የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ

መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ሪፖርታዥ

TAKLL2004 534የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት፤ የመምሪያ ሓላፊዎች፤ ቀሳውስትና ካህናት፤ የፌደራል ጉዳዮች የሃይማኖት ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም.በድምቀት ተጀመረ፡፡

ነሐሴ 29 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዋዜማው ነሐሴ 29 ቀን 2004 ዓ.ም. ከቀኑ ስድስት ስዓት ጀምሮ ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የመጡ የማኅበሩ አባላት ማኅበሩ እያስገነባው በሚገኘው ሕንጻ ውስጥ በመገኘት የሕንጻው ግንባታና በማኅበሩ የአንዳንድ አገልግሎት ክፍሎችን እንቅስቃሴ በመጎብኘት ማብራሪያ እየተሰጣቸው ቆይተዋል፡፡ ከምሽቱ 12፤00 ስዓት ጀምሮ የጠቅላላ ጉባኤው አስተባባሪ ኮሚቴ ባዘጋጀው ትራንስፖርት ከማኅበሩ ዋናው ማእከል አቧሬ ወደሚገኘው አቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በመጓዝ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት፤ የመርሐ ግብር ትውውቅ፤ ሕጽበተ እግርና የእራት መርሐ ግብር ተከናውኗል፡፡

ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም.

ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዐቃቤ መንበረTAKLL2004 533 ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመመራት በመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን በተጋበዙ ቀሳውስትና ካህናት ጸሎተ ወንጌል የተካሄደ ሲሆን በብፁዕነታቸው ጸሎትና ቡራኬ ተከፍቷል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የሁለት ዓመት የአገልግሎት ክንውን ሪፖርት በማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም አማካይነት የቀረበ ሲሆን ሪፖርቱም በማኅበረ ቅዱሳን ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ የአገልግሎት ክፍሎች እየተከናወኑ የሚገኙትን ተግባራት የዳሰሰ ነበር፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በሚዲያ አገልግሎት፤ በግቢ ጉባኤያት፤ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት፤ በቅዱሳት መካናትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ላይ የተሠሩ ከፍተኛና አነስተኛ ፕሮጀክቶች፤ ስለቤተ ክርስቲያናችን የተደረጉ የጥናትና ምርምር ሥራዎች፤ የልማት ተቋማት አስተዳደር፤ የቤተክርስቲያንና የምእመናን ማኅበራዊ አገልግሎት፤ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያደርሱትን ጥቃትና የተወሰዱ እርምጃዎች፤ ወዘተ በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት በቀጣይነት የቀረበው የ2003 ዓ.ም. የማኅበሩ የሒሳብ ሪፖርት ሲሆን በውስጥ ኦዲተርና በውጪ የሂሳብ ኦዲተሮች ሀብተ ወልድ መንክርና ጓደኞቹ በቻርተር የተመሰከረላቸው የሂሳብ አዋቂዎች በተሰኘና እውቅና ባለው ድርጅት አማካይነት ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ በዚህም ሂሳቡ ትክክለኛ እና የማኅበሩን ገጽታ የሚያሳይ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

በቀረበው የማኅበሩ የሁለት ዓመታት አገልግሎት፤ እንዲሁም አጠቃላይ እንቅስቃሴ ላይ አስተያየት እንዲሰጡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል መልካም ፈቃድ ከብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት ተጋብዘዋል፡፡ በተጨማሪም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችም ከበጎ አድራጊ ምእመናን፤ ከነገረ መለኮት ምሩቃን ማኅበር፤ ከፀረ ተሐድሶ የሰባኪያን ጥምረት የተወከሉ እንግዶች በማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ዙሪያ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

TAKLL2004 350አስተያየታቸውን ከሰጡ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳዊ የምስራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ “በገሊላ አውራጃ ጌታ አሥራ ሁለት ሐዋርያትን እንደመረጠ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስም በምሳሌነት ይህች ቤተ ክርስቲያን የተማረ የሰው ኀይል ያስፈልጋታል በማለት 12 የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ይዘው ነው በዝዋይ ሥራ የጀመሩት፡፡ ማኅበሩ ማኅበራችን ነው” በማለት የማኅበረ ቅዱሳንን አመሠራረት አስታውሰዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ማትያስ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት አስተያት “ማኅበረ ቅዱሳን ብዙ ምሁራንና አዋቂዎች የተሰባሰቡበት ነው፡፡TAKLL2004 307 ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ ተጠሪ ነው” በማለት ነበር የገለጹት፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ “ማኅበረ ቅዱሳን በ20 ዓመት ውስጥ ያከናወነው አገልግሎት እኛ የማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊዎች ብቻ ሳንሆን ተቃራኒዎችም የሚመሰክሩት ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡

ሊቀ ካህናት ኃ/ሥላሴ ዓለማየሁ የዴንቨር ደብረ ሰላም መድኀኔዓለም አስተዳዳሪና የካሊፎርኒያ  አካባቢ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ በሰጡት አስተያየት ”ከማኅበሩ ጋር TAKLL2004 347በግጭትም፤ በፍቅርም ተገናኝተናል፡፡ ማኅበሩን ከማወቄ በፊት የተቀበልኩት በበጎ መንፈስ አልነበረም፡፡ ነገር ግን በሚያስደንቅ ሁኔታ እኔን የሚያሳምኑ ነገሮች የተፈጠሩት ውስጣችን ገብተህ አገልግሎታችንን ተመልክተህ ፍረድ የሚል ጥያቄ አቀረቡልኝ፡፡ አላቅማማሁም ገባሁ፡፡ የማኅበሩን ማንነት ውስጡን ሕይወቱን ለማየት በምሞክርበት ጊዜ በትክክል የቤተ ክርስቲያኒቱ የጀርባ አጥንት ሆኖ እያገለገለ መሆኑን ለማወቅ እድል አገኘሁ” በማለት ከማኅበሩ ጋር ያላቸውን ቅርበት ገልጸዋል፡፡

የጠዋቱ መርሐ ግብር የማኅበሩ የመዝሙር ክፍል አባላት በኅብረት ያሬዳዊ ዝማሬ ያቀረቡ ሲሆን በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና በአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

ከስዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብር የማኅበሩ ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ሓላፊ ዲ/ን ንጋቱ ባልቻ ሪፖርት የቀረበ ሲሆን በሪፖርቱም የማኅበሩ ስልታዊ ዕቅድ አፈጻጸም፤ የማኅበሩ ሥራ አመራር አፈጻጸም፤ የጠቅላላ ጉባኤያት ውሳኔ በተመለከተ ያልተተገበሩ፤ የሂሳብ ሪፖርት ላይ ታይተዋል ያሏቸውን ክፍተቶች አቅርበዋል፡፡በተጨማሪም የጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔ ወይም አቅጣጫ የሚሹ ጉዳዮች ተለይተው ጠቅላላ ጉባኤው ቀጣዩን ስልታዊ እቅድ እና የማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ ሲከለስ እንዲካተቱ ትኩረት እንዲሰጣቸው አሳስበዋል፡፡ በኦዲትና ኢንስፔክሽን በቀረበው ሪፖርት ላይና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች እንዲሁም ከአባላት በተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ማኅበሩን ወደፊት ሊጠቅሙ በሚችሉ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡

TAKLL2004 436በመጨረሻም የሚቀጥሉትን አራት ዓመታት ማኅበሩን የሚመሩ የሥራ አመራር አባላትን የሚያስመርጥ 5 አባላትን ያቀፈ አስመራጭ ኮሚቴ ለመምረጥ 7 አባላት አስተያየት ከተሰጠባቸው በኋላ በእጩነት እንዲቀርቡ ተደርጓል፡፡ በብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መሪነት ጸሎተ እግዝእትነ ማርያምና አቡነ ዘበሰማያትን በማድረስ አምስቱን አስመራጭ ኮሚቴ አባላትን በእጣ እንዲለዩ ተደርጓል፡፡ በዚሁ መሠረት የዕለቱ መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ዮናስ ቡራኬተጠናቋል፡፡

ጳጉሜን 1 ቀን 2004 ዓ.ም.

ጳጉሜን 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት በተካሄደው የጠቅላላ ጉባኤው ስብሰባ “በማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎት ጉዞ የአባላት ተሳትፎና የወደፊት ሁኔታ” በተመለከተ ጥናት የቀረበ ሲሆን በአባላት ሰፋ ያለ ውይይት ተካሂዷል፡፡ ከሰዓት በኋላ በቀጠለው ስብሰባም “ስልታዊ ለውጥ ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት ከማኅበረ ቅዱሳን ተልእኮና አቅም አንጻር” በሚል በዲ/ን ያረጋል አበጋዝና ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ጥናታዊ ጽሑፍ ቀርቦ በአባላት ውይይት ተደርጎበታል፡፡ በመጨረሻም የጽ/ቤት ግንባታ ሪፓርት ቀርቦ የመርሐ ግብሩ ፍጸሜ ሆኗል፡፡

ምሽት ላይ ጠቅላላ ጉባኤው በዋነኛነት ሁለት ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ የተወያየ ሲሆን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል እያከናወነ ያለውን ዘርፈ ብዙ ተግባራት ገለጻ ተደርጓል፡፡ ክፍሉም በገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ጋር በተያያዘ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ማእከላት የማበረታቻ ሽልማት ከ19.500.00 ብር በላይ አበርክቷል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፤

  • የደብረ ታቦር ማእከል ብር 5000.00
  • የሆሳእና ማእከል ብር 3000.00
  • የመቱ ማእከል ብር 2000.00
  • የደብረ ማርቆስ ማእከል ብር 3000.00
  • የሽሬ ማእከል ብር 2500.00
  • የአሰበ ተፈሪ ማእከል ብር 2000.00
  • የአርባ ምንጭ ማእከል ብር 2000.00 ተበርክቶላቸዋል፡፡

ይህ ስጦታ ሌሎችንም ማእከላት የሚያበረታታ በመሆኑ አገልግሎታቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ክፍሉ አሳስቧል፡፡

በቀጣይነት በጠቅላላ ጉባኤው የተሰየመውና ማኅበሩን ለአራት ዓመታት ሊመሩ የሚችሉ የሥራ አመራር አባላትን እንዲያቀርብ የተሰየመው አስመራጭ ኮሚቴ ማኅበሩን ሊመሩ ይችላሉ ያላቸውን አባላት ከጠቅላላ ጉባኤው አባላት የተጠቆሙትን ስም ዝርዝር በማሰባሰብ ለጠቅላላ ጉባኤው አቅርቦ በአባላቱ ሰፊ ውይይትና ግምገማ በማድረግ ከ39 እጩዎች መካከል 20 እጩዎችን ለጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ምርጫ እንዲቀርቡ አጽድቋል፡፡ ከ20ዎቹ አጩዎች መካከል የማኅበረ ቅዱሳን የጠቅላላ ጉባኤ የምርጫ ሥነ ሥርዓት ደንብ  አንቀጽ 8 ቁጥር 2 ንዑስ ፊደል ለ በሚያዘው መሠረት ከ20ዎቹ እጩዎች ጸሎት ተደርጎ በእጣ በመለየት 17ቱ እንደሚመረጡ በመግለጽ መርሐ ግብሩ ተጠናቀቀ፡፡

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም.

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት የማኅበረ ቅዱሳን የአራት ዓመት ስልታዊ እቅድ ረቂቅ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ኮሚቴው በዋነኛነት የማኅበሩ ርዕይ፣ ተልእኮና የማኅበሩ እሴቶች ፤የማኅበሩ ጥንካሬና ድክመቶች፣ መልካም አጋጣሚዎችና ስጋቶች እንዲሁም የማኅበሩ የውስጥ ጉዳዮችና ስትራቴጂያዊ ግቦችን በማካተት አቅርቧል፡፡

በተጨማሪም የማኅበሩ ቀጣይ አራት ዓመታት ወሳኝ ጉዳዮችና ግቦች ያሏቸውን የማኅበሩ ተቋማዊ አቅም ማሳደግ፣ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያድግ ማድረግ፣ የግቢ ጉባኤያት ተደራሽነትና ብቃት ማሳደግ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ዝግጁ ማድረግ፣ የአብነት ት/ቤቶችና ገዳማት ድጋፍ ቀጣይ የቤተ ክርስቲያን ችግር በሚፈታ መልኩ ማድረግ፣ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ለሁሉም ተደራሽ ማድረግ ዘላቂነቱን ማረጋገጥ በሚሉ ወሳኝ ጉዳዮች ላይ ሰፋ ያሉ ነጥቦች ቀርበዋል፡፡ በእያንዳንዳቸው ዋና ዋና ጉዳዮችም የአፈጻጸም ስልቶችን አስቀምጧል፡፡

ኮሚቴው የአራት ዓመት ስልታዊ እቅዱን ካቀረበ በኋላ ለአባላት በስልታዊ እቅድ ረቂቅ ላይ መካተት ነበረባቸው ያሏቸውን እንዲያቀርቡ በተጠየቀው መሠረት ማየትና መስማት የተሳናቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆችን ተጠቃሚ እንዲሆኑ በስልታዊ ረቂቅ አቅዱ ውስጥ እንዲካተት ጥያቄ ቀርቧል፡፡ በመቀጠልም አባላት በቡድን በመከፋፈል ውይይት አድርገዋል፡፡

ከሰዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብርም የማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ኮሚቴው ባቀረበው የማሻሻያ ረቂቅ መሠረት በመተዳደሪያ ደንቡ ሊሻሻሉ የሚገባቸው ያላቸውን በማሻሻል፣ መውጣት ያለባቸውን በማስወጣትና አዲስ መግባት አለባቸው ብሎ ያመነባቸውን በማካተት ያቀረበ ሲሆን መተዳደሪያ ደንቡን በማስመልክት የጠቅላላ ጉባኤው አባላት ያላቸውን አስተያየትና ማሻሻያ    በጽሑፍ ለኮሚቴው እንዲያቀርቡ ተደርጓል፡፡

በመጨረሻም ማኅበሩን ለቀጣይ አራት ዓመታት  የሚመሩ የሥራ አመራር ጉባኤ ምርጫ ማካሔድ ሲሆን አስመራጭ ኮሚቴው መድረኩን ተረክቧል፡፡ በአስመራጭ ኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ እሸቱ ታደሰ አማካይነት ኮሚቴው በተሰጠው ኀላፊነት መሠረት እጩዎችን ለማቅረብ የተጓዘበትን ሒደት በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ በቀረበው ማብራሪያም መሠረት  ከጠቅላላ ጉባኤው ተጨማሪ አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡ ከውይይቱ በኋላም ኮሚቴው   የ20 እጩዎችን ስም ዝርዝር አቅርቧል፡፡

ከምርጫው ቀደም ብሎም በእለቱ በጉባኤው ላይ ከብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት መካካል ብፁዕ አቡነ ዲሜጥሮስ የተባበሩት አረብ ኤምሬት ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ የሰሜን ምሥራቅ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ የደቡብና መካካለኛው አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተገኝተዋል፡፡

በዚህም መሠረት በእጩነት ከቀረቡት 20 እጩዎች መካከል በብፁዐን አበው ሊቃነ ጳጳሳት  ፀሎት ከተደረገ በኋላ በእጣ 17ቱ ተመርጠዋል፡፡ 3ቱ ደግሞ በተጠባባቂነት ተሰይመዋል፡፡

በዚህም መሠረት ፡

TAKLL2004 528

  • ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ ሰብሳቢ
  • ወ/ሪት ዳግማዊት ኃይሌ ምክትል ሰብሳቢ
  • ዲ/ን ሙሉዓለም ካሳ ጸሓፊ ሆነው ሲመረጡ በአባልነት ደግሞ፤
  • አቶ ውብሸት ኦቶሮ
  • አቶ ፋንታሁን ዋቄ
  • አቶ አዱኛ ማእምር
  • አቶ ካሳሁን ኃ/ማርያም
  • አቶ ባያብል ሙላቴ
  • አቶ ዳንኤል ገ/መድኅን
  • ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ
  • ዶ/ር ዳኝነት ይመኑ
  • አቶ አንተነህ ሰብስቤ
  • ዲ/ን ዋሲሁን በላይ
  • ዶ/ር ሳሙኤል ኃ/ማርያም
  • ወ/ሪት ገነት ከበደ
  • አቶ ታደሰ አሰፋ
  • አቶ ይላቅ አድማሱ

ለአራት ዓመታት ማኅበሩን ለማገልገል በሥራ አመራርነት ተመርጠዋል፡፡

ተጠባበቂ ሆነው የተመረጡት 3ቱ እጩዎች ደግሞ፤

  • ወ/ሪት ሂሩት በቀለ
  • ዲ/ን ዘመንፈስ ገ/እግዚእ
  • አቶ ዳንኤል ተስፋ ሆነዋል፡፡

የኤዲቶሪያል ቦርድ፡፡

  • ቀሲስ ዶ/ር አሸናፊ በየነ ሰብሳቢ
  • ዲ/ን አባይነህ ካሴ ም/ሰብሳቢ

ኦዲትና ኢንስፔክሽን፡፡

  • አቶ የሺዋስ ማሞ ሰብሳቢ
  • አቶ የትናየት ም/ሰብሳቢ ሆነው ሲመረጡ

አዲሱ የሥራ አመራር ኮሚቴም የማኅበሩን የሥራ አስፈጻሚ አባላትን በመሰየም ለጠቅላላ ጉባኤ አቅርበው አጸድቀዋል፡፡ በዚህም መሠረት

  • ዲ/ን ሙሉጌታ ኃ/ማርያም ዋና ጸሓፊ
  • ዲ/ን አንዱ አምላክ ይበልጣል ም/ዋና ጸሓፊና የሀገር ውስጥ ማእከላት ማስተባበሪያ ክፍል ሓላፊ
  • አቶ ግርማ ተሾመ ም/ዋና ጸሓፊ
  • ቀሲስ ዶ/ር ደረጀ ሺፈራው ትምህርትና ክፍል
  • ዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ የኅትመትና አሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል ኃላፊ
  • አቶ ግዛቸው ሲሳይ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ቦርድ ሰብሳቢ
  • አቶ መስፍን ጥላሁን የሙያ አገልግሎት ክፍል ኃላፊ
  • ዲ/ን ዘመንፈስ ገ/እግዚእ የልማት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ ሰብሳቢ
  • አቶ ዘላለም አያሌው የሰው ኃይል አስተዳደር ኃላፊ
  • ሲ/ር ጽዮን ደሳለኝ የውጭ ማእከላት ማስተባበሪያ ክፍል ኃላፊ
  • አቶ ከፍያለው መርጊያ እቅድ ዝግጅት ክፍል ኃላፊ
  • ዲ/ን ስንታሁ ደምሴ የፋናንስ ክፍል ኃላፊ
  • አቶ አክሊሉ ለገሰ የህዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ
  • ዲ/ን ዮሐንስ አድገህ የጥናትና ምርምር ማእክል ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሰይመዋል፡፡

አዲሱ ሥራ አመራር ኮሚቴ ወደ መድረክ እንዲወጣ በማድረግ ከጠቅላላ ጉባኤው ጋር የተዋወቁ ሲሆን ከቀድሞው የስራ አመራር ኮሚቴ ጋር በሕብረት ፎቶ ግራፍ በመነሳት መልካም የአገልግሎት ጊዜ እንዲሆን ተመኝተዋል፡፡ መርሐ ግብሩም በብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት ጸሎትና ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም.  ሌሊት በተካሔደው  የጠቅላላ ጉባኤው ቀጣይ ውይይት በቀኑ መርሐ ግብር የአራት ዓመት ስልታዊ እቅድ ረቂቅ ላይ የተካሔደውን የቡድን ውይይት ውጤት በየቡድኖቹ ሰብሳቢዎችና ጸሐፊዎች አማካይነት እንዲቀርቡ በማድረግ በጠቅላላ ጉባኤው ውይይት ተካሂዶበት ጸድቋል፡፡ በቀጣይነትም የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ዋና የአገልግሎት ክፍሎች ስለክፍሎቻቸው እንቅስቃሴ ለጠቅላላ ጉባኤው ግንዛቤ የማስጨበጥና አሁን ያሉበትን ደረጃ አቅርበዋል፡፡

የ10ኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ አቢይ ኮሚቴ የተሠጣቸውን ኀላፊነት ለመወጣት ያደረጉት ጥረት፤ ያጋጠሟቸው ችግሮችና ችግሮቹን ለመፍታት ያደረጉት ጥረት ያቀረቡ ሲሆን ዝግጅቱን ለማሳካት የገንዘብ፤ የቁሳቁስና የሃሳብ ድጋፍ ላደረጉ ድርጅቶችና ግለሰቦች ከፍተኛ ምስጋና በማቅረብ የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል፡፡

በመጨረሻም በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ማኅበሩ በማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ጣልቃ የማይገባና የማኅበሩ የሥራ አመራር፤ የሥራ አስፈጻሚ፤ የየማእከላት ሰብሳቢዎች፤ የኤዲቶርያል ቦርድ ጽ/ቤት፤ የኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ጽ/ቤት፤  መምህራን፤ የማኅበሩ ጋዜጠኞች የማንኛውም ፖለቲካ ድርጅት አባል እንዳይሆኑ የሚያግደውን መመሪያ በማብራራት ውይይት ተደርጓል፡፡ በአሉባልታ ላይ የተመሰረተውን ውዥንብር ለማጥራት ይመለከታቸዋል የተባሉ የማኅበሩ አባላት ሃሳባቸውንና አቋማቸውን እንዲገልጹ በማድረግ የተፈጠረውን ውዥንብር ለማጥራት ተችሏል፡፡ በዚህም መሠረት ማኅበሩ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ያጸደቀውን ከፖለቲካና ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በተያያዘ ያለውን አቋም ቀድሞ እንደነበረው እንዲቀጥል አጽንቷል፡፡ በመጨረሻም መርሐ ግብሩ እንደዛሬው ለከርሞው ያድርሰን በሚል ዝማሬ ታጅቦ 10ኛው ጠቅላላ ጉባኤ በድምቀት እንደተጀመረ በድምቀት ከሌሊቱ 9፡00 ስዓት ተጠናቋል፡፡