ማእከሉ ጠቅላላ ጉባኤውን ሊያካሂድ ነው

ጥቅምት 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤውን የፊታችን ቅዳሜና እሑድ እንደሚያካሂድ የማእከሉ ዋና ጸሐፊ አቶ ካሳሁን ኀይሌ አስታወቁ፡፡ ቅዳሜ ጥቅምት 17 ቀን 2005 ዓ.ም ከሰዓት በፊት በሚኖረው የመክፈቻ  መርሐ ግብር ላይ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስን ጨምሮ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ የሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ የዋናው ማእከል ተወካይ፣ የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሊቃነ መናብርት ከየግቢ ጉባኤያትና ከሠራተኛ ጉባኤያት የሚወከሉ ተወካዮች እንደሚገኙ ያስታወቁት አቶ ካሣሁን፡- “የ2004 ዓ.ም የሥራ አፈጻጻምን መገምገም፣ በጸደቀው የማኅበሩ መሪ ዕቅድ ላይ ተመሥርቶ የተዘጋጀውንና ከጥር 1 እስከ ጳጉሜን 5 ቀን 2005 ዓ.ም የሚያገለግለውን ዕቅድ ተወያይቶ ማጽደቅ በዋነኝነት በዚህ ጉባኤ የሚፈጸሙ ተግባራት ናቸው” ብለዋል፡፡

 

ጉባኤው  በሁለት የመወያያ ርዕሶች ላይ እንደሚመክር የታወቀ ሲሆን፤ ከ800 እስከ 1200 የሚደርሱ የማእከሉ አባላት እንደሚታደሙበት ከማእከሉ ጽሕፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል፡፡