የሆሣዕና ምንባብ9(ማቴ. 9፥26-ፍጻ.)

የተአምራቱም ዝና በሀገሩ ሁሉ ተሰማ፡፡ ጌታችን ኢየስስም ከዚያ በአለፈ ጊዜ ሁለት ዕውራን÷ “የዳዊት ልጅ ሆይ÷ ራራልን” ብለው እየጮኹ ተከተሉት፡፡ ወደ ቤትም በገባ ጊዜ እነዚያ ዕውራን ወደ እርሱ መጡ፤ ጌታችን ኢየሱስም “ይህን ማድረግ እንዲቻለኝ ታምናላችሁን?” አላቸው፤ እነርሱም÷ “አዎን ጌታ ሆይ!” አሉት፡፡ “እንደ እምነታችሁ ይሁንላችሁ” ብሎ ዐይኖቻቸውን ዳሰሳቸው፡፡ ያንጊዜም ዐይኖቻቸው ተገለጡ፤ ጌታችን ኢየሱስም÷ “ማንም እንዳያውቅ ተጠንቀቁ” ብሎ አዘዛቸው፡፡ እነርሱ ግን÷ ወጥተው በዚያ ሀገር ሁሉ ስለእርሱ ተናገሩ፡፡

እነዚያም ከወጡ በኋላ ጋኔን ያደረበትን ዲዳ ወደ እርሱ አመጡ፡፡ ያደረበትም ጋኔን በወጣ ጊዜ ዲዳ የነበረው ተናገረ፤ ሰዎችም “በእስራኤል ውስጥ እንዲህ ያለ ከቶ አልተየም” እያሉ አደነቁ፡፡ ፈሪሳውያን ግን “በአጋንንት አለቃ አጋንንትን ያወጣል” አሉ፡፡

ጌታችን ኢየሱስም በምኲራቦቻቸው እያስተማረ÷ የመንግሥት ወንጌልንም እየሰበከ÷ በሕዝቡም ያለውን ደዌና ሕማም ሁሉ እየፈወሰ በየከተማውና በየመንደሩ ሁሉ ተመላለሰ፡፡ ብዙ ሰዎችንም አይቶ አዘነላቸው፤ ደክመው ነበርና÷ እረኛ እንደሌላቸው በጎችም ተበትነው ነበርና፡፡ ያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አላቸው፤ “መከሩሰ ብዙ ነው፤ ሠራተኛው ግን ጥቂት ነው፡፡ እንግዲህ ለመከሩ ሠራተኛን ይጨምር ዘንድ የመከሩን ባለቤት ለምኑት፡፡”