የሆሣዕና ምንባብ11(ማር.11÷1-12.)

ኢየሩሳሌም ለመግባት በደብረ ዘይት አጠገብ ወደ ቤተ ፋጌና ወደ ቢታንያ በደረሱ ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱን ላከ፡፡ እንዲህም አላቸው÷ “በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፤ ወደ መንደርም በገባችሁ ጊዜ÷ ሰው በላዩ ያልተቀመጠበት የአህያ ውርንጫ ታስሮ ታገኛላችሁ፤ ፍቱና አምጡልኝ፡፡ ‹ምን ታደርጋላችሁ?› የሚላችሁ ሰው ቢኖርም ‹ጌታው ይሻዋል› በሉ፤ ወዲያውኑም ወደዚህ ይሰድደዋል፡፡” ሄደውም በበሩ አጠገብ ባለው ሜዳ በመንገድ ዳር የታሰረ ውርንጫ አገኙ፤ ፈቱትም፡፡ ከዚያ ቆመው የነበሩትም÷ “ምን ልታደርጉት ነው ውርንጫዉን የምትፈቱት?” አሉአቸው፡፡ ጌታችን ኢየስስ እንደ አዘዛቸውም ነገሩአቸው፤ እነርሱም ተዉአቸው፡፡ ውርንጫዉንም ወደ ጌታችን ኢየሱስ ወሰዱና ልብሳቸውን በላዩ ደልድለው አስቀመጡት፡፡ ብዙዎችም ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ፤ ሌሎችም ከዛፍ ቅጠሎችን እየቈረጡ ያነጥፉ ነበር፡፡ በፊት የሚሄዱ÷ በኋላም የሚከተሉ እንዲህ እያሉ ይጮኹ ነበር÷ “ሆሣዕና÷ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ስም የምትመጣ የአባታችን የዳዊት መንግሥት የተባረከች ናት፤ ሆሣዕና በአርያም፡፡” ጌታችን ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወደ ቤተ መቅደስ ገባ፤ ሁሉንም ተመልክቶ በመሸ ጊዜ ከዐሥራ ሁለቱ ጋራ ወደ ቢታንያ ሄደ፡፡