የደሴ ማዕከል ግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ ክፍል “መራኄ ፍኖት” የአንድነት የጉዞ መርሐ ግብር አካሔደ

ታኅሣሥ 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

 የደሴ ማዕከል ግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ ክፍል እስከ ዛሬ ከተለመደዉና ግቢ ጉባኤያት ከሚያደርጉት ጉዞ ለየት ባለ መልኩ ደሴና ኮምቦልቻ የሚገኙ 9 ግቢ ጉባኤያትን፣ የደሴ ወረዳ ማዕከል አባላትን፣ አባቶችን እንዲሁም የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትን በአንድነት ያሳተፈ መራኄ ፍኖት የግቢ ጉባኤያት የአንድነት የጉዞ መርሐግብር ኅዳር 14 ቀን 2007 ዓ.ም በደብረ ነጎድጓድ ሐይቅ እስጢፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ ገዳም አካሄደ፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ 1359 የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና ከ70 በላይ የማዕከሉ አባላት፣ አባቶች እና በደሴ ከተማ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጉባኤ ሥር ካሉ ሰንበት ትቤቶች የተዉጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡

 

መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎት ተጀምሮ በግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ያሬዳዊ ዝማሬ፤ በቦሩ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን መምህር አካለወልድ እና በመምህር ኃ/ማርያም ዘዉዱ ወደ ቅዱሳት መካናት ስንጓዝ ምን ማድረግ እንደሚገባ እና እንዲሁም የመንፈሳዊ ጉዞን ዓላማ መሠረት ያደረገ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡ ከደሴ ከተማ ከሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ተጋብዘው በመጡ  መዘምራንም መዝሙር ቀርቧል፡፡

 

የተሳታፊዎችን ቀልብ የሳበዉ ሌላዉ መርሐ ግብር ምክረ አበዉ ሲሆን፤ “ወጣትነትና መንፈሳዊ ሕይወት” በሚል ርዕስ ቆሞስ አባ ኤልያስ ታደሰ፤ መ/ር ኃይለማርያም ዘዉዱ፣ ቀሲስ ጸጋዉ እና መሪጌታ ገብረ ማርያም በጋራ በመሆን በተለይ የወጣቱን ዝንባሌ በማገናዘብ ግቢ ጉባኤያትና ወጣትነት፣ ኦርቶዶክሳዊ  ወጣት ምን መምሰል አለበት፣ ስልጣኔ እና ሃይማኖት፤ እንዲሁም ሃይማኖትና ፍልስፍና በሚሉ ርእሶች ሰፋ ያለ ትምህርተ ሃይማኖትና አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡

 

የማዕከሉ የበገና ድርደራ ሠልጣኞች የበገና መዝሙር በማቅረብ ከተማሪዎች የተሰበሰቡ የተለያዩ ጥያቄዎች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ እንዲሁም በ2006 ዓ.ም በወሎ ዩኒቨርስቲ ደሴ ካምፓስ ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ የነበረዉና የዋንጫና የሜዳሊያ ተሸላሚው ዲ/ን ቶሎሳ ታዬ፤ እንዲሁም በ2006 ዓ.ም የዚሁ ግቢ ጉባኤ ጸሐፊ የነበረችዉ ተማሪ የሺ ሀብተ ሥላሴ ልምዳቸዉንና ተሞክሯቸዉን  ለተሳታፊዎች አካፍለዋል፡፡ በደሴ ደብረ መዊዕ ቅድስት ኪዳነ ምሕረትና ቅዱስ መርቆሪዎስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር በመሪጌታ ዳዊት አስማረ ቅኔ ቀርቧል፡፡