ለእውነት እንጂ በእውነት ላይ ምንም ለማድረግ አንችልም

በአሁኑ ዘመን ዓለማችን በከፍተኛ የአስተሳሰብ፣ የቴክኖሎጂና የማኅበራዊ ለውጥ ሒደት ውስጥ ትገኛለች፡፡ እነዚህን የለውጥ ሒደቶች  የመረዳት አቅም ያጣ ግለሰብም ሆነ ተቋም የሚሻውን በቀላሉ መፈጸምና ማስፈዐም አይችልም፡፡  አላማዎቹ በጎም ይሁኑ ክፉ ከተጨባጭ ሁኔታዎቹ ተነጥሎ ማሳካት አይችልም፡፡ በሀገራችንም ከመንግሥት ጀምሮ በርካታ ድርጅቶች ከሙከራ ትግበራ አንሥቶ ሀገር አቀፍ አፈጻጸም እስኪሆኑ ድረስ እነዚህን ሁኔታዎች ያገናዘቡ የተለያዩ የአሠራር ማሻሻያዎችን ተግባራዊ እያደረጉ ነው፡፡
ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም በዚህ ዓለም ያሉ የለውጥ ሁኔታዎችን ከግምት በማስገባት ለጊዜያችን የሚመጥን፣  የተቀበለችውን የእግዚአብሔርን መንጋ የመጠበቅ ሐላፊነቷን መወጣት የሚያስችላት፣ ከክርስቶስ ፍቅር የማይለይ አሠራርን በአመራርና አስተዳደራዊ ክፍሎቿ ማስገባት ግዴታዋ ሆኗል፡፡ ግዴታውን ያስከተለው ደግሞ ሰው ሳይሆን አጠቃላይ ዓለማዊ ሆኔታው ነው፡፡ ይህ ለውጥ ደግሞ የማይካድ እውነት ነው፡፡ ለዚህ እውነታ መሥራት ደግሞ ተገቢም አስፈላጊም ነው፡፡
ክርስቲያኖች አነሰም በዛም የጊዜውን የአሠራር ለውጥ ሒደት እያፋጠነ ያለው የመረጃ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚዎች እየሆኑ ነው፡፡  የመረጃ ቴክኖሎጂው ደግሞ ክርስቲያኖች ክፉና ደጉን እንዲያውቁ ለማድረግ እገዛ አድርጎላቸዋል፡፡ ከዚያም አልፎ የእነሱ የሆነውን ከሌሎች ጋር ማነጻጸራቸው አይቀሬ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ደግሞ የክርስቲያኖች ነች፡፡ ስለዚህ የእኛ ብለው ላመኑባት ቤተ ክርስቲያን በጎውን እንድትይዝ፣ ከክፉው እንድትሸሽ ይመኛሉ፤ ለሚመለከተው ያሳስቡበታልም፡፡ ለዚያም ይሠራሉ፡፡ ይህም ሌላው እውነታ ነው፡፡

ምእመናን ይህን ወቅታዊ የለውጥ ሒደት ከግምት አስገብተው ቤተክርስቲያናቸውን ከመጠበቅ አንፃር ዛሬ ይዛ እንድትገኘ ከሚፈልጉአቸው ዋና ዋና ጉዳዮች አንዱ የአመራርና አስተዳደራዊ አቅምን የማጠናከር ተግባርን ነው፡፡
የአመራርና አስተዳደር አቅም ማለት ደግሞ የአሠራር፣ የአደረጃጀትና የሰው ኃይል አቅምን ይመለከታል፡፡ ያለን አሠራር ከነቀፋ የሚያድነን፣ ለመተማማት ሰበብ የማይፈጥር /ግልጽ/ ያጠፋ የሚቀጣበት፣ ያለማ የሚከብርበት /ተጠያቂነት የሰፈነበት/ እንዲሆን ነባራዊ ሁኔታው ያስገድዳል፡፡ ለዚህም ከሕገ ቤተክርስቲያኑ ጋር የማይጋጭ፣ በየደረጃው ያሉ የሥራ ክፍሎችን እርምጃ የሚያፋጥን ደንብና መመሪያ አዘጋጅቶ ማጽደቅ ይፈልጋል፡፡  ይህ ደግሞ ያለንን መዋቅርና አደረጃጀት እንድንፈትሽ ይጠይቃል፡፡ አካባቢያዊ ለውጦችን ከግምት አስገብቶ በዘመናዊው የአስተዳደር ዘይቤ የሚመራ የሰው ኃይል በየደረጃው መቀመጥ ይኖርበታል፡፡ እነዚህ ግፊቶች የተወሰኑ ግለሰቦች ወይም ቡድኖች ያመጡት አይደለም፡፡ የአጠቃላዩ የለውጥ ግስጋሴ ያስከተላቸው ናቸው፡፡ ከላይ የተጠቀሱትን ነጥቦች በየጊዜው ከሚፈጠሩ ሁኔታዎች ጋር በማስተያየት፣ ነባር፣ ጠቃሚና መንፈሳዊ የሆኑ፤ መቼም መች የሚያስፈልጉንን ኦርቶዶክሳዊ መገለጫዎቻችንን ከመጠበቅ ጋር እያጣጣሙ ማካሔድ ለነገ የማይባል ተግባር ነው፡፡ በፍጥነት ተግባራዊ እንድናደርግ ያስገደደንም ከላይ የጠቀስናቸው ተጨባጭ እውነታዎች ናቸው፡፡ ለዚህ እውነታ ደግሞ ማድረግ ያለብንን እንድናደርግ ያስፈልጋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስም እነዚህን የምእመናንን ትኩረቶች ተረድቶ በቅርቡ የአመራርና አስተዳደራዊ አቅምን ለመገንባት ወይም የተሻሉ ጠቃሚ ለውጦችን ለማምጣት ያሳየው ፍላጎትና ጅምር እንቅስቃሴ የሚበረታታ ነው፡፡  «ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና ዘመኑን ዋጁ» ያለውን የሐዋርያውን ምክር ሰምቶ እነዚህን ጅምር እንቅስቃሴዎች መደገፍ ደግሞ የክርስ ቲያኖች ሁሉ ድርሻ ነው፡፡

ይሁን እንጂ እነዚህን ተፈላጊ ለውጦች ለማምጣት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች አልጋ በአልጋ ሆነው እንደማይሔዱ በቅርቡ የተከሰተው ውጣ ውረድ አመላካች ነው፡፡ይሁንና የቤተክርስቲያኒቱን አንድነትና የቅዱስ ሲኖዶስን የሥልጣን የበላይነት ከማስጠበቅ ጋር ተገቢ ለውጦችን አቅዶ መተግበርን ጊዜው የማይቀር አድርጎታል፡፡ የአሠራር ማሻሻያዎችን ለማምጣት በሚደረጉ የውይይት ሒደቶች በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት  መካከል የተለያዩ አስተያየቶች ቢከሰቱ እንኳን ልዩነቶቹ ሊከበሩ ይገባል፡፡ ለመግባባት የሚያስችሉ፣ በበጎ ሐሳብ የሚፈጸሙ ተከታታይ ውይይቶችን ማድረግ ግን አስፈላጊ ነው፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሆኑ አባቶች ሁሉ ፍላጎት ለራስ ሳይሆን ለቤተክርስቲያን እስከሆነ ድረስ የአስተያየት ልዩነቶች ቢንፀባረቁም ከብዙኃኑ ብፁዓን አባቶች ውሳኔ ለመለየት አያበቃም፡፡ የራስ ፍላጎቶች እየገነኑ ከመጡ ግን መለያየትን ይጋብዛሉ፡፡ መጽሐፍም «መለየት የሚወድ ቢኖር ምኞቱን ይከተላል» እንዳለ፡፡

ሁሉም የቅዱስ ሲኖዶስ  አባላት  ለሺሕ ዘመናት ብዙ ውጣ ውረዶችን እያለፈች ለኢትዮጵያና ለዓለም ሕዝብ ጭምር እንደብርሃን የሚታዩ በጎ ተግባራትን ስትፈጽም የኖረችው ቤተክርስቲያን ባለአደራዎች እንደሆኑ እናምናለን፡፡  አባቶች ይህንን ተረደተው በስውርም ይሁን በግልጽ፣ በግልም ይሁን በቡድን የሚፈጸሙ ጣልቃ ገብነቶችን ተቋቁመው እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለጊዜያችን የሚያስፈልገውን የአመራርና የአስተዳደር ዓይነትና ደረጃ በቤተክርስቲያን ማስፈን አለባቸው የሚል እምነት አለን፡፡ ለዚህ ደግሞ የተጠሩለትን ሕይወትና ዓላማ ከመረዳት ጀምሮ እውነትን ለማገልገልና ለዚያም መከራ አስከመቀበል ለመትጋት ቁርጠኝነት ይጠይቃል፡፡ ለሚገባና እውነት ለሆነው ነገር መከራን መቀበል የሚገባ ነውና፡፡

በዓለም ያሉት ለውጦች ደግሞ ተጨባጭ ስለሆኑ ለእነዚህ እውነታዎች ተገቢውን ምላሽ በመስጠት ረገድ የሚኖረን ቁርጠኝነትም ከመለያየት ይልቅ ያቀራርባል፡፡ ያሉትን የለውጥ ሒደቶች፣ የክርስቲያኖችን በጎ ፍላጎት ካልካድን በስተቀር በእርግጠኝነት የአሠራር ማሻሻያዎችን የተጠየቅንበት ጊዜ አሁን ነው፡፡ ያሉት ሁኔታዎች እውነት ናቸውና ለእው ነት በእውነተኛ መንገድ ማገልገል አለብን፤ ሐዋርያው እንዳለው «በእውነት ላይ ምንም ለማድረግ አንችልምና፡፡» ስለዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ዛሬም ይሁን ነገ በግልና በቡድን በሚፈጸሙ የጨለማ ሥራዎች ሳይደናገጡ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለመፈጸም ተገቢውን አሠራር  እውን ለማድረግ በረድኤተ እግዚአብሔር እንደሚንቀሳቀሱ እምነታችን ነው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በምልዓተ ጉባኤው አሉ ብሎ ያስቀመጣቸውን በአመራሩና በአሰተዳደሩ የታዩ ችግሮችን ካልፈታና መፍታት የሚያስችሉ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነባቸው አሠራሮችን ለመዘርጋት ቁረጠኝነት ካጣ ቤተክርሰቲያን በሒደት ሊገጥማት የሚችለው ፈተና ማኅበረ ቅዱሳንን በእጅጉ ያሳስበዋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በምልዓተ ጉባኤው በቤተ ክርስቲያኒቱ ተንሰራፍተዋል ያላቸውን የአሠራር ችግሮች ግልጽ ካደረገበት ጊዜ ጀምሮ ቤተክርስቲያኒቱ በሁለት ተገቢ ባልሆኑ የአካሔድ አጣብቂኝ ውስጥ እንዳትወድቅ ማኀበራችን  ስጋት አለው፡፡ አንደኛው ቅዱስ ሲኖዶስ በምልዓተ ጉባኤው ግልጽ ያደረገው የውስጥ አሠራር ችግር ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ እነዚህን የአሠራር ችግሮች አጋኖ በማራገብ ቤተክርስቲያኒቱን በቅጥረኛነት ለማጥፋት የሚካሔደው የተሐድሶ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ከዚህ አጣብቂኝ ሌላ በሚኖሩ ኋላቀርና ብልሹ አሠራሮች በመመረር ምእመናን የተለያየ አደረጃጀት ፈጥረው በራሳቸው ማስተዋል በመንቀሳቀስ ለቤተክርስቲያን መከፋፈል ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እንዲሁም የያዝነውን ደካማ አሠራር የጠሉ በመንፈስ ያል ጠነከሩ ምእመናን ይሰናከላሉ፡፡ ሥራዎቻችንን ከሚሠሩበት መሥሪያ ቤት፣ ካላቸው ድርጅት ተሞክሮ፣ ከሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት ዕድገትና ግስጋሴ ጋር የሚያስተያዩት ደግሞ የአመራርና የአስተዳደር ዘይቤያችንን በመናቅ ይለዩናል፡፡ ከዚያም አልፎ የቤተክርስቲያኒቱ ቅርስ፣ ሀብትና አስተዳደር በአጽራረ ቤተክርስቲያን እጅ እስከ መያዝ ሊደርስ ይችላልና፡፡ ቤተክርስቲያን የማትሸነፍ ቢሆንም የብዙ ምእመናን ሕይወት መፈተኑ የማይቀር ይሆናል፡፡

ማኀበራችን ደግሞ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ሲንቀሳቀስ የነበረው ቤተክርስቲያን ይህ እንዳይገጥማት ነው፡፡ ስለዚህ ያሉ እውነታዎችን ያገናዘበ ችግር ፈቺ አሠራር እንዲዘረጋ ይፈልጋል፡፡ የምንጊዜም ፍላጎቱ ይህቺን ታሪካዊ፣ ሐዋርያዊና ቅድስት ቤተክርስቲያን ያሉአትን ትውፊት፣ ቅርስና አስተምህሮ ጠብቆ የሚያቆይ የአመራርና የአስተዳደር ሥርዓት እንዲኖራት ብቻ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በአቢዮት ሳይሆን ሓላፊነት ያለበት ቅዱስ ሲኖዶስ በሚሰጠው አቅጣጫ መሠረት በተገቢ ባለሙያዎች በተጠና መንገድና ከመቼውም ጊዜ በላይ በፍጥነት ተግባራዊ እንዲሆን ይፈልጋል፡፡   

በመሆኑም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አባቶች  ለዚህ ትውልድ የደረሰችው ቤተክርስቲያን ወሳኝ ባላደራነታቸውን ተረድተው ከቀደሙት አባቶቻቸው ቆጥረው ሰፍረው የተረከቡትን የቤተክርስቲያኒቱን መንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብት ለተተኪው ትውልድ በአግባቡ ማስረከብ ይገባቸዋል፡፡ ለዚህም ይህንን ለማድረግ የሚያስችል ኦርቶዶክሳዊና ዘመናዊ አስተዳደርን የማስፈን ሐላፊነታቸውን በሰከነና አሳማኝ በሆነ አካሔድ እንደሚፈጽሙ እምነታችን ነው፡፡ ይህንንም ስንል ያንን በማድረግ ሒደት የሚኖሩ የተለያዩ አስተያየቶችም አንዱን አሸናፊ ሌላውን ተሸናፊ አደርጎ ከማሳየት ይልቅ በየጊዜው ከሚኖሩ ለውጦች ጋር እየተፈተሹ የሚተገበሩ የአካሔድ ዓይነቶች ተደረገው መወሰድ እንዳለባቸው ከመጠቆም ጋር ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ሕገ ማኅበሩን አጽድቆ የሥራ ፈቃድ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶስ እነዚህን ተፈላጊ የአሠራር ማሻሻያዎች ለማምጣትና ተግባራዊ ለማድረግ በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ የሚሰጠው ሓላፊነት ካለ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ ይገልጻል፡፡  

ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶችም አባቶቻችን የሚያደርጉአቸውን የለውጥ ምክክሮች በበጎ በመመልከት ለጊዜያችን የሚገቡና አላራመድ ላሉን ለቤተክርስቲያናችን ችግሮች መፍትሔ የሚሆኑ የአመራርና የአስተዳደር አቅም ግንባታ እንቅስቃሴዎቹ ተጨባጭ እስኪሆኑ ድረስ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጎን መቆማችን ተገቢ እርምጃ ነው፡፡ የአመለካከት ልዩነቶች ቢኖሩ እንኳን እነዚህን ሁኔታዎች እንደዕድል ተጠቅመው መለያየትና ማሰናከያን የሚያደርጉ ግለሰቦችና ቡድኖችን ለማስታገስ መረባረብ ይገባናል፡፡
በአጠቃላይ ምእመናን እግዚአብሔር አስቀድሞ የሰበሰባትን፣ ኋላም ከብዙ መከራ ታድጐ እዚህ ያደረሳትን ቤተ ክርስቲያን አሁንም እንዲጠብቅልን በጸሎት መቆም ይገባናል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተክርስቲያኒቱን አመራር ለስብከተ ወንጌልና ለልማታዊ ተግባራት በሚመች መልኩ ለመቃኘት የሚያደርገውንም እንቅሰቃሴ እንድንደግፍ፤ ያንንም ለማኮላሸት የሚደረጉ ስውርና ግልፅ የሆኑ ሕገወጥ አካሔዶችን ሥርዓተ ቤተክርስቲያን በሚፈቅደው አግባብ ለማስቆም አንድንጥር ማኅበራችን ይጠይቃል፡፡
 
                                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር
KidaneMihret.JPG

ኪዳነ ምህረት

KidaneMihret.JPG

የኆኅተ ሰማይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንን ለማጠናከር የልማት ሥራ ጥሪ ቀረበ

በድሬዳዋ ኈኅተ ሰማይ ቅድስት ማርያም ሰበካ ጉባኤ ሥር የተቋቋመው የአካባቢ የልማት ኮሚቴ እያከናወነ ያለውን የልማት ሥራ ለማገዝ ሕብረተሰቡ የድጋፍ እጁን እንዲዘረጋ የደብሩ አሰተዳዳሪ ጥሪ አቀረቡ፡፡ ልማት ኮሜቴው ከሦስት ነጥብ አራት ሚሊዮን ብር በላይ ውጪ የሚጠይቅ ትምህርት ቤት ግንባታ ጀምሯል፡፡  
የደብሩ አሰተዳዳሪ መጋቢ ካህናት አባ ገብረየሱስ አሻግሬ ሰሞኑን እንደገለጹት፤ ቤተክርስቲያኒቱ ለአካባቢው ምእመናን ከምትሰጠው መንፈሳዊ አገልግሉት በተጓዳኝ በዘላቂ ልማት ራሷን እንድትችል ለተጀመረው ጥረት የልማት ኮሚቴው እንቅስቃሴ ሊበረታታ ይገባዋል፡፡

በልማት ኮሚቴው አማካኝነት ቤተክርስቲያኒቱ ባላት ሰፊ ግቢ ውስጥ ከ1999 ዓ.ም አንስቶ አንድ መዋዕለ ሕፃናትና 1ኛ ደረጃ ት/ቤት አገልግሎት እየሰጠበት መሆኑን የገለጹት አስተዳዳሪው፤ ይህንኑ ት/ቤት አስፋፍቶ እስከ 2ኛ ደረጃ ለማሳደግ ባለ 3ፎቅ ህንፃ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ልማት ኮሚቴው ከከተማው አስተዳደር አስፈቅዶ በቤተ ክርስቲያኒቱ አቅራበያ ከሐረር ቢራ አክሲዮን ማኅበር ባገኘው ሙሉ ድጋፍ የሕዝብ መናፈሻ እየሠራ እንደሚገኝ አስተዳዳሪው ገልፀው፤ ልማት ኮሚቴው እያከናወነ ያለው ተግባር ለቤተክርስቲያኒቱም ሆነ ለአካባቢው ማኅበረሰብ ጠቃሚ በመሆኑ ሕብረተሰቡ የድጋፍ እጁን እንዲዘረጋ ጠይቀዋል፡፡

የልማት ኮሚቴውና የትምህርት ቤቱ አመራር ቦርድ ጸሐፊ አቶ አደፍርስ ተሾመ በበኩላቸው የኮሚቴው ዋና አላማ ቤተክርስቲያኒቱ በራሷ ቋሚ ገቢ እየታገዘች መንፈ ሳዊ አገልግሎቷን በተሳካ ሁኔታ እንድታከናውን እንዲሁም የአካባቢው ማኅበረሰብ ልጆች የጥሩ ሥነ ምግባርና እውቀት ባለቤት የሚሆኑበትን ትምህርት ቤት ማስፋፋት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ዐውደ ምህረት ላይ በአካባቢው ማኅበረሰብ የተቋቋመው 18 አባላት ያለው የልማት ኮሚቴ ከቤተክርስቲያኒቱ ሰበካ ጉባኤ፣ ከአካባቢው ማኅበረሰብና ከከተማው የመንግሥት ሥራ ሓላፊዎች ጋር በመቀናጀት እቅዱን በተግባር እያዋለ እንደሚገኝ የገለጹት ጸሐፊው፤ ለጥረቱ መሳካት የሕብረተሰቡ ትብብር እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ኮሚቴው ከኅብረተሰቡ፣ ከባለሀብቶች፣ ከደብሩ ሰበካ ጉባኤ፣ ከልማት ኮሚቴው አባላትና ከመንግሥት ሠራተኞች ባገኘው ድጋፍ ከግማሽ ሚሊዩን ብር በላይ ውጪ አንድ የመዋዕለ ነሕፃናት እና 1ኛ ደረጃ ት/ቤት ሠርቶ በማጠናቀቅ በአሁኑ ወቅት ከ350 በላይ ተማሪዎችን በጥሩ አገልግሎት እያስተማረ እንደሚገኝ ጸሐፊው ገልጸው ከእነዚህ ውስጥ ከአሁን ቀደም በከተማው ተከስቶ በነበረው የጎርፍ አደጋ ወላጆቻቸውን ያጡና የችግረኛ ቤተሰብ የሆኑ ሃያ ልጆች በነፃ እየተማሩ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

የኮሚቴው ራእይ ይህንን ት/ቤት እስከ ኮሌጅ ማድረስ መሆኑን የገለጹት ጸሐፊው በአሁኑ ወቅት እስከ 10ኛ ክፍል ማስተማር የሚያስችል ባለ 3 ፎቅ ሕንፃ ግንባታ ተጀምሮ መሠረት ወጥቶለት የመጀመሪያው ፎቅ እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡

ግንባታውን ለማጠናቀቅ ከሦስት እስከ አራት ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚያስፈልግ ጠቁመው፤ አሁን ባለው ሁኔታ ኮሜቴው ይህንን ሕንፃ ለመቀጠል ከፍተኛ የገንዘብ እጥረት እንዳለበት ጸሐፊው ገልጸዋል፡፡ በመ ሆኑም  የአካባቢው ማኅበረሰብ፤ በሀገር ውሰጥ እና በውጭ ያሉ በጎ አድራጊዎች ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡

የእርዳታ እጃቸውን መዘርጋት ለሚፈልጉ በቅድስት ማርያም መዋዕለ ሕፃናትና የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ስም በተከፈተው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬደዋ ዐቢይ ቅርንጫፍ የባንክ ሒሳብ ቁጥር 4076 ቢልኩ እንደሚደርስም ጠቁመዋል፡፡

 

ጾመ ፍልሰታ ለቤተ ክርስቲያን ሰላም

ኢትዮጵያ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአሥራት አገር ናት፡፡ ሊቃውንትም ነቢያት የተነበዩትን ትንቢት የቆጠሩትን ሱባዔ መሠረት በማድረግ ቅድስት ድንግል ማርያም በኪደተ እግሯ ኢትዮጵያን መባረኳን ያስተምራሉ፡፡ «ነቢዩ ዕንባቆም የኢትዮጵያ ድኳኖች ሲጨነቁ ዐየሁ፤» ዕንባ. 3፡7 ብሎ የተናገረው ቃለ ትንቢት እመቤታችን የኢትዮጵያን አውራጃዎች ለመባረኳ ማስረጃ መሆኑን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይተረጉማሉ፤ ያመሠጥራሉ፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ ኢትዮጵያን ለእናቱ አሥራት አድርጐ በመሥጠቱ በእርሷ በኩል ለሰው ልጆች ሁሉ የሚሆን የነገረ ድኅነት ምሥጢር በመከናወኑ ኢትዮጵያውያን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተለየ ፍቅር አለን፡፡ የአብነት /የቆሎ/ ተማሪዎች በትምህርት ዓለም ከአንዱ ወደሌላው እየተዘዋወሩ /የአብነት/ ትምህርት ሲማሩ በእንተ ስማ ለማርያም፤ ስለማርያም እያሉ፡፡ የእመቤታችን ስም ስንቅ ምግብ ሆኗቸው ይጠቀሙበታል፡፡ ግሼን ደብረ ከርቤ የልጇ ግማደ መስቀል ከከተመበት አምባም የሚጓዙ ምእመናን «አንድ እፍኝ ሽምብራ አልያዝኩም ከቤቴ ስሟ ስንቅ ነው የእመቤቴ» እያሉ በፍቅሯ ተማርከው ግብር ሰፍረው ዕጣን ቋጥረው ሱባዔ እየገቡ ይማፀኗታል፡፡ እርሷም ከልጇ ዘንድ ባገኘችው የመወደድ ሞገስ ምልጃቸውን በመቀበል ጸሎታችውን በማሣረግ የእናትነት ሥራ ሥትሠራላቸው ኖራለች፡፡ ዛሬም እየሠራች ነው፡፡ እመቤታችን ከልጇ ያገኘችውን /የተቀበለችውን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ በዐራቱ ማእዘን «ሰዓሊ ለነ ቅድስት፤ ቅድስት ሆይ ለምኝልን» የማይላት የለም፡፡
በፍቅሯ ተደስተው በአማላጅነቷ ተማምነው «የእመቤቴ ፍቅሯ እንደ ሰማይ ክዋክብት፣ እንደምድር አሸዋ በዝቶልኝ፣ እንደ ልብስ ለብሼው፣ እንደምግብ ተመግቤው» እያሉ ተማጽነው ልመናቸው ሠምሮ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊው፣ ቅዱስ ያሬድ ዘኢትዮጵያና አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ያዘጋጁላትን፣ አባ ጽጌ ድንግል የደረሱላትን የምስጋና መጻሕፍት በመድገም እመቤታችን ዘወትር መማጸን የቀደምት ኢትዮጵያውያንም የዛሬዎች ገዳማውያንና ምእመናን ዕለታዊ ግብር ነው፡፡
ጌታችን ለቀደሙት ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችን አማላጅ እና እናት ሆኗ እንድታገለግል በገቢርም በነቢብም ከአደራ ቃል ጋር አስረክቧል፡፡ በገቢር በቃና ዘገሊላ የሰውን ችግር ፈጥና የምትረዳ ርኅርኅሪት እናት አማላጅ መሆኗን አሳይቷል፡፡ «ለዚሁም የወይን ጠጅ አልቆባቸዋል» ብላ ያቀረበችው ቃለ ምልጃ ምስክር ነው፡፡ እናት ሆኗ እንድታጽናናቸው በቅዱስ ዮሐንስ በኩል ከእግረ መስቀሉ ስር ሰባቱን አጽራሐ መስቀል ሲያስተጋባ ቅዱስ ዮሐንስን ጠርቶ «እኖኋት እናትህ፤ ድንግል ማርያምን ጠርቶ እነሆ ልጅሽ» ዮሐ. 19፡26፡፡ በማለት እመቤታችን የእናት ሥራ ለሁሉም ቅዱሳን ሐዋርያት እንድትሠራላቸው ምእመናንም ልጅ እንዲሆኗት በማያሻማ ቃሉ ተናግሯል፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችንን በእናትነት ከተረከቧት ጊዜ ጀምረው ልጇ በዕርገት በአካለ ሥጋ ሲለይ እንደ ልጅ አገልግለዋታል፡፡ በቤታቸው አኑረዋታል፤ ብትሠወርባቸው ፈልገዋታል፡፡ ብትርቃቸው ናፍቀዋታል፡፡ እርሷም ሲጠሯት ታደምጣቸዋለች፣ ሲፈልጓት ትገኝላቸዋለች፡፡ ይኸውም የሆነው ልጇ በአዳምና በልጆቿ ኃጢአት ምክንያት የፈረደውን ለራሱም ያላስቀረውን ሥጋዊ ሞት እናቱ ብትቀምስ በእናትነት የተረከቧት ቅዱሳን ሐዋርያት መካነ ዕረፍት ለይተው በንጹሕ በፍታ ከፍነው በጌቴ ሰማኒ እንደቀበሯት ስለ እመቤታችን የተጻፉ መጻሕፍት በዝርዝር ያስረዳሉ፡፡
የእመቤታችን ሥጋዊ ዕረፍት «ከመ ትንሣኤ ወልዳ» እንደ ልጇ ትንሣኤ ነውና ሙስና መቃብር ሳያገኛት ከሦስት ቀናት ሥጋዊ ዕረፍት በኋላ ከሞት ተነሥታ ወደ ሰማይ ስታርግ በዕለተ ቀብሯ ያልተገኘው ቅዱስ  ቶማስ ደመና ጠቅሶ በደመና ሰረገላ ሲመጣ ዕርገቷን ይረዳል፡፡ እማኝ ደግሞ የተከፈነችበትን በፍታ /ጨርቅ/ ይቀበላታል፡፡ ለቅዱስ ቶማስ የተገለጠው የዕረፍቷ ምሥጢር ሌሎች ቅዱሳን ሐዋርያት እንዲገለጥላቸው ቢማጸኑ እመቤታችን ዳግም ተገልጻላቸው፡፡ ትንሣኤዋን ለማየት በቅተዋል፡፡
እነዚህ በቅድስናቸው የተመሠከረላቸው ቅዱሳን እመቤታችንን በሁለት ሱባዔ ማግኘታቸውን መሠረት በማድረግ በቤተ ክርስቲያናችን ከነሐሴ 1-16 በየዓመቱ አንደሚጾም ይታወቃል፡፡ ይህ እመቤታችንን የምንማጸንበት ጾመ ፍልሰታ ቤተ ክርስቲያናችን መፍትሄ የምትፈልግባቸውን ጉዳዮች ለእመቤታችን የምታቀርብበት ሰዓት ነው ብለን እናምናለን፡፡
ኢትዮጵያ የእመቤታችን አሥራት አገር ስትሆን እመቤታችን ለኢትዮጵያውያን እናት መሆኗ እየተነገረ ለምን በፈተና ውስጥ አለፍን? ልጇ በአሥራት ኢትዮጵያን የሰጠባት ሀገር አባቶች ማስፈራሪያ ሲደርስባቸው መንፈሳዊነት /ኀይለ መንሳዊ/ ተዘንግቶ ሥጋዊ ጥበብ በቤተ ክርስቲያን መድረክ ሲታይ ምን ይባላል? «እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የጥፋት ርኩሰት በተቀደሰችው ሥፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል በዚያን ጊዜ በይሁዳ ያሉት ወደ ተራራዎች ይሽሹ» ማቴ. 24፡15፡፡ የተባለው ቀን ደርሶ ይሆንን?
ቤተ ክርስቲያን ለረጅም ዓመታት ለገጠማት ችግር መፍትሔ እመቤታችን እጅ ላይ አለ ብለን እናምናለን፡፡ እመቤታችን ብትሠወርባቸው አባቶች ሱባዔ ገብተው እንዳገኟት የፍቅር እናት ናትና ፍቅር አንድነት እንድትሰጠን እርሷን መማጸን፤ የዶኪማስን ጓዳ እንደሞላች የጐደለውን እንድትሞላ ውዳሴዋን እየደገሙ ድንግልን መማጸን ያስፈልጋል፡፡
በውዳሴ ማርያም፣ በጸሎተ ማርያም የሚመካ በጉልበቱ አይመካም፡፡ ጊዜ ረዳኝ ብሎ በወገኖቹ ላይ ግፍ አይፈጽምም፡፡ ስለዚህ በዚህ በወርኀ ጾም እመቤታችን ምልጃዋ ከአገራችን፣ ከቤተ ክርስቲያናችን ጋር እንዲሆን በሱባዔ እንማጸናት፡፡
በጾመ ፍልሰታ ከሊሂቅ እስከ ደቂቅ በማስቀደስ፣ በጾምና በጸሎት ሁለቱን ሳምንታት እንደሚያሳልፉት ይታወቃል፡፡ በሱባዔው የቤተ ክርስቲያናችን ችግሮች የሚወገድበት ምእመናን በበረከት የሚጐበኙበት ቅድስና የሚሰፍንበት መንፈሳዊነት ትልቅ ከበሬታ የሚገኝበት ጾም እንዲሆን ሁሉም ምእመን መትጋት አለበት፡፡
ሁለቱ ሳምንታት በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ዘወትር እየተገኘን ምሕላ የምናደርስበት፣ የተጣላነውን ይቅር ለእግዚአብሔር፣ የበደልነውን የምንክስበት ጾም መሆን አለበት፡፡
ቀናቱን እየቆጠርን እስከተወሰነው ሰዓት ብቻ መጾም ብቻ በሕይወታችን መሠረታዊ ለውጥ አያመጣም፡፡ እመቤታችን የአገራችን አሥራት የሁላችን እናት በመሆኗ የእናትነት ሥራ እንድትሠራልን በሚገባ ልንማጸናት ይገባል እንጂ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ሱባዔ ብለን ውዳሴ ማርያም በደገመ አፋችን ሰው የምናማ በሰው ሕይወት ገብተን የምንፈተፍት ከሆነ እመቤታችንን አናውቃትም፡ እመቤታችንም አታውቀንም፡፡ ስለዚህ ጾመ ፍልሰታን እስኪ ሁላችን ኢትዮጵያውያን የተዋሕዶ ልጆች ድንግልን በአንድ ድምፅ እንጥራት፡፡
የእመቤታችንን ጾመ ፍልሰታ፤ እንደ ብርሃን ተስፋ በማድረግ በተለይም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚተጉ አባቶች እና ምእመናን ለተሰደዱ፣ ለተራቡ፣ በፈተና ውስጥ ለሚገኙ ይማጸኑ እንላለን፡፡ ውዳሴ ማርያሙ፤ ሰዓታቱ ጨለማን ተገን አድርጐ ከሚቃጣ ማስፈራሪያ እና ዛቻ ድርብ ኀይል አለው፤ እስኪ ለቅድስና፣ ለንጽሕና ለመንፈሳዊነት ቅድሚያ እንስጥና የእግዚአብሔርን ብድራት እንጠብቅ፡፡ ጾመ ፍልሰታ መንፈሳዊነት፣ እውነት፣ ቅድስና የጠራ አሠራር፣ በቤተ ክርስቲያን የሚሰፍንበት እንዲሆን እንመኛለን፡፡
 
                                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዘጠነኛው የአውሮ­ ማዕከል ጉባኤ ተጠናቀቀ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአውሮ­ ማዕከል ዘጠነኛ ጠቅላላ ጉባኤ ከሐምሌ 3 ቀን እስከ 5 ቀን 2001 ዓ.ም በኦስትሪያ ሽቬካት ከተማ ተካሔደ፡፡ በጉባኤው ላይ ከተለያዩ ቀጠና ማዕከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች የተውጣጡ ከ45 በላይ አባላት የተሳተፉ ሲሆን የማዕከሉ የ2001 ዓ.ም የአገልግሎት እንቅስቃሴና የኦዲት ሪፖርት ቀርቦ ውይይት በማድረግ ማጽደቁን የአውሮ­ ማዕከል የላከልን መረጃ ያመለክታል፡፡

በተለይ የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማዕከል ጽ/ቤት ግንባታና የማዕከሉ ድርሻ፣ የአውሮ­ አኅጉረ ስብከት አጠቃላይ እንቅስቃሴና የማዕከሉ ድርሻ፣ ወቅታዊ የቤተክርስቲያን ሁኔ ታና በሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሰፊና ጥልቅ ውይይቶችን አድርጎ ውሳኔዎችን እንዳሳለፈ ከዘገባው ለመረዳት ተችሏል፡፡

እንደዚሁም የማኅበሩን የአራት ዓመት ዕቅድ መሠረት በማድረግ ዕቅዱ ለማዕከሉ ቀርቦ ከገመገመ በኋላ ያጸደቀ ሲሆን በተመሳሳይ መልኩ የሚቀጥለውን ዓመት ዕቅድ ዐይቶ ማሻሻያ በማድረግ እንዳጸደቀም ይኸው መረጃ ጠቁማል፡፡

ዘጠነኛው የአውሮፖ ማዕከል ጉባኤ ሲካሔድ ለተሳታፊዎቹና ጥሪ ለተደረገላቸው ምእመናን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መሰጠቱንም ተወስቷል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ጉባኤው የተካሔደበት ከተማ ከንቲባው ለጉባኤው ለተሳታፊዎች ደማቅ አቀባበል እንዳደረጉ ዘገባው አመልክቶ ስለ ኦስትሪያ አጠቃላይ ኢኮኖማያዊ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳይ በሚመ ለከትገለጻ አድርገዋል ተብሏል፡፡

ከተማቸው የጥንታዊ ቤተክርስቲያን ወጣቶችን ዓመታዊ የአውሮፓ­ ማዕከል ጉባኤ በማዘጋጀቷ ታላቅ ደስታ እንደተሰማቸው ከንቲባው ገልጸዋል ሲል የማዕከሉ መረጃ ያመለክታል፡፡

እንደዚሁም የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን በማኅበረ ቅዱሳን አማካኝነት ስለምትሠራቸው መጠነ ሰፊ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ከጉባኤው ተሳታፊዎች ለከንቲባው ገለጻ መደረጉን ተወስቷል፡፡

በጉባኤው ማጠቃለያ ላይ ለዝግጅቱ መሰካት አስተወጽኦ ላደረጉት የቪየና ኪዳነ ምሕረት ካህናትና የሰበካ ጉባኤ ከፍ ያለ ምስጋና መቅረቡም ተገልጿል፡፡

በተለይ ለጉባኤው መሰብሰቢያ አዳራሽ በመፍቀድና ለተሳታፊዎችም ማረፊያ በመስጠት ለተባበሩት የሽ ቬካት ቅዱስ ያዕቆብ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ሓላፊ ለቄስ ጌራልድ ጉም ፕና ለሥራ ባልደረቦቻቸው ከምስጋና ጋር የመታሰቢያ ስጦታ ተበርክቶላ ቸዋል፡፡

በመጨረሻም ቀጣዩ የማዕከሉ 10ኛ ዓመት ጠቅላላ ጉባኤ በጀርመን ሀገር እንዲዘጋጅ ተወስኖ በዚህም ከወትሮው በተለየ መልኩ የማዕከሉን የ10 ዓመት የአገልግሎት እንቅስቃሴ የሚያመለክት ዝግጅት እንዲዘጋጅ ከስምምነት ላይ ተደርሶ ጉባኤው መጠናቀቁን ከዘገባው ለማወቅ ተችሏል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ለቅኔ ትምህርት ትኩረት መስጠት እንደሚገባ ተገለጸ

ዓውደ ርእዩ ኅብረተሰቡ ስለአብነት ትምህርት ቤቶች ግንዛቤ እንዲኖረው ረድቷል

 «ቅኔ የአብነት ትምህርቱ ፍልስፍና መሠርተ» በሚል ርዕስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በማኅበራዊ አገልገሎት ልማት ዋና ክፍል የተዘጋጀው የግማሸ ቀን ዐውደ ጥናት በስ ድስት ኪሎ ስብሰባ አዳራሽ ተካሄደ፡፡  ዐውደ ጥናቱን በመክፈቻ ንግግር የከፈቱት የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም እንደገለጹት፤ ዐውደ ጥናቱ በቅኔ ትምህርት አገልግሎቱና ፍልስፍናው ላይ የሚያተኩር ነው፡፡
የቅኔ ትምህርት የቤተክርስቲያን ትምህርተ ሃይማኖት፣ የሀገራችን ታሪክ እና የቀደምት አባቶችና የዛሬዎች ሊቃውንት ፍልስፍና ጥበብ እንዲሁም ማኅበራዊ ሒስ የተላለፈበት የዕውቀት ዘርፍ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ቅኔ በሀገሪቱ ሕዝቦች የአኗኗር ሥርዓትና ባሕል ውስጥ የራሱ አሻራ ያስቀመጠ ትምህርት ነው ያሉት ሰብሳቢው፤ በአሁኑ ወቅት በርካታ የውጭ ሙሁራን በትምህርቱ ላይ ምርምር እያደረጉ እንደሚገኙ ጠቁመው፤ በአንጻሩ በሀገሪቱ የተሰጠው ትኩረት አናሳ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡
ትምህርቱን ለማሳደግ የሁሉም ርብርብ የሚያስፈልገው እንደሆነና ዐውደ ጥናቱም የጠለቀ ጥናትና ምርምር ማድረግ ለሚፈልጉ ምሁራንን መነሻ የሚያመላክትና የሚያነሳሳ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

«ቅኔ የግእዝ ቋንቋ ሥነ ጽሑፍ» በሚል ርእስ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከል መምህር እና ተመራማሪ ዶ/ር ሥርግው ገላው በበኩላቸው፤ የቤተ ክርስቲያንና የሀገሪቱ ሊቃውንት የአብነት ትምህርት ቤቶች በመሆናቸው የአብነት ትምህርት ቤቶችን በመጠበቅና በመንከባከብ የቅኔን ትምህርት ማሳደግ እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡
የቅኔን ትምህርት በማሳደግ የነገይቱን ቤተክርስቲያንና ሀገርን ወደተፈለገው እድገትና ለውጥ ለማድረስ የሚችሉትን የአብነት ትምህርት ቤት ሊቃውንት በተገቢው መንገድ ማዘጋጀት እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡

የቅኔ ትምህርት እንዲስፋፋ ለማድረግ የቅኔ ትምህርት ቤቶችን ወደ ኮሌጅና ዩኒቨርስቲ ደረጃ በማሳደግና ሥርዓተ ትምህርት ሊቀረጽላቸው እንደሚገባም ዶ/ር ሥርግው አስተያየ ታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በዐውደ ጥናት ላይ «ቅኔ በቤተክርስቲያን አገልግሎት» ና «ቅኔ ለመጽሐፍት ትርጓሜ» በሚል ርዕስ ሌሎች ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች የማኅበረ ቅዱሳን ጥናት እና ምርምር ማዕከል ከፍተኛ ተመራማሪ በመምህር ደሴ ቀለብና በስዋሰው ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ የሐዲስ ኪዳን መምህር በመጋቤ ሐዲስ እሸቱ ዓለማየሁ የቀረበ ሲሆን፤ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ ከተሳታፊዎች ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡

የቅኔን ትምህርት ለማሳደግና ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ ቤተክርስቲያን ሰፊ ድርሻ እንዳላትና ትኩረት ልትሰጠው እንደሚገባ የዐውደ ጥናቱ ተሳታፊዎች አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡
የዕለቱ የክብር እንግዳ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ክቡር አምባሳደር ሙሀሙድ ድሪር እንደገለፁት፡፡ በዘርፉ የተሰማሩ ወገኖች ለአብነት ትምህርት ቤቶች የሰጡት ትኩረት እጅጉን እንደሚደነቅ ጠቁመው፡፡

ያብነት ትምህርት ቤቶችን በመደገፍ የቅኔን ትምህርት ለማሳደግ የሚመለከታቸው አካላት ጥረታቸው ከዳር ይደርስ ዘንድ የባህልና የቱሪዝም ሚኒስቴር ያላሰለሰ ድጋፍ እንደሚያደርግም ቃል ገብተዋል፡፡
በሲምፖዝየሙ በተለያዩ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ቅኔ የተዘረፈ ሲሆን «ቅኔ ያብነቱ ፍልስፍና» የተሰኘ ዶክመንተሪ ፊልም ተመርቆ ለእይታ በቅቷል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ዋና ክፍል «በጌጠኛ ቤትህ ልማት ይሁን» በሚል መሪ ቃል ለ10 ቀናት የተዘጋጀው ዐውደ ርእይ ተጠናቀቀ፡፡
ከሐምሌ 18 እስከ 26 ቀን 2001 ዓ.ም ድረስ የተዘጋጀው ዐውደ ርእይ በዓይነቱም በይዘቱም የተለየ እንደነበረ የገለጹት የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ዋና ክፍል የቅስቀሳና ገቢ አሰባሳቢ ክፍል ሓላፊ ወ/ሮ ዓለምፀሐይ መሠረት፤ ዐውደ ርእይው በፎቶ ግራፍና በተለያዩ ገላጭ መረጃዎች የተደራጀ በመሆኑ ለመእመኑ ስለ አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅታዊ ሁኔታ ግንዛቤን እነደፈጠረ ተናግረዋል፡፡
በዐውደ ርእዩ ላይ ዋና ክፍሉ በ2002 እና 2003 ዓ.ም ገዳማትና አድባራት ላይ የሚያከናውናቸው 12 ፕሮጀክቶች ለዐውደ ርእዩ ተመልካቾች ማስተዋወቁንም ጠቁመዋል፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
 

Kalitie.GIF

ለጥምቀት ወጥታ የቆየችው ታቦት ወደ አዲሱ ሕንጻ ቤተክርስቲያን ገባች

የቃሊቲ ቁስቋም ማርያም ታቦተ ሕግ ባለፈው ጥምቀት ወጥታ ተመልሳ መግባት ፈቃዷ ባለመሆኑ የተፈጠረውን የምእመ ናንና የካህናት ጭንቅ፣ ሐዘን፣ ድንጋጤ በብዙ የሚክስ የደስታ ዕለት፡፡ ሐምሌ 25 ቀን 2001 ዓ.ም፡፡

Kalitie.GIF

 
በዚህ ዕለት ማለዳ ጀምሮ ወደ ደጇ ይጎርፍ የነበረው ምእመን አካባቢውን ጠጠር መጣያ አሳጥቶታል ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ ጸሎት፣ ምሕላ. . . ሲደረግ ተውሎ ከቀኑ 9፡30 ለሰባት ወራት ከርማ ከነበረችበት ድንኳን በብፁዓን አባቶች፣ በካህናትና በበርካታ ምእመናን ታጅባ የወጣችው ታቦተ ሕግ የምእመናኑን የደስታ ስሜት እጥፍ ድርብ አድርጋው ነበር፡፡

በእልልታው በዝማሬውና በምስጋና ታጅባ ከድንኳኑ አቅራቢያ ወደ ተሠራላት አዲስ ሕንፃ ቤተክርስቲያን ስታመራ እርኩስ መንፈስ ያደረባቸው ብዙዎች ከተለያየ አቅጣጫ ሲጮሁ፣ ሲንፈራገጡ፣ ሰውነታቸውን ሲንጡ እና እልልታውን ለማወክ ሲጥሩ የተስተዋለበት ይህ አጋጣሚ በእርግጥም የእመቤታችን ክብር ምን ያህል እንደሆነ ለመገንዘብ የሚያስችልም ነበር፡፡
በእመቤታችን ትእዛዝ አቶ ክንፈ ሚካኤል ረታ በተባሉ ምዕመን በተሠራው አዲሱ ሕንፃ ቤተክርስቲያን ዑደት አድርጋ ወደ መንበረ ክብሯ የገባችው ታቦተ ቁስቋም ማርያም ታቦተ መድኃኔዓለም እና ታቦተ ጊዮርጊስንም አስከትላ ነበር፡፡

በከፍተኛ ጉጉት ሲጠበቅ የነበረው ይህ ዕለት ልዩ ያደረገው ብራ መሆኑ ብቻ ሳይሆን በዋዜማው ዓርብ ምሽት ሦስት ነጫጭ ርግቦች የእመቤታችን ታቦት በከረመበት ድንኳን ላይ ማረፋቸው እና ከዚያ ቀደም ብሎ የንብ መንጋ ድንኳን ውስጥ መክተማቸው ነው፡፡
ዕለት ተዕለት የሕንፃ ቤተክርስቲያኑን ሥራ በመከታተል እመቤታችን ያዘዘቻቸውን የፈጸሙት አቶ ክንፈ ሚካኤል ረታ በዓውደ ምሕረቱ ላይ ባስተላለፉት መልእክት፤ «ታቦተ ቁስቋም ማርያም በድንኳን እያለች እኛ ቤታችን አንገባም ብላችሁ ከእርሷ ጋር የቆያችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች፣ ካህናት፣ የሰበካ ጉባኤ አባላትና ምእመናን እንኳን ደስ አላችሁ!» ብለዋል፡፡

መጋቢት 29 ቀን 2001 ዓ.ም ለዮሐንስ አጥቢያ እመቤታችን ተገልጣላቸው ከዚህ ቀደም አስተውለውት ከማያውቁት ቦታ ሕንፃ ቤተክርስቲያኑን እንዲያንጹ ባዘዘቻቸው መሠረት በሁለት ወር ከ 10 ቀናት ውስጥ ሠርተው ያጠናቀቁት እርሳቸው የማያውቋቸው እግዚአብሔር የሚያውቃቸው እየተራዷቸው መሆኑንም አቶ ክንፈ ሚካኤል ተናግረዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳዉሎስ ¬ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዘዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት በክብረ በዓሉ ላይ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ከሰጡ በኋላ ባስተላለፉት መልእክት «እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልጆቼ ሳይሰባሰቡ፣ እኔ እዚህ መሆኔን ሳያውቁ ሕሊናቸውና መንፈሳቸው ሳይደሰት አልነሳም የማለት ምልክት መስጠቷ እንጂ ድንኳን መክረም እምቢተኝነት አይደለም» ብለዋል፡፡  
«ታቦተ ቁስቋም ማርያም አልነሣም ማለቷ የተቸገሩትን ለማማለድ፣ የታመሙትን ለመፈወስና በአካባቢው የምትሠራው ብዙ ተዓምራት እንዳለ ለማሳየት ድንኳን ከርማለች፤ ዛሬ ግን ወጥታ ልጆቿን ባርካለች፤ እንኳን ደስ ያላችሁ!» ያሉት ቅዱስነታቸው፤ ዕለቱ እናታችን ቅድስት ማርያም በየጊዜው እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እየተገለጸች ከልጆቿ የምትነጋገርበት ሀገራችን ሀገረ እግዚአብሔር መሆኗን የምንገነዘብበት ዕለት መሆኑን ተና ግረዋል፡፡ ይህ ሥፍራ የቃሊቲ ደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም መሆኑንም አብስረዋል፡፡
በዚህ ታሪካዊ ዕለት ከተገኙት ሊቃነ ጳጳሳት ውስጥ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ እና ብፁዕ አቡነ ገብርኤል በሰጡት ትምህርት የቅድስት ድንግል ማርያም ድንቅ ሥራ ተነግሮ የማያልቅ ነው፡፡

«እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሀገራችንና ከሕዝባችን በተአምሯ፣ በበረከቷ ያልተለየችን የአፍ መፍቻ ቋንቋችን ናት» ያሉት ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ሕዝባችን «ሰአሊ ለነ ቅድስት» የሚለው አጠራሩ አማላጅነቷን የቱን ያህል እንደሚያምንበት ያሳያል ብለዋል፡፡
ታቦተ ቁስቋም በቦታው ድንቅ ተአምር እንዲሠራበት ስለመረጠች ድንኳን መቆየቷን፣ በሰው እጅ ተሠራ ለማለት የሚያዳግት ሕንፃ ቤተክርቲያን በአጭር ጊዜ ተሠርቶ መጠናቀቁ፣ እመቤታችን በተአምሯ የሠራችው መሆኑን እንደሚያሳይ የገለጹት ብፁዕ ነታቸው፤ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑን ያሠሩት ምእመን ዕድለኛ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡

የእመቤታችንን ተአምር በመንገር ከደጇ ጠፍተው የማያውቁት አገልጋይ አባ ገብረሥላሴ መለሰ በሰጡት አስተያየት «ጸሎተ ምህላችንን ተቀብላ እመቤታችን ፈቃዷን ስለገለጸችልን ደስታችን ወሰን የለውም. . .» ነው ያሉት፡፡
«ሰኔ 25 ቀን 2001 ዓ.ም ታቦተ ቁስቋም ባረፈችበት ድንኳን ውስጥ አንዱን ንብ ተከትለው ጥቂት ንቦች ገቡ፤ ሐምሌ 16 ቀን ጀምሮ ግን ሦስት ቀፎ የሚገመት የንብ መንጋ ወንበሯን ተረክቦ ዛሬ ድረስ ይገኛል፡፡ ይህን ስናይ እመቤታችን ልጆቿን ልትጠራ፣ በረከቷን ልታወርድ መሆኑን ተረዳን፡፡ አዲሱ ሕንፃ ቤተክርስቲያን እንደ ምትገባልንም እምነታችን ሆነ፡፡ እንዳሰብነውም ተሳካ. . .» ያሉት አባ ገብረሥላሴ «ሐምሌ 24 ምሽት ድንኳን ላይ ያረፉት ሦስት እርግቦችም ሌላው ምልክታችን ነበር» ይላሉ፡፡

ጥር 16 ቀን 2001 ዓ.ም ታቦቷን አንግሠው ዳግም ወደ ቤተመቅደስ እንድትገባ ጥረት ቢያደርጉም ሳይሳካላቸው የቀረው ዛሬ ግን የእመቤታችን ፈቃድ እጅግ ያስደሰታቸው መሪጌታ ቤዛ የሻው «ሐዘናችን በደስታ ተለውጧል፡፡ ይህን ተዓምር ማየቴ ዕድለኛ ነኝ፡፡ ለእመቤታችን ክብር ምስጋና ይግባት» ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ይህ ዕለት በእርግጥም የደስታ ዕለት ነው፡፡ ብዙዎች የሚሰጡት አስተያየት ከደስታ እንባ ጋር ነው፡፡ በዕለቱ እየተጨባበጡ፣ እየተቃቀፉ ደስታቸውን የሚገልጹ በዓውደ ምሕረቱ በእመቤታችን የተደረገላቸውን ተአምር የሚመሰክሩ ብዙዎች ነበሩ፡፡

እሑድ ሐምሌ 26 ቀን 2001 ዓ.ም የቃሊቲ ደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም ሕንፃ ቤተክርስቲያን ቅዳሴ ቤት ሲከበር እጅግ ከፍተኛ ሕዝብ እንደተገኘም ታውቋል፡፡

ከአዘጋጁ- ባለፈው የጥምቀት በዓል ከቅዱስ ሚካኤል ታቦት ጋር ወደ ጥምቀተ ባሕር ሥፍራ ወጥታ ተመልሳ ወደ ቤተመቅደሷ ሳትገባ በራሷ ፈቃድ ድንኳን ስለከረመችው የቁስቋም ማርያም ታቦት ታሪክ በተከታታይ ስንዘግብ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ወደፊትም በዚሁ ሥፍራ ስለተከናወኑ ገቢረ ተዓምራት የምንገልጽ መሆኑን ከወዲሁ እንጠቁማለን፡፡
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
 
 

ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለወደዱ …/ዮሐ.3-19/

ብርሃን ወደ ዓለም ስለመጣ፣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለወደዱ ፍርዱ ይህ ነው፡፡ ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፡፡ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤ እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጐ እንደሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል፡፡ /ዮሐ.3-19/

ለዚህ እትም መልእክታችን መግቢያ ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ከእውነት ይልቅ ሐሰትን የመረጡ ሰዎችን ማንነት ለመግለጥ የተናገረውን አምላካዊ ቃል መርጠናል፡፡ ብርሃን እውነት፤ ብርሃን የጠራ አሠራር፤ ብርሃን የዘመድ አሠራር ባላንጣ፤ ብርሃን የሕገ ሲኖዶስ መከበር፤ ብርሃን የቤተ ክርስቲያን ልዕልና መገለጫ ነው፡፡ ጨለማ ግን የብርሃን ተቃራኒ ነው፡፡

ካሳለፍነው ወርኃ ግንቦት መጋመሻ ጀምሮ በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ለዘመናት ሰፍኖ የቆየውን የአስተዳደር ችግር በሠለጠነ መንገድ፣ በመወያየት፣ በመተማመን ለመፍታት ሁሉም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ከስምምነት ላይ መድረሳቸውን ባለፈው እትም ከመንበረ ፓትርያርክ ጽሕፈት ቤት የወጣውን መረጃ መሠረት በማድረግ አሰንብበናል፡፡

በቤተ ክርስቲያን አባቶች ዘንድ ተፈርቶ ይፋ ሳይወጣ ለዘመናት ሲጉላላ የቆየው የአስተዳደር ችግር፣ የቤተ ዘመድ አሠራር፣ ሙስና፣ ተገቢውን ሰው በተገቢ ቦታ አለመመደብ፣ የተዝረከረከ የሒሳብ አሠራር እና ተገቢ ያልሆነ የሀብት አጠቃቀም ችግር ይፋ ወጥቶ የመወያያ አጀንዳ ሆኖ በቃለ ጉባዔ ሰፍሮ መቀመጡ ለነገዋ ቤተ ክርስቲያን ዕድገት አንድ እርምጃ ነው፡፡

«አትስረቅ፣ መመለጃ አትቀበል፣ እውነቱን እውነት በሉ» የተባሉት አምላካውያት ቃላት መመሪያዋ በሆነ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከሠናይ ይልቅ እኩይ ሥነ ምግባሮች በቅለው ሐዋርያዊ ጉዞዋን በፍጥነት እንዳይካሔድ የኋሊት ሲጓተት እያዩ «ሆድ ይፍጀው» ብለው ማለፍ ቀርቶ ብፁዓን አባቶች ችግሮችን አፍረጥርጠው መነጋገራቸው ያስደስታል፡፡

በቤተ ክርስቲያን አባቶች መኖራቸው የታመነባቸው ችግሮች እንዲፈቱ በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሥራ አስፈጻሚ አባላት መመረጣቸውም ይታወሳል፡፡ ለሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላቱ ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጣቸው ሓላፊነት መሠረት የቤተ ክርስቲያን ችግር ለመፍታት ሲንቀሳቀሱ በተፈጠረው አለመግባባት ችግሩ ወርኃ ሐምሌ ላይ ደርሷል፡፡ እኛም የተፈጠረው ችግር ከምንም በላይ የቤተ ክርስቲያን ክብር ባስቀደመ መልኩ እንዲፈታ ሐሳባችን ሰንዝረናል፡፡ በመግቢያችን እንደጠቀስነው «ብርሃን ወደ ዓለም ስለመጣ» የቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ችግር ይፈታ ስለተባለ፤ ሥራቸው ክፉ የነበረው «የዘመድና የብልሹ አሠራር ተጠቃሚ የሆኑ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ችግር መፍታት ይልቅ ጨለማን ስለወደዱ ወደ ብርሃን አንመጣም አሉ፡፡ ጨለማን ተገን አድርገው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ቤት መዝጊያ ሰበሩ፣ ፎከሩ፣ አስፈራሩ፣ ዛቱ፣ ቆይ ትኖራላችሁ አሉ፡፡ ዛቻና የድብደባ ሙከራ የተፈጸመባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እንደገለጹት ድርጊቱ የቤተ ክርስቲያንን ክብር ዝቅ ያደረገና አሳፋሪ ተግባር ነው፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው «ክፉን የሚያደርግ ብርሃንን ይጠላልና ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም» እንደተባለው  ክፉ የሚያደርጉ ቤተ ክርስቲያንን የሚመዘብሩ ሰዎች ብርሃንን ስለሚፈሩ ነው፡፡

ብርሃን እውነትን የሚፈሩ የጨለማው ቡድን አካላት፤ «በሊህ እገሪሆሙ ለኪኢወ ደም፤ ደም ለማፍሰስ እግራቸው ፈጣን ነው» «ሐሳር ወቅጥቃጤ ውስተ ፍኖቶሙ፤ ጥፋት ጉስቁልና በመንገዳቸው አለ፤ የሰላም መንገድ አያውቋትምና እግዚአብሔርን መፍራት በዓይናቸው ፊት የለም» ሲል ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት የገለጣቸው ዓይነት ናቸው፡፡ መዝ. 13-6፡፡ በኃይል፣ በዛቻና በማስፈራሪያ የቤተ ክርስቲያን ችግር ስለማይፈታ የእነዚህ ቡድኖች ዓላማ ቤተ ክርስቲያን ወደተሳ ሳተ ጐዳና የሚመራ ነው፡፡ የጨለማ ቡድን ዘመቻ ከቤተ ክርስቲያን ልጆች አልፎ ወደ ብፁዓን አባቶች አምባ መደረሱ እጅግ ያሳዝናል፡፡

ሕገ ሲኖዶስ እንዳይከበር እንቅስቃሴ የሚያደርጉ የጨለማው ቡድን አባላት» እውነት ተድበስብሶ እንዳይወጣ የሚያደርጉት እኩይ ጥረት ከሠመረ ቤተ ክርስቲያን «ቤትየሰ ትሰመይ ቤተ ጸሎት አንትሙሰ ረሰይክምዋ በአተ ፈያት ወሠረቅት፤ ቤቴስ የጸሎት ቤት ትባላላች እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ» አደረጋችኋት፡፡ የሚለው ዕጣ ይገጥማታል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ከጨለማ አስተዳደር ወደ ብርሃን እንድትወጣ «እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጐ እንደሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል» እንደተባለ የቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ችግር እንዲፈታ ጨለማ የሆኑ ወደ እውነት እና ወደ ብርሃን መምጣት አለባቸው፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተመረጠው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ሥራውን እንዲቀጥል እገዳ እንደተነሳለት ከመንበረ ፓትርያርክ የተሰጠው መግለጫ ያመለክታል፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ የመረጣቸውና ሓላፊነት የተሰጣቸው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በጠቅላይ ቤተ ክህነት አሉ የተባሉ ችግሮች እንዲፈቱ ቤተ ክርስቲያን የጣለችባቸውን ሓላፊነት መወጣት አለባቸው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ያለው ብልሹ አሠራር መፈታት ከምእመናን ጀምሮ እስከ መንግሥት አካላት እንደ ሚደግፉት እናምናለን፡፡

ችግሩን ለመፍታት ሐሳብ የሰጡ ብፁዓን አባቶችን የማሸማቀቅ አሳፋሪ ተግባር ማንነታቸው ባልታወቁ ግለሰቦች ስለተፈጸመባቸው መንግሥት አስፈላጊውን ጥበቃ ሊያደርግላቸው ይገባል፡፡ የብፁዓን አባቶች ዓላማ መንፈሳዊ ዓላማ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ከመፍታት ውጪ የተለየ አንዳች ዓላማ እንደሌላቸው ከሰጡት ሐሳብ መረዳት ይቻላል፡፡

በመሆኑም ምንጊዜም የሕዝብን በሕይወት የመኖር መብት የሚያስከብረው መንግሥት ጨለማን ተገን አድርገው የቤተ ክርስቲያንን ሕልውና ነፃነት ደፍረው በብፁዓን አባቶቻችን ላይ የመዝጊያ ሰበራ፣ የድብደባ ሙከራ የፈጸሙ አካላትን በቁጥጥር ስር አውሎ የእርምት ርምጃ መወሰድ አለበት፡፡

ከሀገር ሀገር ዞረው «በእንተ ስማ ለማርያም» ብለው የተማሩ አባቶች ዕድሜ ዘመናቸውን ሁሉ በእግርና በፈረስ ተዘዋውሮ ቤተ ክርስቲያን ያገለገሉ «ሕገ ቤተ ክርስቲያን ሕገ ሲኖዶስ ይክበር» በማለታቸው ዛቻ፣ ማስፈራሪያ፣ የመዝጊያ ሰበራ ሲፈጸምባቸው መሰማት ቤተ ክርስቲያን ወደየት እየተጓዘች ነው ያሰኛል፡፡

በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን የውስጥ ጠላቶች መከራ መቀበል የአባቶች ሕይወት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለማገልገል በቅዱስ መሰዊያው ፊት ቃል ኪዳን የገቡት አባቶቻችን ስለቤተክርስቲያን ክብር ዛቻና እንግልት ቢፈጸምባቸው እንኳ መከራውን በአኮቴት ተቀብለው ሓላፊነታቸውን መወጣት ይኖርባቸዋል፡፡ በሰላማዊ መንገድ በሠለጠነ መንገድ ችግሮች እንዲፈቱ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ መወያየት የጀመሩትን ከፍጻሜ ማድረስ አለባቸው፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ካህናት፣ የሰንበት ት/ቤት አባላት፣ የሰበካ ጉባኤ አካላት፣ በአጠቃላይ ምእመናን ምን ጊዜም እውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን በማዕበል የምትገፋ መሆኗን ተረድተው በተፈጠረው ችግር መረበሽ የለባቸውም፡፡ የተፈጠረው የአስተዳደር ችግር በጠራና አስተማማኝ በሆነ መንገድ እስከሚፈታ ድረስ በመረጋጋት፣ በጾም፣ በጸሎት መትጋት ይኖርባቸዋል፡፡

«የገበያ ግርግር ለቀጣፊ ያመቻል» እንዲሉ የተፈጠረውን ችግር መነሻ በማድረግ በቤተ ክርስቲያን አካባቢ ምዝበራ፣ ዘረፋ፣ ሕገ ወጥ ድርጊት እንዳይስፋፋ ምእመናን የቤተ ክርስቲያን ንብረት ንብረታቸው፤ ሕልውናዋ ሕልውናቸው ስለሆነ ቤተ ክርስቲያናቸውን መጠበቅ አለባቸው፡፡

 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቅዱስ ሲኖዶስ ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣን ይከበር!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም የሐዋርያትን ሥልጣን የያዘ የራሷ ቅዱስ ሲኖዶስ ባለቤት ከሆነች እነሆ ሃምሳ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱም በሐዋርያት መንገድ አካሔዱን አጽንቶ ለመገኘት የራሱን ሕገ ቤተ ክርስቲያን አዘጋጅቶ ተቋማዊ አመራሩን ለማጠንከር ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በዚህም ሕገ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶሱ፣ የቅዱስ ¬ትርያርኩ፣ የቋሚ ሲኖዶስ፣ የመንበረ ¬ትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣ የሊቃነ ጳጳሳትና የአስተዳደር ጉባኤው … ሥልጣንና ተግባር በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በግልጽ ተቀምጧል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም የሕግ አውጪው አካል እርሱ በመሆኑ ለጊዜው በሚያስፈልጉና ወቅቱ በሚጠይቃቸው አግባቦች የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ጥንካሬ ለማስጠበቅና ከቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ጠብቆ፤ ለቀጣይ ትውልድ ከመንፈስ ቅዱስ የተቀበለውን አደራ ለማስረከብ ያወጣቸውን ሕግጋት ያስጠብቃል፤ ያሻሽላልም፡፡ ለሚያወጣቸውም ሕግጋትና ለውሳኔዎቹ መነሻ የሚሆኑት ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍትና የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ረድኤት ናቸው፡፡ ያሉ ችግሮችንም አጉልተው ሊያሳዩ የሚችሉ እውነተኛ መነጽሮቻችን እነርሱ ናቸውና፡፡

ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በቅዱስ ሲኖዶስ አሠራር ውስጥ ጣልቃ የሚገቡና ካለው ሕግና ሥርዓት ውጪ የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦችና ቡድኖች እየተስተዋሉ ነው፡፡ ለዚህም ማሳያው ከግንቦት 5 እስከ 13 ባደረገው ጉባኤ ያሳለፈውን ውሳኔ ተከትሎ የተከሰተው ችግር ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያኒቱ ታይቷል ያለውን «የአስተዳደር ችግሮች፣ የሙስናና፣ የቤተሰባዊ አስተዳደር» አካሔድ መኖሩን በማመን ዘመኑን የዋጀ በተጠና ዕቅድና አፈጻጸም የሚከናወን፤ ሓላፊነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት ዘመናዊ የአስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት ውሳኔ አስተላልፏል፡፡ በውይይቱም ወቅት በአሠራሮች ውስጥ የመልካም አስተዳደር፣ የፋይናንስ አጠቃቀም፣ የሰው ኃይል አደረጃጀት ችግሮች መታየታቸውንና በልማት ሥራዎችም የሚፈለገውን ያህል ለውጥ አለመኖሩ ላይ ከስምምነት ደርሷል፡፡ እነዚህን ችግሮች ለማስተካከልና ከእርሱ የሚጠበቀውን የቅድስና አሠራር ለማስፈን የሚያስችል ከብፁዓን አባቶች የተውጣጣ ኮሚቴ የሰየመ ቢሆንም ተግባሩን ለማከናወን ያደረገው ጅምር እንቅስቅሴ ግን ውዝግብ አስከትሏል፡፡ ለዚህ ችግር መፈጠር ደግሞ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረጉ ያሉት ከብፁዓን አባቶች ውጪ ያሉ ግለሰቦች መሆናቸው በተከታታይ እየሆኑ ያሉት ነገሮች ያመለክታሉ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ይጠቅማል በማለት የወሰነው ውሳኔ ገና ተግባራዊ እንቅስቅሴ ሳይጀመርበት አለመግባባት እንዲከሰት የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች ማንነት ደግሞ አጠያያቂ ሆኗል፡፡ ምክንያቱም የውሳኔው አተገባበር ገና በሒደት ላይ እያለ ይህ ዓይነት ውዥንብር እንዲፈጠር መፈለጉም ማኅበራችንን ጨምሮ ለብዙ ምእመናን ያሳዘነ አካሔድ ሆኗል፡፡

ከዚህ አልፎም የቤተ ክርስቲያኒቱን አባቶች ክብርና ስም የሚያጐድፍ ተያይዞም የቤተ ክርስቲያንን እውነተኛ መንገድ የሚያሰድቡ የሕትመት ውጤቶችን በማሠራጨት የብፁዓን አባቶችን እንቅስቅሴ ለማዳከም፣ ለስምና ለክብራቸው በመሰቀቅ መልካሙን እንዳይሠሩ ለማድረግ የተለያዩ አፍራሽ እርምጃዎች ተወስደዋል፡፡ ከቅዱስ ¬ትርያርኩ ጀምሮ ብፁዓን አባቶች በሚያጠፉት ጥፋት ጠያቂ፣ ከሳሽ፣ ፈራጅ፣ መካሪ … ራሱ ቅዱስ ሲኖዶስ ሆኖ ሳለ ከዚያ አግባብ ውጪ፣ ከክርስቲያኖች በማይጠበቅ መንገድ፣ ለቤተ ክርስቲያን በመቆርቆር ስም የሚደረጉ የጥፋት ዘመቻዎች መቆም እንዳለባቸው ማኅበራችን የጸና እምነት አለው፡፡

በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መሠረት ያለውን ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣን ራሱ የማስከበር ሓላፊነት ያለበት ሲሆን የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የሆኑ ሁሉም ብፁዓን አባቶች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሁሉ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን ጠብቀው እየተከናወኑ መሆኑን ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል እንላለን፡፡ ችግሮችም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተወሰኑ ውሳኔዎችን ተግባራዊ በማድረግ ሒደት ላይ የተከሰቱ ስለሆነ የሲኖዶሱን ውሳኔ አፈጻጸም እንዲከታተል ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ሓላፊነት የሰጠው አካል ሓላፊነቱን እንዲወጣ ያስፈልጋል፡፡

በውሳኔ አሰጣጥ፣ ውሳኔዎችን በመተርጐም ሒደት ብፁዓን አባቶች ያላቸውን ግልጽ ድርሻ በረድኤተ መንፈስ ቅዱስ፣ በቅዱሳት መጻሕፍትና በሕሊና ምስክርነት ላይ ተደግፈው መፈጸም እንዳለባቸው የሁሉም እምነት ነው፡፡ በዚህ መንገድም አካሔዱን ካላጸና ሓላፊነት ያልተሰጣቸው ሌላ አካላት ጣልቃ ገብተው ተጽዕኖ እንዲፈጥሩ እድል ስለሚሰጥ ዘወትር አስፈላጊ የሆኑ ጥንቃቄዎች ሁሉ መደረግ እንዳለባቸው እናምናለን፡፡

የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ጉባኤም በቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠው የማስፈጸም ሥልጣን የተወሰኑትን ደንቦች፣ መመሪያዎችና ልዩ ልዩ ውሳኔዎች ተግባራዊ ማድረግ፤ ከእያንዳንዱ የሥራ ዘርፍ በሚቀርበው ጉዳይ ላይ እየተወያየና የሥራ አፈጻጸም ስልት እያወጣ መወሰን፤ በሚመለከተው ደረጃ የአስተዳደር ችግሮች ሲፈጠሩ እያጠና መፈትሔ መስጠት፤ ከየሀገረ ስብከቱ በይግባኝ የሚመጡ ጉዳዮችን መወሰን እንደሆነ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ተግባራት ሁሉ ግን የቅዱስ ሲኖደስን ሥልጣን ከማክበር ጋር፤ ለወሰናቸውም ውሳኔዎች ከመገዛት ጋር የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን በቅዱስ ሲኖደስ ውሳኔ ላይ ተጽዕኖ የመፍጠርና አግባብ ያልሆነ የውሳኔ አተረጓጐምን የመከተል አካሔድ እንዳይኖር ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበት እናምናለን፡፡

በአጠቃላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በቤተ ክህነቱ አሠራር ውስጥ ይመለከተናል የሚሉ ወገኖች ሁሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን የሕግ አውጪነትና ተርጓሚነት ሥልጣን አምኖ መንቀሳቀስ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ አሠራር ሕልውና የግድ የሚያስፈልግ ነው፡፡ በመሆኑም እነዚሁ አካላት ለቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች ተግባራዊነት እንዲተባበሩና በውሳኔዎቹ ይዘቶች ላይ ያሉ ብዥታዎችንም ራሱ ቅዱስ ሲኖዶስ ግልጽ የሚያደርግበትን የራሱን አሠራር መጠበቅና ማስጠበቅ ይገባቸዋል፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔን እየተሰበሰቡ በመቃወም ሥልጣንና ቅድስናውን የመፈታተን አካሔድ ከወዲሁ ሊገታ ይገባዋል፡፡

በሃይማኖት ተቆርቋሪነት ስም የብፁዓን አባቶችን ስም በማጉደፍ፣ ለማጉደፍም በመዛት በአባቶች መካከል መለያየትን የሚያሰፍኑ በሥልጣንም ሆነ በሓላፊነት የማይመለከታቸው ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች ከድርጊቶቻቸው መቆጠብ ይኖርባቸዋል፡፡ እንዲህ ያሉ ወገኖች ከምንም በላይ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት የማይጨነቁ ከሆነ፣ በመንፈስ ቅዱስ ለተሾሙ አባቶችም ክብርን የመስጠት ፍላጐት ካጡ፣ እንዲሁም አባቶች በቅዱስ ሲኖዶስ በሚኖራቸው የመወሰን ድርሻ ላይ ተጽእኖ የመፍጠር አዝማሚያ ማሳየታቸውን ከቀጠሉ ማኅበራችን ድርጊታቸውን ከማውገዝ ባለፈ በሃይማኖት ወገንተኝነታቸው ላይ ጥያቄ ይኖረዋል፡፡

በሌላም በኩል አንዳንድ የግል መገናኛ ብዙኃን በሚያቀርቡት የተዛባ መረጃ ጉዳይ በሚመለከታቸው የቤተ ክህነቱ ወገኖች ላይ ስጋትና ጥርጣሬ ከመፍጠር አልፎ ከፍተኛ ችግሮች እያስከተለ ነው፡፡ ይህ አካሔድ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዕድገትና ጥንካሬ ለዓመታት ሲንቀሳቀስ የቆየውን ማኅበራችንን ማኅበረ ቅዱሳንን በእጅጉ ያሳስበዋል፡፡ በመሆኑም እነዚህ የመገናኛ ብዙኀን በእውነተኛ ምንጮች ላይ ተደግፈው እውነተኛ መረጃዎችን በመስጠት ችግሩን ለመፍታት እንዲንቀሳቀሱ መጠየቅ እንወዳለን፡፡

ካህናትና ምእመናንም ቤተ ክርስቲያናችን ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝባት የክርስቶስ ሙሽራ መሆኗ ተጠብቆ እንዲቀጥል የፈጣሪም ረድኤትና በረከት እንዳይለየን ለሰላሟና አንድነቷ በንቃት መቆም ይገባናል፡፡ ምእመናን ዓሥራት በኩራት አውጥተው የሚያስተዳድሯት ቤተ ክርስቲያን በመሆኗ የቅዱስ ሲኖዶስ ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣንን በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መሠረት የማስከበር የማይተካ ሚና አላቸውና፡፡ በመሆኑም ምእመናን ጉዳዮችን የራሳችን ጉዳይ በማድረግ ቤተ ክርስቲያን በየጊዜው ከሚያጋጥማት ፈተና እንድትድን በጾም በጸሎት እንድንበረታ መልእክታችን ነው፡፡

ምእመናንን ዕለት ዕለት በማገልገል ከምድር የሆነውን ብቻ ሳይሆን ሰማያዊውን ደመወዝ በተስፋ የሚጠባበቁ ካህናትም በጾም በጸሎት ከመትጋት ባሻገር በፈተና ጊዜ ፈተናን ለማስረግ አጋጣሚዎችን የሚጠቀሙ የቤተ ክርስቲያንን ጠላቶች መከታተልና ማስታገስ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ከምንም በላይ ደግሞ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ምዕራፍ ሁለት አንቀጽ ስድስት እንደተቀመጠው የክርስቲያን ወጣቶች እንቅስቃሴ እንዲጐለብት ቅዱስ ሲኖዶስ ዓላማው አድርጐ እየሠራ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መመሪያ ሥር ሆነን አገልግሎት እየሰጠን ያለን ሰንበት ት/ቤቶችና ማኅበራት የቅዱስ ሲኖዶስን ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣን ማስከበር ለሥራችን ስኬትና ለምናገለግላት ቤተ ክርስቲያን ተቋማዊ ጥንካሬ ወሳኝ መሆኑን ልንረዳ ይገባል፡፡ ስለዚህም በተለያዩ ጊዜያት ቤተ ክርስቲያናችን ከውስጥና ከውጪ የሚገጥማትን ፈተና ለመቋቋም ጥረት ማድረግ ይገባናል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ይህን ድርሻውን ተረድቶ የሚንቀሳቀስ መሆኑን እየገለጸ፤ በቀጣይም በቅዱስ ሲኖዶስ የሥልጣን የበላይነት በቤተ ክርስቲያናችን አንድነት እና በቅዱስ ¬ትርያርካችን አባትነት ላይ የጸና አቋም እንዳለው በግልጽ ማስቀመጥ ይፈልጋል፡፡ ለዚህም እውን መሆን ከሚተጉ አካላት በመተባበር ያላሠለሰ ጥረት ማድረጉን እንደሚቀጥል መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

                                                            ወስብሐት ለእግዚአብሔር።

የቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ስብሰባ ተጠናቀቀ

በግንቦቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ የቤተክርስቲያኒቱን አስተዳደራዊና የልማት ሥራዎች እንዲያከናውን የተመረጠውንና በአዲስ አበባ ሀገረ ስብ ከት የተነሳውን ችግር ለመፍታት የተጠራው አስቸኳይ የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ተጠናቀቀ፡፡

ከቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በተሰጠውና ቅዱስ ፓትርያርኩ ባነበቡት መግለጫ እንደተመለከተው፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ የሚታየውን የአፈጻጸም ችግር እንዲከታተል በግንቦቱ የርከበ ካህናት ጉባኤ የተሰየመው የሥራ አስ ፈጻሚ ኮሚቴ ከተሰየመበት መደበኛ ተግባሩ ጋር በቤተክርስቲያኒቱ የልማት ዘርፍ ላይ ውጤቶች ለማጠናከር የገቢ ምንጭ የሚያስገኙትን ፕሮጀክቶች ለመፍጠር የሚያስችለውን ረቂቅ አላዘጋጀም ይላል፡፡
ውስጥ ደንቡን አዘጋጅቶ ወደ ሥራ ከመግባቱ በፊት በተፈጠረው ሰው ሠራሽ ችግር ምክንያት የቤተክርስቲያኒቱን ማዕከላዊ አስተዳደር ለትችት የዳረገ ውዘግብ ተፈጠሮ እንደነበር ቅዱስ ፓትርያርኩ ያነበቡት መግለጫ አስታውሶ፤ ቅዱስ ሲኖዶስ የችግሩን መነሻ ከምንጩ በመመርመር ሁሉ ንም በየሥራ ዘርፉ ማስተናገድ የሚያስችል ውሳኔ ማሳለፉንም መግለጫው አመልክቷል፡፡
በቅዱስ ¬ትርያርኩ የተነበበው መግለጫ እንደሚያመለክተው፤ በአም ስተኛው ¬ትርያርክ አሥራ ሰባተኛ ዓመት በዓለ ሲመት አከባበር ማግስት ጀምሮ በተካሄደው ስብሰባ የሚከተሉትን ውሳኔዎች ማሳለፉን አስተውቋል፡፡

አንደኛ ታግዶ የነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ እግዱ ተነስቶ ሊመራበት የሚያስችለውን ውስጠ ደንብ ከሚመድቡለት ባለሙ ያዎች ጋር በመሆን አዘጋጅቶ እን ዲያቀርብ፤ የሚያዘጋጀውን የመተዳ ደርያ ደንብ እስከሚያቀርብ ድረስም ከቤተክርስቲያኒቱ የአመራር አካላት ጋር እየተመካከረ እንዲሠራ መወሰኑን በቅዱስነታቸው የተነበበው መግለጫ ያመለክታል፡፡
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አስተ ዳደር ችግር በተመለከተ ምልዓተ ጉባኤው በረጋ መንፈስ በነቃ አእ ምሮ ሊተኮርበት የሚገባ ታላቅ ሀገረ ስብከት መሆኑን በመገንዘብ ለውዝግቡ መነሻ የሆነውን የፋይናንስና የመልካም አስተዳደር እጦት ችግር አጣርቶ ለጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የሚያቀርብ ገለልተኛ ኮሚቴ እንዲቋቋም ጉባኤው መስማመቱንም መግለጫው ጠቁሟል፡፡

ቀደም ሲል በቅዱስ ¬ትርያርኩ እገዳ ተጥሎባቸው የነበሩት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የብፁዕ ወቅዱስ ¬ትርያርኩ ረዳት ጳጳስ አቡነ ሳሙኤል እገዳ እስከ ጥቅምት 2002 ሲኖዶስ ስብሰባ እን ዲቆይና እንዲታይ፤ እስከዚያው ድረ ስም ሀገረ ስብከቱ ቅዱስ ሲኖዶስ በሾመው ሥራ አስኪያጅ እየተመ ራና እየተዳደረ እንዲቆይ መወሰኑን ከመግለጫው ለመረዳት ተችሏል፡፡
በመግለጫው ላይ እንደተመለከተው፤ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተክርስተያኒቱን አጣዳፊ ተግባር ለማከናወን ከተሰየመ በት ሐምሌ 6 ቀን 2001 ዓ.ም ጀምሮ በሀገር ውስጥና በውጭ አህጉር እንዲሁም በተለያዩ ጋዜጦችና መጽሔቶች ሲነገር የሰነበተው፤ ከቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌለው፤ ከእውነት የራቀ ዘይቤ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም ሲልም መግለጫው አስረድቷል፡፡

በቅዱስ ¬ትርያርኩ የተነበበው መግለጫ በመጨረሻ እንዳመለከተው፤ ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዘው ከሚያስተላልፋቸው መልእክቶች መካከል ሰላምና መረጋ ጋት የመጀመሪያውን አጀንዳ ይዘው ይገኛሉ በማለት ጠቁሞ፤ እግዚአብሔርን ማመስገን፣ ቤተክርስቲያንና ወገንን ማገልገል፣ ሀገርን ማልማት የሚቻለው ፍቅር፣ አንድነትና ሰላም ሲኖር ብቻ ነው ይላል፡፡

በመሆኑም ከራሳችን ከእያንዳን ዳችን ከቤተሰባችን ቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ ሁሉም ኅብረተሰብ በሰላም የተመሠረተ ሕልውና እንዲኖረው በቅዱስ ¬ትርያርኩ የተነበበው መግለጫ ያመለክታል፡፡

በሌላ ዜና የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ብፁዓን አባቶች ማንነታቸው ባልታ ወቁ ግለሰቦች ሐምሌ 8 ቀን 2001 ዓ.ም ምሽት በመንበረ ¬ትርያርክ ጽ/ቤት ግቢ በሚገኘው መኖሪያቸው የመደብደብ ሙከራ እንደደረሰባቸው ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል፣ ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ፣ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ገልጸዋል፡፡

እንደ ብፁዓን አባቶች ገለጻ ማግሥቱ ለመሰብሰብ እየተዘጋጁ፣ ጸሎት እያደረሱ ሳለ ሌሊት ማንነታ ቸው ያልታወቁ ሰዎች ቤታቸውን በኃይል በመደብደብ በር እንዲከፍቱ ላቸውና የሚያወያዩአቸው ነገር እንዳለ ሲገልጹላቸው ማንነታቸውን ስለማያውቁ እንደማይከፍቱ ምሽትም በመሆኑ ማንነታቸውን የማያውቋቸውን ሰዎች ለማነጋገር ፈቃደኛ እንዳልሆኑ በመግለጽ እንደመለሷቸው አስተያየታቸውን የሰጡን አባቶች አስረድተዋል፡፡

ዓላማቸው ያልተሳካላቸው ማንነታቸው ያልታወቁት ግለሰቦች ቅዱስ ¬ትርያርኩ ባልተገኙበት ወቅት ቅዱስ ሲኖዶሱን በሰብሳቢነት ይመሩ የነበሩትን የብፁዕ አቡነ ቄርሎስን በር ሰብረው በመግባት ጭምር ጉዳት ለማድረስ እንደሞከሩ ብፁዓን አባ ቶች ጠቁመው፤ የአንዳንዶቹን በር በኃይል በመምታትና በማስጠንቀቅ «ጠብቅ እናሳይሐለን» የሚሉ ዛቻዎች በመሰንዘር ያስፈራሩ እንደነበረም ገልጸዋል፡፡

ጉዳት ለማድረስ የመጡት ግለሰ ቦች በመጀመሪያ የብፁዓን አባቶችን በር ሲያንኳኩ «ፖሊሶች ነን ክፈቱ» ይሉ እንደነበርና የብፁዓን አባቶቹ ቤት የደበደቡበት ሰዓት ተመሳሳይ እንደነበር አስተያየት ከሰጡን አባቶች ለመረዳት ችለናል፡፡

ምዕመናን በተከሰተው ነገር ሳይደና ገጡ ሁሉን ማድረግ ወደሚችለው አምላክ ይጸልዩ ያሉት ብፁዓን አባ ቶች፤ መንግሥት ጉዳዩን በጥልቅና በትኩረት በመከታተል ጥበቃ እንዲ ያደርግና የቤተክርስቲያንን ችግር እንዲፈታ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በጠቅላይ ቤተክህነት የጥበቃ ሓላፊውን በአባቶች ላይ የደረሰውን የድበደባ ሙከራ አስመልክተን ያደረግነው ሙከራ አጥጋቢ ምላሽ ባለመገኘቱ አልተሳካም፡፡

በጉዳዩ ላይ ቤታቸው የተደበደበ ባቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ቤተሰቦቻውን አነጋግረናል ከዚህ እን ደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡ ብፁዕ ነታቸው ሌሊት በቅጽረ ቤተ ክህነት ስለተፈጠረው ጉዳይ ጠይቀናቸው ምላሻቸው የሚከተለው ነበር፡፡

ሐምሌ 8 ቀን የነበረው ስብሰባ በጣም ጥሩ ስብሰባ ነበር፡፡ የመንግሥት ባለ ሥልጣናት በተገኙበት እየተነጋገርን አንድ ሁለቱ ችግር ተቃሎ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን ጉዳይ ለማነጋገር እሳቸው ስላልነበሩ ነገ እሳቸው ባሉበት እንነጋገራለን፡፡ ብለን ነው በሰላም የወጣነው፡፡ ከዚያ በኋላ በሰላም ወደ ቤታችን ገባን፡፡

ሌሊት የአባቶች ቤት ተመቷል፤ የአቡነ ቄርሎስ ግን በጣም የበዛ ነበር መዝጊያውም ተሰብሯል፡፡ ይህን ዐይቻለሁ፤ በውስጡም በውጭውም «የ¬ሊስ ያለህ፣ የመንግሥት ያለህ» ድረሱልኝ በእንደዚህ ቁጥር ቤት ያለን እየተደበደብን ነው ብዬ ስጮህ ገለል ብለው ሔዱ፤ እንጂ ወደ መኝታ ቤቱ ሊገቡ ትንሽ ነበር የቀረው ብለው ነግረውኛል፡፡ በማለት የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

ዲ/ን ተክለ ወልድ የብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ረዳት ነው፡፡ ጉዳዩን አስመልክቶ የሚለው አለ፡፡ «ዋናውን በር ገንጥለው ገብተዋል፡፡ ቀጥለው የመኝታ ክፍሉን በር ለመስበር ሲታገሉ ብፁዕ ነታቸው ውስጥ ሆነው ስልክ መደወላቸውን ሲሰሙ ትተው ሔዱ፡፡ ማዕድ ቤት ገብተው ያሉትን ዕቃዎች ሁሉ ፈትሸዋል፣ መሳቢያዎች ሁሉ ተከፋፍ ተው ተበርብረዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አሁን ደህና ናቸው፡፡ አጋጣሚ አንዲት ነርስ እኅታችን ጤንነታቸውን እየተከተለች የሕክምና ርዳታ ታደርግላቸው ትከታተላቸው ስለነበር እሷ የሳሎኑ በር ሲሰበር መኝታ ቤቱን ቆልፋ ለሕይወታቸው መትረፍ ምክንያት እንደሆነችም ይገልጻል፡፡

የጉራጌ ከንባታና ሀዲያ እና ሲልጤ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ ምን ይላሉ?

«ነገሩ ያሳዝናል ግን እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነን፡፡ ለሁሉም የኛ አለቃ፣ ንጉሥ፣ ባለሥልጣን፣ እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህ ለእግዚአብሔር ከመንገርና ከመስጠት ሌላ የምንለው የለም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሕግ ሕገ ቅዱስ ሲኖዶስ ይከበር ነው ያልነው፡፡ ሌላ ያልነው ነገር የለም፡፡

በአሁኑ ሰዓት በእውነቱ ቤተክርስቲያን የጠበቀችውን ያህል አልተጓዘችም ብለናል፡፡ አባቶችም ሲታገዱ በሲኖዶሱ ሕግ፣ ሲኖዶሱ ያግድ፣ ከሲኖዶሱ ጋር ይሥሩ፣ እንርዳዎት፣ እናገልግልዎት፣ እናግዝዎት ነው ያልነው እኛ ሌላ ነገር ያልነው ነገር የለም፡፡ እኛ በየሀገረ ስብከታችን እያገለገልን እየተሯሯጥን ነው፡፡
ባለሥልጣናት ባለፈው ዓርብ መጥተው የቅዱስ ሲኖዶስን፣ የቤተክርስቲያንን ቃለ አዋዲ አክብራችሁ፣ ተደማመጡ፣ ቤተክርስቲያኒቱ እንኳን ለራሷ ለአፍሪካም መሆን የም ችል ናት አሉን፡፡

ሕዝቡም ተበጥብጧል፣ ተጨንቋል እባካችሁ ሰላም አውርዱ፣ መንግሥት ሓላፊነት አለበት፡፡ አመራርና አካሔድ ልንነግራችሁ ነው የመጣነው፡፡ ከተበጣበጠ መንግሥት ጣልቃ ይገባል፣ ሓላፊነት አለበት፡፡ እናንተ አባቶች ናችሁ፤ የምትመክሩንና የምትረዱን እንጂ እኛ እናንተ ውስጥ ጣልቃ መግባት አንችልም፡፡ የራሳችሁን ችግር በራሳችሁ አክብሩ፤ የሐምሌ 5 ቀን በዓልን በሰላም አክብሩ፤ የራሳችሁ በዓል ነው ብለው ጥሩ መመሪያ ሰጡን ተወያዩ አሉን፡፡ እንደገና ተሰባሰብን ሐምሌ 7 ቀን ሰላም ይኖራል ብለን፡፡ ነገር ግን የባሰ ነበር ጉዳዩ፡፡

አሁን ደግሞ እየታየ ያለው ደስ የማይል ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አምላክ ይፍረደን፤ እሱ እንደፈቀደ ይሁን፣ ቅዱስ አባታችንን ለመንቀፍ አይደለም፣ እሳቸውን ለማዋረድ አይደለም እናከብራቸዋለን፡፡ እኛ ያልነው ሕግ አክብረው ያስከብሩን፣ በሕግ ይምሩን ነው የምንለው፡፡

እኛ መሠረታችን እግዚአብሔር ነው፡፡ ጠባቂያችን እግዚአብሔር ነው፡፡ ቀጥሎ ደግሞ መንግሥት ነው፡፡ በመንግሥት ተስፋ አንቆርጥም፡፡ የማጣራት ሥራ ሠርቶ መግለጥ አለበት፡፡

ሁሉንም የሚያውቀው ጌታ እግዚአብሔር ነው፡፡ ለሁሉም ጽዋው ይሞላል፤ ዋጋውን ይከፍላልና ብዙ ችግሮች ደርሰዋል፣ እየደረሱም ናቸው፡፡ ግን አባቶች ለሞትም ቢሆን የተዘጋጀን ነን፡፡

የበር መስበር አይደለም፣ ማስፈራራት አይደለም ለቤተ ክርስቲያን ካስፈለገ እንሞታለን፤ የቀደሙትም ሞተውላታል፡፡ አሁንም ቢሆን አባቶች ወደ ኋላ አንልም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሁል ጊዜ በፈተና እየተፈተነች ነው ዘመናትን የተሻገረችው ከፈተና ወጥታ አታውቅም፡፡

አሁንም ቢሆን ሲኖዶሱ የተወያየው፣ እርሳቸው ስብሰባውን እንዲመሩ፣ አስተዳደራዊ ሥራውን ሌሎች እንዲሠሩ ሁልጊዜ የምንነጋገረው፣ ለመንግሥትም እያሳሰብን ያለነው ይሄን ነው፡፡

እሳቸው በአባትነታቸው፣ በሊቀ መንበርነታቸው ጉባኤውን ይምሩ፤ ሲኖዶሱ ግን በሲኖዶሱ ሕግ መሠረት ተወያይቶ ይወስን የሚል ሐሳብ ለብዙ ዓመታት ስናነሣ ቆይተናል፡፡ ስለልማት፣ ስለ ሃይማኖት ተጨቃጭቀን አናውቅም፡፡ አሁን ሰለቸን ብዙዎች አባቶች፣ ደከማቸው፤ በጣም ያሳዝናል፡፡

በዋናነት ኃይለኛ ክርክርና ጭቅጭቁ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ይከበር ነው፡፡ መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን ነው፣ በጀት በሥነ ሥርዓት እንዲመራ ነው፡፡ ሥራ አስፈጻሚውንም ቅዱስ ሲኖዶስ ሲመድበው ሥራ እንዲሠራ ነው፡፡ ኮሚቴው ቅዱስነትዎ በጥርጣሬ ሊያዩት አይገባም፡፡ ኮሚቴው እርስዎን የሚረዳና የሚያግዝ ነው ያልነው፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ላይ በአብዛኛው አባቶች አንድን ዓይነት መንፈስ ነበራቸው፡፡ የሃሳብ ግጭቶች ይኖራሉ፣ እያንዳንዱ የራሱ የሆነ አመለካከት ይኖረዋል ግን በአብዛኛው ሲኖዶሱ ደግሞ አንድ ዐይነት መንፈስ የሚታይበት ነው፡፡

በመጨረሻ የማስተላልፈው ቤተ ክርስቲያን በመርከብ ትመሰላለች፡፡ በባሕር ላይ ያለች መርከብ አውሎ ንፋስ ሊያንገላታት ይችላል፡፡ ስለዚህ ሐዋርያትን እናስታውስ፡፡ አውሎ ንፋስ የተሳፈሩበትን መርከብ ሲያናውጠው ክርስቶስም አብሮ ነበር፡፡ ክርስቶስ ያለባት መርከብ ዐውሎ እንደተነሣባት ነው፤ ሁሉም ሐዋርያት «አድነን» ነው ያሉት፤ ወደ እሱ ነው የጮሁት መጨረሻ ላይ ነፋሱን የገሰጸው እሱ ነው፡፡ አሁንም የቤተ ክር ስቲያን አምላክ ይህንን ማዕበል ፀጥ ያደርገዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ጾም ጸሎት ያስፈልጋልና፡፡ ምእመናን ወደ እግዚ አብሔር እንዲጮሁ ነው የማሳስበው፡፡ በዚህ ምክንያት እንዳይሸማቀቁ እንዳ ይደናገጡ ሃይማኖታቸውን ብቻ ይጠብቁ፡፡ በማለት አባታዊ ጥሪያቸውን በእንባም ጭምር አስተላልፈዋል፡፡

አቡነ ፋኑኤል የሲዳማ፣ የጌድዮ፣ የአማሮ፣ የቡርጂ ዞኖችና ልዩ ወረዳ ዎች አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡ ጥቃት ባይደርስባቸውም ሙከራ ተደርጎባቸው እንደ ነበር ሰማንና የደረሰባቸውን እንዲያብራሩልን ጠየቅናቸው ቃላቸውን እነሆ «እኔ ዘንድ የተፈጠረው ችግር ሐምሌ 9 ቀን ከምሽቱ 4፡30 ላይ ነው፡፡ ማንነታቸውን የማላውቅ ሰዎች ወደ መኖሪያዬ በመኪና መጡ፡፡ በኃይል የቤቴን መዝጊያ ደበደቡ፡፡ ጠባቂዎችን ተጠንቀቁ፤ በር አትክፈቱ አልኩ በዚያ ሰዓት እንግዳ እንደማይመጣ አውቃለሁ፡፡

ውጭም ያሉ ልጆችም በመስኮት አንኳኩተው ምንድን ነው አሉኝ፤ ዝም በሉ አልኳቸው፡፡ በጣም አንኳኩ በጣም ጠንከር አለ፡፡ በዚህ መሐከል ለቤተ ሰብና ለፖሊስ እንዲደወል አደረግሁ፡፡ 10 ደቂቃ ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ተመልሰው በመኪናቸው ሄዱ ወዲያው ቤተሰብም ፖሊስም መጣ፡፡ ነዕለታዊ ሪፖርት ፖሊስ ጣቢያ ሄጄ አስመዘገብኩ፡፡

ድርጊቱ የተፈጸመው እኔ ላይ ብቻ መስሎኝ ነበር፣ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሌሊት ስደውል እዚያም የባሰ እንደነበር ሰማሁ፡፡ እኔ የምኖረው ቃሊቲ ገብርኤል አካባቢ ነው፡፡ ይህ ሁሉ የመጣው በቅዱስ ሲኖዶሱ ሽኩቻ ነው፡፡

መቼም እኛ ሌላ ተቃዋሚ ወይም ጠላት የለንም፡፡ ምን ተፈልጐ ለምን እንደተፈጸመ አይገባኝም፡፡ በወቅቱ ስብሰባው የተካሄደው ለግማሽ ቀን ነው፡፡ ለሥራ አስፈጻሚ ተብሎ የተመረጠው ኮሚቴ እገዳው ተነሥቶለታል፡፡ ሌላው የብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ጉዳይ ነው እሱን ነገ እናየዋለን ነበር ያልነው፡፡ ስብሰባ ውም ቁጣ የተሞላበት አልነበረም፡፡ የተረጋጋና በሰከነ መንፈስ የተካሄደ ነበር፡፡ በማለት ጥቃቱ በተፈጸመበት ዋዜማም ቢሆን ለዚህ ድርጊት የሚያ ነሣሣ ምንም ዓይነት ምክንያት እንዳ ልነበር ገልጸዋል፡፡

ሕገ ሲኖዶስን አስመልክተው በርግጥ ቅዱስነታቸው ተቀባይነት የሌለው ሐሳብ አቅርበው ነበር፡፡ መሻሻል አለበት፣ ብዙ ነገር ጐድሎታል ይሉም ነበር ምን እንደሚጨምሩ፣ የትኛው አንቀጽ እንደሆነ የሚሻሻለው ባይገልጹም በድፍኑ ግን ቅሬታ እንዳላቸው ይገልጹ ነበር፡፡

በስብሰባው ወደ 6 አጀንዳ ቀርቧል እስካሁን የታየው ገና አንዷ ብቻ ነው፡፡ አሁን የተፈለገው ጠቅላላ ነገሮቹ እንዳይታዩ ሊሆን ይችላል ብዬ እገምታለሁ፡፡

በመጨረሻ የማስተላልፈው መልእክት ይሄ ፈተና ነው፤ በእኛ ላይ የመጣ ማዕበል ፈተና ነው ሁሉም በሃይማኖቱ ጸንቶ ቤተ ክርስቲያኒቱንም እኛንም ያስበን ሁላችንም በያለንበት እንጸልይ በሃይማኖት እንጽና ነው የምለው፡፡ እኛ ሁል ጊዜ ሕይወታችን ከወንጌል አገልግሎት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ አሁንም የምናደርገው ይህንኑ ነው፡፡ ቀጣዩም ሕይወታችን በወንጌል ማገልገል ነው፡፡

የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደራዊ ጉዳይ በተመለከተ ለውጥ ያስፈልጋል፡፡ ለውጥም ስለሚያስፈልግ ነው ይሄ ሁሉ የተከሰተው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በሁለንተናዋ በልማቱም በወንጌል አገልግሎቱም ወደኋላ ቀርተናል ማለት ይቻላል፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን ችግር ከኢትዮጵያ ሕዝብ የተሰወረ አይደለም፡፡ አሁን በሲኖዶስ ደረጃ ጐልቶ ወጣ፤ እንጂ ሕዝብ ተነጋግሮበት ያበቃለት ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በሃይማኖት በጸሎት ጸንተን መኖር ይገባ ናል፡፡ በተፈጠረው ሁኔታም ሳንደናገጥ ሳንሸበር ባለንበት ጸንተን የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕልውና የሚቀጥልበትን መንገድ ማሰብ ያስፈልገናል በማለት መልእክታቸውን ያጠቃልላሉ፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊና የዋግ ህምራ ሊቀ ጳጳስ ስለጉዳዩ በጥልቅ ሐዘን ይናገራሉ፡፡ይህ ነገር ይበጃል) ምእመኑ በጭን ቀት ላይ ነው ያለው የኛን ድምፅ መስማት ይፈልጋል፡፡ እኔ በሁኔታው ተረብሼ ሳልተኛ ነው ያደርኩት በቃ አሞኛል፡፡ አሁን ይህን የማስብበት የተረጋጋ አእምሮ የለኝም፤ ብለዋል፡፡
የቦረናና ጉጂ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስም ከዛቻና ስድብ ባያልፍም የጥቃቱ ሰለባ ነበሩና የሚናገሩት አላቸው፡፡«እግዚአብሔር በቸርነቱ በደላችንን ሳይመለከት አትርፎናል፡፡ ቤታችን በምሽት ባልታወቁ ግለሰቦች ተደበደበ በግምት ከምሽቱ አራት ሰዓት አካባቢ ይሆናል፡፡ የመጡት ሰዎች በሩን በኃይል ደበደቡ ክፈት አሉኝ፡፡ አልከፍትም አልኳቸው «አይ ልናማክሮት ነው አንዳንድ ነገሮችን ልናዋዮት ነው በሩን ክፈቱ አሉኝ» ሰዓቱ አልፏል እኔ አልከፍትም አልኳቸው «¬ሊሶች ነን» አሉኝ ፖሊሶችም ብትሆኑ በዚህ ሰዓት ሕጉ አይደለም፤ የሰውን በር ማስከፈት ስለዚህ አልከፍትም አልኳቸው፡፡ ክፈት እያሉ በሩን በኃይል መደብደብ ጀመሩ፡፡ እኔም በውሳኔዬ ጸናሁ፤ እነሱም ድብደባውን አጠነከሩ፣ በኋላ የውስጥ በር ዘግቼ ስልክ ወደ ፖሊስና ቤተሰብ ደወልኩ፡፡ ከዛም በኋላ ብዙ ሰዓት ይሆናል በሩን የቀጠቀጡት እኔ እንደውም ሰብረው የገቡ መስለውኝ ነበር፡፡ ሌላ ክፍል ውስጥ ቆልፌ ተቀምጬ ሳለ እግዚአብሔር መለሳቸው፡፡ የሔዱ ሲመስለኝ ቀጥሎ የሌላ አባት ቤት ሲደበደብ ሰማሁኝ፤ የማንን ቤት ነው የደበደቡት እያልኩ ነበር፡፡

ከኔ ቤት ቀጥሎ ያለውን ቢመስለ ኝም የሳቸው ቤት አልተነካም፣ ነገር ግን ብዙ ቤት ነው የተደበደበው በአጠቃላይ የጳጳሳቱ ቤት ነው የተደበደበው ግን እኛ በቸርነቱ ተርፈናል፡፡

ምክንያት ይሆናል የምለው ምናልባት በሲኖዶስ ስብሰባ ላይ በሰጠነው ሐሳብ ይሆናል ብዬ አስባለሁ፡፡ እንግዲህ ከዚህ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል ሌላ የተጣላነው ሰው የለንም ያው መነሻው በስብሰባው ላይ ሕገ ሲኖዶስ ይከበር ማለታችን ይመስለኛል፡፡

የቤተ ክህነት ግቢ ጥበቃ አለው፡፡ ድርጊቱ ሲፈጸም ለዘበኞች ደወልኩ እንመጣለን ይላሉ እንጂ አንዳች እርዳታ አላገኘሁም፡፡ ለወደፊቱ መንግሥት ጥበቃ ካላደረገልን እንግዲህ ለሕይወታችን በጣም የሚያሰጋ ጉዳይ ነው፡፡ ብዙ ጥረው መጨረሻ ሳይሳካ በመቅረቱ ነው እየተሳደቡ የሔዱት፡፡ ታገኛታለህ ቆይ እያሉ ነው ሲዝቱብኝ የነበረው፡፡

ማንም የደረሰልን የለም፣ እግዚአብሔር ግን ረድቶናል፡፡ ፖሊሱ መጣ ተባለ ነገር ግን ወደ ውስጥ መግባት የቻለ አይመስለኝም፤ መብራትም አልነበረም፡፡ በወቅቱ ያው ጨለማን ተገን አድርገው ነው፤ ለድብደባ የተሰማሩት አጥቂዎቹ፤ እንግዲህ የነገን ባናውቅም ለአሁን ተርፈናል፡፡

እኛ ለእግዚአብሔር አመልክተናል፡፡ መንግሥትም ጥበቃ እንዲያደርግልን ነው ጥሪያችንን አቅርበናል፡፡ ይህ ችግር በስብሰባው ላይ በተፈጠረ ያለመግባባት የመጣ ነው፡፡ ምክንያቱም በአቋማችን በጸናነው አባቶች ላይ ብቻ ተለይቶ ነው ድብደባው የተፈጸመው፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ትከበር፣ አስተዳደሯ ይከበር፣ ሙስና ይጥፋ ሁሉም ነገር በቤተ ክርስቲያን ሕግ ይሁን በማለታችን ዛቻና የበር ድብደባ ተፈጽሞብናል፡፡

የትናንት /ሐምሌ 8 ቀን 2001 ዓ.ም/ የስብሰባ ውሏ ችን የሰባቱን ሊቃነ ጳጳሳት እግድን ስለማንሣት ነበር የተወያየነው፡፡ ከዛ በኋላ በሌላ አጀንዳ ለዛሬ /ለሐምሌ 9/ ልነነጋገርና የመንግሥት አካላት እንዲገኙ ልን ተነጋግረን ነው የተለያየነው፡፡
የቤተ ክርስቲያን መዋቅርና አስተዳደራዊ መሠረቷ ሕገ ሲኖዶስ ነው፡፡

ያባቶች ሐሳብ አንድ ነው፡፡ ሁኔታዎች ላይ መስማማት እንጂ የመለያየት ነገር የለም፤ የሁሉም ዓላማና ራእይ አንድ ነው፡፡ ሐሳባቸው ዓላማቸው አስተዳደር ይስተካከል ሕገ ቤተ ክርስ ቲያኑ ይከበር ነው የተለያየ አይደለም፡፡ በመሠረታዊ ጉዳዩ የሁሉም አባቶች አቋም አንድ ዓይነት ነው፡፡ ለምሳሌ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ቤት እንደገናም በ¬ትርያርኩ መሪነት የተሰበሰቡ አሉ ይባላል፡፡ እንግዲህ ¬ትርያርኩም ጋር ሄደው ቢሰበሰቡ ሐሳባቸው አንድ ነው፡፡ እርስዎ ፊት የተወያየነውን ነገር በሲኖዶሱ ፊት እንስማማበታለን /እንፈራረምበታለን/ ነው ያሉት እንጂ በሐሳብ መከፋፈል የለም፡፡

በተፈጠረው ነገር ምእመናን እን ደተረበሹ እናውቃለን፡፡ ምእመናን የተበላሸ ነገር በአንዴ ሊስተካከል አይችልም፤ ያለ እምነት ውጤት አይ ገኝምና አሁንም በትዕግሥት እግዚኦታቸውን ይቀጥሉ፡፡ ምእመናንን የሚረብሽ ነገር የለም፡፡ ሁሉም ምእ መን በጸሎት ሆኖ እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያንን ከፈተና እንዲታደ ጋት በጸሎት እንዲጠይቅ ነው፡፡ በጸሎት እንዲያስቡን ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔርን በጸሎታቸው እንዲ ጠይቁልን ነው የሚያስፈልገው፡፡» በማለት ነበር ስለሁኔታው የገለጹት፡፡
ጥቃቱን የፈጸመው ቡድን ሆን ብሎ ብፁዓን አበውን የሚያሳድድ በመሆኑ ለብፁዓን አበው ጥበቃ እንዲ ደረግላቸውና ወንጀለኞቹም ለፍርድ እንዲቀርቡ ምእመናን እየጠየቁ ነው፡፡
ብፁዓን አበው ምእመናን በጾምና በጸሎት እንዲተጉ ደጋግመው የጠየቁት ሲሆን በሃይማኖት ጸንተው የእግዚአብሔርን ፍርድ እንዲጠጣበቁ አሳስበዋል፡፡

 
 
 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር