kahinatSeltena

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ

በ ዲ/ን  ኅሩይ ባየ

kahinatSeltenaበማኅበረ ቅዱሳን አዘጋጅነት ከጥር 16-18 ቀን 2004 ዓ.ም ድረስ  የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ሴሚናር   በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል  ተካሔደ ፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የሀገር ውስጥ ማዕከላት ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል ሓላፊ የሆኑት ዲያቆን አንዱአምላክ ይበልጣል እንደገለጡት የንስሐ አባቶች በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙ ተማሪዎችን ዘመኑን የዋጀ ትምህርት እንዲያስተምሩና አባታዊ ተልእኳቸውን እንዲወጡ ሴሚናሩ እንደሚያግዛቸው አብራርተዋል፡፡ በተጨማሪም በሥልጠናው ላይ የተገኙ ካህናት ከተለያዩ ቦታ የመጡ በመሆናቸው በአንድ የሥልጠና ቦታ ተገኝተው ልምዳቸውን እንዲለዋወጡና እንዲመካከሩ ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ ሴሚናር መሆኑን ገልጠዋል፡፡

ከደብረ ታቦር፣ መቀሌ፣ ሽሬ፣ ደሴ፣ ደብረ ማርቆስ፣ ወሊሶ፣ አሰበ ተፈሪ፣ ጋምቤላ፣ ድሬዳዋ፣ ሐዋሳ፣ ፍቼ፣ ባሕርዳር፣ ሚዛንተፈሪ፣ ወላይታ ሶዶ፣ ጅማ፣ መቱ፣ ሰቆጣ፣ ሎጊያ፣ ዲላ፣ ደብረ ብርሃን እና ከአዲስ አበባ የተገኙ 53 ካህናት በሴሚናሩ ተሳትፈዋል፡፡

የሴሚናሩ መርሐ ግብር እንደሚያመለክተው ለተከታታይ 3 ቀናት “የቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ሁኔታ ከተልእኮዋ አንጻር፣ የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ በማስፈጸም ረገድ የንስሐ አባቶች ሚና ምን መሆን እንዳለበት፣ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ተሞክሮ የንስሐ ልጆቻቸውን ከመጠበቅ አንጻር ያላቸው ተልእኮ እንዲፋጠን ለማድረግ፣ ሉላዊነት እና ዓለማዊነት፣ መንፈሳዊ የምክር አገልግሎት ከሌሎች የምክር ዐይነቶች የሚለይበትን ጠባይ ምን እንደሆነ፣ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች መንፈሳዊ ዕድገት ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት ያለው ሚና፣ እና ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ያለው አገልግሎት የሚሉ ዐበይት ጉዳዮች በተያዘላቸው ጊዜ ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

ሴሚናሩ በተጀመረበት ዕለት ካህናቱ የሕዝብ መሪ ከመሆናቸው አንጻር እንዲህ ዐይነቱ የውይይት መርሐ ግብር እጅግ ጠቃሚና አስፈላጊ መሆኑን ተሳታፊዎች ገልጠዋል፡፡ “አንድ በግ ከሚመራቸው አንድ መቶ አናብስት ይልቅ አንድ አንበሳ የሚመራቸውን አንድ መቶ በጎችን እፈራለሁ” እንደሚባለው፡፡ ጌታ በወንጌል በጎቼን ጠብቅ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ ግልግሎቼን ጠብቅ ብሎ አደራ የሰጠው ለካህናቱ በመሆኑ የጠባቂነት አደራቸውን እንዲወጡ ሴሚናሩ አስገንዝቧል፡፡ ካህናቱ የልጆቻቸውን ሥነ ልቡና ከመረዳት አኳያ ተፈላጊውን ክብካቤ የሚያደርጉበትን መንገድ ማሰብ እንዳለባቸው ሴሚናሩን ያቀረቡት ሊቃውንት አብራርተዋል፡፡

ለሦስት ተከታታይ ዕለታት የዘለቀው ሴሚናር በብሔራዊ ሙዚየም ጉብኝት ከተከናወነ በኋላ ተጠናቅቋል፡፡

ቃና ዘገሊላ(ለሕፃናት)

ጥር 17/2004 ዓ.ም

በአቤል ገ/ኪዳን
አንድ ቀን በገሊላ አውራጃ ቃና በሚባል ቦታ የሚኖር አንድ ዶኪማስ የሚባል ሰው ሰርግ ደግሶ እመቤትችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እና ሌሎች ብዙ ሰዎችን ጋበዘ፡፡ እመቤታችንም በግብዣው ላይ ከልጇ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር፣ ከሐዋርያት ጋር ተገኘች፡፡
ምግቡና መጠጡ ቀረበ፡፡ ትንሽ ቆይቶ ግን የወይን ጠጁ አለቀ፡፡ በዚህ ጊዜ የሰርጉ አስተናጋጆች በጣም መጨነቅ ጀመሩ፡፡ ለእመቤታችንም የወይን ጠጅ ማለቁን  አማከሯት እመቤታችንም የሰርጉን ቤት አስተናጋጆች በተለይም ዶኪማስን ተጨንቆ ስታየው በጣም አዘነች፡፡ ለልጇ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የወይን ጠጁ እንዳለቀባቸውና አስተናጋጆቹ እንደተጨነቁ ነገረችው፡፡
ጌታም ባዶ የሆኑት የወይን ጋኖች ላይ ውኃ እንዲሞሉ አዘዛቸው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ጌታችን የሚለውን እንዲያደርጉ ነገረቻቸው፡፡ አስተናጋጆቹም ጋኖቹ ላይ ውኃውን ሞሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ውኃውን ወደ ወይን ለወጠው፡፡ ዶኪማስም በጣም ደስ አለው፡፡ በሰርጉ ላይ የተጋበዙት እንግዶችም አዲሱን የወይን ጠጅ ሲጠጡ በጣዕሙ እጅግ ተደነቁ፡፡ ዶኪማስንም ጠርተው ሌሎች ሰዎች ጥሩውን መጠጥ አስቀድመው ይሰጡና በኋላ ደግሞ ብዙም የማይጥመውን ያቅርባሉ፡፡ አንተ ግን  የማይጥመውን አስቀድመህ አቅርበህ ጣፋጩን ወይን ከኋላ አመጣህ በማለት አሞገሱት፡፡
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምላክ መሆኑን ከሚያሳዩት ተአምራት አንዱን በዚያ ዕለት በሰርጉ ቤት አደረገ፡፡ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትም በዚያን ዕለት ታወቀ፡፡ ይህ ተአምር የተፈጸመው በጥር 12 ቀን በመሆኑ ሁል ጊዜ ጥር 12 ቀን “የቃና ዘገሊላ” በዓል በመባል ይከበራል፡፡
Picture

ቡቱሽና ኪቲ /ለሕፃናት/

ጥር 15/2004 ዓ.ም.

በቴዎድሮስ እሸቱ

ውድ ሕፃናት እንደምን ሰነበታችሁ ለዛሬ አንድ ተረት አስነብባችኋለሁ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ቡቱሽና ኪቲ የሚባሉ ሁለት እኅትማማች እንቁራሪቶች በአንድ ወንዝ ውስጥ ይኖሩ ነበር፡፡ ኪቲ የእናቷን ምክር የምትሠማ ጎበዝ ልጅ ስትሆን ቡቱሽ ግን የእናቷን ምክር የማትሰማ የታዘዘችውን የማትፈጽም ልጅ ነበረች፡፡ እናቷ “ተይ ቡቱሽ ወደ ወንዙ መሐል አትግቢ አደጋ ይደርስብሻል፡፡” ስትላት አትሰማም ነበር ከጓደኞቿ ጋር ወደ ውኃው መሐል እየገባች ትጫወታለች ቡቱሽ ወደ ወንዙ መሐል እየገባች ስትጫወት ኪቲ ደግሞ እቤት ሆና እናቷን በሥራ ታግዛታለች ትምህርቷንም ታጠናለች፡፡

Picture

ከዕለታት አንድ ቀን በእነ ቡቱሽ ሰፈር እሳት ተነሣና የሰፈሩ ሰዎች በሙሉ ባልዲ፣ ጀሪካንና ሌሎችም የውኃ መቅጃ እቃዎችን ይዘው ወደ ወንዙ ሔዱ በዚህ ሰዓት ቡቱሽ ከጓደኞቿ ጋር በመሆን ወደ ወንዙ መሐከል ሔዳ እየተጫወተች ነበር፡፡ ሰዎቹም ከውኃው ጋር እፍስ አድርገው ይዘዋት ሔዱና እሳት ውስጥ ጨመሯት እሷም በእሳቱ ተቃጥላ ሞተች፡፡ ኪቲ ግን እቤት ሆና እያጠናች ስለነበር በእሳት ከመቃጠል ተረፈች፡፡

መቼም ልጆች ከዚህ ተረት ጥሩ ቁም ነገር እንደ ጨበጣችሁ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ አያችሁ ልጆች የታላላቆችን ምክር መስማት ምን ያህል ጠቃሚ እንደሆነ፡፡ ኬቲ የእናቷን ምክር በመስማቷ እና ከቤት ባለመውጣቷ በእሳት ከመቃጠል ስትድን ቡቱሽ ግን የእናቷን ምክር አልሰማም ብላ ወደ ወንዙ መሐከል ገብታ ስለተጫወተች በእሳት ተቃጥላለች፡፡ ስለዚህ ልጆች እናንተም የተለያዩ ችግሮች እንዳይገጥሙአችሁ የታላላቆቻችሁን ምክር በሚገባ ስሙ፡፡

dsc01723

የ2004 የከተራ በዓል አከባበር ከዓድባራቱ እሰከ ጃንሜዳ፡፡

ጥር 11/2004ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ዐበይት በዓላት ተብለው ከሚጠቀሱት መካከል የጥምቀት በዓል አንዱ ነው፡፡ይህንም በዓል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእደ ዮሐንስ፤ በማእከለ ዮርዳኖስ የተጠመቀበትን  ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ከዋዜማው ከጥር 10 ጀምሮ በደመቀ ሁኔታ በማክበር ላይ ትገኛለች፡፡ ለእኛ አብነት ይሆነን ዘንድ፤ የእዳ ደብዳቤያችንን እንደ ገል ቀጥቅጦ እንደ ሰም አቅልጦ በደላችንን ይደመስስ ዘንድ ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህንን መሠረት በማረድግ በየአብያተ ክርስቲያናቱ የሚገኙ ታቦታት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ በካህናትና ዲያቆናት፤ እንዲሁም በሰንበት ት/ቤቶች መዘምራንና ምእመናን በዝማሬ በመታጀብ በአቅራቢያቸው ወደሚገኘው ታቦት ማደሪያ በማምራት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ በመሔድ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ማምራቱን ያበሥራሉ፡፡ ‹‹ያን ጊዜም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ናዝሬት መጣ ዮሐንስም በዮርዳኖሰ ወንዝ አጠመቀው›› እንዲል፡፡/ማቴ.3፡1/

 

dsc01723

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሥራቿን መድኀኔዓለም ክርስቶስን ለዓለም የምትሰብክበት፣ ከእርሱም ያገኘችውን፣ ይህም ዓለም እንደሚሰጠው ያልሆነውን፣ የእግዚአብሔር ልጅነት፣ ሰላም፣ ፍቅርና ትሕትና ለዓለሙ ትሰብክበታለች፡፡ እንዲሁም ለአገራችን በጎ ገጽታን በመፍጠር ረገድ ከተለያዩ አገራት የሚመጡ ጎብኚዎች ተደንቀው የሚያዩትና አንዳንዶች ልባችውን ለእውነት ክፍት ያደረጉ የሚያምኑበት በመስተንግዶው የሚደመሙበት በመሆኑ ሃይማኖታዊ በዓሉን በልዩ ትኩረት ታከብራለች፡፡

 

ለዚህ በዓል አከባበር ቤተ ክርስቲያን ቅድመ ዝግጅቶችን በማድረግ ታቦታት በሰላም ወጥተው dsc01724በሰላም እንዲመለሱ ጉልህ ሚናዋን ትወጣለች፡፡ በዚህ መሠረት  በየአጥቢያው የሚገኙ ወጣቶች ከክብረ በዓሉ ቀደም ብሎ ለሓላፊነት በመሰብሰብ ቅዱሳት ሥዕላትን በታቦታት ማረፊያዎች በማዘጋጀት፣ በተለያዩ ኅብረ ቀለማት ያሸበረቁ ጨርቆችን /ባነሮችን/፤ የኢትዮጵያ ባንዲራን በየአብያተ ክርስቲያናቱ አደባባዮች በመስቀል፣ የቤተ ክርስቲያናትን ቅጥርና አስፋልት በማጽዳት፤ለታቦት ክብርን በመስጠት ምንጣፎችን በማንጠፍ በዓሉን ያደምቁታል፡፡

 

‹‹ያሰባሰበንና ያነሳሳን እግዚአብሔር ነው፡፡ በራሳችን ያደረግነው አንዳችም ነገር የለም፡፡ ይህንን ክብረ በዓል ከዐራት ዓመታት ወዲህ ነው በዚህ ሁኔታ በማክበር ላይ የምንገኘው፡፡ በየወሩ ከእያንዳንዱ አባል ዐሥር ዐሥር ብር በማዋጣት፤ ከምእመናን በመጠየቅ፤ እንዲሁም በጎ አድራጊ ምእመናንን በማነጋገር የገንዘብ ድጋፍ  በማድረግ እናሰባስባለን፡፡ ባገኘነው ገንዘብ የኢትዮጵያ ባንዲራን፤ የተለያዩ ኅብረቀለማት ያላቸው ጨርቆችን በchurchesማዘጋጀት፤ ምንጣፎችን በመግዛት  በቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን የበኩላችን እንድንወጣ ከበረከቱ ተሳታፊ እንድንሆን እያገለገልን እንገኛለን›› በማለት ስሜቱን ያካፈለን ከመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስና  የቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያናት አጥቢያ፤ የስድስት ኪሎ አካባቢ ወጣቶች መካከል አንዱ ወንድም ነው፡፡ በየአጥቢያው ተዘዋውረን የበዓሉን ቅድመ ዝግጅት ለመቃኘት በሞከርንበት ወቅት ያገኘናቸው ወጣቶች የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ገዳም አጥቢያ ወጣቶች፤ የቅድስት ማርያም ቤዛዊት ዓለም ማኅበር አባላት፤የዐራት ኪሎ አካባቢ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያኒቱንና አደባባዮችን በማስጌጥ ሥራ ላይ ተጠምደዋል፡፡ ስለ ዝግጅቱም የተሰማቸውን ሲገልጹ  ነበር፡፡ በተጨማሪም ‹‹ከፖሊስ አባላት ጋር በመቀናጀት ቅድመ ዝግጅቶችን በማድረግና በመወያየት  አስፈላጊውን ጥበቃ ለማድረግ ተዘጋጅተናል፡፡›› በማለት የገለጹ ሲሆን ባስተላለፉት መልእክትም ወጣቶች የእነሱን አርአያነት በመከተል ቤተ ክርስቲያን ከእነሱ የምትጠብቀውን አገልግሎት እንዲሰጡ እንዲሁም እምነታቸውን አጥብቀው እንዲይዙ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

‹‹ኀዲጎ ተስዐ ወተስዐተ ነገደ››
ምእመናን ከየቤታቸው ለበዓሉ በሚገባው ልብስ አሸብረቀው ወጥተዋል፡፡ እናቶቻችን ከየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ የሚሰሙትን የሊቃውንት አባቶቻችን ወረብ ተከትልው፣ የታቦታቱን መውጣት በመጠባበቅ እልልታቸውን ያሰማሉ፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችም ዝግጅቶቻቸውን አጠናቅዋል፣ የዝማሬ ልብሳቸውን ለብሰዋል፡፡ የሻይ የእረፍት ሰዓታቸውን በመጠቀም ከየመሥሪያ ቤታቸው በር ላይ የታቦታትን ማለፍ በእነርሱም መባረክን ዐይናቸው ተስፋ እያደረገች ታቦታቱ የሚመጡበትን አቅጣጫ ያማትራሉ፡፡

begena04
የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራንም ለወትሮው በሚታወቁበት፤ እኅቶች በሙሉ ነጭ ልብስ ወንድሞችም በነጭ ልብስና በቀይ ጃኖ ደምቀው የመንግሥተ ሰማያት ሙሽራ መስለዋል፡፡ ዘንድሮ ግን ሁሉንም ያስደመመ ነገር ይዘው ቀርበዋል፡፡ በርካታ ምእምናንን ዐይናቸውን ማመን እንዳልቻሉ ያስታውቃሉ፡፡ ‹‹በውኑ ይሄን ያህል በገና ደርዳሪ አለን?›› የሚሉ ይመስላል፡፡ አንዳንዶቹም በደስታ ፊታቸው እያበራ በተመሰጦ ‹‹እመቤቴ በምልጃሽ መድኀኒቴ ነሽ›› በሚለው መዝሙር ከበገና ደርዳሪዎቹ ጋር ወላዲተ አምላክን ያመሰግናል፤ ይማጸናል፡፡ ቁጥራቸው ወደ 150 የሚጠጋ የቅዱስ ዳዊት የበገና ቤተሰብ አባላት በገናችውን ወድረው ለዝማሬ ማየት በእውነት ልብን በሐሴት ይሞላል፡፡ ዐይንን ሳይነቅሉ ዐሳብን ሣይከፍሉ ለመከታተል ለመዘመርም ያስገድዳል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርትና ሥልጠና ማእከልን በርቱ ቀጥሉበት ያስብላል፡፡

ከሰዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብር በተለይም በጃንሜዳ ከየአድባራቱ ዐሥራ ሦስት ታቦታት በአንድነት የሚገኙበት በመሆኑ ሕዝቡን ለመባረክ የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፤ በመዘምራንና ምእመናን በመታጀብ ጉዞ የተጀመረ ሲሆን አመሻሽ ላይ ጃን ሜዳ ሊደርሱ ችለዋል፡፡ የየሰንበት ት/ቤቶቹ መዘምራን፤ የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዜማ እየዘመሩ፤ ምእመናን በእልልታና በሸብሸባ ታቦታቱን በማጀብ በዓሉን አድምቀውታል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከጋዜጠኞች ለቀረበ ጥያቄ ዕለቱን በማስመልከት በሰጡት መግለጫ ‹‹የዛሬው በዓላችን በሃይማኖታችን ውስጥ የእግዚአብሔርን ጸጋና በረከት የምናገኝበት፤ ሁላችንም በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የምንወለድበት፤ ልጅነት የምናገኝበት በዓል ነው፡፡›› በማለት  ገልጸዋል፡፡

በዓሉን በተመለከተ ያነጋገርናቸውና ከፈረንሳይ ሀገር የመጡት ቱሪስት በዓሉን በመገረም እየተከታተሉ ‹‹ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡ የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተከታይ ነኝ፡፡ ኢትዮጵያውያን በጣም የተለያችሁ ናችሁ ማለት ይቻላል ፡፡ እንደዚህ ዓይነት የበዓል አከባበር ዐይቼ አላውቅም፡፡ በጣም አስደሳችና ታላቅ በዓል ነው፡፡ ሕዝቡ በእልልታና በዝማሬ፣ በሽብሸባና በጭብጨባ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ፍጹም አስደሳች ነው፡፡›› በማለት ገልጸዋል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የኦሃዮ ስቴት ኮሎምበስ ከተማ የደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የሆኑት ቀሲስ ያሬድ ገ/መድኅን  dsc05178ከበዓሉ ተሳታፊዎች መካከል አንዱ የነበሩ ሲሆን ከረጅም ጊዜ በኋላ በሀገራቸው ማክበር በመቻላቸው መደሰታቸውን፤ ወጣቶች ለታቦታቱ ምንጣፍ በማንጠፍ የሚያደርጉት ጥረት እንዳስደነቃቸው የገለጹ ሲሆን፤ በውጭ ሀገር የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን  የሚያደርጉት ጥረት በተመለከተ ‹‹እኛ እምነታችንን ለዓለም የምናስተዋውቅበት ጊዜ እየደረሰ ነው፡፡ በውጭው ዓለም አብያተ ክርስቲያናት መተከላቸው፣ በዓላትን በጋራ ማክበራችን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ለዓለም ሕዝብ ማስተዋወቅ የጀመርንበት ወቅት እንደሆነ ያሳያል፡፡ እግዚአብሔር ከፈቀደ እነሱም ተጠምቀው የማይመለሱበት፤ የቤተ ክርስቲያን ልጆች የማይሆኑበት ምክንያት አይኖርም ›› በማለት ወደፊት ብዙ መሠራት እንዳለበት ገልጸዋል፡፡

በበዓሉ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ከውጭ ሀገር በዓሉን ለመከታተል የመጡ እንግዶችና ቱሪስቶች የተገኙ ሲሆን  የዓመቱ ተረኛ የሆነው የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን መዘምራን ዕለቱን በማስመልከት ያሬዳዊ ዝማሬ ‹‹ተሰአልከ እግዚኦ ምደረከ ሃሌ ሉያ ወረደ ወልድ እም ሰማያት ውስተ ምጥማቃት በፍስሐ ወበሰላም›› በማለት አቅርበዋል፡፡ በብፁዕ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ገሪማ ሰፋ ያለ  ቃለ እግዚአብሔር  ተሰጥቷል፡፡ በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ጳውሎስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተሰጥቶ ታቦታቱ ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ ቦታ ገብተዋል፡፡  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
p1180004

ሁለቱ የዘመነ አስተርዮ ክብረ በዓላት በዳግማዊት ኢየሩሳሌም

ጥር 11/2004ዓ.ም

ዲ/ን ጌታየ መኮንን

የ2004 ዓ.ም የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ከርስቶስ የልደት (የገና) እና የጥምቀት በዓላት አከባበር እንደወትሮው ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀና ያማረ ነበር፡፡

p1180004

ካህናቱ ከታኅሣሥ 27 ቀን ጀምሮ በመድኀኒዓለም ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስጠት የጀመሩ ሲሆን፤ የአማኑኤል በዓል ዋዜማ ጠዋት ደወል ተደውሎ በጣም በደመቀ ሁኔታ ዋዜማው ተቆሞ ውሏል፡፡ 7 ሰዓት ሲሆን ቅዳሴ ተገባ እስከ 9 ሰዓት ቅዳሴ ተጠናቀቀ፡፡ ማታ 2 ሰዓት ማሕሌት ተደውሎ እስከ ለሊቱ 10 ሰዓት የቀጠለ ሲሆን ከ10 ሰዓት እስከ 12 ሰዓት የቅዳሴው ሥርዓት ተከናውኗል፡፡ ጠዋት 3 ሰዓት የልደት በዓል ዋዜማ ተደውሎ እስከ 10 ሰዓት እንደቦታው ትውፊትና ሥርዓት መሠረት የቦታው ቀለም እየተባለ የዋዜማው ቅኔ ለባለ ተራዎቹ እየተሰጠ ተከናውኗል፡፡ ማታ 2 ሰዓት የበዓሉ ደወል ተደውሎ ከተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የመጡ ምእመናን፣ የውጭ ሀገር ዜጎች፣ የቤተ ማርያምን የውስጥና የውጭ ቦታ ማሜ ጋራ የተባለውን ቦታ ከበው በእልልታ በጭብጨባ ጧፍ እያበሩ ማኅሌቱ በመዘምራኑ፣ በካህናቱ፣ በዲያቆናቱ በድምቀት ቃለ እግዚአብሔሩ እየተዘመረና እየተወረበ አድሯል፡፡

 

ከቦታው ቀለሞች   «ክርስቶስ መጽአ ውስተ ዓለም»

«ኮከብ ርኢነ ወመጽአነ ንሰግድ ሎቱ ለዘፈለጠ ብርሃነ»

 

 

ሥርዓተ ቅዳሴው እንዳለቀ የአስራ አንዱም አብያተ ክርስቲያናት ካህናትና ዲያቆናት ልብሰ ተክህኖ ለብሰው መስቀል፣ ጥላ፣ ስዕላት ይዘው ወደ ማሜ ጋራ ይወጣሉ መዘምራኑ ከሁለት ተከፍለው ከላይና ከታች ሆነው ምሳሌውም የመላእክትና የኖሎት በአንድነት እግዚአብሔርን ያመሠገኑበት ሲሆን «ቤዛ ኩሉ ዓለም ዮም ተወልደ» እያሉ እየተቀባበሉ በዓሉን በደማቅ ሁኔታ አክብረውታል፡፡ ልክ 3 ሰዓት ሲሆን ቤዛ ኩሉ አልቆ ትምሀርትና ቃለ ምዕዳን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ  ቄርሎስ ተደርጎ ልክ 4 ሰዓት የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

 

በዘንድሮው ክብረ በዓል ምንም እንኳን የሀገር ውስጥ ምዕመናን ቁጥር አነስተኛ ቢሆንም፣ ከውጭ የመጡት ቱሪስቶች ቁጥር ግን ከቀድሞው የበለጠ እንደነብር ታውቋል፡፡

የጥምቀት በዓልም እንደ ልደት በዓል በቅዱስ ላሊበላ ለየት ባለ መልኩ የሚከበር በዓል ነው፡፡ ገና በዋዜማው ጠዋት 3 ሰዓት  ዋዜማ ተደውሎ እስከ 7 ሰዓት  ድረስ ዋዜማ ከተቆመ በኋላ ከ7 ሰዓት  እስከ 9 ሰዓት ድረስ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኗል፡፡

 

ልክ 10 ሰዓት ታቦታቱ ከአስራ አንዱም አብያተ ከርስቲያናት ተነስተው በቦታው ሥርዓት መሰረት ወደ 750 የሚጠጉ ካህናትና ዲያቆናት ልብሰ ተክህኖ ለብሰው መምህራኑና መዘምራኑ ጥንግ ድርብ፣ ካባ፣ ሸማ ለብሰው ጠምጥመው መቋሚያና ፀናጽል ይዘው በተራ፤ ምዕመናኑ በእልልታና በሆታ ወደ ጥምቀት ባሕሩ ተጉዘዋል፡፡

p1180055

ጥምቀት ባሕር እንደደረሱ ውዳሴ ማርያም፣ መልክዓ ማርያም፣ መልክዓ ኢየሱስና፣ መልክዓ ላሊበላ ተደግሞ ስለ ጥምቀት ትምህርት ተሰጥቶ ለውጭ ሀገር ዜጎችም በእንግሊዝኛ ቋንቋ ገለጻ ተደርጎ በጸሎት ከታረገ በኋላ ታቦታቱ ወደ መንበረ ክብራቸው ገብተዋል፡፡

 

በአጠቃላይ የጥምቀት በዓል በቅዱስ ላሊበላ ከጥንት ጀምሮ ባማረና በደመቀ ሁኔታ የሚከበር ሲሆን የውጭ ሀገር ዜጎችም በተለያዩ ጊዜያት ከዓመት ወደ ዓመት ቁጥራቸው እየጨመረ መጥቷል፡፡ በከተማው ያሉ ሆቴሎች ሁሉም ተይዘው በርካታ ቱሪስቶች ድንኳን ተከራይተው በጥምቀተ ባሕሩ ዙሪያ ማረፋቸው ታውቋል፡፡

በዚህ ዓመትም ወደ 6 የሚጠጉ የውጭ ዜጎች በጥምቀት የእግዚአብሔርን ልጅነት እንዳገኙ የቅዱስ ላሊበላ ደብር ዋና ጸሐፊ ሊቀ ሥዩማን መንግሥቴ ወርቁ ገልጸውልናል፡፡

ምሽት 2፡00 ሰዓት የበዓሉ ደወል ተደውሎ አገልግሎት የሚጀመር ሲሆን 10 ሰዓት ሲሆን ቅዳሴ ይገባል፡፡  ልክ 12፤00 ሰዓት ወደ ባሕረ ጥምቀቱ ይኬድና ጸሎቱ ይቀጥላል፡፡ 3፡00 ሰዓት ፍጻሜ ይሆናል፡፡ 5፤00 ሰዓት ሲሆን ታቦታቱ ይነሱና ወደ አብያተ ክርስቲያናቱ ይሄዳሉ፡፡ 9፡30 አካባቢም የበዓሉ ፍጻሜ ይሆናል፡፡

በዚህ ሁሉ ሂደት ልክ እንደ ቤዛ ኩሉ በዓል መዘምራኑ የክብር ልብሳቸውን ለብሰው በዝማሜ በወረብ በእልልታ በሆታ በትውፊቱና በሥርዓቱ መሠረት ይከናወናል፡፡

 

በዕለቱ ታቦታቱ ሲነሱ « ሀዲጎ ተሥዐ ወተስዐተ ነገደ» የሚለው ቃለ እግዚአብሔር ተወርቦ ይጀመርና «ወወጽአ በሰላም ቆመ ማእከለ ባሕር ገብዐ » በሚለው ወረብ ይደመደምና ታቦቱ በተለምዶ ማርያም ጥንጫ  በሚባለው ቦታ በደብሩ አለቃ ምዕዳንና ፀሎት ከተደረገ በኋላ ታቦታቱ ወደ አብያተክርስቲያናቱ ይገባሉ፡፡

ካህናቱ እንደ መላእክት ያለ ድካም በዝማሬ በዝማሜ በወረብ በአንድ ድምጽ ይዘምራሉ፡፡ የወጭ አገር ዜጎችና የሀገር ውስጥ ምእመናን ካሜራቸውን በመያዝ ቪዲዮና በፎቶ ይቀርጻሉ ያነሳሉ፡፡ እንደዚሁ ሁሉ የቃና ዘገሊላ የቅዱስ ሚካኤልና የቅዱስ ላሊበላ ታቦታት እንደቦታው ሥርዐት እንደ ጥምቀቱ ምሉዕ ካህናት አጅበውት ቃለ እግዚአብሔሩ እየደረሰ ይመለሳሉ፡፡

በከተራ የሚወርዱት 12 ታቦታት ሲሆኑ አስሩ የጥምቀት ዕለት ሲመለሱ ሁለቱ የቃና ዘገሊላ ዕለት ይመለሳሉ፡፡ አካሄዳቸውም እንደቦታው ሥርዓት ሲሆን ይህም ከጥንት የተገኘ ለመሆኑ ገድለ ላሊበላ ላይ ተገልጾ  ተቀምጦአል፡፡

ሥርዓቱ አባቶቻችን ጠበቀው በማቆየታቸው ዛሬም በዚሁ ሥርዓት ይቀጥላል፡፡ ለምሳሌ የታቦታቱ ቅደም ተከተል ይሄውም በየተራ በሰልፍ የሚሄዱበት መንገድ፣ የመዘምራን ዝማሜ፣ ጥንግ ድርብ ሻሽና ካባ ለባሽ ሆነው በሁለት ተከፍለው በተራ ይዘማሉ፡፡ ወረቡ በተራ በሊቃውንቱ እየተቃኘ ሌሎች እየተቀበሉ ይደርሳል፡፡

 

p1180070ቱሪስቶች ከዓመት ወደ ዓመት ፍሰታቸው እየጨመረ መጥቷል፡፡ ይህም ዝማሜው፣ አልባሳቱ፣ የበዓሉ ድምቀት ፣ የቦታው ሥርዓት ለየት ያለ እንዲሁም በእግዚአብሔር ድንቅ ጥበብ በቅዱስ ላሊበላ የታነጸው ህንጻ ከሊቃውንቱ፣ ሊቃውንቱ ከህንጻው ጋር አብረው የሚታዩና የማይጠገቡ በመሆናቸው እንደሆነ ሊቀ ሥዩማን ገልጸውልናል፡፡

ከሌሎች ቦታ ለየት የሚያደርገው በዓሉ የተለየ ቃለ እግዚአብሔርም አለ፡፡ ይህም በአባቶች ከቦታው ጋር እንዲስማማ ሆኖ በመደረሱ ነው፡፡

 

ለምሳሌ፡- «ዘከለሎ ብርሃን ዘከለለሎ»

«ወወጽአ በሠላም ቆመ ማዕከለ ባህር ገባዐ»

«አይኑ ዘርግብ ልብሱ ዘመብረቅ»የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡


በአጠቃላይ በዓሉ አመት እስኪደርስ የሚናፈቅ የሚወደድ ባላለፈ ባላለቀ ጥምቀት ለምን አንድ ጊዜ ብቻ ሆነ የሚያሰኝ ነው፡፡ ሁሉም ህብረተሰብ ወደ ቦታው ሄዶ አይቶ በረከት ቢቀበል በጣም ጥሩ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የጌታ ጥምቀት(ለሕፃናት)

ጥር 10/2004 ዓ.ም.

በእኅተ ፍሬስብሐት

የጥምቀት በዓል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀበትን ዕለት የምናከብርበት በዓል ነው፡፡

 

ጌታችን ከተወለደ በኋላ 30 ዓመት ሲሆነው ዮርዳኖስ ወደሚባለው ወንዝ ሔደ፡፡ በዚያም መጥምቁ ዮሐንስ አጠመቀው፡፡ ጌታችን ሲጠመቅ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ነበር፡፡ ሌሊት ደግሞ ርግብ አይኖርም፤ ምክንያቱም ወደ ጎጇቸው ስለሚገቡ ነው፡፡ በዚያች ዕለት ግን ጌትችን ሲጠመቅ ርግብ መጥታ በራሱ ላይ አረፈች፡፡ ከዚያም ከሰማይ አንድ ድምጽ ተሰማ፤ ድምጹም

“የምወደው ልጄ ይህ ነው፡፡ እርሱን ስሙት” የሚል ነበር፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ድምጽ ነበር፡፡

 

በጥምቀት በዓል ጌታችን ወደ ዮርዳኖስ ሄዶ እንደተጠመቀ ለማስታወስ ጥር 10 ቀን ሁሉም ታቦታት በአቅራቢያቸው ወደሚገኝ ውኃ ወዳለበት ስፍራ በመሔድ በድንኳን ውስጥ ያድራሉ፡፡ ይህ እለት ከተራ ይባላል፡፡ ከተራ የተባለው በአካባቢው ያለው ውኃ እንዳይፈስ ተገድቦ ሕዝቡ እንዲጠመቅበት ስለሚዘጋጅ ነው፡፡ ታቦታቱ ወደ ድንኳኑ ከገቡ በኋላ ሌሊቱን ካህናቱ ሲያመሰግኑ፣ ሲዘምሩና ሲቀድሱ እና እለቱን የተመለከተ ትምህርት ለሕዝቡ ሲያስተምሩ ያድራሉ፡፡ ጠዋት ከ12 ሰዓት ጀምሮ በተጠራቀመው ውኃ አጠገብ ጸሎት ከተደረገ እና ከተባረከ በኋላ ለተሰበሰበው ሕዝብ ይረጫል፡፡ ይህ እለት ጥር 11 ቀን ጥምቀት ይባላል፡፡ ካህናቱ ሕዝቡን ጸበል ከረጩ በኋላ ልዩ ልዩ ሥርዓቶች ይደረጋሉ፡፡ ከዚያም ታቦታቱ ከድንኳን ወጥተው ወደየመጡበት ቤተ ክርስቲያን ይሔዳሉ፡፡

በነገር ሁሉ ደስ ልታሰኙ ለጌታ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን ቆላ.1፥19

ጥር 9/2004 ዓ.ም

በዓላት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን ከምትፈጽምባቸው ሥርዓቶች መካከል እንደ አንዱ ሆነው ይጠቀሳሉ፡፡ በበዓላት ምእመናን ረድኤት በረከት ከማግኘታቸው ባለፈ ቤተ ክርስቲያን የምትሰጣቸውን አገልግሎቶች የሚቀበሉባቸው መንፈሳዊ መድረኮች ናቸው፡፡ በበዓላቱ መምህራን ትምህርተ ወንጌልን ለምእመናን ያደርሳሉ፡፡ በበዓላት አከባበር ሥርዓት ውስጥ ምእመናን በቤታቸው፤ በአካባቢያቸውና በአደባባይ ሁሉም በጋራ በኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነትና ጌትነት፣ ለሰውም ያደረገውን የማዳን ሥራ የሚመሰክሩበት፣ በቤተ ክርስቲያን እምነትና ሥርዓት ላይ ያላቸውን ጽናት ለየትኛውም ወገን ያለሀፍረት የሚገልጹበት የአገልግሎት ዕድል ነው፡፡

ጌታችን “በሰው ፊት የሚመሰክርልኝን እኔም በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ” /ሉቃ.12፥8/ ያለውን ቃሉን በማክበርና በመጠበቅ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአዋጅና በአደባባይ የምታከብራቸው ማራኪ በዓላት አሏት፡፡ እነዚህ በዓላት በዓይነታቸው ሁሉንም የክርስቲያን ቤተሰብ በየመዓርጉ፣ በየጸጋው እንደየ አቅሙ የሚያሳትፉ በመሆናቸው ደማቅ ናቸው፡፡ በተለይ የጌታችን የመድኀኒትችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥራ፣ ተአምራትና የማዳን ነገር የሚዘክሩትን በዓላት /በዓለ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ መስቀል/ ዐበይት ሆነው ይከበራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የበዓላት ቀን ቀመር መሠረትም ብሔራዊ በዓላት እንዲሆኑ በሕግ ተመዝግበው የሚታወቁና ደምቀው የሚከበሩ ናቸው፡፡

እነዚህ ወንጌልን መሠረት ያደረጉ የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዐበይት በዓላት በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ውስጥና በምእመናን ልብ ከፍ ያለ ቦታ ተሰጥቷቸው መገኘቱ ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ ሁሉ ለስብከተ ወንጌል የሰጠችውን የማያቋርጥ ትኩረት ይመሰክራል፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያን ሕይወቷም አገልግሎቷም ነውና፡፡ እንዲህም ሆኖ እስከዚህ ዘመን ደርሷል፡፡

የዚህ ዘመን የቤተ ክርስቲያን ትውልድም እነዚህን ዐበይት የጌታችንን በዓላት ከጊዜ ጊዜ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት የማክበር ዝንባሌው164149_1457139283455_1682564302_893573_395312_n እያደገ ነው፡፡ ወንጌል በተግባር እየተሰበከ ነው፡፡ ይህም መናፍቃን እኛን ኦርቶዶክሳውያንን ወንጌልን እንደማንሰብክ አድርገው በሚያሙበት ነገር የበለጠ እንዲያፍሩ አገልግሎቱም የበለጠ እንዲሰፋ አድርጓል፡፡ በተለይ በዓለ ጥምቀትን የመሰሉ የአደባባይ በዓላት በየጊዜው እየደመቁ በአከባበር ሥርዓታቸውም ከባህላዊ ይዘታቸው ይልቅ ፍጹም ሃይማኖታዊ መልክ እየያዙ እንዲመጡ እየተደረገ ነው፡፡ ወደፊትም እነዚህ በዓላት በቅዱስ ወንጌል ያለንን እምነት በሰዎች ሁሉ ፊት የምንሰብክባቸው ዓውደ ምሕረቶቻችን ሆነው ደምቀው መከበር እንዳለባቸው ማኅበረ ቅዱሳን የጸና አቋም አለው፡፡ ለዚህም ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ሁሉም በቤቱና በአደባባይም ሁሉ በዚህ በረከት በሚገኝበት አገልግሎት መሳተፍ ይጠበቅበታል፡፡ በፍጹም ሰላም፣ ሃይማኖታዊ /መንፈሳዊ/ ፍቅር የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራና ትምህርቱን፣ ሰውንም የወደደበትን ታላቅ ፍቅር፣ በሰው ሁሉ ፊት በመመስከር በደስታ እንዲያከብሩ ልናነሣሣቸው ይገባል፡፡

ወቅቱን የዋጀ አገልግሎት ከመስጠት አንጻር ደግሞ ከዚህ ቀደም ከነበረው አገልግሎታቸው በበለጠ ትጋት የሚፈለግባቸው ሊቃውንቱና ካህናቱ ናቸው፡፡ ሊቃውንቱና ካህናቱ የበዓላት አገልግሎታችን ሥርዓቱን ጠብቆ በቅልጥፍና እንዲካሔድ ሥምረትም እንዲኖረው ከምእመናን በኩል ያለውን ተነሣሽነት ያገናዘበ ተሳትፎ ልናደርግ ይገባል፡፡ ዞሮ ዞሮ የበዓሉ ማእከል በካህናቱ የሚሰጠው አገልግሎት በመሆኑ በየአጥቢያው ባሉ ማኅበረ ካህናት ምክክር ሊደረግበትም ይገባል፡፡ በበዓላቱ የምንሰጠውን የወንጌል አገልግሎት ሁሉ ምእመናን አውቀው በእምነት አሜን፣ በደስታም እልል እንዲሉ ተርጉመን ምስጢሩን ማስረዳት ይገባናል፡፡ የተቀደሰውን ቅዳሴ፣ የተቆመውን ቁመት፣ የተነበበውን ወንጌል፣ የተሰበከውን ምስባክ፣ የቀረበውን ወረብ ቃሉን ተርጉመን ምስጢሩን ተንትነን ስንነግራቸው የምእመናን ተሳትፎ ይጨምራል፡፡ የአገልግሎቱ ፍቅር የበለጠ ያድርባቸዋል፡፡

164149_1457139483460_1682564302_893577_6995263_nያነሣነውን ታቦት ክብርና ምስጢር፣ የጥምቀተ ባሕሩን ምንነት፣ በዚህም ላይ ቅድስት ወንጌል ያላትን ኀይል ማሳየት ይጠበቅብናል፡፡ ይህ ሲሆን ምእመናን ለካህናት አባቶች ያላቸው የልጅነት መንፈስ ካህናት አባቶችም ለምእመናን ያላቸው የአባትነት መንፈስ ይጨምራል፡፡ በፍቅርና በአገልግሎታችን የበለጠ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንስባቸዋለን፡፡ በዓላትን ለማየት ብቻ የሚታደሙ የውጭና የሀገር ውስጥ ተመልካቾችን ወደ ድኅነት እንጠራለን፡፡

በየበዓላቱ ጉባኤያትን በማዘጋጀት፣ በአደባባይ ዝማሬን በማቅረብ፣ ምእመናንን በመቀስቀስ ታላቅ ድርሻ ያላቸው ሰንበት ትምህርት ቤቶችም የበዓላት አገልግሎቱ ምሰሶና ማገር መሆናቸውን የበለጠ ሊጠብቁ ይገባል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በምታከብራቸው የጌታችን ዐበይት በዓላት ያለውን አጠቃላይ የምእመናንን ተሳትፎ የመምራት በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረትም ቅርጽ የያዘ እንዲሆን የበለጠ መትጋት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የዝማሬያችን ጣዕም የአለባበሳችን ድምቀት፣ የዝማሬ ሥርዓታችን ስባት፣ በትሕትናና በፍቅር በመመላለሳችን፣ አንድነታችንና መተሳሰባችን በበዓላቱ ወንጌልን የምንሰብክበትን ክርስቲያናዊ አገልግሎት የበለጠ ያፈካዋል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያቱ በዓለሙ ሁሉ “ምስክሮቼ ትሆናላችሁ” /የሐ.ሥ.1፥9/ ያለውን ቃሉን እያሰብን የበዓላቱን መለከት ልንነፋ ይገባል፡፡ /2ሳሙ.6፥1/ በዓላቱን በማድመቅ ዋጋ እንደሚያገኙ በማመን የሚተጉ፣ እግዚአብሔር በጊዜው ጊዜ ያነሣሣቸውን የየአጥቢያውን ወጣቶችም ለአገልግሎታችን እንደተሰጠን እንደ አንድ ጸጋ ተቀብለን ልንጠቀምባቸው ይገባል፡፡

ምእመናንንም ከበዓላቱ ጋር ተያይዘው የሚዘወተሩ ሌሎች ደባል ሥጋዊ ክንውኖች ሳያዘናጓቸው ሃይማኖታዊ በዓላቱ ለወንጌል አገልግሎት ያላቸውን ድርሻ ማስጠበቅ ይገባቸዋል፡፡ በተለይም ባህላዊ ገጽታ ተላብሰው በበዓላቱ የጎንዮሽ የበቀሉ የሰይጣን ማዘናጊያዎችን ፈር ማስያዝ አለብን፡፡ በዓላችን ቅዱስ ወንጌልን የምንመሰክርበት ነው ካልን የትኛውም ዓይነት የሥጋ /የኀጢአት/ ሥራ ተደባልቆ እንዳይሠለጥንበት ደረጃ በደረጃ ከቤተሰቦቻችን ጀምረን በማስተማር ወደ ፍጹም ክርስቲያናዊ ባህል ማድረስ አለብን፡፡ በዓላቱ ለእግዚአብሔር የተቀደሱ ቀናት ናቸው፡፡ ስለዚህ በስካር፣ በዝሙት፣ በመዳራት፣ በዘፈን፣ በአምልኮ ባዕድ በማመንዘር፣ በጠብ በክርክር ወዘተ ሳይሆን እግዚአብሔርን ደስ በሚያሰኝ ፈሪሐ እግዚአብሔር ባለበት በትሑት መንፈስ በፍቅርና በደስታ በምስጋናም ማክበርን ጠብቀን ሌሎችንም ልናስተምር ይገባል፡፡

በበዓላቱ ሕፃናት፣ አረጋውያን፣ አካል ጉዳተኞችም ያለ ምንም ችግር በበዓላቱ እንዲሳተፉ ምቹ ሁኔታ መፍጠርም ይገባል፡፡ በዓላት በባህሪያቸው ደስ ብሎን የምናመሰግንባቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም ምስኪኖችን በማጽናናት በመደገፍ ከበዓሉ የክርስቲያን ወገን የሚገኘውን ደስታ ሁሉ ተሳታፊ ሆነው አምላካችንን እንዲያመሰግኑ እናግዛቸው፡፡ በዓሉን የክርስቲያን ወገን የሚያገኘውን ደስታ ሁሉ ተሳታፊ ሆነው አምላካችንን እንዲያመሰግኑ እናግዛቸው፡፡ በዓሉን የክርስቲያን ወገን የሚያገኘውን ደስታ ሁሉ ተሳታፊ ሆነው አምላካችንን እንዲያመሰግኑ እናግዛቸው፡፡ በዓሉን ለመድኀኒታችን ክብር ለእኛም በረከት እንዲሆን ብለን እስከ ጠበቅነው ድረስ ታናናሾችን መቀበልና ማክበር እርሱን መቀበልና ማክበር መሆኑን የነገረንን ቃሉን ማሰብ ተገቢ ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ ሐዋርያው “በነገር ሁሉ ደስ ልታሰኙ ለጌታ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን” እንዳለው በዓላት ማንንም ሳናሳዝን ለሁሉም ወገን ሐሴትን የምንሞላበት እንዲሆኑ ያስፈልጋል፡፡ ይህንንም ስናደርግ ጌታችን ደስ በሚሰኝበት የወንጌል ቃሉን በማሰብ፣ በመመስከር ሊሆን ይገባል እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ሐመር 19ኛ ዓመት ቁጥር 8 ታኅሣሥ 2004 ዓ.ም

ትምህርተ ጥምቀት በአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ

 

ጥር 7/2004 ዓ.ም
{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}Temkete{/gallery}

መግቢያ

ይህ ጽሑፍ መጽሐፈ ምሥጢር ከሚባለው ከአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ድርሰት የተወሰደ ሲሆን አባ ጊዮርጊስ ጥምቀትን አስመልክቶ የሰጠውን ድንቅ የሆነ አስተምህሮ እናስተውልበታለን፡፡

“…እነሆ ቅዱስ ጳውሎስ መንፈስ ቅዱስን “የክርስቶስ ሕይወት” በማለት ሰየመው መንፈስ ቅዱስ የክርስቶስ ሕይወት ከሆነ እንዴት አያየውም? ከማየት ዐሳብ ይቀድማልና ከውጫዊ እይታ የአእምሮ እይታ ይበልጣልና ዳግመኛ ቅዱስ ጳውሎስ የሰውን ዐሳብ ከራሱ ከሰውየው በቀር የሚያውቅ የለም፡፡ እኛ ግን የተሰወረውን ገልጦ ጥልቁን መርምሮ የሚያውቅ የእግዚአብሔር መንፈስ አለን” 1ቆሮ.2፥11 አለ፡፡ አንተ ግብዝ ሆይ አብን እንደሚያውቀው ዕወቅ /አስተውል/፡፡ በወንጌል እንደተነገረው ወልድ ብቻውን ምንም ምን ሊያደርግ አይችልም ከአብ ያየውን ይሠራል እንጂ፡፡ አብ የሚሠራውን ወልድም ይህንኑ እንደእሱ ይሠራል፣ አብ ልጁን ይወዳልን የሚሠራውንም ሥራ ሁሉ ያሳየዋል፡፡ ከዚህም የሚበልጥ ሥራ ያሳየዋል፣ እናንተም ታውቁና ታደንቁ ዘንድ ስለ መንፈስ ቅድስም  አስቀድመን ነገርናችሁ፡፡ በደለኞች ሆይ ከዛሬ ጀምሮ “ወልድ ከአብ ያንሳል አያህለውም” አትበሉ፡፡ “መንፈስ ቅዱስም ከወልድ ያንሳል አያህለውም ” አትበሉ፡፡

38138_128397600536483_127725783936998_143662_568874_nእኛ ግን አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ ባሕርይ፤ አንድ መንግሥት አንድ መገለጥ አንድ አኗኗር አንድ ሥልጣን አንድ አመለካከት አንድ መለኮት አንድ ዐሳብ አንድ ፈቃድና ሥርዐት አላቸው እንላለን፡፡ ፈቃዳቸው አንድ ነው ዐሳባቸው አንድ ነው፣ ሥርዐታቸውና ሕጋቸው አንድ ነው፣ ኀይላቸው አንድ ነው፣ እንደ አሕዛብ ልማድ ሦስት አማልክት አይባሉም፡፡ በሦስት አካል አንድ አምላክ ይባላሉ እንጂ፡፡  አንዱ አንዱን አይከተለውም ሁለተኛውም ሦስተኛውን አይከተለውም ከያዕቆብ አስቀድሞ ይስሐቅ ከይስሐቅ አስቀድሞ አብርሃም እንደነበረ ሁሉ ከአንዱ በፊት አንዱ አልነበረም፡፡

የአብ አኗኗር ከወልድ በፊት አልነበረም የመባርቅት ብልጭታ መታየት ታህል የዐይን ሽፋን እንቅስቃሴን የምታህል አይቀድመውም፡፡ እናት ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ታመናለች እንዲህም ታሳምናለች፡፡

እናታችንም ቤተ ክርስቲያን በረድኤተ እግዚአብሔር ጥላ ሥር ጸንታ ትኖራለች፡፡ አቤቱ በረድኤት ጥላ ሥር ጸንቶ የሚኖር ማን ነው? መቅደስህም በተሠራበት ቦታ አድሮ የሚኖር ማነው? ተብሎ እንደተጻፈ በሙሽራዋ ክርስቶስ ደስ እያላት የወልድን ኀይል አምና በምእመናን ፀንታ ትኖራለች፡፡ ቀኝ ክንዱ ታቅፈዋለች ግራ ክንዱም ከራሴ በታች ናት ተብሎ እንደተጻፈ በመንፈስ ቅዱስ ብርሃንነት ወደ ገነት ዓፀዶች ትመራለች፡፡ መንፈሰ ረድኤትህ መርቶ ወደ ምድረ ጽድቅ ያድርሰኝ ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ /መዝ.14፥1/

ከዚህም በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጠመቅን ስትፈልግ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ትመለሳለች፤ በዮርዳኖስ ወንዝ ለልጁ በመሰከረ0619156797-xlarge በእግዚአብሔር አብ ስም አንድ ጊዜ ትጠመቅ ዘንድ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ትወርዳለች፡፡ ዳግመኛም በዘካርያስ ልጅ በዮሐንስ እጅ በተጠመቀ በእግዚአብሔር ወልድ ስም ትጠመቅ ዘንድ ሁለተኛ ትወርዳለች፡፡ ዳግመኛም በዘካርያስ ልጅ በዮሐንስ እጅ በተጠመቀ በእግዚአብሔር ወልድ ስም ትጠመቅ ዘንድ ሁለተኛ ትወርዳለች የርግብ መልክ ባለው አካል አምሳል ከሰማየ ሰማያት ወርዶ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ በተቀመጠ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ስም ሦስተኛ ትጠመቃለች፡፡

ከዚህም በኋላ ከዮርዳኖስ ወንዝ ወጥታ አመተ ክርስቶስ ትባል ዘንድ ቅብዓ ሜሮንን ተቀብታ ማዕተበ ክርስትናን ገንዘብ ታደርጋለች፡፡ ቅብዓ ሜሮን የሃይማኖት ኀይል ነውና ሐዋርያት በዲዲስቅልያ መጽሐፋቸው እንደገለጹት በጥምቀት የተወለደ ሰው አምላክ ከድንግል የተወለደውን ልደት ይመስላል፤ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም እንደተወለደ ከርሷም ከተወለደ በኋላ ማኅተመ ድንግልናዋ ሳይለወጥ ተገኘ፡፡
በጥምቀት የተወለደ ሰውም እንደዚሁ ነው ከውኃውም ከወጣ በኋላ ወደ ጥምቀተ ባሕር የገባበትና የወጣበት ምልክቱ አይገኝም፤ መንገድህ በባሕር ውስጥ ነው ተብሎ በመዝሙረ ዳዊት እንደተነገረ ዱካህም ከጥልቅ ውኃ ውስጥ ነው ፍለጋህም አይታወቅም፡፡

ወደ እናታችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አርእስተ ነገር እንመለስ፡፡ ከዚህም በኋላ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በሰላም የተሰበከላችሁን የወንጌል ኀይል ተጫምታችሁ ያለውን ቃል ሰምታ የወንጌልን ቃል ጫማ በመጫማት አካሔዷን አሳምራ ወደ እግዚአብሔር ቤት ትገባለች ኤፌ.6፥15 በራሷም ላይ የዕንቊን ዘውድ ትቀዳጃለች ይኸውም የሃይማኖት አክሊል ነው ዳግመኛም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በራሳችሁ ላይ የሚያድነውን የራኀስ ቊር ድፉ የመንፈስ ቅዱስንም ሰይፍ በእጃችሁ ያዙ ይሄውም የእግዚአብሔር ቃል ነው ብሎ እንደተናገረ፡፡ ኤፌ.6፥17 በጣቶቿ ላይም የክብር ቀለበትን ታደርጋለች ይሔውም የድኅነት ምልክት የሆነ የክብር ማዕተብ ነው፡፡

ከዚህም በኋላ አብርሃም ወዳለባት ይስሐቅም በበግ መሥዋዕትነት ወደ ዳነባት ከምድር እስከ ሰማይ ድረስ የእግዚአብሔር መላእክትም ሲወጡባትና ሲወርዱባት ያዕቆብ ባያት የወርቅ መሰላል ወደ ሙሸራው አዳራሽ ትገባለች፤ በእስራኤል ልጆች በደል ምክንያት ምስክር የሚሆኑ ሕግና ትእዛዝ የተጻፈባት ሙሴ የተሸከማት ጽላት ናት መልከጼዴቅም የቤተ ክርስቲያንን ምሥጢረ ቊርባን ሥርዐት የሚገልጽ የኅብስትና የወይን ግብር ያቀረበባት ናት ዘፍ.14፥18

5546126301-xlargeዳዊትም አቤቱ አንተ ታቦትህን ይዘህ ወደምታርፍባት ቦታ ተነሥ፡፡ እያለ የእግዚአብሔር ሕግ በተጻፈባት ታቦት ተነሥ፤ እያለ የእግዚአብሔር ሕግ በተጻፈባት ታቦት ፊት ምስጋና ያቀረበባት ናት አሳፍ የተቀኘላት፣ የቆሬ ልጆችም በምስጋና መሰንቆዎች የሚዘመሩላት የቆሬ ልጆችም በምስጋና መሰንቆዎች የሚዘምሩላት ናት፡፡ ነቢዩ ኤርምያስ ዐለቱን ሰንጥቆ የደብተራ ኦሪቱን ንዋየ ቅድሳት ያስቀመጠባት፣ የተሠነጠቀችውን ዐለት መልሶ እንደነበረችው ያደረጋት፣ እንደ ብረት መዝጊያም የሆነችለት፣ ቁልፎቿንም ለፀሐይ አደራ የሰጠባት ናት፡፡ መዝ.131፥8፣ ተረፈ ኤር.83፥18

ኤልያስ መልአኩ ያቀረበለትን የተዘጋጀ ኅብስት የበላባት፣ በተመገበው ምግብ ኀይልም ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት የተጓዘባት ናት፡፡ ዕዝራ ሱቱኤል መጻሕፍተ ብሉያትን የምታሳውቀውን ከመልአኩ ዑራኤል እጅ ተቀብሎ የምስጋና ጽዋን የጠጣባት፣ አእምሮውም በዕውቀት ተሞልቶ ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ብሉያትን አፉ ከመናገር ሳያቋርጥ የቆየባት ናት፡፡ /1ነገ.19፥5-8 ዕ.ሱ.3 40/ ዘካርያስ ነጫጭና ጥርኝ ፈረሶችን ያየባት ናት፡፡ ዘካ.1፥8

ዳንኤልም የእሳት ሠረገላን ያየባት ናት፤ ዘመናት የማይወስኑት አምላክ ከሰው ልጅ ጋር ከበላያቸው ላይ የተቀመጠባቸውን ዙፋኖች ዳንኤል ያየባት ናት፤ ዕንባቆም በሁለቱ እንስሳት መካከል እግዚአብሔርን ያየባት ነቢያትም ሁሉ ደስ የሚያሰኝ ድምጽ የትንቢት ምስጋናን የሚያሰሙባት ናት፡፡ የገሊላ ሕፃናትም ኅሊናን የሚመስጥ፣ ልቡናን የሚማርክ፣ አጥንትን የሚያለመልመውን ማኅሌታዊ ምስጋናን የሚያመሰግኑባት ናት፡፡ ዳን.7፥9፣ ዕን.3፥2

ጴጥሮስ የመንግሥተ ሰማያትን ቁልፍ የተቀበለባት፤ ጳውሎስም የቤተ ክርስቲያን ብርሃን ይሆን ዘንድ የተጠራባት፤ ዮሐንስም እንደነጋሪት6161970531-xlarge ድምጽ እያሰማ ምሥጢረ መለኮትን የሰበከላት፤ ሐዋርያትም መንፈስ ቅዱስን በአምሳለ እሳት የተቀበሉባት ናት፡፡ የእግዚአብሔርን መሥዋዕት የሚያቀርቡበትን መንበረ ታቦት ለመጐብኘት ማኅበረ መላእክት የሚፈሯት ማኅበረ ሰማዕታትም የመከራቸውን ዋጋ ተቀብለው የክብር አክሊልን የሚቀዳጁባት ናት፡፡

ከዚህም በኋላ በሙሽራይቱ መጋረጃ ውስጥ ለምእመናን ምሳ ይሆን ዘንድ ሙሽራው ይሠዋባታል፤ መሥዋዕቱንም ከማየቷ የተነሣ ጉልበቶቿ ይብረከረካሉ፤ በደሙ ጽዋ ውስጥ ደሙ ሲንጠፈጠፍ ባየችም ጊዜ አንጀቷ ይላወሳል፤ ሥጋውን በፍርሃት፤ ትበላለች ደሙንም በመንቀጥቀጥ ትጠጣለች፤ ከዚህም በኋላ የሃይማኖት ነበልባል በልቡናዋ ውስጥ ይቀጣጠላል፤ ከሆዷም ውስጥ የፍቅር ሞገድ ይናወጣል፡፡

አሁንም በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት ላይ የክህደትን ቃል የተናገረውን የአርጌንስን ነቀፋ እነሆ ፈጽመን ፍጥረቱን ሁሉ ፈጥሮ ለሚገዛ ለእግዚአብሔር አብ ምስጋና፣ የመንግሥትና የነገሥታት ጌታ ለሆነው ለወልድ ስግደት፣ ልቡና ያሰበውን ኩላሊት የመላለሰውን መርምሮ ለሚያውቅ ለመንፈስ ቅዱስ ጌትነት ይገባል እንላለን፡፡ ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ልቡናው ስንኩል ዐሳቡ ብኩን የሆነ የአርጌንስ ነቀፋው ተፈጸመ የጽዮን ወገን የምሆን የቄስ ልጅ የምሆን እኔ ጊዮርጊስ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ መለኮት የአንዱ ከአንዱ በለጠ እንዳይባል ለሥላሴ አንድነት ሦስትነት ሃይማኖት ቀንቼ እየደረስኩ በቃሌ አጻፍኳት በባሕርና በየብስ በበረሃና በደሴት ለእርሱ ክብር ምስጋና የሚገባው ነው ሥጋዊ ደማዊ የሆነ ፍጥረት ለእርሱ ሊሰገድለት ይገባል ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ግዝረት

ጥር 5/2004 ዓ.ም

በዲ/ን አሻግሬ አምጤ

ግዝረት ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ንዑሳን በዓላት አንዱ ነው፡፡ እነዚህ ንዑሳን በዓላት የሚባሉትም ስብከት፣ ብርሃን፣ ኖላዊ፣ ግዝረት፣ ቃና ዘገሊላ፣ ልደተ ስምዖን፣ ደብረ ዘይት፣ የመጋቢት መስቀልና መስቀል ናቸው፡፡ ነቢያት ይወርዳል፤ ይወለዳል ብለው በትንቢት ይጠባበቁት የነበረው መሲሕ የዓለም ብርሃን፣ የነፍሳት ጠባቂ መሆኑን አምነን የምናከብራቸው ስብከት፣ ብርሃንና ኖላዊ ይባላሉ፡፡ ከእናቱና ከደቀመዛሙርቱ ጋር በሰርግ ቤት የተገኙበት ቃና ዘገሊላ፣ በአርባ ቀኑ ወደ ቤተ መቅደስ የገባበትና አረጋዊ ስምዖንን የሰላሳ ዓመት ጎልማሳ የሆነበት “ባሪያህን በሰላም ታሰናብተዋለህ ዐይኖቼ ማዳንህን አይተዋልና” በማለት የተናገረበት ልደተ ስምዖን ከንዑሳን በዓላት ይመደባሉ፡፡ የዚህ ጽሑፍ ትኩረት ግዝረት በመሆኑ ሀተታዬን ወደ እሱ እመልሳለሁ፡፡

ፍቅር ወልድን ከዙፋኑ ስቦት ወርዶ ሥጋ ማርያምን ተዋሕዶ፣ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ማሕፀኗን ዓለም አድርጎ ከቆየ በኋላ ታኅሣሥ ሃያ ዘጠኝ በዘመነ ማቴዎስ ተወለደ፡፡ በተወለደ በስምንተኛ ቀኑ ሥርዓተ ኦሪትን ሊፈጽም ተገረዘ፡፡ ግዝረትን በስምንተኛው ቀን መፈጸሙ፣ በተወለደ በአርባ ቀኑ ወደ ቤተ መቅደስ መሔዱ ሕገ ኦሪትን ሊያጸና፣ ሊፈጽም፣ ምሳሌውን በአማናዊው ሊተካ እንጂ ኦሪትን ሊሽር ላለመምጣቱ እማኝ ምስክር ነው፡፡ የተሻረ ነገር መታሰቢያ የለውም የተፈጸመ፣ በምሳሌና በትዕምርታዊነት የተወከለ ግን ጥንተ ታሪኩን፣ ትንቢቱን ጠይቀን ምሳሌውን ከትርጓሜ መጻሕፍት እንረዳለን፡፡

ግዝረት አይሁድ የአብርሃም ልጅ መሆናቸውን ማረጋገጫ ማኅተም ነው፡፡ በሕግና በሥርዐት የሚመሩ መሆናቸውን አንድ አምላክ ማመናቸውን የገለጡበት ነው፡፡ አይሁድ በግዝረት የአብርሃም ልጅነታቸውን እንዳረጋገጡ፣ ክርስቲያኖችም በጥምቀት የሥላሴ ልጅነታቸውን ያረጋግጣሉ፡፡ ይህም የሚሆነው ግዝረት የጥምቀት ምሳሌ መሆኑን ያስረዳል፡፡ በሐዲስ ኪዳን ጥምቀት እንጂ መገረዝ፣ አለመገረዝ አይጠቅምም፡፡ በሐዲስ ኪዳን ግዝረት በፍቃድ እንጂ እንደ አይሁድ እኛም የአብርሃም ልጆች እንድንባል የምንገረዝ አይደለም፡፡ ለእኛ ለክርስቲያኖች ከሥላሴ በመንፈስ ቅዱስ መወለድ እንጂ መገረዝ የአብርሃም ልጆች አያሰኘንም፡፡ አለመገረዝ እንደማይጠቅም ቢያውቅም ጌታችን መገረዝ ያስፈለገው ሕገ ኦሪትን ለመፈጸም ሲሆን በእኔ ግን ምስጢረ ጥምቀትን ፈጽሜ አድናችኋለሁ ሲለን ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የማይጠቅምና ለነገረ ድኅነት የማያበቃ ነገር ቢያጋጥመን እንኳ በጥበብና በማስተዋል እንድናደርገው ሲያስተምረን ነው፡፡ ሥርዐተ ኦሪታችንን ስላፈረሰብን ለሞት አበቃነው ብለው ምክንያት እንዳያገኙና ይህንን ስበብ አድርገው ከነገረ ድኅነት ተለይተው እንዳይቀሩ የሚያደርጉትን በማድረግ፣ የሚወዱትን በመውደድና አብሯቸው የሥርዐታቸው ተካፋይ በመሆን በፍቅር ስቦ ወደ አማናዊው ድኅነት፣ ወደ ጥምቀትና የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ወደማመን መልሷቸዋል፡፡

የመምህሩን አሰረፍኖት የሚከተለው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በደርቤን በሚያስተምርበት ወቅት ጢሞቴዎስ ሲከተለው መገረዝ አለመገረዝ ጥቅምም ጉዳትም እንደሌለው እያወቀ የገዘረው በዙሪያው ብዙ አይሁድ ስለነበሩ እነርሱን ላለማስከፋትና ላለማስደንበር መሆኑን ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ “.. የኦሪት ሕግ ለማዳን ብቁ አለመሆኗን እየደጋገመ በድፍረት ይሰብክ የነበረው መምህረ አሕዛብ ቅዱስ ጳውሎስ እንኳ አይሁድን ላለማስደንበር ሲል ሥርዐተ ኦሪትን ይፈጽም ነበር፡፡” /1978፣ 29/ በማለት ገልጸዋል፡፡

ግዝረት ለእስራኤል ከአብርሃም ለመወለዳቸው ምልክት ብቻ ሳይሆን የአብርሃምን ሃይማኖት ለመያዛቸውም መታወቂያ ነበረች፡፡ ጌታችንም ምንም እንኳ የባሕርይ አምላክ ቢሆን በሥጋ የአብርሃም ልጅ ነውና የአብርሃም ልጅነቱን የአብርሃምን ሃይማኖት ማጽናቱን ለማስረገጥ ግዝረትን ፈጸመ፡፡ አንድም በግዝረት ደም ይፈስሳለና አብርሃም በዘጠና ዘጠኝ ዓመቱ በመገረዝና ደሙን በማፍሰስ አበ ሰማዕታት ተብሏልና ግዝረት የሰማዕትነት ምሳሌም ነው፡፡

ጥር ስድስት በሚነበበው ስንክሳር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አረጋዊ ዮሴፍን ሕፃኑን የሚገርዝ ባለሙያ ፈልጎ እንዲያመጣ እንደነገረችው፣ አረጋዊውም ባለሙያውን ፈልጎ እንዳመጣ ይናገራል፡፡ ባለሙያውም ሕፃንን በደምብ ያዙልኝ ብሎ ለመግረዝ ሲሰናዳ ባለሙያ ሆይ ደሜ ሳይፈስ መግረዝ ትችላለህን ብሎ እንደጠየቀው፣ ከስቅለቱ በፊት ደሙ እንደማይፈስ እንዳስተማረው፣ በዚህም ምክንያት ለመግረዝ የመጣው ባለሙያ፣ አምላክ ወልደ አምላክ መሆኑን አምኖ እንደሰገደለት ለመግረዣ ያዘጋጀው ምላጭም እሳት ላይ እንደተጣደ ቅቤ መቅለጡን ይተርካል፡፡ በመቀጠልም ክርስቶስ ዘር ምክንያት ሳይሆነው እንደተፀነሰ፣ ማኅተመ ድንግልናዋን ሳይለውጥ እንደተወለደ እንደ ነቢዩ ሕዝቅኤል “ሳይከፈት ገብቶ ሳይከፍት እንደወጣ” ስለት ምክንያት ሳይሆነው፣ በግዝረት ምክንያት ደም ሳይፈስ በተአምራት ተገረዘ፡፡ በአጠቃላይ ግዝረት በኦሪት የአብርሃም ልጅነትን፣ የአብርሃምን ሃይማኖት መያዝን ማረጋጋጫ ማኅተም ሲሆን በሐዲስ ኪዳን በጥምቀት ተተክቷል፡፡ ለአማናዊው ግዝረት /ለጥምቀት/ ምሳሌ በመሆኑም በሥራ የአብርሃም ልጅነትን፣ በእምነት የሥላሴ ልጅነትን አግኝተንበታል፡፡ ወርደህ ተወልደህ፣ በነፍስ በሥጋ፣ ከተቆራኘን ባለጋራ አድነን ብለን የተጣራነው ተሰመቶ፣ ሥርዓተ ኦሪትን ፈጽሞ ወደ ሥርዓተ ሐዲስ የሚያሸጋግረን መሆኑን ያመንበት፣ በጥምቀቱ ቦታ በዮርዳኖስ የተቀበረው የባርነታችን ደብደቤ የሚቀደድ መሆኑን በምሳሌ ያወቅንበት ግዝረት ነው፡፡

Begamogofa

በዲታ ወረዳ የቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን የቃጠሎ አደጋ ደረሰበት

ጥር 5/2004 ዓ.ም

ምንጭ፡- አርባ ምንጭ ማእከል

በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት፣ በዲታ ወረዳ፣ ጋና ደሬ ቀበሌ፣ የቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ 29 ቀን 2004 ዓ.ም. ከሌሊቱ በስድስት ሰዓት አካባቢ በእሳት ቃጠሎ አደጋ ደረሰበት፡፡

Begamogofa

የቦታው አቀማመጥና አደጋው የደረሰበት ሰዓት ሌሊት በመሆኑ በቦታው ምንም ዓይነት ነዋያተ ቅድሳት ማትረፍ እንዳልተቻለ በቦታው የሚገኙት የደብሩ አገልጋይ ገልጸዋል፡፡ የአደጋውን መከሰት ሰምተው የመጡት የአካባቢው ምዕመናን ከሌሊት ጀምሮ ጥልቅ ሀዘናቸውን በለቅሶ ሲገልጹ እንደነበር በቦታው የተገኙት የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ዘግበዋል፡፡

የአካባቢው ምዕመናን በወቅቱ አደጋውን ሰምተው ለመጡት ለብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱሰ ሲኖዶስ አባል፣ ለሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ በአርባ ምንጭ ከተማ ለሚገኙ የደብር አለቆች፣ ለአርባ ምንጭ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ ከመንግሥት በኩል ለጋሞ ጎፋ ዞን ፕሬዝዳንት ለአቶ ጥላሁን ከበደ፣ ለተለያዩ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ለፌደራል ፖሊስ ጸጥታ አስከባሪዎች እንደተናገሩትና በተደረገው ገለፃ የአደጋው መንስኤ ታኅሣሥ 28 ቀን በወረዳው ከተማ ዛዳ በሚገኘው የአካባቢው አብያተ ክርስቲያናትም ለጥምቀተ ባሕር የሚገለገሉበትን ቦታ ላይ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮች የገና በዓልን ለማክበር በመውጣታቸው ግጭት እንደነበርና ይህ በሆነ ማግስት ቤተ ክርስቲያኑ መቃጠሉን ገልጸዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱሰ ሲኖዶስ አባል፣ የሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ በአርባ ምንጭ ከተማ የሚገኙ የደብር አለቆች፣ የአርባ ምንጭ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ የመንግሥት ባለሥልጣናትና የፌደራል ፖሊስ ጸጥታ አስከባሪዎች በቦታው ተገኝተው ምዕመናንን ለማረጋጋትና ለማጽናናት ችለዋል፡፡ ከዚህ በተያያዘ በወረዳው የሚገኙ አጎራባች ቀበሌዎች ውስጥ የሚኖሩ ምዕመናን ወደ ወረዳው ከተማና ቤተ ክርስቲያኑ ወደ ተቃጠለበት ቀበሌ በመድረስ ህዝቡን አጽናንተው የአብሮነት ስሜታቸውንም ሲገልጹ እንደነበር ተስተውለዋል፡፡

በዕለቱ በቃጠሎ አደጋ ለደረሰበት ቤተክርስቲያን የዕርዳታ ማሰባሰብ ሥራ የተጀመረ ሲሆን የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በማኅበረ ቅዱሳን የአርባ ምንጭ ማእከልና ምዕመናን በዕለቱ ማድረግ የሚችሉትን ቃል ገብተዋል፡፡ የአካባቢው ምዕመናንም ሥራውን በፍጥነት ለማስጀመር በዕለቱ እንጨት በማምጣት የተሠማሩ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኑ በፍጥነት እንዲሠራላቸው ያላቸውን ጥልቅ ጉጉት ሲገልጹ ተስተውለዋል፡፡