የአበገደ ፊደላት ትርጉም

ዲያቆን ዐቢይ ሙሉቀን

የአበገደ ፊደላት የየራሳቸው መጠሪያ ስም እና ትርጉም አላቸው፡፡ በመጀመሪያ ፊደላቱን ከዚያም መጠሪያቸውን፤ ማለትም የሚወከሉበትና ትርጉማቸውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡-

አ ፡- አልፍ፤ አሌፍ ብሂል አብ ፈጣሬ ኵሉ ዓለም፤ አ፤ አልፍ፤ አሌፍ ማለት ዓለምን

          ሁሉ የፈጠረ አብ ማለት ነው፡፡

በ፡- ቤት ፡- ቤት ብሂል ባዕል እግዚአብሔር፤ በ፤ ቤት፤ ማለት ባለጸጋ እግዚአብሔር

         ማለት ነው፡፡

ገ፡- ጋሜል፡- ጋሜል ብሂል ግሩም እግዚአብሔር፤ ገ፤ ጋሜል ማለት የሚያስፈራ እግዚአብሔር

          ማለት ነው፡፡

ደ፡- ዳሌጥ፡- ዳሌጥ ብሂል ድልው እግዚአብሔር፤ ደ፤ ዳሌጥ ማለት «ዝግጁ የሆነ»         እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡

ሀ፡- ሄ ፡- ሄ ብሂል ህልው እግዚአብሔር፤ ሀ፤ ሄ ማለት እግዚአብሔር ህልው ዘለዓለማዊ ነው ማለት ነው፡፡

ወ፡- ዋው፡- ዋው ብሂል ዋሕድ እግዚአብሔር፤ ወ፤ ዋው ማለት እግዚአብሔር አንድ ነው

         ማለት ነው፡፡

ዘ፡- ዛይ፡- ዛይ ብሂል ዝኩር እግዚአብሔር፤ ዘ፤ ዛይ ማለት እግዚአብሔር አሳቢ ነው

        ማለት ነው፡፡

ሐ፡- ሔት፡- ሔት ብሂል ሕያው እግዚአብሔር ፤ሐ፤ ሔት ማለት ሕያው፤ ዘለዓለማዊ

          እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡

ጠ፡- ጤት፡- ጤት ብሂል ጠቢብ እግዚአብሔር፤ ጠ፣ ጤት ማለት ጠቢብ፤ ጥበበኛ እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡

የ፡- ዮድ፡- ዮድ ብሂል የማነ እግዚአብሔር፣እደ እግዚአብሔር፤ የ፤ ዮድ ማለት የእግዚአብሔር

        ቀኝ ፤ የእግዚአብሔር እጅ ማለት ነው፡፡

ከ፡- ካፍ፡- ካፍ ብሂል ከሃሊ እግዚአብሔር፤ ከ፤ ካፍ ማለት ሁሉን ቻይ እግዚአብሔር

        ማለት ነው፡፡

ለ፡- ላሜድ፡- ላሜድ ብሂል ልዑል እግዚአብሔር፤ ለ፤ ላሜድ ማለት እግዚአብሔር ታላቅ ነው

     ማለት ነው፡፡

መ፡- ሜም፡- ሜም ብሂል ምዑዝ እግዚአብሔር፤ መ፤ ሜም ማለት ጣፋጭ እግዚአብሔር

      ማለት ነው፡፡

ነ፡- ኖን፡- ኖን ብሂል ንጉሥ እግዚአብሔር፤ ነ፤ ኖን ማለት እግዚአብሔር ንጉሥ ነው ማለት ነው፡፡

ሠ፡- ሣምኬት፡- ሣምኬት ብሂል ሰፋኒ እግዚአብሔር፤ ሠ፤ ሣምኬት ማለት ገዥ  እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡

ዐ፡- ዔ፡- ዔ ብሂል ዐቢይ እግዚአብሔር፤ ዐ፤ ዔ ማለት እግዚአብሔር ታላቅ ነው ማለት ነው፡፡

ፈ፡- ፌ ፡- ፌ ብሂል ፍቁር እግዚአብሔር፤ ፈ፤ ፌ ማለት እግዚአብሔር የሚወደድ ነው ማለት ነው፡፡

ጸ፡- ጻዴ፡- ጻዴ ብሂል ጻድቅ እግዚአብሔር፤ ጸ፤ ጻዴ ማለት እግዚአብሔር እውነተኛ ነው ማለት ነው፡፡

ቀ፡- ቆፍ፡- ቆፍ ብሂል ቅሩብ እግዚአብሔር ፤ ቀ፤ ቆፍ ማለት እግዚአብሔር ቅርብ ነው

        ማለት ነው፡፡

ረ፡- ሬስ ፡- ሬስ ብሂል ርኡስ እግዚአብሔር፤ ረ፤ ሬስ ማለት እግዚአብሔር አለቃ ነው

        ማለት ነው፡፡

ሰ፡- ሳን፡- ሳን ብሂል ስቡሕ እግዚአብሔር፤ ሰ፤ ሳን ማለት እግዚአብሔር ምስጉን ነው

        ማለት ነው፡፡

ተ፡- ታው፡- ታው ብሂል ትጉህ እግዚአብሔር፤ ተ፤ ታው ማለት እግዚአብሔር ትጉህ ነው ማለት ነው፡፡

ኀ የሐ፤ እና ፀ የጸ ድርቦች ተደርገው የግእዝ ፊደል በቊጥር ፳፪ እንደሆኑ የሚገልጹ ሊቃውንት አሉ፡፡ ለምሳሌ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ኀ የሐ እና ፀ የጸ ድርቦች እንደሆኑ ሁለቱ ፊደላት ፐ እና ጰ ደግሞ ከጊዜ በኋላ እንደተጨመሩ ይገልጻሉ፡፡ የተጨመሩበትንም ምክንያት ሲያስረዱ ሁለቱ ፊደላት በጽርእ፣ በቅብጥና በሮማይስጥ ያሉ ፊደሎች ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹ  መጻሕፍት ደግሞ የተተረጎሙት ከእነዚህ ነውና መጻሕፍቱ ከተተረጎሙበት ቋንቋ ጋር ለማስማማት እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡

ፊደላት ነገረ እግዚአብሔርን እንደሚያስረዱ በሀለሐመ እንዲሁም በአበገደ አስረድተናል፡፡ የጥንቱ የግእዝ ፊደል የአበገደ እንደሆነ በአለፈውም ገልጸናል፡፡ ይህ የአበገደ የፊደል ቊጥር ፳፪ ነው ይህም የ፳፪ቱ ሥነ ፍጥረት ምሳሌ ነው፡፡ ስለዚህ ፊደል የዕውቀት ሁሉ መሠረት፤ የጥበብ ምንጭ ነውና ምርምራችንን ከፊደል እንድንጀምር ከሚል እሳቤ ይህን አቅርበናል፡፡

ማስታወሻ፡- ኀ የሐ፣ ፀ የጸ ድርቦች ናቸው ስለተባለ ግን የትርጉም ልዩነት አያመጡም ወይም ተመሳሳይ ድምፆች ( ዘረ ድምፆች) ናቸው ማለት አይደለም፡፡ ሠረቀ፡- ወጣ፤ ተወለደ፤ ሰረቀ፡- ሰረቀ፤ በንጉሡ «ሠ» እና በእሳቱ «ሰ» ሲጻፍ የትርጉም ልዩነት እንደሚያመጣ ሁሉ ኀ እና ፀም የትርጉም ልዩነት ያመጣሉ፡፡ ለምሳሌ፡- ፈፀመ በፀሐዩ “ፀ” ሲጻፍ  አሰረ፤ ለጎመ፤ የሚል ትርጉም ሲሰጥ፤ ፈጸመ በጸሎቱ «ጸ» ሲጻፍ ደግሞ ጨረሰ የሚል ትርጉም  ይሰጣል፡፡ እንዲሁም ነስሐ በሐመሩ «ሐ» ሲጻፍ ተጸጸተ፣ ተመለሰ የሚል ትርጉም የሚሰጥ ሲሆን ነስኀ በብዙኃን «ኀ» ሲጻፍ ደግሞ ሸተተ፤ ከረፋ የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ ስለዚህ በቋንቋ ሥርዓት አንድ ድምፅ የፍች (የትርጉም) ለውጥ ካመጣ ሞክሼ ወይም ዘረ ድምፅ ሊባል አይችልም፡፡ በመሆኑም ራሳቸውን የቻሉ የግእዝ ድምፆች እንደሆኑ ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡

ምንጭ፡- ሐመር ፳፮ኛ ዓመት ቁጥር ፲