ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ

ዲያቆን መልአኩ ይፍሩ

ታኅሣሥ ፭ ቀን ፳፻፲፬ ዓ.ም

በከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመነ መንግሥት ንጉሡ መልኳ (ሥነ ላህይዋ) ውብ የሆነች ብላቴና ሊያገባ ወዶ መልእክተኞችን መርጠው ያመጡለት ዘንድ ላከ። እነርሱም መላ ሀገሪቱን ሲያስሱ ከቆዩ በኋላ ንጽሕት ቅድስት አርሴማ እናታችንን በአንድ በሮሜ ባለ ገዳም ውስጥ ከሌሎች ደናግል ጋር አገኟትና ሥዕሏን ስለው ለንጉሡ ላኩለት። ብፅዕት እናታችን ቅድስት ንጽሕት መርዓተ ክርስቶስ ቅድስት አርሴማም ሥነ ላህይዋ እጅጉን ልዩ የሆነ መልከ መልካም ነበረች።

ንጉሡም ይህን ሥዕል እንዳየ በልቡ በእጅጉ ፈቀዳ፤ እንዲያመጡለትም አዘዘ። ይህን እንደሰሙ እኒያ ደናግልና ቅድስት አርሴማ የገዳሙም እመምኔት የሆነችው ቅድስት አጋታ ሸሽተው ወደ አርማንያ ሄዱ። በዚያም ሳሉ ንጉሥ ድርጣድስ የሚገዛው ግዛቱ ነበርና ከንጉሡ ድዮቅልጥያኖስ መልእክት ደርሶት ሲያስፈልጋት ከደናግሉ ጋራ አገኛቸው። እርሱም በመልከ መልካምነቷ በእጅጉ ተስቦ እንዲህ ያለችቱንማ ለራስ ነው እንጂ ማን ሞኝ አለ በሚል ለንጉሡ ድዮቅልጥያኖስ መሥጠቱን ትቶ ለራሱ እዚያው አኖራት። ከደናግሉም ጋራ ካሠራቸው በኋላ ቅድስት እናታችንን ብዙ ሊያታልላት ሞከረ። እርሷ ግን በመንፈሳዊ ሕይወቷ ፍጹም ጥብዓት ያለባት ራሷንም ለቸሩ አምላካችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ሙሽራ ያደረገች ናትና ለሰማያዊ ሙሽርነቷ የታመነች ሆነች። ንጉሡም ደጋግሞ ቢሞክር አልሆንለት አለ። በኋላም እመ ምኔቷን እንድታባብላት ላካት፤ እመ ምኔቷ ግን ይበልጡኑ አጽናናቻት፤ ‹‹አይዞሽ! እንዲ ላለው ምድራዊ ኃላፊ ነገር እንዳትታለይ፤ ሰማያዊ ሙሽርነትሽንና ንጽሕናሽን አጽኚ›› ብላ እንዲያውም ይበልጥ አስጨከነቻት። በኋላም ንጉሡ በግድ ይዞ ሊሄድ ቢል ኃይለ መንፈስ ቅዱስ አድሮባት ነበርና ያንን በጦር የጎለመሰ ሰውነት ያለውን ብርቱ ንጉሥ ከመሬት ፈጠፈጠችው። ንጉሡም አንዲት ትንሽ ወጣት እንደምን ጣለችኝ ብሎ እጅግ አፈረ።

ንጉሡም በዚህ ሁሉ ተቆጥቶ ቅድስት አርሴማን ሥቃይዋን ሊያበዛባት ወዶ እኒያን ደናግል እርሷን ፊት ለፊታቸው አሠራትና አንድ በአንድ አንገታቸውን ቀላቸው። እርሷ ግን ‹‹አይዟችሁ!›› እያለች ታጽናናቸው ነበር። የሚደንቀው ትሰቀቃለች ብሎ ያደረገላት ነገር እንዲያውም ቅዱሳኑ ሰማያዊ አክሊልን ሲቀበሉ ትመለከትበት ነበር። በኋላም ‹‹አንቺንስ እንደሌሎቹ ቶሎ አልገድልሽም›› ብሎ እጅግ ብዙ ሥቃያትን አሠቃያት። ከእነዚህም አንደኛው ሁለቱን ድንግል ጡቶቿን ቆረጠ፤ ይህም አልበቃ ብሎት ሁለቱን ዐይኖቿን አወጣ፤ እርሷም እንዲህ ሳለች እመቤታችን ንጽሕት ድንግል ማርያም የብርሃን ልዩ ዐይኖችን ሰጠቻት። በመጨረሻም ማሠቃየትን በሰለቸ ጊዜ ከእኒያ ከቀሩት ደናግል ጋራ በመስከረም ሃያ ዘጠኝ ቀን  አንገቷን ሰየፈና ሁላቸውም የሰማዕትነትን የድል አክሊል ተቀዳጁ። እኒህም ቁጥራቸው ሰባ አምስት ወንዶችና ሠላሳ ዘጠኝ ሴቶች ነበሩ።

ቅድስት አርሴማ ከሃያ ሰባቱ ደናግል ጋራ ሰማዕትነት ከተቀበለች በኋላ ንጉሡ ድርጣድስ ፈጽሞ ታመመ ታወከ። ቅዱስ ጎርጎርዮስም ሊቀ ጳጳሳትን አስቀድሞ አሥሮት ነበር። (ይኸውም በትውፊት ታላቅ ወንድሟ እንደኾነ ይገራል)። በኋላም ቅዱስ ጎርጎርዮስን ፈታውና ከደዌው ዳነ፤ የቅዱሳን ደናግል እና የቅድስት አርሴማንም የቅዱሳን ሰማዕታቱን ዕፅም ፍልሠታቸው በዚህ በቅዱስ ጎርጎርዮስ እንዲደረግ ሆነ፤ ይህም ታኅሣሥ ስድስት ቀን ነው፡፡ እንዲሁ ደግሞ የእርሷ ማኅበርተኞች የሚባሉ የመቶ ዐሥራ ዘጠኝ ሰማዕታት ዝክራቸው ነው። ከዚያም በስሟ ያማረ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው እንዲሁ ያከበሩበት ነውና እናከብረው ዘንድ ይገባናል።

ለእግዚአብሔር አምላካችን በዚህች ድንቅ የክርስቶስ ሙሽራ ቅድስት አርሴማ እና በደናግሉም ሁሉ ጸሎት ይማረን፤ ለዘላለሙ አሜን።

ምንጭ:- መጽሐፈ ስንክሣር ዘወርኃ መስከረም