‹‹ጌትነቱን ገለጠ፤ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ፤›› /ዮሐ. ፪፥፲፩/፡፡

%e1%8c%88%e1%88%8a%e1%88%8b

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ጥር ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የበዐላት አከባበር ቀመር ከበዓለ ልደት፣ ግዝረት እና ጥምቀት ቀጥሎ ቃና ዘገሊላ ይከበራል፡፡  ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ለማዳን ወደዚህ ዓለም በመጣበት ወቅት ልዩ ልዩ ድንቅ ተአምራትን አድርጓል፡፡ ከእነዚህ መካከልም በቃና ዘገሊላ በሰርግ ቤት ተገኝቶ ያደረገው ተአምር ተጠቃሽ ነው፡፡

ይህንንም ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ እንዲህ ጽፎታል፤ ‹‹በሦስተኛው ቀን በገሊላ ቃናርግ ኾነ፡፡›› ምን በተደረገ በሦስተኛው ቀን የሚል ጥያቄ በኹላችንም አእምሮ እንደሚመላለስ አያጠያይቅም፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማየ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ ጥር ፲፩ ቀን ተጠምቆ ሳይውል ሳያድር ዕለቱን ገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ጾሞ፤ ዲያብሎስን ድል ነስቶ፤ መዋዕለ ጾሙን ፈጽሞ፤ ለእኛም ዲያብሎስን ደል የምንነሳበትን መንገድ አሳይቶ ከገዳመ ቆሮንቶስ መልስ ደቀ መዛሙርቱን መረጠ፡፡

ከጥር ፲፩ እስከ የካቲት ፳ ቀን ያለው ጊዜ ፵ ቀን ይኾናል፡፡ ጌታችን መዋዕለ ጾሙን የካቲት ፳ ቀን ፈጽሞ በወጣ በሦስተኛው ቀን በገሊላ አውራጃ ቃና በተባለች መንደር ሰርግ ኾነ፡፡ በዚህ ሰርግ ብዙ ሰዎች መታደማቸውን ወይን ጠጁ ማለቅ ያስረዳናል፡፡ የተጠሩት ሰዎች ብዙ ለመኾናቸው ባሻገር ብዙዎችን መመገብ የሚችል አምላክ በሰርግ ቤት መጠራቱ ልዩ ዕለቱን ያደርገዋል፡፡ በዚህ ሰርግ ከሰዎች በተጨማሪ ሦስት አካላት ተጠርተዋል፡፡

፩. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ

‹‹ወጸውዕዎ ለእግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ጌታ ኢየሱስንም ጠሩት›› /ዮሐ.፪፥፪/፣ ተብሎ እንደ ተጻፈ እናትን ጠርቶ ልጅን መተው ተገቢ አይደለምና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ጠርተው ልጇን ኢየሱስ ክርስቶስንም ጠርተውታል፡፡ ይህም ፍጹም ሰው መኾኑን ያስረዳል፡፡ ጌታችን እንደ ሰውነቱ ወደ ሰርግ ቤት ተጠራ፤ እንደ አምላክነቱ ተአምራቱን በማሳየት ጌትነቱን፣ አምላክነቱን ገለጠ፡፡

ከሚደሰቱት ጋር መደሰት፤ ከሚያዝኑት ጋር ማዘን ተገቢ መኾኑን መድኀኒታችን ክርስቶስ በተግባር አስተማረን፡፡ በቃና ዘገሊላ ከሰርግ ቤት እንደ ሔደው በአልዓዛር ቤት ለለቅሶ መገኘቱን ልብ ይሏል፡፡ ወደ ሰርግ ቤት የሔደው በደስታ ነበር፡፡ ‹‹ሖረ ኢየሱስ በትፍሥሕት ውስተ ከብካብ እንዘ ይገብር ተአምረ ወመንክረ በውስተ አሕዛብ፤ ኢየሱስ በአሕዛብ ፊት ተአምራትንና ድንቆችን እያደረገ በደስታ ወደ ሰርግ ሔደ፤›› በማለት ቅዱስ ያሬድ እንደ ገለጠው፡፡

ጌታችን ወደ አልዓዛር ቤት ሲሔድ ግን በኀዘን ውስጥ ኾኖ ነበር፡፡ ‹‹ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እርሷ (ማርታ) ስታለቅስ ባየ ጊዜ በልቡ አዘነ፤ በራሱም ታወከ (ራሱን ነቀነቀ – የኀዘን ነው) ዕንባውን አፈሰሰ፡፡ አይሁድምምን ያህል ይወደው እንደ ነበር እዩ› አሉ፤›› እንዳለ ወንጌላዊው /ዮሐ.፲፩፥፴፫-፴፰/፡፡

ጌታችን ‹‹አምላክ ነኝና ከሰርግ ቤት አልሔድም፤ ከልቅሶም ቤትም አልገኝም፤›› አላለም፡፡ ከዚህም ጌታችን ከኀጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ እንደ ሠራ፤ የሰውን የተፈጥሮ ሕግ እንዳከበረ እና እንደ ፈጸመ እንረዳለን፡፡ በመደሰት እና በማዘን ፍጹም ሰው መኾኑን፤ በሰርጉ ቤት ውኀውን የወይን ጠጅ በማድረግ፤ እንደዚሁም አልዓዛርን ከአራት ቀናት በኋላ ከሞት በማስነሣት ደግሞ ፍጹም አምላክ መኾኑን አስረዳን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ነውና በሰርግ ቤት የጎደለውን መላ፡፡ አምላክ ነውና የሞተውን አልዓዛርን ‹‹መግነዝ ፍቱልኝ? መቃብር ክፈቱልኝ? ሳይል›› ከሞት እንዲነሣ አደረገ፡፡

‹‹ወሶበ ኀልቀ ወይኖሙ ወትቤሎ እሙ ወይንኬ አልቦሙ፤  የወይን ጠጅ ባለቀባቸው ጊዜም እናቱ (እመቤታችን)የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም› አለችው›› /ዮሐ.፫፥፫/፡፡ እርሱም ‹‹አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም፤›› አላት፡፡ ይኸውም ‹‹ያልሽውን ልፈጽም ነው ሰው የኾንኩት፤ ያልሽኝን እንዳልፈጽም ከአንቺ ጋር ምን ጠብ አለኝ?›› ማለት ነው፡፡ ‹‹ጊዜዬ ገና አልደረሰም›› የሚለው ቃልም ጌታችን ሥራውን ያለ ጊዜው እንደማይፈጽመው ያሳያል፡፡ ‹‹ለእግዚአብሔር የሥራ ጊዜ አለው፤›› እንዲል /መዝ.፻፲፰፥፻፳፮/፡፡

በሌላ መልኩ ‹‹ጊዜዬ ገና አልደረሰም›› የሚለው ቃል እግዚአብሔር አምላካችን ይህን አድርግ ብሎ በግድ ማንም ሊያዝዘው የማይቻለውና በራሱ ፈቃድ የወደደውን ዂሉ የሚያደርግ፤ ቢፈልግ የሚያዘገይ፣ ሲፈልግ ደግሞ በዐይን ጥቅሻ በፈጠነ መልኩ መፈጸም የሚችል፤ በራሱ ፈቃድ እንጂ በሰምች ፈቃድ የማይመራ አምላክ መኾኑን ያስተምረናል፡፡ ‹‹ፈቃድህ በሰማይ እንደ ኾነች እንዲሁ በምድር ትኹን›› ብላችሁ ለምኑኝ ያለውም ለዚህ ነው፡፡

የወይን ጠጁም ሙሉ ለሙሉ አላላቀም ነበር፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ያለውን ቢያበረክተው ተአምራቱን አናደንቅም የሚሉ ይኖራሉና ፈጽሞ ጭልጥ ብሎ እስከሚያልቅ ድረስ መጠበቅ እንደሚገባ ሲያስረዳ ‹‹ጊዜዬ ገና አልደረሰም›› አለ፡፡ ሰው ቢለምን፣ ቢማልድም እግዚአብሔር በእርሱ ፈቃድ ጊዜው ሲደርስ ነው የሚፈጽመው፡፡ ምልጃው አልተሰማም፤ ተቀባይነት አላገኝም ማለት ግን አይደለም፡፡ ተቀባይነት ያገኘ መኾኑ የሚታወቀው በመደረጉ ነውና፡፡ ተማላጅነት የአምላክ፤ አማላጅነት ደግሞ የፍጡራን መኾኑን ጌታችን በዚህ ሰርግ ቤት አስተምሯል፡፡ ጌታችን በሰርግ ቤት ባይገኝላቸው ኖሮ ሰዎቹ ምን ያህል ኀፍረት ይሰማቸው ይኾን? የእርሱ እንደዚሁም የእናቱ በሰርጉ ቤት መገኘት ለባለ ሰርጉና ለታዳሚዎች ሙላት ነበር፡፡ እርሱ ባይኖር የሰርጉ ቤት ከደስታ ይልቅ በኀዘን ሊሞላ ይችል እንደ ነበር ምንም ጥርጥር የለውም፡፡

አማላጅ ያስፈለገውም እርሱ የማያውቀው ምሥጢር ኖሮ፤ ሥራውን የሚሠራውም በስማ በለው ኾኖ አይደለም፡፡  ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር ይታወቅ ዘንድ እና የሰው ልጆችን ከችግር የሚያወጣበት መንገዱ ብዙ መኾኑን ለማስረዳት ነው እንጂ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሚዜዎችን ‹‹ኵሎ ዘይቤለክሙ ግበሩ፤ ያዘዛችሁን ዂሉ አድርጉ፤›› ማለቷ ‹‹አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ?›› የሚለው የጌታችን መልስ እሺታን (ይኹንታን) የሚገልጽ ቃል መኾኑን ያስረዳል፡፡

ጌታችንም ‹‹ውኀ ቅዱና ጋኖችን ምሏቸው›› ባላቸው ጊዜ በታዘዙት መሠረት ውኃውን ቀድተው ጋኖችን ሞሏቸው፡፡ ውኃውንም ክብር ይግባውና በአምላካዊ ችሎታው ወደ ወይን ጠጅ ለወጠው፤ ለአሳዳሪውም ሰጠው፡፡ አሳዳሪው የወይን ጠጅ የኾነውን ውኀ ቀምሶ አደነቀ፤ ከወዴት እንደ መጣ ግን አላወቀም፡፡ ድንቅ በኾነ አምላካዊ ሥራ እንደ ተለወጠም አልተረዳም፡፡ ያን ምሥጢር የሚያውቀው ባለሰርጉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ውኀውን የቀዱ ሰዎች ናቸውና፡፡ ታዳሚዎችም ‹‹ሰው ዂሉ የተሻለውን ወይን አስቀድሞ ያቀርባል፤ በኋላም ተራውን የወይን ጠጅ ያቀርባል፡፡ አንተስ መናኛውን ከፊት አስቀድመህ ያማረውን ከኋላ ታመጣለህን?›› በማለት አደነቁ፡፡

ቀድሞም የአምላክ ሥራ እንደዚህ ነው፤ ብርሃን ከመፍጠሩ አስቀድሞ ጨለማን ፈጥሯል፤ ከጨለማ ቀጥሎ ‹‹ብርሃን ይኹን!›› በማለት ብርሃንን ፈጥሯል፡፡ መጀመሪያ ብርሃን ተፈጥሮ ኋላ ጨለማ ቢፈጠር ይከብድ ነበርና መጀመሪያ ፳፩ ፍጥረታት ፈጥሯል፡፡ በመጨረሻም በአርአያውና በአምሳሉ የሰው ልጅን ፈጥሯል፡፡ ናትናኤልንም፤- ‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ከዚህ የሚበልጥ ታያለህ›› ብሎታል፡፡ ይህንን ማለቱም የእግዚብሔር ሥራ እየቆየ ውብ፣ ያማረ መኾኑን ያመለክታል፤ ሰው ግን ‹‹የወደዱትን ቢያጡ ያጡትን ይቀላውጡ›› እንዲሉ ጥሩ ነው የሚለውን ነገር ያስቀድማል፤ ያ ሲያልቅበት ደግሞ የናቀውን መፈለግ ይጀምራል፡፡

ተራውን ከፊት፣ ታላቁን ከኋላ ማድረግ የእግዚአብሔር ልማዱ ነው፡፡ ለሰው ልጅ በመጀመሪያ የተሰጠው የሚያልፈው ዓለም ነው፤ በኋላም የማያልፈው መንግሥተ ሰማያት ይሰጠዋል፡፡ ሰው መጀመሪያ ይሞታል፤ በመጨረሻ ትንሣኤ አለው፡፡ ሰው መጀመሪያ ሲወለድ ርቃኑን ነው፤ በኋላ የጸጋ ልብስ ይለብሳል፤ ሀብታም ይኾናል፡፡ ሰው ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ዓለምን የሚያገኛት፣ የሚተዋወቃት በልቅሶ ነው፤ በኋላ ግን ይደሰታል፡፡ ተመልሶ በኀሣር፣ በልቅሶ ወደ መቃብር ይወርዳል፡፡ በደስታ ‹‹መቃብር ክፈቱልኝ? መግነዝ ፍቱልኝ?›› ሳይል ይነሣል፡፡ ይህን የአምላክ ሥራም አድንቆ መቀበል እንጂ መቃወም አይችልም፡፡

፪. እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም

‹‹ወሀለወት ህየ እሙ ለእግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስየጌታ እናት ከዚያ ነበረች፤›› እንዲል፡፡ የተገኘችውም እንዲያው ዝም ብሎ አይደለም፡፡ በደግ ሰው ልማድ ተጠርታ እንጂ፡፡ ይህም እመቤታችን በማኅበራዊ ሕይወት የነበራትን ተሳትፎ እና በሰዎች ዘንድ የነበራትን ክብር ያመለክታል፡፡ በሌላ መልኩ በቤተ ዘመድ ልማድ ማንኛውም ዘመድ እንደ ተጠራው ዂሉ እርሷም በገሊላ በነበሩት ሰዎች ዘንድ ታላቅና ቤተ ዘመድ በመኾኗ በዚህ ሰርግ ተጠርታ ነበር፡፡ የተገኘችበት ሰው ሰውኛው ምክንያት ይህ ቢኾንም በዚያ ሰርግ ቤት ማንም ሊሠራው የማይችል የሥራ ድርሻ ነበራት፡፡

ይህ በሰዎች ዘንድ የማይታወቅ በእግዚአብሔርና በእርሷ መካከል ያለ አማላጅነት ነው፡፡ ይኸውም የጎደለውን መሙላት ለሚችል ውድ ልጇ የጎደለውን እንዲሞላ ማማለድ ነው፡፡ እመቤታችን ከሰው ልጆች የተለየች ክብርት፣ ቅድስት፣ ንጽሕት፣ ልዩ በመኾኗ የምታውቀው ምሥጢርም ከሰው የተለየ ነው፡፡ ‹‹ወእሙሰ ተዐቀብ ዘንተ ኩሎ ነገረ ወትወድዮ ውስተ ልባ፤ ማርያም ግን ይህንን ዂሉ ትጠብቀው፣ በልቧም ታኖረው ነበር፤›› /ሉቃ.፪፥፲፱/ የሚለው ቃልም ድንግል ማርያም አምላክን በመውለዷ ከሰው ልጆች የራቀ ምሥጢር እንደ ተገለጠላት ያስረዳል፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ‹‹ጸጋን የተሞላሽ›› በማለት የገለጠው ለእርሷ የተሰጠው ባለሟልነት ልዩ መኾኑን ለማስረገጥ ነው፡፡ ከዚህ የተነሣ በሰርጉ ቤት የምትሠራውን ሥራ በውል ታውቅ ነበር፡፡

 ፫. ቅዱሳን ሐዋርያት

መምህርን ጠርቶ ደቀ መዝሙርን መተው ተገቢ አይደለምና፤ ደቀ መዛሙርቱ ከመምህራቸው ከክርስቶስ ጋር አብረው በሰርግ ቤት ተገኝተው ተአምራቱን ተመልክተዋል፤ በተደረገው ተአምርም አምላክቱን አምነዋል፡፡ ሐዋርያት ከዋለበት የሚውሉ፤ ከአደረበት የሚያድሩ፤ ተአምራት የማይከፈልባቸው፤ ወንጌሉን ለማስተማር የተመረጡ ናቸውና፡፡  ምክንያቱም አየን ብለው እንጂ ሰማን ብለው ቢያስተምሩ አይታመኑምና፡፡

የሐዋርያት በሰርጉ ቤት መገኘትም ካህናት በተገኙበት ዕለት ሥርዓተ ጋብቻን መፈጸም ተገቢ መኾኑን ያስገነዝባል፡፡ በሰርግ ቤት የካህናት መገኘት እና ቡራኬ መስጠት አስፈላጊ ነውና፡፡ በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፳፬ የተገለጸውም ይህ ትምህርት ነው፤ ‹‹ወማዕሰረ ተዋሰቦሶ ኢይትፌጸም ወኢይከውን ዘእንበለ በሀልዎተ ካህናት ወጸሎት ዘላዕሌሆሙ፤ የጋብቻ አንድነት ካህናት ቢኖሩ እንጂ ያለ እነርሱ አይጸናም፡፡ እነርሱ ጸሎት ሲያደርጉ እንጂ ያለ ጸሎት አይፈጸምም፤›› እንዲል፡፡ በጥንተ ፍጥረት ‹‹ሰው ብቻውን ይኾን ዘንድ መልካም አይደለም ረዳት እንፍጠርለት፤›› /ዘፍ.፪፥፲፱/ በማለት የተናገረ አምላክ ጋብቻ በካህናት ቡራኬና ጸሎት መከናወን እንደሚገባው ሲያስተምረን በቃና ዘገሊላው ሰርግ ቅዱሳን ሐዋርያትን ይዞ ተገኝቷል፡፡

በአጠቃላይ የቃና ዘገሊላ ሰርግ እና በሰርጉ ላይ የታዩ ተአምራት ምልጃዎች ዂሉ ሌላ ምሥጢርንም ያዘሉ ናቸው፡፡ እመቤታችን ‹‹የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም›› በማለት መናገሯ ሕዝብህን (ምእመናንን) ‹‹ደምህን አፍሰህ፣ ሥጋህንርሰህ አድናቸው›› ማለቷ ሲኾን፣ ይህም ‹‹ወይን›› በተባለው የልጇ የክርስቶስ ደም ቤዛነት ዓለም ይድን ዘንድ እመቤታችን ያላትን የልብ መሻት ያስገነዝባል፡፡ ‹‹ጊዜዬ ገና አልደረሰም›› የሚለው የጌታ ምላሽም ደሙ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ የሚፈስበት ጊዜ ገና መኾኑን ያመላክታል፡፡ በሰርግ ቤት የተገኘው በሥጋው መከራ ከመቀበሉ አስቀድሞ ነውና፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት በረከት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡