Abune Timotiwos.JPG

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የርቀት ትምህርት መርሐግብር ጀመረ

 በመንግስተአብ አበጋዝ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በሰርተፊኬት መርሐግብር የርቀት ትምህርት መስጠት መጀመሩን የኮሌጁ ዲን ዶክተር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ አስታወቁ፡

Abune Timotiwos.JPG

የኮሌጁ ዲን ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ/ዶክተር/

የርቀት ትምህርት መርሐግብሩን አስመልክቶ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በሰጡት መግለጫ፤ የትምህርት መርሐግብሩ በርካታ ሊቃውንት የደከሙበት ረዥም ጊዜ የወሰደ ዝግጅት እንደተደረገበት ገልጸዋል፡፡ የኮሌጁ ዲን አያይዘውም፤ «ኮሌጁ ወደፊት የርቀት ትምህርቱን መርሐግብር ወደ ዲፕሎማና ዲግሪ ደረጃ አሳድጎ ለመቀጠል ዛሬ መሠረቱን ጥለንለታል፡፡ ምእመናንም ካለፈው ይልቅ በቅርበት ቤተክርስቲያናቸውን የሚያውቁበትን፣ ለአገልጋዮችም የተሻለ አገልግሎት ሊፈጽሙ የሚችሉበትን ዕድል ፈጥረንላቸዋል፡፡» በማለት የትምህርት መርሐግብሩ መጀመር ኮሌጁ ለቤተክርስቲያኒቱ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ዕድገት የሚያደርገውን አስተዋጽኦ ለማሳደግ እንደሚያግዘው ብፁዕነታቸው ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የኮሌጁ አካዳሚክ ምክትል ዲን መምህር ፍስሐጽዮን ደሞዝ እንደገለጹት፤ ኮሌጁ የማስፋፊያ መርሐግብሮችን ቀይሶ መንቀሳቀስ ከጀመረባቸው ሥራዎች የርቀት ትምህርት መርሐግብር የመጀመሪያው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም የትምህርት መርጃ መጽሐፎቹ /ሞጁል/ የተዘጋጁበትን ቋንቋ ማንበብና መረዳት የሚችሉ በውጪና በሀገር ውስጥ የሚገኙ ምእመናን ሁሉ ሊሳተፉበት የሚችሉበትን ቅድመ ዝግጅት ከየአህጉረ ስብከት ሓላፊዎች ጋር የተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የርቀት ትምህርቱን መከታተል የሚሹ ሁሉ በአቅራቢያው ወደሚገኙ የአህጉረ ስብከት ጽ/ቤት የርቀት ትምህርት ማእከል በመቅረብ ሊመዘግቡና ሊከታተሉ የሚችሉ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በትምህርት ዝግጅቱ ወቅት ልዩ ልዩ እገዛዎችን ያደረጉና በማድረግ ላይ የሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ኮሌጆችና የኮሌጁ ማኅበረሰብ አባላትን በማመስገን የሚጀምሩት መምህር ቸሬ አበበ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ መምህርና የርቀት ትምህርት መርሐ ግብር ጸሐፊ ናቸው፡፡ እንደ መምህር ቸሬ ገለጻ፤ እስከ አሁን ሙሉ ለሙሉ ሥራቸው ተጠናቅቆ የታተሙ የትምህርት መርጃ መጻሕፍት /ሞጁልስ/ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ሥራ አመራር፣ ሥነ-ምግባር፣ ትምህርተ አበው፣ ትምህርተ ሃይማኖት መግቢያ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መግቢያ ሲሆኑ የሌሎች ትምህርቶችም ዝግጅት የቀጠለ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የትምህርቱን መጀመር ከሩቅም ከቅርብም የሰሙ የቤተክርስቲያን ልጆች መመዝገብ መጀመራቸው ታውቋል፡፡ የኮሌጁ ዲን ዶክተር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ዕድሉ ለመላው ምእመናን የተሰጠ በመሆኑ በተለይ የቤተክርስቲያን አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናት ተጠቃሚዎች እንዲሆኑ ጥሪያቸውን አስተላለፈዋል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔ