niqodimos_

ኒቆዲሞስ/ለሕፃናት/

መጋቢት 21 2004ዓ.ም

በቴዎድሮስ እሸቱ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? መልካም ይኸው ዘወረደ ብለን በመጀመሪያው ሳምንት የጀመርነው ጾም ዛሬ ኒቆዲሞስ ላይ ደርሷል፡፡ ኒቆዲሞስ የ7ኛው ሳምንት መጠሪያ ነው፡፡

niqodimos_

ልጆች የአይሁድ መምህር የሆነ አንድ ኒቆዲሞስ የሚባል ሰው ነበር፡፡ ይህ የአይሁድ መምህር ማታ ማታ እየመጣ ከክርስቶስ እግር ስር ቁጭ ብሎ ትምህርት ይማር ነበር፡፡ ልጆች ማታ ማታ እየመጣ የሚማረው ለምን መሰላችሁ፡፡

 

አንደኛ የአይሁድ መምህር ስለሆነ ሲማር እንዳያዩት ነው፡፡ ሲማር ካዩት ገና ሳይማር ነው እንዴ የሚያስተምረን እንዳይሉት፡፡ ሁለተኛ አይሁድ ክርስቶስን ያመነና የተከተለ ከሀገራችን /ከምኲራባችን/ ይባረራል ብለው ስለነበር እንዳይባረር ፈርቶ ሦስተኛ ደግሞ ሌሊት ሲማሩ ምንም የሚረብሽና ዐሳብን የሚሰርቅ ነገር ስለሌለ ትምህርት በደንብ ይበገባል ብሎ በማሰብ ነው፡፡ እናንተስ በሌሊት ትምህርታችሁን የምታጠኑት እንዲገባችሁ አይደል ልጆች? በሌሊት ዐሳባችሁ አይበተንም፡፡

ታዲያ አንድ ቀን ማታ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ስለ ጥምቀት አስተማረው፡፡ “ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔር መንግሥት ሊወርስ አይችልም” አለው፡፡ ኒቆዲሞስም “ሰው ከሸመገለ ካረጀ በኋላ እንዴት ድጋሚ ሊወለድ ይችላል” ብሎ ጠየቀ ክርስቶስ ዳግም ልደት ማለት ሰው በጥምቀት የሚያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት እንደሆነ ሰው ተጠምቆ የእግዚአብሔር ልጅ ካልሆነ መንግሥተ ሰማያትን እንደማይወርስ አስተማረው፡፡ ኒቆዲሞስም ስለ ጥምቀት በሚገባ ተረዳ፡፡

አያችሁ ልጆች እንግዲህ በዚህ ሳምንት ከሚነገረው ታሪክ በርካታ ቁም ነገሮችን እናገኛለን ለምሳሌ እኛ ልጆች የእግዚአብሔርን ቃል ቀን ከሌሊት ሳንል ሁል ጊዜ መማር እንዳለብን፤ ያልገባን ነገር ካለ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ጠይቀን መረዳት እንዳለብን ነው፡፡ እንደዚህ በማድረግ ስለ እምነታችን በቂ እውቀት ልንጨብጥ ይገባናል ማለት ነው፡፡ ለዛሬ አበቃሁ ደህና ሰንብቱ፡፡