700 ምእመናን ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው ተመለሱ

ጥቅምት 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


በቄለም ወለጋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ሐዲስ ለማ በየነ አማካኝነት፥ ለ31ኛው ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አጠቃላይ መንፈሳዊ የሰበካ ጉባኤ የቀረበው ሪፖርት፤ ለ28 ዓመታት ያህል በሰዩ ወረዳ ሹሻ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያንና በአጥቢያው የሚገኙ ምእመናን ከእናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸው በመለየት የቆዩትን ሁለት ቀንደኛ የተሐድሶ መናፍቃን መሪዎች ተውግዘው  መለየታቸውን አመለከተ፡፡

 

በተሐድሶ መናፍቃን ሴራ በየዋህነት የተወሰዱ ምእመናንን በንስሐ  ለመቀበልና መናፍቃኑ “የሹሻ ቅዱስ ገብርኤል ምክር ቤት ” በሚል ስያሜ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት የተነጠሉትን በብፁዕ አቡነ ሄኖክ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ትዕግሥት የተሞላበት በሳል አመራር የሹሻ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያንን ለማስመለስ ስድስት ወራት መውሰዱን ሥራ አስኪያጁ መጋቤ ሐዲስ ለማ በየነ  አስረድተው፤ ምእመናኑ ባለማወቅና በመናፍቃኑ ስውር ሴራ ተታለው ከቤተ ክርስቲያን ተለይተው መቆየታቸው እንዳሳዘናቸውና በመጨረሻ ግን የተለዩአትን እናት ቤተ ክርስቲያንን ለመቀላለቀል መቻላቸው እንዳስደሰታቸው በመግለጽ፡- “የሰባክያነ ወንጌልና የአገልጋይ ካህናትን ችግር ለመቅረፍ በመላው ዓለም የሚገኙ የቅድሰት ቤተ ክርስቲያን የቁርጥ ቀን ልጆች ከሀገረ ስብከቱ ጎን በመቆም የተቻላቸውን ድጋፍ እንዲያበረክቱልን በታላቅ ትሕትና እጠይቃለሁ” ብለዋል፡፡

 

በመናፍቃኑ ተታለው የቆዩት ምእመናን መጋቢት 19 ቀን 2004 ዓ.ም በሹሻ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መጽሐፈ ቄደር በተደረሰበት ማየ ንስሐ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት ተቀላቅለዋል፡፡