ክብረ ሰሙነ ሕማማት – ክፍል ሦስት

በሊቀ ማእምራን ብርሃነ መስቀል አጠና (የሊቃውንት ጉባኤ አባል)

ሚያዝያ  ቀን ፳፻፱ .

በዚህ አንጻር ጌታችን እስከ መስቀል ሞት ድረስ ከፊቱ ከባድ መከራ ተደግሶለት እያለ በሕጽበተ እግር ሐዋርያትን አጠመቀ፤ ልጅነትን ሰጠ ማለት አያስሔድም፡፡ ምክንያቱም አንድ መንግሥት ሕገ መንግሥቱን የሚያውጀው፤ ሹመት፣ ሽልማትን መስጠት የሚጀምረው ጠላቱን ድል አድርጎ መንግሥቱን ካደላደለ በኋላ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዓለሙን ያዳነውና ልጅነትን የሰጠው ዲያብሎስን በመስቀል ድል ከነሣው በኋላ ነው እንጂ በሕጽበተ እግር አይደለም፡፡ ከሕጽበተ እግር በኋላ ሊይዙት ወደ እርሱ የመጡትን የካህናት አለቆችን፣ የቤተ መቅደስ ሹሞችንና ሽማግሌዎችን ጌታችን እንዲህ ብሏቸዋል፤ ‹‹ሌባን እንደምትይዙ በሰይፍና በጎመድ ልትይዙኝ መጣችሁን? ዘወትር ከእናንተ ጋር በቤተ መቅደስ ስኖር እጃችሁን እንኳ አልዘረጋችሁብኝም፤ ነገር ግን ጊዜያችሁ ይህ ነው፡፡ የጨለማው አበጋዝም ሥልጣኑ ይህ ነው፡፡›› (ሉቃ. ፳፪፥፶፪-፶፫)፡፡

ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር ካጠበበት እና በአትክልት ቦታ ከጸለየበት ከሐሙስ ማታ እስከ ዓርብ እኩለ ቀን ድረስ ለመግለጽ እጅግ የሚከብድና የሚያሰቅቅ ሥቃይና መከራን በፈቃዱ ተቀብሏል፡፡ ከዚህ አሰቃቂ መከራና ሞት በፊት ቅዱሳን ሐዋርያት ተጠመቁ፤ ልጅነትን አገኙ ማለት ከጋብቻ በፊት ልጅ መውለድ እንደ ማለት ከመኾኑም በላይ የዓለም ቤዛ የኾነውን የጌታችንን ሞት ከንቱ ዋጋ አልባ ማድረግ ነው፡፡ እንዴት ቢባል በክርስቶስ ክርስቲያን የተባለ በሙሉ ከሐዋርያት በተገኘ ልጅነት ነው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ሞት በፊት በተከናወነ ሕጽበተ እግር ተጠመቁ ከተባለ ሞቱ ምንም ሥራ አልሠራም ማለቱ ነውና፡፡ ወገኔ ሆይ ከዚህ በላይ እንደ ተገለጠው የዳንኸውና ልጅነትን ያገኘኸው በክርስቶስ ሞትና ደም እንጂ በእግር መታጠብ እንዳልኾነ ልብ በል፡፡

የሐዋርያት አማናዊ ጥምቀት እንዴትና መቼ ተከናወነ?

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመሰቀሉ በፊት ‹‹የሙት ልጆች ትኾኑ ዘንድ አልተዋችሁም፡፡ እኔ ወደ እናንተ እመጣለሁና ገና ጥቂት ጊዜ አለ፡፡ ከእንግዲህ ወዲህም ዓለም አያየኝም፡፡ እናንተ ግን ታዩኛላችሁ፡፡ እኔ ሕያው ነኝና እናንተም ሕያዋን ትኾናላችሁ፤›› በማለት ለአባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያት የማይለወጥ አምላካዊ ጽኑ ተስፋ ሰጥቶአቸው ነበረ (ዮሐ. ፲፬፥፲፰-፲፱)፡፡ ይህም ሲብራራ እንደ ሙት ልጆች እንድትኾኑ ሐሙስ ማታ እንደ ተለያኋችሁ አልቀርም፡፡ እኔ ከጥቂት ቀን ማለትም ከሁለት ቀን በኋላ በትንሣኤ ወደ እናንተ እመጣለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ዓለሙ አያየኝም፤ እኔ በማይራብ፣ በማይጠማ፣ በማይታመም፣ በማይሞት ሕያው ሥጋ እነሣለሁና እናንተም በልጅነት ሕይወት ልዩ ሕያዋን ትኾናላችሁ ሲላቸው ነው፡፡

ከዚያ በፊት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱሳን ሐዋርያትን ‹‹ዅላችሁ በዚህች ሌሊት እንደማታውቁኝ ትክዱኛላችሁ›› በማለት ደጋግሞ ነግሯቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ዅሉም ቢክዱህ እኔ ፈጽሜ አልክድህም›› ቢለው ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዶሮ ሳይጮኽ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ›› ሲል አስረግጦ ነግሮታል፡፡ ስለኾነም የአምላክ ቃል አይታበይምና የአይሁድ ጭፍሮች ጌታችንን በያዙት ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ዅሉ ትተው ሸሹ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹አንተ የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ›› ሲሉት ‹‹የምትሉትን ፈጽሞ አላውቀውም›› ብሎ ደጋግሞ ምሎ ተገዝቷል (ማቴ. ፳፮፥፶፮፤ ማር. ፲፬፥፳፯-፶)፡፡

በተነሣ ጊዜም ቅዱሳን መላእክት ‹‹ተነሥቶአል፤ ከዚህ የለም፤›› ብለው ለቅዱሳት አንስት እንደነገሩአቸውና ራሱ ጌታችንም በመንገድ ተገልጦ እንዳነጋገራቸው ለቅዱሳን ሐዋርያቱ ሲያበሥሯቸው ሙቶ ይቀራል ብለው ተስፋ ቈርጠዋልና እንደ ተነሣ አላመኗቸውም፡፡ ከዚህ በኋላ ከእነርሱ መካከል ለሁለቱ ወደ ገጠር ሲሔዱ በሌላ መልክ ተገለጠላቸው፡፡ እነርሱም ጌታችን እንደ ተገለጠላቸው ሔደው ለባልንጀሮቻቸው ነገሩ፡፡ እነርሱንም ቢኾን አላመኗቸውም፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ዐሥራ አንዱ ደቀ መዛሙርት በማዕድ ተቀምጠው ሳሉ ተገለጠላቸው፡፡ አሁንም መነሣቱን ያዩ ደቀ መዛሙርትን አላመኗቸውም ነበር፡፡ ጌታችንም ስለ ሃይማኖታቸው ጉድለት ገሥፆአቸዋል፤ የልባቸውንም ጽናት ነቅፏል (ማር. ፲፮፥፲፪-፲፬)፡፡ በዚህ ኹኔታ ለቅዱሳን ሐዋርያት ካሣ ሳይፈጸም ከስቅለት በፊት በሕጽበተ እግር ተጠመቁ ቢባል እንኳ ትንሣኤውን አላመኑም ነበር፡፡ እንዳውም የክርስቶስ ትንሣኤ ተረት እንደ መሰላቸው ተጽፋል (ሉቃ. ፳፬፥፲፩)፡፡ አንድ ሰው ከካደ ደግሞ ልጅነት ሊኖረው አይችልም፡፡ ስለኾነም የሐዋርያት ጥምቀት እግር በመታጠብ እንዳልኾነ እንረዳለን፡፡

እርግጠኛው የቅዱሳን ሐዋርያት ጥምቀት ግን ካሣ ከተፈጸመ በኋላ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከሃሊነቱ ዲያብሎስን ድል ነሥቶ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ በተነሣ ጊዜ ነው፡፡ ቀድሞውንም አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ‹‹ከልጅ ልጅህ ተወልጄ፣ በአደባባይህ ተመላልሼ፣በመስቀል ተሰቅዬ አድንሃለሁ፤›› ብሎ ለአዳም በሰጠው ተስፋ መሠረት ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ዅሉንም በእርሱ ይቅር ብሎ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙ በምድርና በሰማይ ላሉ ሰላምን አደረገ (ቆላ. ፩፥፳)፡፡ ‹‹በውኂዘ ደሙ ቅዱስ አንጽሖሙ ለመሐይምናን ወለሕዝብ ንጹሐን፤ በከበረ ደሙ ፈሳሽነት በዓለመ ሥጋ በዓለመ ነፍስያሉትን አዳነ፤›› እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም (የእሑድ ውዳሴ ማርያም)፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹ክርስቶስም ስለ ሰው ኃጢአት አንድ ጊዜ ሙቶአልና ጻድቅ እርሱ እኛን ወደ እግዚአብሔር ያቀርበን ዘንድ ስለ እኛ ኃጢአት በሥጋ ሞተ፤ በመንፈስ ግን ሕያው ነው፡፡ በእርሱም በወኅኒ ወደሚኖሩ ነፍሳት ሒዶ ነጻነትን ሰበከላቸው›› በማለት ጌታችን በዕለተ ዓርብ ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ሥጋው በገዛ ሥልጣኑ መለየቱንና በሲኦል የነበሩ ነፍሳትን ማውጣቱን አስረድቶናል (፩ኛ ጴጥ. ፫፥፲፰-፲፱)፡፡

መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ በዓለመ ነፍስ በሲኦል ሥቃይ ውስጥ የነበሩትን ነፍሳት ሕያው በኾነ ደሙ አንጽቶና ቀድሶ ወደ ገነት ከመለሰ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹እግዚአብሔርነቱ ግን የሞትን ማሰሪያ ፈቶ ከሙታን ለይቶ አስነሣው፡፡ ሞት እርሱን ሊይዘው አይችልምና፤›› እንዳለው ጌታችን ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ሞትን ድል ነሥቶ እሑድ በመንፈቅ ሌሊት ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷል፡፡ እንደ ተነሣም በቀጥታ ወደ ቅዱሳን ሐዋርያት ነው የሔደው፡፡

ደቀ መዛሙርቱም አይሁድን ስለ ፈሩ ደጁን ቈልፈው ተሰብስበው የነበሩበት ቤት ሳይከፈት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እነርሱ ገብቶ በመካከላቸው ቆመና ‹‹ሰላም ለእናንተ ይኹን!›› አላቸው፡፡ እነርሱም ፈሩ፤ ደነገጡ፡፡ ጌታችንም ‹‹እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፤›› አለና እጆቹንና እግሮቹን፣ ጎኑንም አሳያቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ጌታችንን ባዩት ጊዜ ደስ አላቸው፡፡ ማለትም ፍርኃቱ ተዋቸው፤ ጥርጣሬው ተወገደላቸው፡፡ ፈጣሪያቸው ሙቶ እንደ ተነሣ አመኑ፤ ተረዱ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በዚህ መልኩ ካሳመናቸው በኋላ ዳግመኛ ‹‹ሰላም ለእናንተ ይኹን! አብ እኔን እንደ ላከኝ እንዲሁ እኔ እናንተን እልካችኋለሁ፤›› አላቸው፡፡ ይህንም ብሎ እፍ አለባቸው፤ መንፈስ ቅዱስንም ተቀበሉ (ዮሐ. ፳፥፳፩-፳፪)፡፡

‹‹እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር ፈጠረው፤ በፊቱም ሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት፡፡ ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ኾነ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዘፍ. ፪፥፯) አዳም በተፈጠረ በዐርባ ቀኑ እግዚአብሔር አምላክ በፊቱ እፍ ብሎ ያሳደረበትን ልጅነት ዕፀ በለስን በልቶ ቢያስወስዳት ዳግማይ አዳም ክርስቶስ አዳም ስላጠፋው ጥፋት ደሙን በመስቀል ላይ አፍስሶ፣ ውድ ሕይወቱን ክሦ በቅዱሳን ሐዋርያት ፊት እፍ በማለት ልጅነትን ዳግመኛ አሳደረባቸው፡፡ በዚህም ቀድሞ በዕፀ በለስ ምክንያት የሔደች ልጅነት በዕፀ መስቀል ምክንያት ተመለሰች፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት የትንሣኤ ዕለት እንደ ተጠመቁ ራሳቸው በመጽሐፈ ኪዳን እንደሚከተለው ገልጸውታል፤

‹‹… ኮነ እምድኅረ ተንሥአ አስተርአየነ ወተገሠ እምቶማስ ወማቴዎስ ወዮሐንስ ወተፈወስነ (ወአእመርነ) ከመ ተንሥአ እግዚእነወይቤለነአማን አማን እብለክሙ ኢትከውኑ ውሉደ እግዚአብሔር ዘእንበለ በመንፈስ ቅዱስ፡፡ ወተሰጠውናሁ ወንቤእግዚኦ ሀበነ መንፈሰ ቅዱሰወነፍሐ ላዕሌነ ኢየሱስ፡፡ ወእምድኅረ ነሣእነ መንፈሰ ቅዱሰ ይቤለነአንትሙ እለ መንግሥተ ሰማያት ዘእንበለ ኑፋቄ ልብእንዲህ ኾነ፤ ጌታችን ከተነሣ በኋላ ተገለጠልን፡፡ በቶማስ በማቴዎስና በዮሐንስ እጅ ተዳሰሰ፡፡ ጌታችን እንደ ተነሣም አወቅን፡፡ እርሱምእውነት እውነት እላችኋለሁ፤ በመንፈስ ቅዱስ ካልተወለዳችሁ የእግዚአብሔር ልጆች አትኾኑምአለን፡፡ እኛምመንፈስ ቅዱስን ስጠን?› ስንል መለስንለት፡፡ ኢየሱስም በእኛ ላይ እፍ አለ፡፡ መንፈስ ቅዱስን ከተቀበልን በኋላእናንተ ጥርጥር በሌለው ልብ የመንግሥተ ሰማያት ባለቤቶች ናችሁአለን፤›› (መጽሐፈ ኪዳን አንቀጽ ፩)፡፡

ይቆየን