ማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቪዥን ሥርጭት አገልግሎቱን በይፋ መጀመሩን አበሰረ

ግንቦት 16 ቀን 2005 ዓ.ም.

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲየን ማኀበረ ቅዱሳን ላለፉት ሃያ ዓመታት በመንፈሳዊ መገናኛ ብዙኃን ሲሰጥ የቆየውን አገልግሎት በማስፋት የቴሌቪዥን ሥርጭት በኦፊሴል መጀመሩን ለምእመናን የሚያበስርበት ጉባኤ ቅዳሜ ግንቦት 17 ቀን 2005 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ስብሰባ ማእከል እንደሚያካሂድ ተገለጸ፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሚሳተፉበት በዚህ ጉባኤ ማኅበሩ ዐቢይ ተልዕኮ አድርጎ ይዞት የተነሣውን የስብከተ ወንጌል አገልሎት ለማሳካት መንፈሳዊ መገናኛ ብዙኃንን እንዴት ሲጠቀም እንደቆየና በዘርፉ አገልግሎቱን ለማጠናከር ያለው ዕቅድ በብሮድ ካስት መገናኛ ብዙኃን የቴሌቪዥን ሥርጭት አገልግሎትን ለምን እንደጀመረ፣ ወደፊትም አጠናክሮ ለመቀጠል ያለውን ዕቅድና በአገልግሎቱ ምእመናን ሊኖራቸው ስለሚገባው ተሳትፎ መነሻ የሚሆኑ አሳቦች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው ተጠቁሟል፡፡

ማኅበሩ ከየካቲት 16 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቪዥን ሥርጭት ጣቢያ በየሳምንቱ እሑድ ከረፋዱ 5፡30 እስከ 6፡00 እና ሐሙስ ከጠዋቱ 1 ሰዓት እስከ 1፡30 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ሥርዓተ እምነትና ትውፊት የሚያስተላልፉ ዝግጅቶችን እንደሚያቀርብ ይታወቃል፡፡