st.Tomas

ዳግም ትንሣኤ (ለሕፃናት)

ሚያዝያ 12/2004 ዓ.ም.

በእኅተ ፍሬስብሐት

st.Tomasጌታችን በተነሣበት ዕለት የክርስቶስ ደቀመዛሙርት ተሰብስበው ሳለ ጌታችን በመካከላቸው ቆመና “ሰላም ለእናንተ ይሁን “አላቸው፡፡ የነበሩበት ቤት በሩም መስኮቱም ተቆልፎ ስለነበር ደቀ መዛሙርቱም በጣም ደነገጡ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም  “አትፍሩ እኔ አምላካችሁ ነኝ” ብሎ የተወጋ ጎኑን እና የተቸነከሩ እጆቹን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ጌታ ከሞት መነሣቱን አመኑ፡፡ ደቀመዛሙርቱንም(ተማሪዎቹንም) ሕዝቡን እንዲያስተምሩ ላካቸው፡፡

በዚህ ዕለት ከ12ቱ ደቀመዛሙርት አንዱ የሆነው ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ ደቀመዛሙርቱ የጌታን መነሣት እና እነርሱም እነዳዩት ነገሩት፡፡ እርሱ ግን በዓይኔ ካላየሁ አላምንም አለ፡፡

 

ከስምነት ቀን በኃላ እንደገና ቶማስ አብሯቸው ሳለ በሩ እንደተዘጋ ጌታችን መጣ፣  በመካከላቸውም ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡ ቶማስ ትንሣኤውን እነደተጠራጠረ ስላወቀ  እጅህን አምጣና የተወጋ ጎኔን እና የተቸነከሩ እጆቼን ዳስስ አለው፡፡ ቶማስም በዳሰሰው ጊዜ አምላክ መሆኑን ዐወቀ፡፡ ይኽ ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሁለተኛ ጊዜ ቶማስ ባለበት  ለደቀመዛሙርቱ የተገለጠበት ዕለት በመሆኑ ዳግም ትንሣኤ ተብሎ ተሰየመ፡፡ ዳግም ማለት ሁለተኛ ማለት ነው እሽ ልጆች፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት በሌላ ታሪክ እሰክንገናኝ ደኅና ሁኑ!