የጎንደር ማዕከል 2ኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አካሄደ

 

 

 

ታኅሣሥ 4 ቀን 2007 ዓ.ም.

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ /ከጎንደር ማእከል/

 

 

በማኅበረ ቅዱሳን የጎንደር ማእከል ሁለተኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በጎንደር ዙሪያ ወረዳ ማክሰኝት ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው በጥንታዊው ደብረ ገነት ባሕሪ ግንብ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 28 ቀን 2007 ዓ.ም አካሄደ፡፡

በመርሐ ግብሩ የማኅበሩ መልእክት በአቶ አማረ አበበ የሰሜን ምዕራብ ማዕከል ማስተባበሪያ ክፍል ሓላፊ፣ ትምህርተ ወንጌል በዶ/ር አለማየሁ ዋሴ፣ መዝሙር በማእከሉ መዘምራን ቀርቧል፡፡

ከስዓት በኋላ በቀጠለው መርሐ ግብር ገዳማውያን አባቶች አባ ኃይለ ሚካኤል የማን እንደ አባ አቡነ ያሳይ ገዳም መነኩሴ እና አባ ገብረ ዋሕድ የዋልድባ ገዳም ቤተ ሚናስ አበምኔት መንፈሳዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡ በአብርሐም ቤት እንግዳም ዶ/ር አለማየሁ ዋሴ የሕይወት ልምዳቸውን አካፍለዋል፡፡

ምን እንጠይቅልዎ በተሰኘው መርሐ ግብርም በነገረ ክርስቶስ እና በነገረ ማርያም ዙሪያ ጥያቄዎች ተነስተው በመልአከ ታቦር ኃይለ ኢየሱስ የደብረ ታቦር ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ዋና አስተዳዳሪ መልስ ተሰጥቷል፡፡ በመጨረሻም በአበራ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ ጉባኤ ቤት መምህር ቅኔ ቀርቧል፡፡

በመርሐ ግብሩ ከ1800 በላይ ምእመናን የተሳተፉ ሲሆን፤ በጎንደር ፋና ኤፍ ኤም 98.1 ሬድዮ ጣቢያ ከጉባኤው በፊትና በኋላ የዘገባ ሽፋን አግኝቷል