ብፁዕ ሥራ አስኪያጁ የአንድነት ኑሮውን አበረታቱ

ነሐሴ ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

IMG_0049

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

‹‹ለቤተ ክርስቲያናችን ንዋያተ ቅድሳትን ብቻ ሳይኾን ሰውም እንስጥ›› በሚለው መሪ ቃሉ የሚታወቀው ጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ የአንድነት ኑሮ ማኅበር ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ካህናትና በርካታ ምእመናን በተገኙበት ነሐሴ ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስብከተ ወንጌል አዳራሽ የገቢ ማሰባሰቢያ ጉባኤ አካሒዷል፡፡

በዕለቱ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ በክልል ትግራይ ደቡባዊ ዞን ማይጨው፣ ደቡባዊ ምሥራቅ ትግራይና የምሥራቃዊ ዞን አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የአንድነት ኑሮው ከየብሔረሰቡ የተውጣጣጡ ሰባክያንን በማሠልጠን ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት የሚያደርገውን አስተዋጽዖ አድንቀው ‹‹በዚህ አገልግሎታችሁ በርቱ፤ እኛም ከጎናችሁ ነን›› ሲሉ የአንድነት ኑሮውን አበረታተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሰላማ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በበኩላቸው ‹‹እግዚአብሔር ንጹሕ ልብ፣ ንጹሕ ሰውነት ይፈልጋልና በንጽሕና ኾናችሁ እንድታገለግሉ እግዚአብሔር ይርዳችሁ፤ ማኅበራችሁን ያስፋላችሁ›› የሚል አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡

IMG_0073

ብፁዕ አቡነ ሰላማ

በተመሳሳይ መልኩ የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ቀሲስ ታምሩ እሸቱ የሀገረ ስብከቱን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስን ወክለው ‹‹እኛም ከጎናችሁ ኾነን የምንችለውን ኹሉ እናደርጋለን›› ብለዋል፡፡

በዕለቱ በቀሲስ እሸቱ ታደሰና በዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲኾን፣ በተጨማሪም የገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሰንበት ት/ቤትና የአንድነት ኑሮው መዘምራን፣ እንደዚሁም የአንድነት ኑሮው ሠልጣኞች ያሬዳውያን ዝማሬያትን አቅርበዋል፡፡

በመቀጠልም የአንድነት ኑሮው መግለጫ በስብከተ ወንጌል ሥልጠና ኰሚቴው አባል በአቶ ማናየ አባተ የቀረበ ሲኾን በመግለጫውም ከአዲስ አበባ ከተማ በ፻፶ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ የገጠር ቤተ ክርስቲያን ቆመው መሔድ የማይቻላቸው ካህን ታቦቱን አክብረው፤ ሌላ ጐልማሳ ደግሞ እርሳቸውን ተሸክሟቸው በበዓለ ጥምቀት ወደ ባሕረ ጥምቀት ሲወርዱ መታየታቸውን አስመልክቶ የቀረበው ዘገባ የጉባኤውን ተሳታፊዎች ያሳዘነ ነበር፡፡

IMG_0046

የጉባኤው ተሳፊዎች በከፊል

‹‹የአንድነት ኑሮው ዓላማና ተልእኮ ከመላው የኢትዮጵያ ክፍሎች የተውጣጡ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ማስተማር የሚችሉ ሰባክያነ ወንጌልን በማሠልጠን ወንጌልን ማዳረስና የአብነት ትምህርት በማስተማር በአገልጋይ ካህን እጦት ምክንያት የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ ነው›› ያሉት የቦርድ ሰብሳቢው ዲያቆን ሙሉጌታ ምትኩ የጉባኤው ዓላማም ለዚህ አገልግሎት ማስፈጸሚያ የሚውል ገንዘብ ለማሰባሰብ መኾኑን አስታውቀዋል፡፡ አክለውም ኹሉም ሕዝበ ክርስቲያን ከአንድነት ኑሮው ጋር በመኾን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠናከር የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ሰላማ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ የጉባኤው ፍጻሜ ኾኗል፡፡