የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ተተኪ መምህራንን አስመረቀ

ነሐሴ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በሐዋሳ ማእከል

Hawasa

በማኅበረ ቅዱሳን የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ከልዩ ልዩ ግቢ ጉባኤያት በመመልመል ለአንድ ወር ያሠለጠናቸውን ፶፮ የደረጃ ሁለት ተተኪ መምህራን የሲዳማ፣ ጌድዮ፣ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣ የሐዋሳ ማእከል አባላት፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን በተገኙበት በሐዋሳ ደብረ ታቦር ቅዱስ ሩፋኤል የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም ነሐሴ ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም አስመረቀ፡፡

በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ጉባኤ አባ ሀብተ ማርያም ‹‹እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራል›› /ዮሐ.፫፥ ፴፬ / በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

የዋናው ማእከል ተወካይ ዲ/ን ሙሉጌታ  ኃይለ ማርያም ባስተላለፉት መልእክት ምሩቃኑ ለአገልግሎት እንዲተጉና የተጣለባቸውን አደራ በትጋት እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

ሠልጣኞቹ ከወሰዷቸው ኮርሶች መካከል ትምህርተ ሃይማኖት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ሥርዓትና ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ ነገረ ቅዱሳን፣ ትምህርተ ክርስትና፣ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር፣ ሐዋርያዊ ተልእኮ፣ ትምህርተ አበው፣ ነገረ ማርያምና ኦርቶዶክሳዊ የጾታ ትምህርት የሚገኙ ሲኾን በተጨማሪም ስለ ኦርቶዶክሳውያን መዝሙራትና ሐራ ጥቃዎች በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ላይ እያደረሱት ያለውን የተሐድሶ እንቅስቃሴ የሚመለከት የግንዛቤ ማስጨበጫ ገለጻ ተደርጎላቸዋል፡፡

ሚዲያ ክፍላችን ያነጋገራቸው አንዳድ ምሩቃን በሥልጠናው ጠቃሚ ዕውቀት እንደቀሰሙበትና በርካታ ቁም ነገሮችን እንዳገኙበት ገልጸው ለወደፊቱም ‹‹የየማእከላቱ ክትትልና ድጋፍ እንዳይለየን›› ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

በመጨረሻም የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ሓላፊ አቶ ዘሪሁን ከበደ የሀገረ ስብከቱን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገብርኤልን፣ የሀገረ ስብከቱና የወረዳ ቤተ ክህነቱ ሓላፊዎችን፣ የሐዋሳ ደብረ ታቦር ቅዱስ ሩፋኤል አስተደዳሪና ካህናትን፣ መምህራንን እንደዚሁም ሥልጠናው እንዲሳካ ልዩ ልዩ ድጋፍ ያደረጉ አካላትን በማኅበሩ ስም ካመሰገኑ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎት ተጠናቋል፡፡