ግሽን ማርያም

የግማደ መስቀሉ መገኛ!

መስከረም ፳ ቀን ፳፻፲፭ ዓመተ ምሕረት

በሀገራችን ኢትዮጵያ በወሎ ክፍለ ሀገር አምባሰል አውራጃ የሚገኘው ታላቁ የግሸን ማርያም ደብር የግማደ መስቀሉ መገኛ በመሆኑ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ትልቅ ተስፋና መመኪያ ነው፡፡ መስቀል የክርስትናችን መገለጫ፣ የብርሃናችን ዐምድ እንዲሁም የሰላማችን መገኛ ነውና፡፡

የከበረ ግማደ መስቀሉ በቅድስት ዕሌኒ ተገኝቶ በታላቅ ቤተ መቅደስ በጎልጎታ በክብር ከተቀመጠበት ዘመን ጀምሮ እንደ ፀሐይ እያበራ፣ ድውይ እየፈወሰ፣ አጋንንት እያስወጣ፣ ልዩ ልዩ ተአምራትን እያደረገ፣ ሙት እያነሳና ዕውር እያበራ በነበረበት ጊዜ ከኃያላን ነገሥታት መካከል የፋርስ ንጉሥ መስቀሉን ማርኮ ፋርስ ወስዶ አስቀመጦት ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ የኢየሩሳሌም ምእመናን የሮማውን ንጉሥ ሕርቃልን ዕርዳታ በመጠየቅ እንዲመለስ አድርገው በኢየሩሳሌም ብዙ ዘመን ሲኖር እንደገና ኃያላን ነገሥታት ይህን መስቀል ለመውሰድ ጠብ በመፍጠራቸው የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በአንድ ቦታ ሊቀመጥ አልቻለም፡፡

በዚህ ጊዜ የኢየሩሳሌም፣ የቁስጥንጥንያ፣ የአንጾኪያ፣ የኤፌሶን፣ የአርማንያ፣ የግሪክ፣ የእስክንድርያና የመሳሰሉት የሃይማኖት መሪዎች ጠቡን ለማብረድ ችለው ነበር፡፡ ሆኖም ግን በኢየሩሳሌም የሚገኘውንም የጌታችን የክርስቶስን መስቀል ከ፬ በመክፈል በዕጣ አድርገው በስምምነት ለመካፈል ተገደዋል፡፡ ከሌሎቹ ታሪካዊ ንዋያት ጋር በየሀገራቸው በመውሰድ በክብር አስቀመጠውታል፡፡ የቀኝ ክንፉ የደረሰው ለአፍሪቃ ስለነበር ከታሪካዊ ንዋያተ ቅድሳት ጋር በግብጽ የሚገኘው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ተረክቦ ወስዶ በክብር አስቀመጦት ነበር፡፡

ግማደ መስቀሉም ለብዙ ዘመን በእስክንድርያ ሲኖር በግብጽ ያሉ እስላሞች እየበዙ ኃይላቸው እየጠነከረ በሔዳቸው ምክንያት በእስክንድርያ የሚኖሩትን ክርስቲያኖች ሥቃይ አጸኑባቸው፡፡ በዚያን ጊዜም ክርስቲያኖቹም አንድ ሆነው መክረው ለኢትዮጵያዊ ዓፄ ዳዊት እንዲህ የሚል መልዕክት ልከው ነበር፤ ‹‹ንጉሥ ሆይ! በዚህ በግብጽ ያሉ እስላሞች መከራ አጽንተውብናልና ኃይልህን አንሥተህ አስታግሥልን›› ዳግማዊ ዓፄ ዳዊትም ለመንፈሳዊ ኃይማኖት ቀንተው የክርስቶስ ፍቅር አስገድዶአቸው ፳ ሽህ ሠራዊት አስከትለው ወደ ግብፅ ዘመቻ አደረጉ፡፡ በግብጽ ያሉ ኃያላን ፈርተውና ተሸብረው ነበር፡፡ በዚያን ጊዜም ንጉሡ ዳግማዊ ዳዊትም እንዲህ የሚል መልእክት ለእስላሞች ላከው ነበር፤ ‹‹በተፈጥሮ ወንድሞቻችሁ ከሆኑት ክርስቲያኖች ጋር ካልታረቃችሁ ሀገራችሁን መጥቼ አጠፋዋለሁ፡፡›› የንጉሡ መልእክት ለእስላሞች እንደደረሳቸው ፈርተው እንደጥንቱ በየሃይማኖታቸው ጸንተው በሰላም እንዲኖሩ ከክርስቲያን ወንድሞቻቸው ጋር ታርቀዋል፡፡

ይህንንም ዳግማዊ ዳዊት በሰሙ ጊዜ በጉዳዩ ንጉሡ በጣም ደስ ብሏቸው ነበር፤ እግዚአብሔርንም አመስግነዋል፡፡ በወቅቱም በግብጽ የሚኖሩ ክርስቲያኖችም ደስታቸውን ለመግለጽ ከ፲፪ ሽህ ወቄት ወርቅ ጋር ለኢትዮጵያዊው ንጉሥ  ዳግማዊ ዳዊት በደብዳቤ አድርገው እንደላኩላቸው ታሪካቸው ላይ ተገልጿል፡፡ ነገር ግን ንጉሡ ደብዳቤውን ተመልከተው ደስ ቢላቸውም ወርቁን መልሰው በመላክ እንዲህ የሚል ደብዳቤ ጽፈው ልከዋል፤ ‹‹በግብጽ የምትኖሩ የክርስቶስ ተከታዮች ሆይ እንኳን ደስ አላችሁ! የላካችሁልኝን ፲፪ ሽህ ወቄት ወርቅ መልሼ ልኬላችኋለሁ፤ የእኔ ዓላማ ወርቅ ፍለጋ አይደለም፤ የክርስቶስ ፍቅር አስገድዶኝ በተቻለኝ ችግራችሁን ሁሉ አስወገድኩላችሁ፡፡ አሁንም የምለምናችሁ በሀገሬ በኢትዮጵያ ረኃብ፣ ቸነፈርና ድርቅ ስለወረደብኝ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰቅሎበት የነበረውን መስቀልና የቅዱሳንን አጽም ከሌሎች ክቡራን ዕቃዎች ጋር እንድትልኩልኝ ነው፡፡››

በእስክንድርያም ያሉ ምእመናን ይህ መልዕክት እንደደረሳቸው ከሊቃነ ጳጳሳቱና ከኤጲስ ቆጶሳቱ ጋር ውይይት በማድረግ ‹‹ይህ ንጉሥ ታላቅ ክርስቲያን ነው፡፡ ስለዚህ ልቡን ደስ እንዲለው የፈለገውን የጌታችንን ግማደ መስቀል ከቅዱሳን አጽምና ንዋየ ቅድሳት ጋር አሁን በመለሰው ፲፪ ወቄት ወርቅ የብር፣ የንሐስ፣ የመዳብና የወርቅ ሣጥን አዘጋጅተን እንላክለት›› ብለው ተስማሙ፡፡ በክብር በሥነ ሥርዓት በሠረገላና በግመል አስጭነውም ስናር ድረስ አምጥተው ባስረከቡአቸው ጊዜ በእጃቸው እያጨበጨቡና በግንባራቸው እየሰገዱ በክብር በደስታ ተቀብለዋቸዋል፡፡ ይህም የሆነው መስከረም ፳፩ ቀን ነው፡፡ በኢትዮጵያም ታላቅ ብርሃን ሌት ተቀን ፫ ቀን ሙሉ ሲበራ ሰነበተ፡፡

ግማደ መስቀሉ ወደ መካከለኛው ኢትዮጵያ ሳይደርስ በድንገት ዓፄ ዳዊት ስናር ላይ በማረፉቸው ግማደ መስቀሉም የግድ በዚያው በስናር መቆየት ነበረበት፡፡ ከዚህ በኋላ የሟቹ የዳግማዊ ዳዊት ልጅ ዘርዐ ያዕቆብ እንደነገሡ ወደ ስናር ሔደው ግማደ መስቀሉን ከሌሎቹ ንዋያተ ቅድሳት ጋር አምጥተው በመናገሻ ከተማቸው በደብረ ብርሃን ላይ ቤተ መቅደስ ሠርተው ለማስቀመጥ ሲደክሙ አንድ ራእይ እንዳዩ ተገልጿል፡፡ በዚያም ጊዜ ‹‹ወዳጄ ዘርዐ ያዕቆብ ሆይ፥ መስቀሌን በመስቀልኛ ቦታ ላይ አስቀምጥ›› የሚል ትእዛዝም ተቀብለው  በኢትዮጵያ አውራጃዎች ሁሉ መስቀለኛ ቦታ በመፈለግ ከብዙ ቦታ ላይ አስቀምጠውት ነበር፡፡ ለምሳሌ በሸዋ በደርሄ ማርያም፣ በመናገሻ ማርያም እንዲሁም በወጨጫ መስቀሉን አሳርፈውት ነበር፡፡ ነገር ግን የመጨረሻውን ቦታ ያላገኙ በመሆኑ በራእይ እየደጋገገመ ‹‹መስቀሌን በመስቀልኛ ቦታ ላይ አስቀምጥ›› እያለ ይነግራቸው ነበር፡፡

ዓፄ ዘርዐ ያዕቆብም ለሰባት ቀናት ያህል ሱባዔ በመግባታቸው ‹‹መስቀለኛውን ቦታ የሚመራህ ዓምድ ብርሃን ይመጣል›› የሚል መልእክት ሊደርሳቸው ችሏል፡፡ እርሳቸውም ከዚያ እንደወጡ መስቀለኛውን ቦታ የሚመራ ዓምደ ብርሃን ከፊታቸው መጥቶ ቆሞ በዚያ መሪነት ወደ ወሎ ክፍለ ሀገር አምባሰል አውራጃ ውስጥ ግሸን ከምትባል ስፍራ መርቶ አደርሷቸዋል፡፡ በርግጥም ይህች ግሽን የተባለች አምባ ጥበበኛ ሰው እንደቀረፃት የተዋበች መስቀልኛ ቦታ ሁና ስለአገኟት የልባቸው ደርሶ ደስ ብሏቸው ነበር፡፡ በዚያችም አምባ ታላቅ ቤተ መቅደስ ሠርተው መስቀሉንና ሌሎች ንዋያተ ቅድሳቱን በየማዕረጋቸው የክብር ቦታ መድበው አስቀምጠዋቸዋል፤ ዘመኑም በ፲፬ኛው ክፍለ ዘመን ነበር፡፡

በሀገራችን ከመጡት ንዋያተ ቅዱሳት ውስጥም ከእስክንድርያ ሀገር ከመስቀሉ ጋር በልዩ ልዩ ሣጥን ተቆልፈው የመጡትም ዝርዝር፣ ጌታ በዕለተ ዓርብ ለብሶት የነበረው ቀይ ልብስ፣ ከሮም የመጣ ከለሜዳው፣ ከአፍርጌ ሀገር የመጣው ሐሞት የጠጣበት ሰፍነጉ፣ ዮሐንስ የሳለው የኲርዓተ ርእሱ ሥዕል፣ ቅዱስ ሉቃስ የሣላቸው የእመቤታችን ሥዕሎች፣ የበርካታ ቅዱሳን አጽምና በኢየሩሳሌም ውስጥ ከልዩ ልዩ ቅዱሳት መካናት የተቆነጠረ የመሬት አፈር፣ የዮርዳኖስ ውኃ እንዲሁም በግብጽ ውስጥ ከሚገኙት ታላላቅ ገዳማት የተቆነጠረ አፈር ናቸው፡፡

በወቅቱም የእነዚህንም ዝርዝር ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለግሸን ካህናት መስከረም ፳፩ ቀን ፩ ሽህ ፬፻፵ ዓ.ም. ላይ ተናግረዋል፡፡ በመጀመሪያም ይህ ግማደ መስቀል ከእስክንድርያ ስናር የገባው መስከረም ፲ ቀን ነው፡፡ ኢትዮጵያም የገባው ደግሞ በመስከረም ፳፩ ቀን ነው፡፡ አሁንም በመጨረሻ ግሸን አምባ የገባው መስከረም ፳፩ ቀን ሲሆን ቤተ መቅደስ ተሠርቶ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረውና አፄ ዘርዐ ያዕቆብ ለመላው ኢትዮጵያ በጽሑፍ በመዘርዘር የገለጹበትም መስከረም ፳፩ ቀን ነው፡፡

በዚያም ዘመን የነበሩት የኢትዮጵያ ጳጳሳት የነበሩት አባ ሚካኤልና አባ ገብርኤል የተባሉ ከንጉሡ ከዓፄ ዘርዐ ያዕቆብ ጋር ሆነው የምሕረት ቃል ኪዳን ለመቀበል በዚህች በግሸን ደብር ሱባዔ ገብተዋል፡፡ በሱባዔአቸውም በመጨረሻ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ ‹‹ይህች ቦታ እኔ ተወልጄ ያደኩባትን ኢየሩሳሌምን ትሁን፤ የተሰቀልኩባትን ቀራንዮን ትሁን፤ የተቀበርኩባትንም ጎልጎታን ትሁን፤ በዚች ቦታ እየመጣ የሚማጸነውን ሁሉ ቸርነቴ ትጎበኘዋለች፤ ጠለ ምሕረቴም አይለይባትም፤  ከሩቅም ሆነ ከቅርብ መጥቶ የተቀበረ ኢየሩሳሌም እንደተቀበረ ይሁን›› የሚል የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡  በዚያ ለተገኙት ምእመናን ሁሉ በጽሑፍ ካሰሙ በኋላ ጠቅላላ የግማደ መስቀሉንና የሌሎቹን ታሪካውያን ንዋያተ ቅዱሳትንም ዝርዝር ታሪክ የያዘውን መጽሐፈ ጤፉት ብለው ሰይመው ድንጋጌውን ሁሉ በመዘርዘር ለግሸን እግዚአብሔር አብ ሰጥተዋል፡፡

ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብም በዚህ ብቻ ሳይወሰኑ ዕሌኒ እኅታቸው  የተሰኘችው በእመቤታችን ማርያም ስም ቤተ መቅደስ እንድትሠራ አዘው የእመቤታችን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን አጠገብ  አሳንጻ ጥር ፳፩ ቀን ቅዳሴ ቤቱ ተከብሯል፡፡ ዓፄ ዘርዐ ያዕቆብም ይህችንደብር ደብረ ከርቤ ብለው በመሰየም እንኳንስ ሰው የሠገረ ቆቅ፤ የበረረ ወፍ እንዳይገደል ዳሯ እሳት መካከል ገነት ትሁን ብለው ደንብና ሥርዓት በጤፉት መጽሐፍ ውስጥ አጽፈዋል፡፡

ከዚያም የሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም ሲመሠረት ሐይቅ ‹‹ደብረ ነጎድጓድ›› ተብሎ ሲሰየም ግሸን የሐይቅ ግዛት በመሆኑ ‹‹ደብረ ነጎድጓድ›› ተብሏል፡፡ በ፲፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት የክርስቶስ ግማደ መስቀሉ ግሸን ገብቶ ሲቀመጥ ‹‹ደብረ ከርቤ›› ተብሎ ተሰየመ፡፡ ከዐፄ ድልናአድ ዘመን ፰፻፹፮ዓ.ም እስከ ፲፩ኛው ክፍለ ዘመን በአሁኑ ስያሜ ‹‹ደብረ ከርቤ›› በመባል ይታወቅ ነበር። በዚህ ጊዜ የነበረው የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መምህረ እስራኤል ዘደብረ ከርቤ ይባል ነበር። በመጨረሻም ከደብረ ከርቤ ግሸን ማርያም ተብሎ ተሰይሟል፡፡

ይህ ደብር የተቀደሰ በመሆኑ ከበረከቱ ለማካፈል ወደ በግሸን ማርያም ምእመናን በየዓመቱ መስከረም ፳፩ ቀን እየሄዱ በዓሉን ያከብራሉ፡፡

አምላካችን እግዚአብሔር ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፤ አሜን፡፡

ምንጭ፡- መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መጽሐፈ ጤፉት