ዐውደ ርእዩን በርካታ ምእመናን ጐበኙት

ነሐሴ ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

Mini 3

ዐውደ ርእዩ በአባቶች ቡራኬ ሲከፈት

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን በሚኒያ ፖሊስ ንዑስ ማእከል አዘጋጅነት ‹‹ማዕዶት ዘቤተ ጉባኤ ወገዳማት›› በሚል መሪ ቃል ከነሐሴ ፯-፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በሚኒያ ፖሊስ  ርእሰ አድባራት ጽርሐ አርያም ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቅፅር ውስጥ የተካሔደውን ዐውደ ርእይ በርካታ ምእመናን እንደ ጐበኙት የሚኒያ ፖሊስ ንዑስ ማእከል አስታወቀ።

በዐውደ ርእዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና የገዳማት ታሪክ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርትና ችግሮቶች፣ የደቀ መዛሙርቱ የኑሮ ኹኔታ፣ ማኅበሩ በገዳማትና በአብነት ት/ቤቶች ላይ እየሰጠው ያለው አገልግሎትና የተመዘገቡ ውጤቶች፣ እንደዚሁም ወደፊት ምእመናን ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስገነዝቡ ነጥቦች በ፰ ክፍላተ ትዕይንት ተከፋፍለው ቀርበውበታል፡፡

ዐውደ ርእዩ በሚኒያ ፖሊስ ርእሰ አድባራት ጽርሐ አርያም ቅድስት ሥላሴ ካቴድራልና የሴንት ፖል ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች መልአከ አርያም ቆሞስ አባ ኃይለ ሚካኤል ሙላት እና መልአከ ገነት ቆሞስ አባ ዘርዐ ዳዊት ብርሃኔን ጨምሮ በአጥቢያዎቹ አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናትም ተጐብኝቷል፡፡

Mini 4

ካህናትና ዲያቆናት የአብነት ሥርዓተ ትምህርትን ሲያሳዩ

የሚኒያ ፖሊስ ቅድስት ሥላሴ ካህናትና ዲያቆናት የአብነት ት/ት አሰጣጥ ሒደትን በክውን ትዕይንት መልክ ማቅረባቸው ለዐውደ ርእዩ ድምቀት ከመስጠቱ ባሻገር የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት በምን ዓይነት ሥርዓተ ት/ት አልፈው ለማዕረግ እንደሚደርሱ ጐብኚዎቹ ግንዛቤ እንዲኖራቸው አድርጓል፡፡

Mini

የዐውደ ርእዩ ጐብኚዎች በከፊል

ከጐብኚዎቹ መካከልም ጥቂት የማይባሉ ምእመናን በዐውደ ርእዩ መዘጋጀት የተሰማቸውን ደስታ በዕንባ ሲገልጹ የታዩ ሲኾን በአስተያየቶቻቸውም ማኅበሩ በየአገሩ እንደዚህ ዓይነት አስተማሪነት ያላቸውን መርሐ ግብራት ደጋግሞ እንዲያቀርብ አሳስበው ለዚህም የሚያስፈልገውን ኹሉ ድጋፍ ለማድረግ ፈቃደኛ መኾናቸውን ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ለዐውደ ርእዩ መሳካት በገለጻ፣ በማስተባበርና ድጋፍ በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከቱ አባቶችን፣ የሰበካ ጉባኤ አመራሮችን፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችንና በጎ አድራጊ ምእመናንን ንዑስ ማእከሉ በማኅበረ ቅዱሳን ስም መንፈሳዊ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡