፻፴፬ ኛው የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ ላይ በቅዱስነታቸው የተላለፈ አባታዊ መልእክት

፻፴፬ ኛው የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ ላይ በቅዱስነታቸው የተላለፈ አባታዊ መልእክት

ሚያዝያ ፳፳/፳፻፲፰ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ የግንቦት ርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የመክፈቻ አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል።
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ ኣምላክ ኣሜን!
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤
ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት፣
በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የተገኛችሁ በሙሉ፦
ማሕየዊት በምትሆን ሞቱ ሰማያውያንና ምድራውያንን ያስታረቀ፣ በቅድስት ትንሣኤውም የሙታንን ሕይወት በተስፋ ያለመለመ ጌታችን፣ ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንኳን ለዓመታዊው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አደረሰን አደረሳችሁ!
“እስመ ተዋለጠ እግዚአብሔር ዓለመ በክርስቶስ አናኅስዮ ኃጢአቶሙ ወኢነጺሮ ጌጋዮሙ፤ ወረሰየ ላዕሌነ ቃለ ሥምረቱ፤ ወወሀበነ መልእክተ ሣህሉ፤ እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና በደላቸውን አይቈጥርባቸውም ነበር፤ በእኛም የማስታረቅ ቃል አኖረ” (2ኛቆሮ. 5፥19)
የእግዚአብሔርም ልጅ፣ የሰውም ልጅ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም ሰው ሆኖ ሲገለጽ ግልጽ የሆነ ዓላማና ግብ እንደነበረው ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል፤ እርሱም በሰማይም፣ በምድርም ያሉትን በሙሉ ማስታረቅ፣ ማገናኘትና አንድ ማድረግ ነበረ፤
ጌታችን ይህንን ሲያደርግ ሰማያውያኑንና ምድራውያኑን የለያየውን ምክንያት በማስወገድ ነው፤ የመለያየቱ ምክንያት ክፉ ኅሊና አምጦ የወለደው በደልና እርሱን ተከትሎ የተከሠተው ኃጢኣት ነበረ፤ በኃጢኣት ምክንያት የገባው ሞት ደግሞ የቅጣቱ ማሳያ ፍርድ ነበረ።
የመጀመሪያዎቹ ሰዎች በፈጸሙት ስሕተት መነሻነት ምድርንና ምድራውያንን ለከባድ ቅጣትና መርገም የዳረገው ይህ መለያየት ለሰማያውያኑም ተርፎአል።
ምክንያቱም መለያየቱ በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰውና በሰው፣ በነፍስና በሥጋ ጭምር የጥል ግድግዳን ገንብቶ እስከ ክርስቶስ ዕለተ ስቅለት መዝለቁን በቅዱስ መጽሐፍ የምናውቀው ስለሆነ ማለት ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!

ቀዳማዊና ዘላለማዊ የሆነው ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰብእናችንን ተዋሕዶ በዚህ ዓለም የተገለጸው ሰማያውያንንና ምድራውያንን የለያየው የጥል ግድግዳን ለማፈራረስ ነው።
ለመለያየት ምክንያት የሆነችውን ኃጢኣት በሰውነቱ በመቅጣት የሕግን ትእዛዝ ከፈጸመ በኋላ የዕርቁን ተግባር በወሳኝ መልኩ አከናውኖታል።
በክርስቶስ ቤዛነት የሆነው ይህ ዕርቅ በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ የተወደደ ነበረና እሱ ራሱ በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር አስታረቀ።
ለዚህም ነው ተበዳይ እርሱ፣ ቤዛዊ መሥዋዕት ሆኖ የቀረበው እርሱ፣ ኣስታራቂ እርሱ፣ ታራቂ እርሱ ሆኖ የምናገኘው፤ ለእርሱ የሚሳነው ነገር የለምና ለእኛ ግር የሚል ቢመስልም ለእርሱ ቀላል ነበረ።
በዚህ የዕርቅ ተግባር ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሰውና ሰው፣ ነፍስና ሥጋ ታርቀው በይፋ ተገናኙ፤ በኅብረትና በአንድነትም መኖር ቻሉ፤ በቀኙ ለተሰቀለው ወንበዴ “ዛሬውኑ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ” የሚለው ቃለ ምሕረትና “አባት ሆይ፥ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” የሚለው ቃለ አማኅፅኖ የዕርቁ፣ የግንኙነቱና የኣንድነቱ ማሳያ ኣስረጅ ናቸው።
ስቅለተ ክርስቶስ ነፍሶቻችን ወደ ግዞት ቤት ሳይሆን ወደ ገነት እንዲገቡ፣ የሚቀበላቸውም ራሱ እግዚአብሔር እንዲሆን ያስቻለ ታላቅ መለኮታዊ ፍጻሜ ነው።
እኛ “ክርስቶስ መድኃኒታችን ነው፤ አድኖናል” ብለን በፍጹም ልባችን አምነን የምንመሰክረው፣ እርሱም በመስቀል ላይ ውሎ “ሰላሜን ሰጠኋችሁ” በማለት በመስቀሉ ስላዳነን አጽናኝ መንፈስ ቅዱስንም ስለላከልን ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
የድኅነታችንና የሰላማችን መሠረት የሆኑትን የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ለዓለም ማኅበረሰብ የማብሰርና የማሥረጽ ተግባር የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቍጥር አንድ ተልእኮ ነው፤
ነገረ ሞቱና ነገረ ትንሣኤው በአስተውሎት፣ በጥልቀትና በተመሥጦ ስናስተምር በውስጡ የምናገኘው የዕርቅ፣ የሰላምና የኣንድነት ምስጢር ነው፤
እንደ እውነቱ ከሆነ እኛ የክርስቶስ መልእክተኞች እንደ ቃሉ ራሳችንን ክደን በሚጠበቀው መጠን ተልእኮኣችንን መወጣት ብንችል ኖሮ፣ ኣሁን በዓለማችን የተፈጠረው መለያየትና ግጭት አይኖርም ነበር።
ችግሩን ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ባንችልም በእጅጉ መቀነስና ዓቅሙን ማዳከም እንችል ነበር፤ ነገር ግን ተልእኮአችንን በአግባቡ አለመወጣት ኣንድ ነገር ሆኖ የዓለሙ መሣሪያ ሆነን መገኘታችን “በዕንቅርት ላይ…” ሆኖ ይስተዋላል።
ይሁንና አሁንም ሕዝቡን ወደ አንድነት፣ ወደ ፍቅር፣ ወደ ሰላም፣ ወደ ዘላቂ የጋራ ጥቅምና ወደ ፈሪሀ እግዚአብሔር ማምጣት የጉባኤያችን ዐቢይ ተግባር ሊሆን ይገባል፤ እነዚህ ካሉ የምናጣውም ሆነ የሚያመልጠን የለምና ነው፤
ሀገርን በኀላፊነት ተረክባችሁ በላዕላዊ፣ በማእከላዊና በታሕታዊ መዋቅር የምትገኙ፣ እንደዚሁም አማራጭ ሐሳብ አለን ብላችሁ የምትንቀሳቀሱ ልሂቃነ ሀገር ፣ ሁላችሁም እግዚአብሔርን ከሚያውቅ፣ ከሚያመልክና ከሚፈራ ሕዝብ የተገኛችሁ ናችሁና በልባችሁ እግዚአብሔርን ፍሩ፤ ድምፁንም ስሙ፤ የእርሱ ገንዘብ በሆኑ ፍጡራንም አትጨክኑ፤ ሰውን መያዝ የሚቻለው ኅሊናን በመርታት እንጂ በሌላ አይደለምና፣
የሕዝቡን ፍላጎትና የልብ ትርታ በሚገባ አዳምጡ፤ ሕዝቡ የሚፈልገው በአንድነትና በእኩልነት መኖር፣ በሰላም ወጥቶ መግባት፣ ፍትሕን ማስፈን፣ ለኑሮው የሚበቃ ምጣኔ ሀብትን ማግኘት፣ የእምነት ነፃነትና እኩልነት መረጋገጥ የመሳሰሉት ናቸው።
ሕዝቡ እነዚህ ከተሟሉለት ተደመጠ ማለት ነው፤ ከተደመጠ ደግሞ እርሱም በበኩሉ ያደምጣል፤ ይከተላልም።
ስለሆነም ለሁሉም ልጆቻችንና ወገኖቻችን የምናስተላልፈው ወቅታዊ ጥሪ ሁሉንም ችግሮቻችንን በሰላም ብቻ ለመፍታት ተባበሩ የሚል ነው፤ ከዚህ ውጭ የሚደረገው አማራጭ ሁሉ ለዘላቂ ሰላማችን አይበጅም እንላለን።
በመጨረሻም፦
በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ከበዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን የሚካሄደው ዓመታዊው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተጀመረ መሆኑን ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለመላው ኢትዮጵያውያን እናበሥራለን!!!
እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤
አሜን!!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤
ሚያዝያ ፳፰ ቀን ፳፻፲፰ዓ.ም
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

ዘገባው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ መገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት ነው።

በአሜሪካ ቦስተን ከተማ የበገና እና የመሰንቆ ተማሪዎች ተመረቁ

ሚያዝያ ፳፰/፳፻፲፰ ዓ.ም

 

በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል ቦስተን ንዑስ ማእከል በገና እና መሰንቆ በተለያየ ዙር ሲማሩ የነበሩትን በቦስተን አካባቢ የሚገኙ ሕጻናት እና አዋቂዎቸን ቅዳሜ ሚያዝያ ፳፬ ቀን ፳፻፲፰  ዓ.ም አስመርቋል።

 

በመርሐ ግብሩ አርባ አንድ የበገና እና ሦሰት የመሰንቆ ተማሪዎች የተመረቁ ሲሆን በምረቃው ሥነ ሥርዓት ላይ የበገና እና የመሰንቆ ዝማሬ አቅርበዋል።

 

በመጨረሻም ለተመራቂዎች የምስክር ወረቀት እና የመስቀል ስጦታ ተበርክቶላቸዋል።

 

ዘገባው የአሜሪካ ማእከል ሚዲያ ክፍል ነው።

 

አዲስ አበባ ማእከል 26 ለሚሆኑ የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ለተከታታይ አምስት ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና መጠናቀቁን አስታወቀ

አዲስ አበባ ማእከል 26 ለሚሆኑ የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ለተከታታይ አምስት ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና መጠናቀቁን አስታወቀ

ሚያዝያ ፳፮/፳፻፲፰ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ስብከተ ወንጌልና መንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች አገልግሎት ዋና ክፍል ከተለያዩ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለተውጣጡ 26 የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ለአምስት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ማእከል አስታውቋል።

በሥልጠናው 26 የሚሆኑ የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ አብዛኞቹ የአቡነ ሀብተ ማርያም የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች መሆናቸውን በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል የስብከተ ወንጌልና መንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች ክፍል ኀላፊ አቶ አዘዘ ፀሐዩ ገልጸዋል።

የሥልጠናው ዋና ዓላማ በአብነት ትምህርት ቤት የሚገኙ ደቀ መዛሙርት ብቁ እና ንቁ መሪ አገልጋይ ሁነው እንዲወጡ ማድረግ መሆኑን የገለጹት ኀላፊው በዚህ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ ንቁ ተሳትፎ ያላቸው መሪ ይሆናሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ በማንሳት ሥልጠናው ለነገዋ ቤተ ክርስቲያን ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው ተናግረዋል።

በተጨማሪም ለአብነት ተማሪዎቹ የመጽሐፍ ስጦታ የተበረከተላቸው ሲሆን ነገ ላይ ካህናትና ጳጳሳት ሁነው በቤተ መቅደስ ውስጥ የሚያገለግሉ በመሆኑ ትኩረት ተሰጥቶ ሥልጠናው ሲሰጥ መቆየቱን ገልጸው በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል።

ከዚህ ባሻገር አብነት ትምህርት ቤቶቹ የአልባሳት፣ የመጠለያና የምግብ ችግር ያለባቸው በመሆኑ ማኅበሩ በተለያዩ ጊዜያት ድጋፍ እንደሚያደርግ ያነሱ ሲሆን ዘላቂ መፍትሔ እስኪመጣ ድረስ ምእመናን በተለይም ለዕለት ጉርስ እና ለዓመት ልብሳቸው የሚሆን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።

ዘገባው የአዲስ አበባ ማእከል ነው

👇👇👇👇👇👇👇
የማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ ሚዲያ አውታሮች ይቀላቀሉ
ቴሌግራም፡- http://t.me/mkpublicrelation
የማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት፡- http://www.facebook.com/eotcmkidusan/
ድረገጽ፡- http://www.eotcmk.org
ዩ ቲዩብ፡- http://www.youtube.com/user/EOTCMK
:- https://www.youtube.com/@-zemawetibebzmk7905

ለአንድ ወር ያክል ሲሰለጥኑ የቆዩ 28 ተተኪ አመራሮች መመረቃቸው ተገለጸ

ለአንድ ወር ያክል ሲሰለጥኑ የቆዩ 28 ተተኪ አመራሮች መመረቃቸው ተገለጸ

ሚያዝያ 20/2018 ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል አባላትና ማስተባበሪያ አገልግሎት ዋና ክፍል ከየካቲት 14 እስከ መጋቢት 13 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ለአንድ ወር ያክል ሲያሠለጥናቸው የቆዩ ተተኪ አመራር ሠልጣኞችን  ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም አስመርቋል።

በመርሐግብሩ  የማእከሉ መዘምራን ያሬዳዊ መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን  ትምህርተ ወንጌል በመምህር ወገኔ ማሞ  ተሰጥቷል።

በተጨማሪም ተመራቂ ሠልጣኞች ተግባቦታችን ምን መምሰል አለበት በሚል አጭር ጭውውት ፣ የአመራር ብቃት እና የግጭት አፈታት ላይ ትኩረት ያደረገ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፍ የቀረበ ሲሆን በጥናታዊ ጽሑፉ ላይ ውይይት ተካሒዷል።

በመርሐግብሩ ላይ ተገኝተው ለተመራቂዎች የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት ያስተላለፉትን የማእከሉ ሰብሳቢ ዲ/ን ኃይለማርያም መድኅንን ጨምሮ ሌሎች የማእከሉ አባላት ተገኝተዋል ።

የዋና ማእከሉ የሥራ አመራር አባል የሆኑት አሠልጣኝ ዲ/ን ብርሀኑ ታደሰ በበኩላቸው ተመራቂዎች ለአገልግሎት እንዴት መትጋት እንዳለባቸው፣ በአገልግሎታቸውም በፈተና ሳይረቱ የማኅበሩን ዓላማ እና ርዕይ ተረድተው መቀጠል እንደሚገባቸው አሳስበዋል ።

በመጨረሻም ለተመራቂዎች የምስክር ወረቀት  ተሰጥቶ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆናኗል ።

መረጃው ፦የማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማእከል ሚዲያ ነው

👇👇👇👇👇👇👇
የማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ ሚዲያ አውታሮች ይቀላቀሉ
ቴሌግራም፡- http://t.me/mkpublicrelation
የማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት፡- http://www.facebook.com/eotcmkidusan/
ድረገጽ፡- http://www.eotcmk.org
ዩ ቲዩብ፡- http://www.youtube.com/user/EOTCMK
:- https://www.youtube.com/@-zemawetibebzmk7905

አሜሪካ አቀፍ የአቡነ ጎርጎርዎስ ተማሪዎች ዓመታዊ ውድድር መካሄዱ ተገለጸ

ፖርትላንድ የአጠቃላይ ዋንጫ አሸናፊ ሆነ

ሚያዝያ ፳/፳፻፲፰ ዓ.ም

በአሜርካ በሀገር አቀፍ ደረጃ  ሁለተኛው የአቡነ ጎርጎርዮስ ተማሪዎች የጥያቄና መልስ ውድድር ቅዳሜ ሚያዝያ ፲፯ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም (April 25, 2026)  በችካጎ ከተማ  መደረጉን የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤቶች አስተዳደር ቦርድ ገልጿል::

ውድድሩ በመጀመሪያ በእያንዳንዱ ትምህርት ቤትና ቀጥሎም በማስተባበሪያ ማእከል ደረጃ በአራት የዕድሜ ክልል ተከፍሎ የተደረገ ሲሆን በአንድ የዕድሜ ክልል ሁለት ተማሪዎች ተመድበው ትምህርት ቤቶቻቸውንና የማስተባበሪያ ማእከላቸውን ወክለው በችካጎ ከተማ  ለ National AGA Tewahedo Bee Championship ሃያ አራት ተማሪዎች ተወዳድረዋል።

በዚህ ውድድር በትምህርት ቤቶችና በማስተበባሪያ ደረጃ  ከፍተኛ ውድድር የታየበት መሆኑም ታውቀዋል።

በውድድሩ የምእራብ ማስተባበርያን ወክለው ከተገኙት ት/ቤቶች መካከል አንዱ የሆነው የፖርትላንድ ግ/ጣቢያ አቡነ ጎርጎርዮስ ት/ቤት ከፍተኛ ውጤት በማምጣት የአጠቃላይ ዋንጫው ተሸላሚ ሆኗል።

የዚህ ውድድር ዓላማ በትምህርት ቤቶች የሚሰጠውን የትምህርት አሰጣጥ ወጥነትን ለማስጠበቅ፣ በትምህርት ቤቶችና ተማሪዎች መካከል ያለውን ግንኙኝነት ለማጠናከርና የትምህርት ጥራቱን ለማሻሻል እንደሚጠቅም ተጠቁሟል።

በተጨማሪም ቃለ እግዚአብሔርን ለሌሎች ማስተላለፊያ መንገድ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን ለዚህ ዝግጅት መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉ ለችካጎ የአቡነ ጎርጎርዮስ ተማሪዎች ቤተሰቦች፣ ምእመናን እና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት እንዲሁም  ለችካጎ ንኡስማእከል አባላት ቦርዱ ምስጋናውን አቅርቧል።

ውድድሩ  ቦርዱ ከማእከሉ ሚዲያ ክፍል ጋር በጋራ ያዘጋጀ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል::

ዘገባው የማእከሉ ሚዲያ ክፍል ነው።
👇👇👇👇👇👇👇
የማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ ሚዲያ አውታሮች ይቀላቀሉ
ቴሌግራም፡- http://t.me/mkpublicrelation
የማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት፡- http://www.facebook.com/eotcmkidusan/
ድረገጽ፡- http://www.eotcmk.org
ዩ ቲዩብ፡- http://www.youtube.com/user/EOTCMK
:- https://www.youtube.com/@-zemawetibebzmk7905

የቤተ ክርስቲያን መሪ ዕቅድ

ዲያቆን ይትባረክ መለሰ

ኀዳር ፳፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 ውድ አንባብያን! እንደምን ከረማችሁ? አሜን! የአምላካችን የእግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን! ከወራት በፊት ‹‹የቤተ ክርስቲያን ፍኖተ ካርታ›› በሚል ርእስ የተወሰኑ ጉዳዮችን በተከታታይ አቅርበንላችሁ ነበር፡፡ ዛሬም ከቤተ ክርስቲያናችን አዲሱ የዐሥር ዓመት መሪ ዕቅድ ከዚያው ጋር የተገናኘ ሐሳብ አቅርበንላችኋል፡፡

ዕቅድ የአንድ ተቋም የህልውና ጥያቄን የሚመልስ ትልቅ ጉዳይ እንደሆነ ይታመናል፡፡ የማያቅድ ተቋም ቀርቶ ግለሰብ  እንኳን  ራሱን በትክክል መምራት፣ የሚያስበውንም ማሳካት፣ የሕይወትን እንቅፋቶችንም ማስወገድ፣ ነገን የተሻለ ማድረግ አይችልም፡፡

ቤተ ክርስቲያናችንም ከ ስልሳ ሚሊዮን በላይ አማኞችን (ምንጭ-ፍኖተ ካርታው) ከአርባ ሺህ ያላነሱ ገዳማትንና አድባራትን፣ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ አገልጋዮችን፣ በብዙ ዋጋ የሚገመቱ መንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብቶችን የምታስተዳድር፣ ብዙ መንፈሳዊና አካላዊ ጦርነት ከብዙ አቅጣጫ ያለባት ቤተ ክርስቲያን በዕቅድ ካልተመራች ምድራዊ አገልግሎቷን ሰማያዊ በረከቷን ማቆየትና ማሸጋገር ይከብድባታል፡፡

ዓለም አቀፋዊቷና ጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን እስከዛሬ ድረስ በመሪ ዕቅድ አለመመራቷ እጅግ ዋጋ እንዳስከፈላት ጥናት የሚያስፈልገው አይደለም፡፡ ሀብቷን ከውጭ ወራሪ ከውስጥ ሰርሳሪ እንዳትታደግ፣ መንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብቷ ለልጆቿ ሳይሆን ለአማሳኞችና ለሰርጎ ገቦች ሲሳይ እንዲሆን፣ ዳሯ እየተፈታ ማሐሏ ዳር እንዲሆን አድርጓል፡፡

ብዙ የደከሙ አገልጋዮቿ የሚንከራተቱባት ፍትሕ ርትዕ ጠፍቶ ለጠላት አጀንዳ የተጋለጠች እንድትሆን አድርጓት ከመቆየቱ በተጨማሪ በርካታ ምእመናን ልጆቿ የሌላ በረት ሲሳይ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ ዛሬም ችግሩ አልተቀረም፡፡

ትናንትን ለመዘከር፣ ዛሬን ለመመስከር፣ ነገን ለመፍጠር ዕቅድ ዓይነተኛ መሣሪያ ነው፡፡ ዘግይቶም ቢሆን ቤተ ክርስቲያን የዐሥር ዓመት መሪ ዕቅድ አዘጋጅታለች፡፡ በየደረጃው ላሉ ባለ ድረሻ አካላትም ዕቅዱን እያስተዋወቀች ትገኛለች፡፡

ማኅበረ ቅዱሳንም እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ ዕቅዱ እንዲፈጸም፣ ቤተ ክርስቲያንም ዓላማዋን እንድታሳካ የራሱን አስተዋፅኦ እያደረገ ይገኛል፡፡ ለዚህም ይረዳው ዘንድ ፍኖተ ካርታውን ለመተግበር እንዲቻል በስልታዊ ዕቅዱ ውስጥ በማካተት በርካታ ሥራዎችን እየሠራ ሲሆን ከእነዚህም መካከል ከኅምሳ ባላነሱ ማእከላቱ አማካኝነት የባለሙያዎች ኅብረት እንዲቋቋም፣ ሥልጠናዎች እንዲሰጡ፣ የፓናል ውይይቶች እንዲደረጉ፣ የአሠልጣኞች ሥልጠና እንዲሰጥ፣ የሚድያ ሽፋን እንዲያገኝ፣ ሕዝባዊ ንቅናቄ እንዲፈጠር የሚያስችሉና መሰል ጉዳዮችን በስልታዊ ዕቅዱ አካቶ እየሠራ ይገኛል፡፡

የዚህ ጽሑፍ ዓላማም ፍኖተ ካርታውን ለምእመናን በማስተዋወቅ፣ ግንዛቤን መፍጠር፣ ተነሣሽነትን መጨመር፣ ዕቅዱን በማስፈጸምና በመፈጸም ረገድ የእኔነት ስሜት መፍጠር፣ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችንና የዕቅድ ፈጻሚዎችን ከደጋፊና ባለድርሻ አካለት ጋር እንዲቀናጁ ማመቻቸትን፣ የአመለካከት ለውጥ ማምጣትን ታሳቢ ያደረገ ጽሑፍ ሲሆን ወደፊትም የፍኖተ ካርታውን ዝርዝር ይዘቶች፣ የማስፈጸሚያ ስልቶቹን እንዲሁም ሊያሳካቸው የታሰቡ ግቦችን በተከታታይ ለማድረስ ጥረት የሚደረግ ይሆናል፡፡

ቸር እንሰንብት!

የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልዓተ ጉባኤ መጠናቀቁን አስመልክቶ መግለጫ ተሰጠ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የሚመራው፣ የሐዋርያት መንበር ወራሽ የሆነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ

“ወይኩን ጉባኤ ሊቃነ ኤጴስ ቆጶሳት ወኤጲስ ቆጶሳት ክልዔተ ጊዜ በበዓመት ወይትናገሩ በእንተ ግብረ አብያተ ክርስቲያናቲሆሙ ወያሰስሉ ዕቅፍታተ …

የሊቃነ ጳጳሳትና የጳጳሳት ምልዓተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ ይሁን ስለአብያተ ክርስቲያናት የሚገባውን ሁሉ ይነጋገሩ የሐዋርያዊ ተልእኮ መሰናክሎችንም ሁሉ ያስወግዱ” ተብሎ በመጀመሪያው የሐዋርያት ቀኖና፣ በሁለተኛው ቀሌምንጦስ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ከጥቅምት 11 – ጥቅምት 17 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና የምጣኔ ሀብት ዕድገት፣ ስለ ሀገር ሰላምና አንድነት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና ሐዋርያዊ ተልእኮ መስፋፋት  ስለ ሰው ልጅ ሁሉ ደኅንነት ሰፊ ውይይት አድርጓል፡፡

ወቅቱን ያማከሉና ዘላቂ የቤተ ክርስቲያንን ተቋማዊ ሕልውና የሚያረጋግጡ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ልዕልናንን የሚያስጠብቁ፣ ለምእመናን ደኅንነትና ለአገልጋዮች ሕይወት በሚጠቅሙ፣ መንሳፈዊ አስተዳደርንና ማኅበራዊ ጉዳዮችን መሠረት ባደረጉ አጀንዳዎች ላይ በመንፈስ ቅዱስ አንድነት በመወያየት ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን ጠቃሚ የሆኑ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

በዚሁ መሠረት፡-

1.ሁለንተናዊ ሰላምና መረጋጋት የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሃይማኖታዊ መሠረቷ፥ የሥርዓተ ቅዳሴዋና የምሥጢራት አገልግሎቷ አካል፣ የመንፈሳዊና ማኅበራዊ ሥምሪቷ ማእከላዊ ዐምድ በመሆኑ በግንቦት 2017 ዓ.ም. ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሠየመው የሀገራዊ ሰላምና የቤተ ክርስቲያን አንድነት ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥል፤ የደረሰበትንም ውጤት ለግንቦት 2018 ዓ.ም ምልዓተ ጉባኤ እንዲያቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ መመሪያን አስተላልፏል::

2.በትግራይ አህጉረ ስብከት የሚገኘው ሕዝበ ክርስቲያን ሕዝባችንና ወገናችን ስለሆነ አብያተ ክርስቲያናቱና ገዳማቱም የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ሀብቶች በመሆናቸው፣ አህጉረ ስብከቱም የተደራጁት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በመሆኑ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕግና ቀኖና ተጠብቆ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ልዕልና ተከብሮ፣ የመዋቅር ግንኙነቱን ወደ ቀደመ ቦታው እንዲመለስ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የሰላም፣ የአንድነትና የይቅርታ በር ክፍት መሆኑን ከመግለጽ ጋር ቅዱስ ሲኖዶስ በክልሉ ለሚገኙት አባቶች፣ ካህናትና ምእመናን ያልተቋረጠ የሰላም ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

የቀድሞዎቹ ቅዱሳን አባቶቻችን ዋጋ ከፍለው፣ ቀኖናዊ ሥርዓቷንና ክብሯን ጠብቀውና አስጠብቀው ፣  አንድነቷን አጽንተው ያወረሱንን አሐቲ ቤተ ክርስቲያን የቀደመ ሉዓላዊ ክብሯ እንደተጠበቀ ለመጭው ትውልድ ማስተላለፍ የበለጠ ዋጋ ያሰጣልና ቀደም ሲል ለዚሁ ጉዳይ የተሠየመው ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥል፣ ሊቃውንቱ፣ ካህናቱና መላው ሕዝባችንም  የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት ሁሉ  የበኩላችሁን እንድትወጡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በአጽንኦት ያሳስባል፡፡

3.ቅዱስ ሲኖዶስ አባት እንዲመደብላቸው ጥያቄ ባቀረቡ አህጉረ ስብከት ዙሪያ የውሳኔ ሐሳብ የሚያቀርቡ ብፁዓን አባቶችን በመሰየምና ተገቢውን ውይይት በማድረግ፡

ሀ) ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ የኢሉ አባቦራ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ፣

ለ) ብፁዕ አቡነ ቶማስ የአዊና መተከል አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ የምሥራቅ ጎጃምን ሀገረ ስብከት ደርበው እንዲመሩ፣

ሐ) ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የደቡብ ወሎና ከሚሴ አህጉረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ፣

መ) ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጳጳስ የምሥራቅ ወለጋና ሆሮ-ጉድሩ ወለጋ አህጉረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ

ሠ)  በተጨማሪም የሸካ ዞን ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ተብሎ ራሱን ችሎ በሀገረ ስብከት ደረጃ እንዲቋቋም፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ሀገረ ስብከቱን እንዲያደራጁና እንዲመሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

4.ነባሩና ጥንታዊው የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ገድል እንደተጠበቀ ሆኖ ገድለ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በሚል ያለአግባብ በአንድ ግለሰብ ተዘጋጅቶ እየተሠራጨ ያለው መጽሐፍ በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ ያለበት ግድፈትና የስሕተት ትምህርት በሙሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሰ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የማይወክል ሆኖ በመገኘቱ ተወግዟል፤

በውስጡ የያዛቸውም የተሳሳቱ ትምህርቶች በሙሉ ተቀባይነት ስለሌላቸው መጽሐፉ ለጥናትና ምርምርም ሆነ ለማጣቀሻ አገልግሎት እንዳይውል፣ በሥርጭት ላይ የዋለው መጽሐፍ እንዲታገድና በድጋሚም እንዳይታተም፣ ለየአህጉረ ስብከቱ ሠርኩላር እንዲተላለፍ፣ የአፈጻጸም ክትትል እንዲደረግና አጠቃላይ ሁኔታው በሊቃውንት ጉባኤ በኩል በሚዲያ እንዲገለጽ፣ የአስተምህሮ ስሕተትን በማካተት አሳትመው ያሰራጩት ግለሰብ በቋሚ ሲኖዶስ ተጠርተው እንዲጠየቁና የፈጸሙትን ስሕተት ዐውቀው ወደፊት ተመሳሳይ ስሕተት እንዳይፈጽሙ ጥብቅ መመሪያ እንዲሰጣቸው፣

መጽሐፉ እንዲመረመር ያደረገው የደብረ ሊባኖስ አንድነት ገዳምና የገዳሙ የቅኔ መምህር መጋቤ ምሥጢር አባ ክንፈሚካኤል ወልደ ገብርኤል የምስጋና ደብዳቤ እንዲጻፍላቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

5.በሰሜን ካሊፎርኒያ ኔቫዳና አሪዞና ሀገረ ስብከት የኆኅተ ሰማይ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ወቅድስት አርሴማ አንድነት ገዳም መንፈሳዊ ኮሌጅና የአብነት ምስክር ጉባኤ ቤት ለማቋቋም በጠየቀው መሠረት እንዲፈቀድ ሆኖ የትምህርት አሰጣጥ ፖሊሲውና ሥርዓተ ትምህርቱ፣ የሰው ኃይል አደረጃጀቱና መዋቅራዊ ተጠሪነቱ ተዘጋጅቶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ተጠንቶ ከውሳኔ ሐሳብ ጋር ለግንቦት 2018 ርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ እንዲቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤

6.በምዕራብና በመካከለኛው ካናዳ የሚገኙት ሁለቱ አህጉረ ስብከት ከአሁን በፊት በ2017 ዓ.ም. በተሰጠው ውሳኔ መሠረት ያለ ጣልቃ ገብነት በየራሳቸው እንዲተዳደሩና የኤድመንተንና አካባቢው ሀገረ ስብከት የመካከለኛው ካናዳ ኤድመንተንና አካባቢው ሀገረ ስብከት በሚል ሥያሜ እንዲስተካከል ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡

7.በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በምንጃር ሸንኮራ ወረዳ በአረርቲ ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዓል ለማክበር ሄደው አዲሱን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በመጐብኘት ላይ እያሉ አደጋ በደረሰባቸው ምዕመናን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሰማውን ሐዘን እየገለጸ እግዚአብሔር አምላካች ላረፉት ወገኖቻችን ዕረፍተ ነፍስ እንዲሰጥልን ከመጸለይ ጋር አካላዊ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች ለማሳከምና የተጎጂ ቤተሰቦችን ለመርዳት የገንዘብ ድጋፍ እንዲደረግ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ለወደፊቱም በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ዙሪያ በሚገነቡ ሕንጻ ግንባታዎች አደጋ ከመድረሱ በፊት ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲደረግ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ያሳስባል፤

8.በመላው ኢትዮጵያ በሚገኙ ገዳማት ያሉት መነኰሳትና መነኰሳይያት ለአገልግሎትና ጉዳይ ለማስፈጸም ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ክብራቸውና ገዳማዊ ሕይወታቸው ተጠብቆ ጉዳያቸውን እስከሚፈጽሙ ድረስ የገዳማት ኅብረቱ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በኩል ማረፊያ የሚሆን ቦታ እንዲዘጋጅላቸው፣

የአንድነት ገዳማት ኅብረቱ መተዳደሪያ ደንብ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሕግ አገልግሎት መምሪያ በኩል ታይቶና ተመርምሮ እንዲቀርብ፣

በአጠቃላይ በአንድነት ገዳማት ኅብረት የቀረበው የገዳማውያንና ገዳማውያት ማረፊያ እና የገቢ ማስገኛ ሁለገብ ሕንጻ ግንባታ የትግበራ ዕቅድ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል በዘርፉ ባለሙያዎች ታይቶና ተገምግሞ ከባለሙያ አስተያየቶችና የውሳኔ ሐሳብ ጋር ተጠንቶ ለግንቦት 2018 ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ እንዲቀርብ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወስኗል፡፡

9.በበዓላት አከባበር፣ በመንፈሳዊ አገልግሎት አፈጻጸም ዙሪያ የሚታዩ ግድፈቶች፣  ያልተገቡ እንቅስቃሴዎችና ከሥርዓት የወጡ የአገልግሎት አፈጻጸሞች መታረም ስላለባቸው በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በሚሰየሙ ሊቃውንትና ባለሙያዎች ለመመሪያና ለማስተማሪያ የሚሆን ሰነድ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተገቢውን ውሳኔ ያስተላለፈ መሆኑን እየገለጽን ያለጠባሳ የሚያድኑ ሐኪሞች፣ ያለቅሬታ የሚያስታርቁ ሽማግሌዎች በነበሩባትና ባሉባት ሀገር ተመካክሮ ችግርን አለመፍታት ተገቢ አይደለምና ሀገራችንን እንወዳለን፣ ሕዝባችንን እናከብራለን የምትሉ፣ የዜጎችን ደኅንነት የማስጠበቅ ኃላፊነት ያለባችሁ ሁሉ ክቡር የሆነው የሰው ልጅ ሕይወት በከንቱ እንዳይጠፋ፣ አካሉ እንዳይጐድል የሀገር ልማትና መልካም ገጽታ እንዳይበላሽ ጠላት መባባሉ ቀርቶ፣ የጦር መሣሪያ ትግል ተወግዶ፣ በእኩልነትና በመስማማት ሰላማዊ የችግር አፈታት መንገድን ተከትላችሁ በውይይትና በጥበብ ልዩነቶችን በመፍታት የተሟላ ሀገራዊ ሰላም እንዲሰፍን ታደርጉ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ከአደራ ጭምር ሐዋርያዊ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

በመጨረሻም የሀገራችን ኢትዮጵያና የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ሕልውና ስለማይነጣጠሉ፣ ሀገራችን በሉአላዊነቷ እንድትቀጥል የቤተ ክርስቲያናችን የአንድነት መዋቅሯ የበለጠ ተጠናክሮ፣ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮዋ ሰፍቶ፣ ለትውልድ እንድትሻገር፣ ሕዝባችን ደኅንነቱና ሰላሙ ተጠብቆ እንዲኖር ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ ሁሉም የቤተ ክርስቲያናችን መምህራን፣ ካህናትና ሕዝባውያን፣ መነኰሳትና መነኰሳይያት በሙሉ በፍቅርና በአንድነት ዘወትር በመጸለይ  ዘመኑ ከደረሰበት አሠራርና ጥበብ በላቀ ሁኔታ ከፍ ብለን ትውልዱን ለመዋጀት እንድንችል የበኩላችሁን እንድትወጡ በማሳሰብ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባውን አጠናቋል፡፡

 

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት ፲፯/፳፻፲፰ ዓ.ም

አዲስ አበባኢትዮጵያ

 

ማኅበረ ቅዱሳን ለመጀመሪያ ጊዜ ያስተረጎማቸውን “መጽሐፈ ግንዘት” እና ˝የዮሐንስ ወንጌል ቅጽ ሁለት” መጻሕፍትን አስመረቀ!

ጥቅምት ፲ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ መምህር ዋሲሁን በላይ ከዚህ ቀደም በርካታ መጽሐፍት ተጽፈው፣ ተተርጒመው፣ ታትመው ለአገልግሎት መዋላቸውን ገልጸው እነዚህን “መጽሐፈ ግንዘት” እና  ˝የዮሐንስ ወንጌል በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ  ቅጽ ሁለት”‌ መጻሕፍትን ግን ማኅበሩ ለመጀመሪያ ጊዜ ማስተርጎሙን አሳውቀዋል፡፡

ጥቅምት ፰ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም  በዋናው ማእከል ሕንጻ ሦስተኛ ወለል ንቡረ እድ  ድሜጥሮስ አዳራሽ በተከናወነው መርሐ ግብሩ ላይ መጽሐፍቱ በአባቶች ተመርቀዋል፡፡  መጻሕፍቱን በመተርጎም ኃላፊነታቸውን ለተወጡ አካላትም የምስክር ወረቀትና ስጦታ ተሰጥቶአል።

በተጓዳኝ ዋና ሥራ አስፈጻሚው መጻሕፍቱ እዚህ እንዲደርሱ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላት ምስጋናን አቅርበዋል።

በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት ሊቀ ሊቃውንት ዮሴፍ ደሳለኝ የሊቃውንት ጉባኤ አባልና  የአራቱ መጻሕፍት ጉባኤያት የትርጓሜ መምህር ደግሞ “መጽሐፈ ግንዘት” የተሰኘውን እንዲሁ መምህር ቀሲስ ዐቢይ ሙሉቀን የሐመር መጽሔት ምክትል ዋና አዘጋጅ ˝የዮሐንስ ወንጌል በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ  ቅጽ ሁለት”  በተመለከተ የመጽሐፍ ዳስሳ አድርገዋል።

የቤተ ክርስቲያን ፍኖተ ካርታ

ውድ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! እንደምን ሰነበታችሁ? የአምላካችን የእግዚአብሔር ስም የተመሰገን ይሁን! ባለፈው ክፍለ ጽሑፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የመጪው ዐሥር ዓመታት የመንፈሳዊ እና ዘላቂ ልማት ግቦችን ማስተዋወቅን ዓላማ አድርገን፣ በክፍል አንድ ስለ ፍኖተ ካርታ (ዕቅድ)፣  በክፍል ሁለት ደግሞ ከዋና ዋና ዘርፎች በመንፈሳዊ ዘርፍ የተዘረዘሩ ግቦችን አቅርበንላችሁ ነበር፡፡ በክፍል ሦስት ደግሞ ቀጣዩን ክፍል ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡

አገልግሎቴን አከብራለሁ!

የመዝገበ አእምሮ ዝግጅት ከመጀመሩ በፊት በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር አጥኚዎች የተወሰኑ የቤተ ክርስቲያንን የዕውቀት ሀብቶች ለመሰነድ ጥረቶች መደረጋቸውን የሚያስረዱ መረጃዎች አሉ። በአባቶች ብዙ ድካምና ጥረት ተሰንደው ከሚገኙት የቆዩ የቤተ ክርስቲያን የዕውቀት ሀብቶች መካከል ስንክሳር፣ ሃይማኖተ አበውና ገድላት የሚሉት መጻሕፍት ይጠቀሳሉ፡፡ ስንክሳር “የመላእክትን ማዕርግና ሹመት የሚያስረዳ፣ የነቢያትንና የሐዋርያትን፣ የጻድቃንንና የሰማዕታትን፣ የደናግልንና የመነኮሳትን ምግባር፣ መከራና ዕረፍት ከዕለት እስካመት የሚነግር፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፤ የእመቤታችንን ዜና፣ የልጇንም በጎ ሥራ ኹሉ በሰፊው” የሚያስረዳ መጽሐፍ ነው፡፡ (ደስታ፣ ፲፱፻፷፪፤ ፲፩፻፺፬)