ዜና ዕረፍት

ብፁዕ አቡነ ባስልዮስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኒውዮርክ ሀገረ ስብከት የሮቸስተር ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም የበላይ ጠባቂ ሊቀ ጳጳስ ከዚህ ዓለም ድካም ማረፋቸው ተገልጿል።ዕረፍታቸውንም ተከትሎ የቅዱስ ሲኖዶስ ጽሕፈት ቤት ያደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው ክቡር አስከሬናቸው በሚቀጥለው ሳምንት ቅዳሜ መጋቢት ፱/፳፻፲፭ ዓ/ም ወደ አዲስ አበባ የሚመጣ ሲሆን የቀብር ሥነ ሥርዓቱም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም አስታውቋል።

ዜና ዕረፍት

የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አበምኔት ታላቁ የጸሎት አባት የኔታ መምህር ሐረገ ወይን ምሕረቱ በእርግና ምክንያት በ፺፱ ዓመታቸው መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል።ሥርዓተ ቀብራቸውም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች፣ የመንግሥት ባለሥልጣናትና ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት በዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ተፈጽሟል።

የኔታ ሐረገ ወይን በርካታ ጳጳሳትንና ሊቃውንትን አስተምረው ያበቁ የአቋቋሙ ሊቅ ነበሩ። ከአርባ ዓመት በላይ ወንበር ዘርግተው ያስተማሩ፣ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ጊዜ ጀምሮ ሁለት ጊዜ ያክል ለጵጵስና ቢጠየቁም “ምንኩስናዬ ይበቃኛል” በማለት በዓታቸውን ያጸኑ ጸሎተኛ አባት እንደነበሩም ተገልጿል።

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ፲ኛ ዓመት በዓለ ሢመት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በታላቅ ድምቀት ተከበረ።

ዜና ዕረፍት

ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ በአብነት መምህርነታቸው አያሌ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን በማፍራታቸውና ባበረከቱት የረዥም ዘመን አገልግሎት የመቀሌ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራልና የከሣቴ ብርሃን ሰላማ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ ሆነው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ተሹመው በተመደቡበት ኃላፊነት ሲያገለግሉ ከቆዩ በኋላ የካቲት ፳፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል።

የብፁዕነታቸው በረከት ይደርብን!

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ