mahbre posterpsd

“ለቤተ ክርስቲያን ተልዕኮ መሳካት የገዳማት ድርሻ” በሚል ዐውደ ጥናት ይካሄዳል

ታኅሣሥ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  • የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የገድል መጽሐፍ ይመረቃል

mahbre posterpsdየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ለማሳካት የገዳማት ድርሻ በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ አውደ ጥናት ታህሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ 7፡00 ሠዓት ጀምሮ 6 ኪሎ በሚገኘው በኢትዮጵያ ስብሰባ ማእከል ከሃምሳ በላይ የሚደርሱ ከታላላቅ ገዳማት የተውጣጡ አበምኔቶች በተገኙበት እንደሚካሄድ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲያቆን አእምሮ ይሔይስ ገለጹ፡፡

 

በዕለቱም ከዐውደ ጥናቱ ጋር ተያይዞ በገዳማት ላይ ጎልተው የሚታዩትን  ችግሮች መቅረፍ ይቻል ዘንድ ማኅበረ ቅዱሳን 12 ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ በገዳማት ላይ ተግባራዊ ለማድረግ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር አዘጋጅቷል፡፡ በዚህም መሠረት ከ5000 ለሚደርሱ ምእመናን ጥሪ የተደረገ ሲሆን ዋነኛ ዓላማውም ለፕሮጀክቶቹ ማስፈጸሚያ የሚውል ገቢ ለማሰባሰብ መሆኑን ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

 

በተጨማሪም በዚሁ ዕለት የታላቁ አባት የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫና የአባ በጸሎተ ሚካኤል የገድል መጽሐፍ የሚመረቅ ሲሆን ተተርጉሞ ለኅትመት ለማብቃት ከሦስት ዓመት በላይ እንደፈጀ ተገልጿል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በአገልግሎት ላይ የሚገኙ መንፈሳዊ ማኅበራትና ምእመናን እንደሚገኙ ይጠበቃል፡፡

 

በተያያዘ  ዜና ከየገዳማቱ ለተውጣጡት ከሃምሳ በላይ አበምኔቶች የሚሳተፉበትና ከታኅሣሥ 7 -11 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚቆይ ሥልጠና መዘጋጀቱን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲያቆን አእምሮ ይሔይስ ገልጸዋል፡፡  ሥልጠናው የሚያተኩርባቸው ርዕሰ ጉዳዮችን ሲያብራሩም “ገዳማት በውስጣቸው ያለውን ሀብት እንዴት መጠቀም ይችላሉ? በገዳማት ውስጥ የሥራ ፈጠራን እንዴት ማዳበር ይቻላል? እንዴትስ ውጤታማ ሥራ መሥራት ይቻላል? ከአካባቢ ጥበቃ ጋር በተያያዘ ገዳማት ያላቸውን የደን ሀብት እንዴት ተንከባክበው መያዝና መጠቀም ይችላሉ?  በቅርስ አያያዝ በኩልም በፈራረሰ ዕቃ ቤት ውስጥና አመቺ ባልሆነ ሁኔታ ላይ የሚገኙትን ቅርሶች በተሻለና በተቀናጀ መንገድ ጠብቀው  ለተተኪው ትውልድ እንዴት ማስተላለፍ ይችላሉ? የሚሉት ላይ ያተኩራል” ብለዋል፡፡

 

ሥልጠናው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሰቲ ምሁራን፤ በቅርስ ጥበቃ ባለሙያዎችና በተጋባዥ ምሁራን አማካይነት  እንደሚሰጥ ዲያቆን አእምሮ ይሔይስ ጨምረው ገልጸዋል፡፡