገለጸው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለብዝኀ ሕይወት ጥበቃ ከመቼውም በላይ ከሚመለከታቸው የዘርፉ ባለሞያዎችና መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ አካላት ጋር በጥምረት ይሠራል ያሉት ዶ/ር ሳሙኤል ገልጸው ተፈጥሮአዊ ነገሮችን መንከባከብም ሆነ መጠበቅ ሃይማኖታዊ ግዴታም መሆኑን ነው የገለጹት፡፡

የብዝኀ ሕይወት ጥናት በአሁን ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ትኩረት እያገኘ ሲሆን በዓለማችን በየጊዜው በሚፈጠረው የሙቀት መጠን መጨመር ምክንያት ዓለማችንን አስጊ ደረጃ እያደረሳት ይገኛል፡፡

ምሁራን ለቤተ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ለሙህራን›› በሚል የጥናትና ምርምር ምሁራን የምክክር መርሐ ግብር ይደረጋል

የካቲት 22/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል ከጥናትና ምርምር ማእከል ባለሙያ ምሑራን ጋር የምክክር መድረክ መርሐ ግብር እንደሚያካሔድ አስታወቀ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ዳሬክተርና በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአርኪዮሎጂና ቅርስ አስተዳደር መምህር የሆኑት ዲ/ን መንግሥቱ ጎበዜ እንደገለጹት ምሁራን ለቤተ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን፤ ለምሑራን ያላቸውን ተወራራሽ ጠቀሜታ በማጉላት፣ የምሑራንንም ፋይዳ ከቤተ ክርስቲያን ያገኙትንም ለመግለጽ ዐቢይ መርሐ ግብር መሆኑ ገልጸዋል፡፡ ይህ የውይይት መድረክ ለጥናትና ምርምር ማእከሉ አገልግሎቱን አጠናክሮ ለመቀጠል፣ የሌሎች ምሁራንን ድጋፍ ለማግኘትና ምሑራንም የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት እንዲያግዙ ለማነቃቃት ያግዛል፡፡ ምሑራኑም የጥናት ጽሑፎቻቸውን በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ እንዲያደርጉ ከማገዝም በላይ ቤተ ክርስቲያንም ትልቅ የመረጃ ምንጭ በመሆን ለጥናታቸው ውጤታማነት ፋይዳዋ ታላቅ መሆኑን የሚረዱበት ይሆናል ብለዋል፡፡

በዚህ የጥናትና ምርምር ባለሙያዎች መርሐ ግብር ላይ የዘርፉ ባለሞያዎች የሚገኙ ሲሆን መርሐ ግብሩም በአዲስ አበባ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል የካቲት 23 ቀን 2004 ዓ.ም እንደሚካሔድ ገልጸዋል፡፡

በተያያዘ ዜና የጥናትና ምርምር ማእከሉ የካቲት 24 ቀን 2004 ዓ.ም በብሔራዊ ሙዚየም “የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን፣ ሀገርና የሀገር ሉዓላዊነት” በሚል ርዕስ ጥናት እንደሚቀርብ ገልጻôል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለአድዋ ድል መገኘት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ድርሻ በመሆኑ በዓሉን ጥናታዊ ጽሑፍ እየቀረበ በየዓመቱ እንዲከበር በተሳታፊዎች የተሰጠ ጥቆማ ስለነበር የአድዋ ድል በዓልን ምክንያት በማድረግና ለሀገር አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ሚና ማጉላት ዓላማ ያለው መሆኑ ተገልጿል፡፡

ቅዳሜ የካቲት 24 ቀን 2004 ዓ.ም ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ በብሔራዊ ሙዚየም የሚቀርበው “የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን፣ ሀገርና የሀገር ሉዓላዊነት” ርዕስ በዋናነት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሀገርን ሉዓላዊነት በመጠበቅ አንጻር ምእመኗን አስተባብራ ድል ያስገኘች መሆኗ እና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ከባሕል ወረራ ሀገርን የመከላከል ያላት አስተዋጽኦ ለማስገንዘብ የሚያስችል መሆኑን ዳይሬክተሩ ገልጸው በብሔራዊ ሙዚየም በሚደረገው መርሐ ግብር ሁላችሁም ተጋብዛችኋል በማለት መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

asebot

ሰበር ዜና

የካቲት 21/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

የጥንታዊው አሰቦት ገዳም ደን ዳግም የእሳት አደጋ ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

asebot

የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አባ ሳሙኤል ገዳም ደን ትላንት የካቲት 20 ቀን 2004 ዓ.ም. ባልታወቀ ምክንያት በተነሣ እሳት ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

ትላንት ከቀኑ 5፡00 ሰዓት የተነሣው እሳት እስከአሁን ድረስ ያልጠፋ መሆኑንን የገለጹት የገዳሙ አገልጋይ አባ ወልዴ እንዳሉት እሳቱ እየተስፋፋ ከደኑ አልፎ ወደ ቅድስት ሥላሴ የአባቶች ገዳም እየተቃረበ መሆኑንን ገልጸዋል፡፡

እሳቱን ለማጥፋት የአካባቢው ገበሬ ማኅበር ጥረት እያደረገ ቢሆንም ከውኃ እጥረትና ከሰው ኀይል ማነስ የተነሣ ይህ ዜና እስከ ተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ እሳቱ አለመጥፋቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

ዝርዝርሩን እንደደረሰን እናሳውቃለን፡፡

Derej A5

የመባዕ ሳምንት

Derej A5

abune abusade

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ አረፉ

የካቲት 13/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

abune abusadeብፁዕ አቡነ አብሳዲ በተወለዱ በ92 ዓመታቸው ቅዳሜ የካቲት 10/2004 ዓ.ም. ለእሑድ አጥቢያ በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡ ብፁዕነታቸው በትግራይ ክፍለ ሀገር ሽሬ በ1912 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ በ1926 ዓ.ም ከሽሬ ወደ ኤርትራ በመሔድና ደብረ ማርያም ገዳም በመግባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመከታተል ዲቁናን ከብፁዕ አቡነ ይስሐቅ፣ ቅስናን ደግሞ ከአቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል፡፡ በደብረ ማርያም ገዳም ውስጥ በቆዩባቸው ዐሥር ዓመታት ውስጥ ከአንድ መቶ በላይ ዲያቆናትንና ካህናትን በማስተማር አፍርተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ በ1943 ዓ.ም በሱዳን በኩል ወደ ኢየሩሳሌም በእግራቸው የሔዱ ሲሆን፤ በግብጽ ለሁለት ዓመታት ለመቆየት ችለዋል፡፡ ከ1959 ዓ.ም. ጀምሮ ከ60 ዓመታት በላይ በኢየሩሳሌም የኖሩ ሲሆን ጥር 30 ቀን 1983 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በኤጲስ ቆጶስነት ከተሾሙት ጳጳሳት መካከል አንዱ ናቸው፡፡ በኤጲስ ቆጶስነት እንደተሾሙ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ረዳት ኤጲስ ቆጶስ ሆነው እስከ ዕለተ እረፍታቸው ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ይገኙ ነበር፡፡

በቆይታቸውም በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ይዞታ የሆኑትን አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማትን ለማስከበር ከፍተኛ ጥረት ያደረጉና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሟገት የተጣለባቸውን ሓላፊነት በመወጣት ሰፊ ሥራ ሠርተዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ አብሳዲ ዕብራይስጥንና አረብኛ ቋንቋዎችን አቀላጥፈው ይናገሩም ነበር፡፡

ከቡኢ ምድረ ከብድ የሚወስደው መንገድ አገልግሎት መስጠት ጀመረ

የካቲት 13/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

በጉራጌ ሀገረ ስብከት የሶዶ ወረዳ ዋና ከተማ ከሆነችው ቡኢ ከተማ ጀምሮ ምድረ ከብድ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ገዳም ድረስ የሚወስደው የ18 ኪ.ሜትር ጥርጊያ መንገድ በፌደራል መንገዶች ባለሥልጣን መሥሪያ ቤት ሙሉ ትብብር ሥራው ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን የገዳሙ አበምኔት አባ አብርሃም ወ/ኢየሱስ ገለጹ፡፡

ከዚህ ቀደም ይኸው መንገድ በአካባቢው ምእመናን አማካይነት በእጅ ቁፋሮ፣ ድንጋይ በመሸከምና ከጉልበት እስከ ገንዘብ አስተዋጽዖ በማድረግ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነበር፡፡ ነገር ግን ከጊዜ ብዛት በመበላሸቱ በመኪናም ሆነ በእግር ወደ ገዳሙ ለመሔድ እጅግ አስቸጋሪ ሆኖ ቆይቋል፡፡ በዚህም ምክንያት ወደ ገዳሙ ለክብረ በዓላትም ሆነ ለጉብኝት የሚመጡ ምእመናን በመቸገራቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥራቸው እየቀነሰ መጥቷል፡፡

 

ሙሉ ወጪውን በመሸፈን መንገዱን በጥሩ ሁኔታ ሠርቶ ያስረከበውን የፌዴራል መንገዶች ባልሥልጣንን በእግዚአብሔር ስም ያመሰገኑት አበምኔቱ በመንገዱ መበላሸት ምክንያት ተቋርጦ የነበረውን የምእመናንና የገዳሙን ግንኙነት ለማጠናከር ይረዳል ብለዋል፡፡

 

ቀደም ሲል ገዳሙ ሰፊ የእርሻ መሬት ርስት የነበረው በመሆኑ በገዳሙ ውስጥ የሚገኙ መነኮሳትና መነኮሳይያት እርሻ በማረስና ሰብሎችን በመዝራት የጓሮ አትክልቶችን በማልማት ይተዳደሩ እንደነበር የገዳሙ አበምኔት ተናግረው፤ በአሁኑ ወቅት ግን ገዳሙ በቂ የእርሻ መሬት የሌለው በመሆኑ መተዳደሪያ ያደረገው በዓመት ሁለት ጊዜያት ጥቅምት 5 እና መጋቢት 5 በጻድቁ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ ክብረ በዓላት ከሚመጡ ምእመናን ከሚለግሱት የገንዘብና መባ አስተዋጽኦ ብቻ እንደሆነ የገዳሙ አበምኔት ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ገዳሙ የልማት ሥራዎችን በመሥራት ለማጠናከርና በውስጡ የሚኖሩት መነኮሳት በችግር ምክንያት እንዳይበተኑ እንዲሁም ጥንታዊነቱንና ታሪካዊነቱን ጠብቆ ለማቆየት ከምእመናን ብዙ እንደሚጠበቅና በክብረ በዓላትም ሆነ በማንኛውም ጊዜ ገዳሙ ያለበትን ሁኔታ መጥተው በማየት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡

 

ገዳሙ በንጉሥ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት  በራሳቸው በጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተመሠረተ ሲሆን በጾምና ጸሎት የተጋደሉበት እንዲሁም ያረፉበት እንደሆነ ይታወቃል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቅድስት ቤተልሔም የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ

የካቲት 12/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

{gallery count=1 width=275 height=225 counter=1 links=0 alignment=right animation=3000}Beteleheme{/gallery}በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ፕሮጀክት የተገነባው በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በታች ጋይንት ወረዳ የምትገኘው የድጓ ማስመስከሪያ ቅድስት ቤተልሔም ቤተ ክርስቲያን የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ፡፡

የካቲት 4 ቀን 2004 ዓ.ም በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ እንድርያስ የተመረቀው ይኸው መጻሕፍት ቤትና ጉባኤ ቤት ሙሉ ወጪውን የላስ ቬጋስ ምእመናን በዋናነት መሸፈናቸው ታውቋል፡፡

 

ኅዳር 26 ቀን 2003 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ ተጥሎ በአንድ ዓመት ውስጥ የተጠናቀቀውን ግንባታ አስመልክቶ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ሲናገሩ የአብነት ትምህርት ቤቶች ለቤተ ክርስቲያናችን ህልውና ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን በዚህ ረገድ እያደረገ ያለው አስተዋጽዖ ቀላል የሚባል አይደለም” በማለት አመስግነዋል፡፡

 

በዕለቱ አጠቃላይ የሥራ ሒደቱን ዝርዝር ሪፖርት ያቀረቡት የድጓ ምስክር መምህር የሆኑት ሊቀምሁራን ይትባረክ ካሳዬ እንዳሉት “በግንባታው ምክንያት በተፈቀደልን ቦታ ላይ ፕሮጀክት ተቀርጾ የደብሩ ማኅበረ ካህናት፣ የድጓ አድራሾቹ ሁላችን ልማት እያለማን እራሳችንን የምንችልበት መንገድ ይፈልግልን፤ እስከ አሁን ለጉባኤ ቤታችን ለተደረገልን ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳንን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት የቅስቀሳና ገቢ አሰባሳቢ ክፍል ሓላፊ ዲያቆን ደረጀ ግርማ በበኩሉ ማኅበሩ በቀጣይም ከቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ ጎን በመሆን በጋራ ችግሮቹን በመፍታት እንደሚሠራ ጠቁሞ የገንዘብ ድጋፍ ያደረጉ የላስቬጋስ ምእመናንንና የአካባባውን ማኅበረሰብ ስለቀና ትብብራቸው አመስግኗል፡፡

 

በዕለቱም በድጓ ያስመሰከሩ የተወሰኑ አድራሾችና በግንባታው በጎ እንቅስቃሴ የነበራቸው ምእመናን ከብፁዕ አቡነ እንድርያስ እጅ የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡ በቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ በሀገራችን ብቸኛው ማስመስከሪያ መሆኑ ይታወሳል፡፡

ኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት 49ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን አከበረ፡፡

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምእመናን መታሰቢያ ድርጅት ለኢየሩሳሌም የካቲት 4 ቀን 2004ዓ.ም የተመሠረተበት 49ኛ ዓመት በዓል   ለድርጅቱን መሥራች ክብር አቶ መኮንን ዘውዴ  የመታሰቢያ ሐውልት ቦሌ ሩዋንዳ በሚገኘው መሰብሰቢያ አዳራሽ በር ላይ በማቆም ጭምር ተከብሯል፡፡

በ1955 ዓ.ም. ሚያዝያ 3 ቀን ከሠላሳ በማይበልጡ ኢትዮጵያውያን ወገኖች እንደተመሠረተ የሚነገረው መታሰቢያ ድርጅቱ በክብር አቶ መኮንን ዘውዴ ጠንሳሽነትና አሰባሳቢነት እንደሆነ ይነገራል፡፡ በወቅቱ ቅዱሳን መካናትን ለመሳለም ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም የሔደው የምእመናን ቡድን በዚያ ያለውን ችግርና በገዳማቱ የሚኖሩ አባቶችና እናቶችን በደልና ስቃይ ተመልክቶ የነበረ ሲሆን በተለይ የዴር ሱልጣን ገዳማችን ወደ ጥንቱ ይዞታ ለመመለስ ካልተቻለበት ምክንያቶች አንዱ ከኢትዮጵያ ገዳማውያንን ለመጎብኘት የሚመጣ ሰው የለም የሚል ምክንያት እንደሚሰጥ መረዳታቸው ለድርጅቱ መመሥረት ምክንያት እንደሆነ ተገልጿል፡፡

ክብረ በዓሉን በንግግር የከፈቱት የድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበር ኮሎኔል ተፈራ ይገዙ “የድርጅታችን የተመሠረተበትን 49ኛ ዓመት በምናከብርበትና በተልይም የታሪኩ ባለቤት ለሆኑት ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ የተሠራውን የመታሰቢያ ሐውልት በሚመረቅበት በዚህ ዕለት የተሰማንን ከፍተኛ መንፈሳዊ ደስታ ስንገልጽ ኩራት ይሰማናል” ብለዋል፡፡ “ሰው ለታሪክ የተፈጠረ እንጂ ታሪክ ለሰው አልተፈጠረም ያሉት ምክትል ሊቀ መንበሩ በ1955 ዓ.ም በኢየሩሳሌም ገዳማት የሚደርሰው በደል አሳዛኝ ታሪክ መነሻነት በብሔራዊና በመንፈሳዊ ስሜት በመቆርቆር ከብዙ ጥረትና ድካም በኋላ በርካታ አባላትን በማሰበሳብና የገዳማችንን ታሪክ በማስረዳት ለዚህ የቀደሰ ዓላማ ድጋፍ ለመስጠት ቃል የገቡትን ሰዎች ይዘው የኢየሩሳሌምን መታሰቢያ ድረጅትን የመሠረት ድንጋይ ሚያዝያ 16 ቀን 1956 ዓ.ም ያስቀመጡ የመጀመሪያው ታላቅ ሰው ከመሆናቸውም በላይ የድርጅቱን ዓላማ በተግባር በማዋል ከምንም አንስተው አሁን ያለበት ደረጃ እንዲደርስና በዓለም አቀፍ ደረጃም እውቅና እንዲያገኝ ያደረጉ ታላቅ አባት ናቸው” ብለዋል፡፡

 

ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ በተለይ የዴርስልጣን ገዳማችንን በተመለከተ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ተቃዋሚ ወገኖች አጋጣሚ እየጠበቁ ሁከትና ውዝግብ በሚፈጥሩበት ወቅት ፈጥኖ በመድረስና በየቀጠሮም ቀን ከገዳም አባቶች ጋር  በእስራኤልአገር ፍርድ ቤት በመገኘትና ከአባቶች ጎን በመቆም ከፍተኛ የሞራልና የገንዘብ እርዳታ በየጊዜው ለገዳሙ እንዲሰጥ በማድረግ የሀገርና የቤተክርስቲያን ባለውለታ መሆናቸው ተወስቷል፡፡

 

 

በመክፈቻው ንግግራቸው ምክትል ሊቀመንበሩ ኮሎኔል ተስፋዬ ድርጅቱ ያከናወናቸውን ዋና ዋና ተግባራት የገለፁ ሲሆን “በጋምቤላ ክልል የሚገኙ ወጣቶችን ለማስተማርና በመንፈሳዊ ሕይወት ለማደራጀት በቤተ ክርስቲያን የተነደፈውን እቅድ በመደገፍ የጎዳና ተዳዳሪዎችን ችግር ለማስወገድ መንግሥት በልማት እንዲሳተፉ ለሚያደርገው እንቅስቃሴ የ700,000 ብር ድጋፍ በመንግሥትና በህዝብ ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠውን የሕዳሴ ግድብ ሥራ የግማሽ ሚሊዮን ብር ቦንድ ያለ ወለድ ግዥ በማድረግ  ድርጅቱ  በኢየሩሳሌም ብቻ ሳይወሰን በአገር ውስጥም ለታሪክና መንፈሳዊ ሥራዎች ድጋፍ በመስጠት ላይ ነው” ብለው በተለይ በተፈጥሮ አደጋ ሳቢያ ወላጆቻቸውን ያጡ ሕፃናትን አሰባስቦ በረጲ፣ በአለም ከተማ፣ በደብረ ብርሃን የሕፃናትን በማስተማርና በመንከባከብና በአሁኑ ወቅት ዘላቂነት ያለው ሥራ ለመሥራት የ800,000 ብር ፕሮጀክት በመቅረጽ ውጤታማ ተግባር ለማከናወን በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል” ብለዋል፡፡

በበዓሉ ላይ የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ርዕስ ሊቃነ ጳጳሳት ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ኘሬዝዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሠላም የክብር ኘሬዝዳንት “ክቡር አቶ መኮንን ዘውዴን የማውቃቸው የትምህርት ሚኒስቴር በነበሩበት ወቅት ነው፤ ያስተማሩኝ፣  በአዳሪ ትምህርት ቤትም እንድንማር ያደረጉኝ ታላቅ ሰው ናቸው” ያሉት ቅዱስነታቸው ለትውልድ ታሪክንና ክብርን ላቆዩ ስሞች ክብር ይገባቸዋል ለእኝህ አባት መታሰቢያ ሐውልት እንዲያቆምላቸው ድርጅቱ መወሰኑና ታሪክን ለትውልድ እንዲቆይ በማድረጉ ሊመሰገን ይገባዋል፡፡ መልካምነታቸውን ለትውልድ ልናስተላልፍ ይገባናል) ድርጅቱም አገልግሎቱን አጠናክሮ በመላው ዓለም ጽ/ቤት ከፍቶ ሊሠራ ይገባል” ብለዋል፡፡

የክቡር አቶ መኮንን ዘውዴ የመታሰቢያ ሐውልት ምረቃ ላይ ቅዱስ ፓትሪያርኩን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች፣ የክቡር አቶ መኮንን ባለቤት ከነ ቤተሰቦቻቸው፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የድርጅቱ አባላት ተገኝተዋል፡፡ በበዓሉ ላይም የቅዱስ ኡራኤል ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን ቅድስት ሀገረ ኢየሩሳሌምን በማስመልከት ትምህርት ተሰጥቷል፡፡

IMG_0715

ጦምን አስመልክቶ የቅዱሳን አባቶች አስተምህሮ

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

“በጦም ወቅት አንድ ክርስቲያን  በፈቃደኝነት አንድ በጎ ሥራን  ጎን ለጎን ቢፈጽም መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ከሰዎች ምስጋናን ወይም አንዳችን ነገር ሽቶ የሚጦም ከሆነ ግን ጦሙ በእግዚአብሔር ዘንድ የማይወደድ ጦም ይሆንበታል፡፡ ማንኛውም በጎ ሥራ ስንሠራ ለእግዚአብሔር አምላካችን ካለን ፍቅር የመነጨ ይሁን፡፡ እንዲያ ካልሆነ ግን እግዚአብሔርን ደስ ልናሰኝ አይቻለንም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስን ጌታችን በመንጎቹ ላይ ሲሾመው ለእርሱ ያለውን ፍቅር ተመልከቶ ነበር፡፡ እግዚአብሔን የሚያፈቅር ሰው የሚፈጽማቸው የትኞቹም በጎ ሥራዎች በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደዱለት ይሆኑለታል፡፡ ፍጹማንም ናቸው፡፡ ስለዚህም ማንኛውንም በጎ ሥራዎቻችንን ስነሠራ እርሱን በማፍቀር ላይ የተመሠረቱ ይሁኑ፡፡”

“አንድ ሰው ምንም እንኳ መላ የሕይወት ዘመኑን በትኅርምት ሕይወት መምራት ያለበት ቢሆንም በዚህ በዐቢይ ጦም ግን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ኀጢአቱን  ለካህን ተናዝዞ ለድሆች ምጽዋትን በማድረግ በአግባቡ ሊጦም ይገባዋል፡፡ እነዚህን ዐርባ የጦም ቀናት በአግባቡ በጎ ሥራዎች አክለንባቸው የጦምናቸው እንደሆነ ቸሩ ፈጣሪያችን ዓመት ሙሉ ባለማወቅ የፈጸምናቸውን ኀጢአቶቻችንን ይደመስስልናል፡፡ (ዮሐንስ አፈወርቅ )

IMG_0715ነገር ግን ብዙዎቻችን በጦም ራስን መግዛትን ከምንለማመድ ይልቅ ለሥጋ ምቾቶቻችን መትጋታችን የሚያስገርም ነው፡፡ እኛ ለራሳችን የተጠነቀቅን መስሎን ደስታን ይፈጥሩልናል የምንላቸውን ምግቦችንና መጠጦችን አብዝተን እንበላለን እንጠጣለን፡፡ … ነገር ግን መጨረሻችን ሕማምና ስቃይ ይሆንብናል፡፡ የሥጋን ምቾት የናቁና በጦም በጸሎት እንዲሁም በትኅርምት ሕይወት መንፈሳዊ ሕይወታቸውን የሚመሩ ቅዱሳን ግን ሥጋና ነፍሳቸውን ሕያዋን አድርገው በመልካም ጤንነት ያኖሯቸዋል፡፡ በተድላና በምቾት ይኖር የነበረው ሰውነታችን በሞት ሲያንቀላፋ ከውስጡ ከሚወጣው ክፉ ጠረን የተነሣ ሽቶ በራሱ ላይ እናርከፈክፍበታለን፡፡ ነገር ግን የቅዱሳን ሰውነት በሕይወት ሳሉም ቢሆን በሞት ከሥጋቸው መልካም መዓዛ ይመነጫል፡፡ ይህ እጅግ ድንቅ የሆነ ነገር ነው ፡፡ እኛ ለሥጋችን ምቾት በመጠንቀቅ ራሳችንን ስናጠፋ እነርሱ ግን ሥጋቸውን ለነፍሳቸው በጦምና በጸሎት በማስገዛታቸው ሥጋቸውን ይቀድሷታል፡፡ የነፍሳቸውን በጎ መዓዛ በመጠበቃቸውም ሥጋቸው መልካም መዓዛን እንድታፈልቅ ሆነች፡፡

ነፍሳችን ንጽሕናዋን በጦም ካልጠበቀች በቀር ቅድስናዋን በኀጢአት ምክንያት ማጣቱዋ የማይቀር ነው፡፡ ያለጦም የነፍስን ንጽሕና ጠብቆ መቆየት የማይሞከር ነው፡፡ ሥጋም መንፈስ ለሆነችው ነፍሳችን መገዛትና መታዘዝ አይቻላትም፡፡ አእምሮአችንም በምድራዊ ምቾቶቻችን ስለሚያዝብን ከልብ የሚፈልቅ ጸሎትን ማቅረብ አይቻለንም፡፡ ስለዚህ ሥጋችን ነፍሳችንን በስሜት ስለሚነዳት ነፍስ እውር ድንብሯ በፍርሃት ወደ ማትፈቅደው ትሔዳለች፡፡ በአእምሮአችን ውስጥ ክፉ ዐሳቦች ተቀስቅሰው ኅሊናችንን ያሳድፉታል፡፡ ስለዚህም የእግዚአብሔር ጸጋ ከእኛ ትወሰዳለች፡፡ ስለዚህም በግልጥ አጋንንት እንደ ፈቀዱት ነፍሳችንን ተሳፍረው ወደ ኀጢአት ይመሩዋታል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ከጦመ በኋላ ተራበ፡፡ ሰይጣንም ወደ እርሱ ይቀርብ ዘንድ መራቡን ገለጠለት፡፡ እንዲህ በማድረግም ጠላታችንን እንዴት ድል እንደምንነሳው በእርሱ ጦም አስተማረን፡፡ ይህ አንድ ጦረኛ ላይ የሚታይ የአሰለጣጠን ስልት ነው፡፡ ለተማሪዎቹ ጠላትን እንዴት ድል መንሳት እንደሚቻል ሊያስተምር ሲፈልግ ለጠላቱ ደካማ መስሎ ይታየዋል፡፡ ጠላቱም የተዳከመ መስሎት ሊፋለመው ወደ እርሱ ይቀርባል፡፡ እርሱም በተማሪዎቹ ፊት ከጠላቱ ጋር ውጊያን ይገጥማል፡፡ ጠላትን በምን ድል መንሳት እንደሚችል በእውነተኛ ፍልሚያ ጊዜ በተግባር ያስተምራቸዋል፡፡ በጌታ ጦም የሆነውም ይህ ነው፡፡ ጠላት ሰይጣንን ወደ እርሱ ለማቅረብ መራቡን ገለጠ፡፡ ወደ እርሱም በቀረበ ጊዜ የእርሱ በሆነ ጥበብ በመጀመሪያውም፣ በሁለተኛውም፣ በሦስተኛው፣ ፍልሚያ በመሬት ላይ ጥሎ ድል ነሳው፡፡

እየጦምህ ነውን? ጦምህን በሥራ ተግብረህ አሳየኝ፡፡ ድሀ አይተህ እንደሆነ ራራለት፡፡ ወዳጅህ ከብሮ እንደሆነ ቅናት አይሰማህ፡፡ አፋችን ብቻ አይጡም፤ ዐይናችንም፣ ጆሮአችንም፣ እግራችንም፣ እጃችንም፣ የሰውነት ክፍሎቻችንም ሁሉ ክፉ ከመሥራት ይጡሙ፡፡ እጆቻችን ከስስት ይጡሙ፤ እግሮቻችን ኀጢአትን ለመሥራት ከመፋጠን ይጡሙ፡፡ ዐይናችም የኀጢአት ሥራዎችን ከመመልከት ይጡሙ፡፡  ጆሮዎቻችንም ከንቱ ንግግሮችንና ሐሜት ከመስማት ይከልከሉ፡፡ አንደበቶቻችንም የስንፍና ንግግርንና የማይገቡ ትችቶችን ከመሰንዘር ይቆጠቡ፡፡ ወንድማችንን እያማን ከዓሣና ከእንስሳት ተዋጽኦዎች መከልከላችም ምን ይረባናል? (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)

የማኅበሩን አገልግሎት ለማገዝ የማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ተመሠረቱ

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

በማኅበረ ቅዱሳን ለሀገር ውስጥ ማእከላትና የግቢ ጉባኤያት ማ/ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ተጠሪ የሆኑ 6(ስድስት) ማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች ተቋቋሙ፡፡

ማኅበሩ አገልግሎቱን ይበልጥ አጠናክሮ ለማገልገል የተሰጠውን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሓላፊነት ለመወጣት የማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች ሚናቸው ከፍተኛ መሆኑን ነው የተገለጸው፡፡

መቀመጫቸው የሰሜን ማእከላት ማስተባበሪያ በመቀሌ፣ የሰሜን ምዕራብ ማእከላት ማስተባበሪያ በባሕርዳር፣ የምዕራብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በጅማ፣ የደቡብ ማእከላት ማስባበሪያ ጽ/ቤት በአዋሳ የምሥራቅ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በድሬደዋና የመሀል ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት አዲስ አበባ ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡

ጥር ፳6 እና ፳7 ቀን ፳፻4 ዓ.ም ማእከላት የማስተባበሪያ ጽ/ቤት ምስረታ ላይ የማስተባበሪያ ጽ/ቤት የሚያካልላቸው ማእከላት በተገኙበት ተመስርተዋል፡፡ በምስረታ መርሐ ግብሩ ላይ የማስተባበሪያ ማእከላቱ ጽ/ቤት ተግባርና ሓላፊነት እንዲሁም የሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት በማኅበረ ቅዱሳን ምን መምሰል አለበት በሚሉ ርዕሰ ጉዳይ የስልጠናና የውይይት መርሐ ግብር ተካሔዷል፡፡

15 አባላት ያሉት የማስተባበሪያ ጽ/ቤት አስፈጻሚ አካላት የሀገር ውስጥ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ጨምሮ በዋና ማእከል ከሚገኙ ዋና ክፍሎች ጋር ግንኙነት በማድረግ ለሚከናወኑ ተግባራት ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር እንደሚሠሩ ይጠበቃል፡፡