አውስትራሊያ ማእከል ዝክረ ቅዱስ ያሬድ መርሐ ግብር አካሄደ
የደብረ ልዑላን መድኃኔዓለም የ፬ቱ ትርጓሜ መጻሕፍት ምስክር ጉባኤ ቤት ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት አስመረቀ።
የደብረ ልዑላን መድኃኔ ዓለም የ፬ቱ ትርጓሜ መጻሕፍት ምስክር ጉባኤ ቤት ላለፉት አምስት ዓመታት ያስተማራቸውን ፳፫ ደቀ መዛሙርት ግንቦት ፲፮/፪፳፲፰ ዓ/ም አስመርቋል።
በማማያዝ ጉባኤ ቤቱ ዘመናዊ ባለ ሁለት ወለል የጉባኤ ቤቱን መንታ ሕንጻ ማስመረቁም ተነግሯል።
የደብረ ልዑላን መድኃኔዓለም የ፬ቱ ትርጓሜ መጻሕፍት ምስክር ጉባኤ ቤት በአጼ ቴዎድሮስ መሠረት ጣይነት የተጀመረና ጥንታዊ ጉባኤ ቤት ሲሆን በተለያዩ ምክንያቶች ላለፉት መቶ ዓመታት ተቋርጦ መቆየቱ ተነግሯል።
ከመቶ ዓመታት መቋረጥ በኋላ በ ፪፳፲፩ ዓ/ም በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሚካኤል መልካም ፈቃድ እና በሊቀ ሊቃውንት እዝራ ሐዲስ መሠረት ጣይነት ጉባኤ ቤቱ እንደገና ሥራ እንዲጀምር ተደርጓል።
ጉባኤ ቤቱ በመጀመሪያ ዙር ፳፪ ደቀ መዛሙርትን አስተምሮ ያስመረቀ ሲሆን ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ፳፫ ደቀ መዛሙርትን አስመርቋል።
በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ቃለ ምዕዳን የሰጡት የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ከደቀ መዛሙርቱ ብዙ እንደምትጠብቅና ደቀ መዛሙርቱም ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ እንዲያገለግሏት አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ሥዩማን ቀሲስ ምሕረት ሞላ በበኩላቸው ሀገረ ስብከቱ ከጉባኤ ቤቱ ጋር ተናቦ እየሠራ መሆኑን ገልጸው ለዚህም አጥጋቢ ፍሬ ማየት እንደተቻለ ተናግረዋል።
የምስክር ጉባኤ ቤቱ መምህር መምህረ መምህራን በጽሐ ዓለሙ ” እስካሁን እየተማራችሁ ትፈተኑ ከነበረበት እየተፈተናችሁ ወደ ምትማሩበት ትሄዳላችሁ ” በማለት ተመራቂ ደቀ መዛሙርት ቤተ ክርስቲያን የሰጠቻቸውን አደራ እንዲወጡ አሳስበዋል።
መምህረ መምህራን በጽሐ ዓለሙ ተመራቂ ደቀ መዛሙርት በፍጹም መንፈሳዊነት ሕዝባቸውንና ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ አደራ ያሉ ሲሆን ተመራቂ ደቀ መዛሙርትም ምእመናኑን እጅ በመንሳትና ቃል በመግባት የመምህራቸውን አደራ ተቀብለው በይፋ ተመርቀዋል።
ማኅበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ አንድ መምህርና ለ፳፫ ደቀ መዛሙርት ወርኃዊ ድጎማ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን ሰማንያ አሐዱ ግእዝ መጽሐፍ ቅዱስ ለእያንዳንዳቸው ተመራቂ ደቀ መዛሙርት በስጦታ አበርክቷል።
በምርቃት መርሐ ግብሩ ንግግር ያደረጉት በማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገትና መንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች ዳይሬክተር ዲ/ን ደረጀ ጋረደው በበኩላቸው “ጉባኤ ቤቱ የቀደምት መምህራንን ታሪክ ዳግም እውን አድርጎ ያሳየ መሆኑን አንስተው ተመራቂ ደቀ መዛሙርት የዚህ ታሪክ ተካፋይ ሆናችሁ በመመረቃችሁ ማኅበረ ቅዱሳን ታላቅ ደስታ ይሰማዋል” ብሏል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ጉባኤ ቤቱ ዘመናዊ የሆነና በውስጡ በርካታ ክፍሎችን የያዘ ባለ ሁለት ወለል መንታ ሕንጻ ማስመረቁ ተነግሯል። የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ሕንጻውን በይፋ መርቀዋል።
ጉባኤ ቤቱ ከዚህ በፊት ባልተሟላና በአስቸጋሪ ሁኔታ በአጼ ቴዎድሮስ ባድማ ይካኼድ የነበረ ሲሆን አዲሱ ሕንጻ ግን ማደሪያ ክፍሎችን ጨምሮ መማሪያ አዳራሽ፣ ደረጃውን የጠበቀ ዲጂታል ላይብሪ ፣ ቤተ መጻሕፍት፣ ማማከሪያ ክፍል፣ መመገቢያና ሌሎች ክፍሎችን በማሟላት ለአገልግሎት ዝግጁ ተደርጓል።
መምህረ መምህራን በጽሐ ዓለሙ ሕንጻው ተገንብቶ እንዲጠናቀቅ ርብርብ ያደረጉ ኦርቶዶክሳውያንን አመስግነው ” እውነተኛ የተግባር ሥራ ያየንበት ቢሆንም ሥራችንን ግን ገና አልጨረስንም” ሲሉ ተናግረዋል።
በደቀ መዛሙርቱ እና በጉባኤ ቤቱ ሕንጻ ምርቃት መርሐ ግብር ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ የአካባቢው ምእመናንና የተመራቂ ቤተሰቦች በተገኙበት ተከናውኗል።
“ሕያው ዜማከ ወሕያው ድርሳንከ” በሚል መሪ ቃል የዝክረ ቅዱስ ያሬድ መርሐ ግብር እንደሚከናወን የዜማና ኪነ ጥበባት ማእከል አስታወቀ
ግንቦት ፲፪/፳፻፲፰ ዓ.ም
በማኅበረ ቅዱሳን የዜማና ኪነ ጥበባት ማእከል “ሕያው ዜማከ ወሕያው ድርሳንከ” በሚል መሪ ቃል የዝክረ ቅዱስ ያሬድ መርሐ ግብር በዋናው ማእከል፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ማእከላት፣ በወረዳ ማእከላት እንዲሁም በግቢ ጉባኤያት እንደሚከናወን አስታውቋል።
ማኅበረ ቅዱሳን ከያዛቸው ዕቅዶች መካከል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መዝሙራትን፣ የዜማ መሣሪያዎችንና ኪነ ጥበባትን በተመለከተ የተለያዩ መርሐ ግብራትን፣ ዐውደ ጥናቶችን በማድረግ ሥርዐታቸው እንዲከበርና ምእመናን አገልግሎታቸውን እንዲረዱ ማድረግ ሲሆን አንዱ የዝክረ ቅዱስ ያሬድ መርሐ ግብርን ማከናወን ነው በማለት የዜማና ኪነ ጥበባት ማእከል ገልጿል።
በዚህም መርሐ ግብሩ የሚከናወነው ዝክረ ቅዱስ ያሬድ ለኦርቶዶክሳዊ መዝሙር፣ ለመንፈሳዊ ኪነ ጥበብ፣ ለአስተምሮዋም መሠረት ስለሆነ የእርሱን ሕይወቱን፣ ሥራዎቹን በማውሳትና አርአያ እንዲሆን በማድረግ እንዲሁም ምእመናን እንዲያውቁትና ሥርዐቱ ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ ለማድረግ መሆኑም ተገልጿል።
ቅዱስ ያሬድ የተሰወረበት ዕለት ግንቦት 11 ስለሆነ ሙሉ የግንቦት ወር በማእከላት፣ በወረዳ ማእከላትና በግቢ ጉባኤያት የተለያዩ ጉባኤ በማድረግ የሚከበር ሲሆን የዋናው ማእከልም ከአዲስ አበባ ማእከል ጋር በመሆን እንደሚያከብር ተጠቅሷል።
በማያያዝ እንደ ዋናው ማእከል የዝክረ ቅዱስ ያሬድ መርሐ ግብር መከናወን ከተጀመረ ከ10 ዓመት በላይ እንደሆነው የገለጸው የዜማና ኪነ ጥበባት ማእከል አክሎም በዘንድሮው ዓመትም ሁለቴ የሚያከብር ሲሆን የመጀመሪያው የፊታችን እሑድ ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም ጠዋት ከቅዳሴ በኋላ ከሐመረ ኖኅ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም እና ከሰዓት ከቀኑ 10፡00 ጀምሮ ከጉለሌ አምባ ደብረ መድኃኒት ቅድስት ኪዳነ ምሕረትና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌል ጋር በመተባበር በዐውደ ምሕረት ይከበራል፤ ሁለተኛው ደግሞ ማጠቃለያ መርሐ ግብር ሰኔ 7 ቀን 2018 ዓ.ም በማኅበሩ ሕንፃ ላይ እንደያሚከብር ተገልጿል።
በመጨረሻም በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ ያሉ ጥሪ የሚደረግላቸው መምህራን፣ ዘማሪያን፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋዮች፣ የማኅበሩ አባላትና ምእመናን እንደሚገኙ የገለጸው የዜማና ኪነ ጥበባት ማእከል አያይዞም ሁሉም እንዲገኙ ጥሪ አቅርቧል።
በማኅበረ ቅዱሳን ወሊሶ ማእከል ያስተማራቸውን ዲያቆናት ማዕረገ ቅስና እንዲቀበሉ በማድረግ አስመረቀ
በማኅበረ ቅዱሳን ወሊሶማእከልያስተማራቸውንዲያቆናትማዕረገቅስናእንዲቀበሉበማድረግአስመረቀ
ግንቦት ፲፩/፳፻፲፰ ዓ.ም
በማኅበረ ቅዱሳን ወሊሶ ማእከል ላለፉት ሦስት ወራት በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥር ከሚገኙ ዘጠኝ ወረዳዎች የተወጣጡ 17 ዲያቆናትን ሲያሠለጥን የቆየ ሲሆን ከሠልጣኞቹ መካከል 8 ደቀ መዛሙርት ማዕረገ ቅስና እንዲቀበሉ በማድረግ የተቀሩት ደግሞ ተጨማሪ የአቅም ማጎልበቻ ትምህርቶችን እንዲያገኙ መደረጉ ተገልጿል።
ደቀ መዛሙርቱ ግንቦት 8 ቀን 2018 ዓ.ም በሸገር ሀገረ ስብከት በአጃምባ ደብረ ብርሃን አቡነ ተ/ሃይማኖት ቤተ ክርስተያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ፣ የሸገር አህጉረ ስብከት እና የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም የበላይ ጠባቂ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ማዕረገ ቅስና ተቀብለዋል።
በማኅበረ ቅዱሳን የወሊሶ ማእከል ሰብሳቢ አቶ ንጉሤ አብዴቾ እንደተናገሩት የወሊሶ ማእከል በሀገረ ስብከቱ ያለውን የአገልጋይ እጥረት ለመፍታት ለመምህራን እና ለደቀ መዛሙርት ወርኃዊ ድጎማ በማድረግ ፣ ንዋያተ ቅዱሳትን ጨምሮ የመማርያ መጻሕፍትን እና ሌሎች ቁሳቁሶችን በመደገፍ በርካታ ዲያቆናትን ማፍራት የተቻለ ሲሆን በአሁኑ ሰዓትም በሀገረ ስብከቱ ሦስት ወረዳዎች በሚገኙ ሦስት አጥቢያዎች ከ85 በላይ ዲያቆናትን እያስተማረ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል።
የወሊሶ ማእከል በሀገረ ስብከቱ ስላለው የአገልጋይ እጥረት የዳሰሳ ጥናት በማድረግ መደበኛ አገልጋይ ከሌላቸው አጥቢያዎች አምስት ደቀ መዛሙርትን እንዲሁም አንድ ካህን ብቻ ካላቸው ሦስት ደቀ መዛሙርትን በመውሰድ የክህነት አገልግሎት እና የትምህርተ ሃይማኖት ኮርሶችን ሲወስዱ ከቆዩ በኋላ ማዕረገ ቅስና እንዲያገኙ መደረጉ ተገልጿል።
ተከታታይ ትምህርት በማስተማር ዲያቆናትን ከዲቁና ወደ ቅስና ያሳደገው ወሊሶ ማእከል ይህን እና ሌሎች አገልግሎቶችን ተግባራዊ ለማድረግ ፈተናዎች እንደገጠሙትም ለማወቅ ተችሏል። በሀገረ ስብከቱ የአገልጋይ እጥረት ያለባቸው አካባቢዎች የጸጥታ ችግሮች ያሉባቸው፣ ከወረዳ ከተሞችም የራቁ በመሆናቸው በተፈለገው ጊዜ መድረስ እና መረጃ መሰብሰብ አለመቻሉ፣ ወደ ቅስና ገብተው ቤተ ክርስተያንን ማገልገል የሚችሉ ፍላጎት ያላቸው ደቀ መዛሙርትን ማግኘት አለመቻል እና የምልመላ መሥፈርቶችን የሚያሟሉ ደቀ መዛሙርት ቁጥር ማነስ ማእከሉ አገልግሎቱን በተፈለገው ደረጃ ለማዳረስ ፈተና ሆነው መቆየታቸው ተነግሯል።
አገልጋዮቹ ከዚህ ቀደም ለዓመታት ቤተ ክርስቲያንን በዲቁና ሲያገለግሉ የነበረ እና የተዘጋጀውን የምልመላ መስፈርት ያሟሉ ስለሆነ ወደየ አካባቢያቸው ሲመለሱ የተሟላ የቅስና አገልግሎት ይሰጣሉ ተብሎም ይጠበቃል።
ባለፉት ሦስት ወራት በተሰጠው ሥልጠና የዋናው ማእከልን ድጋፍ ጨምሮ በአጠቃላይ የወሊሶ ማእከል ከአራት መቶ ሺ ብር በላይ ድጋፍ ማድረጉን ከማእከሉ የተገኘው መረጃ አመላክቷል።
“ባለፉት 34 ዓመታት በአገልግሎት የራቁትን ማቅረብ፣ የቀረቡትን ደግሞ ለንስሐ ሕይወት ለእግዚአብሔር መንግስት ማብቃት ትልቅ ነገር ነው።” ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሶማሌ ጅግጅጋና የምሥራቅ አርሲ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል
ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሶማሌ ጅግጅጋና የምሥራቅ አርሲ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ የምስካየ ኃዙናን መድኃኔዓለም አንድነት ገዳም የበላይ ኀላፊ ሊቀ ጳጳስ ተወካይ በጉባኤው ተገኝተው መመሪያ አስተላልፈዋል።
ብፀዕነታቸው ለ34ኛ ዓመት ምሥረታ በዓል እንኳን አደረሳችሁ ያሉ ሲሆን “ባለፉት 34 ዓመታት በአገልግሎት የራቁትን ማቅረብ፣ የቀረቡትን ደግሞ ለንስሐ ሕይወት ለእግዚአብሔር መንግስት ማብቃት ትልቅ ነገር ነው።” በማለት ተናግረዋል።
ብፁዕነታቸው አክለውም “ባለፉት ዓመታት እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር እየሠራ ምእመናንን ወንጌል በማስተማር በሃይማኖታቸው ጸንተው ፍጻሜያቸው እንዲያምር በማድረግ፣ በተለያዩ አካባቢዎች አብያተ ክርስቲያናትን በማስከፈት፣ አብነት ትምህርት ቤቶችን በማስፋፋትና ሌሎች አገልግሎቶችን በማከናወን እዚህ መድረስ ትልቅ ነገር ነውና ከዚህ በበለጠ ደከመን ሰለቸን ሳትሉ እንደትናንትናው እንድታገለግሉ” ሲሉ አሳስበዋል።
በመርሐ ግብሩ ማኅበሩ ከምሥረታ ጀምሮ አሁን ያለበትን የአገልግሎት ሁኔታ ማኅበረ ቅዱሳንን ከመሠረቱት መካከል አንዱ በሆኑት ዲ/ን ዝናዬ ኃ/ማርያምና በቤተ ክርስቲያን 39 ዓመት የአገልግሎት ጊዜ ያላቸው እንዲሁም ወላይታ ማእከልን የመሠረቱት በወ/ሮ መታሰቢያ ለማ ልምድና የሕይወት ተሞክሮ ቀርቧል።
የማኀበረ ቅዱሳን ም/ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዲ/ን ደምሰው ጫላ ባለፉት 34 ዓመታት በትጋት እዚህ መድረስ ትልቅ ነገር ነውና ለምሥረታው በዓል እንኳን አደረሳችሁ በማለት መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት ለማከናወን የ10 ዓመት መሪ ዕቅድ አዘጋጅታ ወደ ተግባር እየገባችበት ባለው በዚህ ጊዜ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት አገልግሎታችንን ከመቸውም ጊዜ በላይ ማጠናከርና በቁርጠኝነት መደገፍ አንዱ የማኅበረ ቅዱሳን ኃላፊነት በመሆኑ የማኅበሩን ሥልታዊ ዕቅድ ከቤተ ክርስቲያን መሪ ዕቅድ ጋር በማጣጣም ለማከናወን፣ የተናበበ እና ውጤታማ ሥራ ለመሥራት ሁላችንም መዘጋጀት ይኖርብናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳንን 34ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል እያከበርን በምንገኝበት በዚህ ቀን ሁላችንም ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ″ሥራህን ሥራ″ በማለት የተናገሩትን ቃል የአገልግሎት መርሕ አድርገን ስንከተል በአገልግሎት መስዋዕትነት ጭምር ማገልገልን እንደምናስቀድም በማመን ነውና ዛሬም ይህንን ቃል እያሰብን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚያግዙ ተልእኮዋን የሚደግፉ አገልግሎቶችን ለማገልገል መትጋት አለብን በማለት ዲ/ን ደምሰው ጫላ አያይዘው ተናግረዋል።
በመጨረሻም ማኅበሩ ባለፉት ዓመታት በየደረጃው የሚገኙ አባቶቻችን፣ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ ከማኅበራት፣ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ከባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ በርካታ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ያከናወነ ሲሆን በቀጣይ የቤተ ክርሰቲያን የዐሥር ዓመታት መሪ ዕቅድ ያስቀመጠቻቸውን የመንፈሳዊ ፣ ማኅበራዊና ምጣኔ ኃብታዊ ግቦችና ለዚህ ስኬት ድጋፍ ሊያደርግ የሚችለውን የማኅበራችን 5ኛውን ስልታዊ ዕቅድ ዓላማዎች ለማሳካት የተቻለንን ሁሉ እንናድርግ ሲሉጥሪአቅርበዋል።
ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል እንኳን ለማኅበሩ የምሥረታ በዓል አደረሳችሁ በማለት መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን ❝34 ዓመት በጣም ትንሽ ናት የተሠራው ሥራ ግን ከዚያ በላይ ነው❞ ብለዋል። አያይዘው አገልግሎታችሁን ከጠረፍ እስከ ጠረፍ ተደራሽ በማድረግ ከዚህ በላይ እንድትሠሩ ሲሉ አሳስበው ከጎናችሁ ነን በማለት አክለውተናግረዋል።
ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ የሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል በበኩላቸው እንኳን አደረሳችሁ ያሉ ሲሆን እግዚአብሔርን በመያዝ ሳትሰለቹ እስከመጨረሻው ጠንክራችሁ አገልግሉ በማለት ቡራኬ ሰጥተው መርሐ ግብሩ ተጠናቅቋል።
ማኅበረ ቅዱሳን 34ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን አከበረ
ማኅበረ ቅዱሳን 34ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በአበው ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬ ግንቦት 2 ቀን 2018 ዓ.ም በማኅበሩ ሕንጻ 3ኛ ወለል ንቡረ ዕድ ድሜጥሮስ አዳራሽ ከቀኑ 8 ሰዓት አክብሯል።
በመርሐ ግብሩ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ የሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣ ካህናት አባቶች፣ የሥራ አመራር ጉባኤ አባላት፣ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ አባላት፣ የየማስተባበሪያ ኃላፊዎች፣ አባላትና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።
በጉባኤው መዝሙር በበኩረ መ/ን ኪነ ጥበብ እና በማኅበሩ መዘምራን የቀረበ ሲሆን ትምርተ ወንጌል በመ/ር ዲ/ን ዮሐንስ ጌታቸው ቀርቧል እንዲሁም ማኅበሩ ባለፉት 34 ዓመታት ያከናወናቸው ዋና ዋና አገልግሎቶችም ተዳሰዋል።
የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር ጉባኤ ጸሐፊ ዲ/ን ብንያም አያሌው የእንኳን ደኅና መጣችሁ መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን ማኅበሩ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ ከተመሠረተበት ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ በሀገር ውስጥ 52 ማእከላት፣ 468 ወረዳ ማእከላት፣ 463 ግንኙነት ጣቢያዎች እና 459 ግቢ ጉባኤያት፤ እንዲሁም በውጪ ሀገር 7 ማእከላት፣ 27 ንኡሳን ማእከላት፣ 29 ግንኙነት ጣቢያዎች እንዲሁም 22 ግቢ ጉባኤያት መኖሩን ገልጸዋል።
ጸሐፊው አክለውም ማኅበሩ ባለፉት 34 ዓመታት ያከናወናቸውን የዋና ዋና ተግባራት ዘገባ ያቀረቡ ሲሆን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ተልእኮዋን ለመደገፍ በወጣቶች የሰብእና ግንባታ ፣ በገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች ድጋፍ፣ በማኅበራዊ ድጋፍ፣ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት፣ በሚዲያ አገልግሎት እና በሌሎች በርካታ ዘርፎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷልም ብለዋል።
፻፴፬ ኛው የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ ላይ በቅዱስነታቸው የተላለፈ አባታዊ መልእክት
፻፴፬ ኛው የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ ላይ በቅዱስነታቸው የተላለፈ አባታዊ መልእክት
ሚያዝያ ፳፳/፳፻፲፰ ዓ.ም
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ የግንቦት ርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የመክፈቻ አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል።
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ ኣምላክ ኣሜን!
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤
ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት፣
በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የተገኛችሁ በሙሉ፦
ማሕየዊት በምትሆን ሞቱ ሰማያውያንና ምድራውያንን ያስታረቀ፣ በቅድስት ትንሣኤውም የሙታንን ሕይወት በተስፋ ያለመለመ ጌታችን፣ ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንኳን ለዓመታዊው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አደረሰን አደረሳችሁ!
“እስመ ተዋለጠ እግዚአብሔር ዓለመ በክርስቶስ አናኅስዮ ኃጢአቶሙ ወኢነጺሮ ጌጋዮሙ፤ ወረሰየ ላዕሌነ ቃለ ሥምረቱ፤ ወወሀበነ መልእክተ ሣህሉ፤ እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና በደላቸውን አይቈጥርባቸውም ነበር፤ በእኛም የማስታረቅ ቃል አኖረ” (2ኛቆሮ. 5፥19)
የእግዚአብሔርም ልጅ፣ የሰውም ልጅ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም ሰው ሆኖ ሲገለጽ ግልጽ የሆነ ዓላማና ግብ እንደነበረው ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል፤ እርሱም በሰማይም፣ በምድርም ያሉትን በሙሉ ማስታረቅ፣ ማገናኘትና አንድ ማድረግ ነበረ፤
ጌታችን ይህንን ሲያደርግ ሰማያውያኑንና ምድራውያኑን የለያየውን ምክንያት በማስወገድ ነው፤ የመለያየቱ ምክንያት ክፉ ኅሊና አምጦ የወለደው በደልና እርሱን ተከትሎ የተከሠተው ኃጢኣት ነበረ፤ በኃጢኣት ምክንያት የገባው ሞት ደግሞ የቅጣቱ ማሳያ ፍርድ ነበረ።
የመጀመሪያዎቹ ሰዎች በፈጸሙት ስሕተት መነሻነት ምድርንና ምድራውያንን ለከባድ ቅጣትና መርገም የዳረገው ይህ መለያየት ለሰማያውያኑም ተርፎአል።
ምክንያቱም መለያየቱ በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰውና በሰው፣ በነፍስና በሥጋ ጭምር የጥል ግድግዳን ገንብቶ እስከ ክርስቶስ ዕለተ ስቅለት መዝለቁን በቅዱስ መጽሐፍ የምናውቀው ስለሆነ ማለት ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
ቀዳማዊና ዘላለማዊ የሆነው ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰብእናችንን ተዋሕዶ በዚህ ዓለም የተገለጸው ሰማያውያንንና ምድራውያንን የለያየው የጥል ግድግዳን ለማፈራረስ ነው።
ለመለያየት ምክንያት የሆነችውን ኃጢኣት በሰውነቱ በመቅጣት የሕግን ትእዛዝ ከፈጸመ በኋላ የዕርቁን ተግባር በወሳኝ መልኩ አከናውኖታል።
በክርስቶስ ቤዛነት የሆነው ይህ ዕርቅ በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ የተወደደ ነበረና እሱ ራሱ በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር አስታረቀ።
ለዚህም ነው ተበዳይ እርሱ፣ ቤዛዊ መሥዋዕት ሆኖ የቀረበው እርሱ፣ ኣስታራቂ እርሱ፣ ታራቂ እርሱ ሆኖ የምናገኘው፤ ለእርሱ የሚሳነው ነገር የለምና ለእኛ ግር የሚል ቢመስልም ለእርሱ ቀላል ነበረ።
በዚህ የዕርቅ ተግባር ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሰውና ሰው፣ ነፍስና ሥጋ ታርቀው በይፋ ተገናኙ፤ በኅብረትና በአንድነትም መኖር ቻሉ፤ በቀኙ ለተሰቀለው ወንበዴ “ዛሬውኑ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ” የሚለው ቃለ ምሕረትና “አባት ሆይ፥ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” የሚለው ቃለ አማኅፅኖ የዕርቁ፣ የግንኙነቱና የኣንድነቱ ማሳያ ኣስረጅ ናቸው።
ስቅለተ ክርስቶስ ነፍሶቻችን ወደ ግዞት ቤት ሳይሆን ወደ ገነት እንዲገቡ፣ የሚቀበላቸውም ራሱ እግዚአብሔር እንዲሆን ያስቻለ ታላቅ መለኮታዊ ፍጻሜ ነው።
እኛ “ክርስቶስ መድኃኒታችን ነው፤ አድኖናል” ብለን በፍጹም ልባችን አምነን የምንመሰክረው፣ እርሱም በመስቀል ላይ ውሎ “ሰላሜን ሰጠኋችሁ” በማለት በመስቀሉ ስላዳነን አጽናኝ መንፈስ ቅዱስንም ስለላከልን ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
የድኅነታችንና የሰላማችን መሠረት የሆኑትን የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ለዓለም ማኅበረሰብ የማብሰርና የማሥረጽ ተግባር የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቍጥር አንድ ተልእኮ ነው፤
ነገረ ሞቱና ነገረ ትንሣኤው በአስተውሎት፣ በጥልቀትና በተመሥጦ ስናስተምር በውስጡ የምናገኘው የዕርቅ፣ የሰላምና የኣንድነት ምስጢር ነው፤
እንደ እውነቱ ከሆነ እኛ የክርስቶስ መልእክተኞች እንደ ቃሉ ራሳችንን ክደን በሚጠበቀው መጠን ተልእኮኣችንን መወጣት ብንችል ኖሮ፣ ኣሁን በዓለማችን የተፈጠረው መለያየትና ግጭት አይኖርም ነበር።
ችግሩን ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ባንችልም በእጅጉ መቀነስና ዓቅሙን ማዳከም እንችል ነበር፤ ነገር ግን ተልእኮአችንን በአግባቡ አለመወጣት ኣንድ ነገር ሆኖ የዓለሙ መሣሪያ ሆነን መገኘታችን “በዕንቅርት ላይ…” ሆኖ ይስተዋላል።
ይሁንና አሁንም ሕዝቡን ወደ አንድነት፣ ወደ ፍቅር፣ ወደ ሰላም፣ ወደ ዘላቂ የጋራ ጥቅምና ወደ ፈሪሀ እግዚአብሔር ማምጣት የጉባኤያችን ዐቢይ ተግባር ሊሆን ይገባል፤ እነዚህ ካሉ የምናጣውም ሆነ የሚያመልጠን የለምና ነው፤
ሀገርን በኀላፊነት ተረክባችሁ በላዕላዊ፣ በማእከላዊና በታሕታዊ መዋቅር የምትገኙ፣ እንደዚሁም አማራጭ ሐሳብ አለን ብላችሁ የምትንቀሳቀሱ ልሂቃነ ሀገር ፣ ሁላችሁም እግዚአብሔርን ከሚያውቅ፣ ከሚያመልክና ከሚፈራ ሕዝብ የተገኛችሁ ናችሁና በልባችሁ እግዚአብሔርን ፍሩ፤ ድምፁንም ስሙ፤ የእርሱ ገንዘብ በሆኑ ፍጡራንም አትጨክኑ፤ ሰውን መያዝ የሚቻለው ኅሊናን በመርታት እንጂ በሌላ አይደለምና፣
የሕዝቡን ፍላጎትና የልብ ትርታ በሚገባ አዳምጡ፤ ሕዝቡ የሚፈልገው በአንድነትና በእኩልነት መኖር፣ በሰላም ወጥቶ መግባት፣ ፍትሕን ማስፈን፣ ለኑሮው የሚበቃ ምጣኔ ሀብትን ማግኘት፣ የእምነት ነፃነትና እኩልነት መረጋገጥ የመሳሰሉት ናቸው።
ሕዝቡ እነዚህ ከተሟሉለት ተደመጠ ማለት ነው፤ ከተደመጠ ደግሞ እርሱም በበኩሉ ያደምጣል፤ ይከተላልም።
ስለሆነም ለሁሉም ልጆቻችንና ወገኖቻችን የምናስተላልፈው ወቅታዊ ጥሪ ሁሉንም ችግሮቻችንን በሰላም ብቻ ለመፍታት ተባበሩ የሚል ነው፤ ከዚህ ውጭ የሚደረገው አማራጭ ሁሉ ለዘላቂ ሰላማችን አይበጅም እንላለን።
በመጨረሻም፦
በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ከበዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን የሚካሄደው ዓመታዊው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተጀመረ መሆኑን ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለመላው ኢትዮጵያውያን እናበሥራለን!!!
እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤
አሜን!!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤
ሚያዝያ ፳፰ ቀን ፳፻፲፰ዓ.ም
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ
ዘገባው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ መገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት ነው።
በአሜሪካ ቦስተን ከተማ የበገና እና የመሰንቆ ተማሪዎች ተመረቁ
ሚያዝያ ፳፰/፳፻፲፰ ዓ.ም
በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል ቦስተን ንዑስ ማእከል በገና እና መሰንቆ በተለያየ ዙር ሲማሩ የነበሩትን በቦስተን አካባቢ የሚገኙ ሕጻናት እና አዋቂዎቸን ቅዳሜ ሚያዝያ ፳፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም አስመርቋል።
በመርሐ ግብሩ አርባ አንድ የበገና እና ሦሰት የመሰንቆ ተማሪዎች የተመረቁ ሲሆን በምረቃው ሥነ ሥርዓት ላይ የበገና እና የመሰንቆ ዝማሬ አቅርበዋል።
በመጨረሻም ለተመራቂዎች የምስክር ወረቀት እና የመስቀል ስጦታ ተበርክቶላቸዋል።
ዘገባው የአሜሪካ ማእከል ሚዲያ ክፍል ነው።
አዲስ አበባ ማእከል 26 ለሚሆኑ የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ለተከታታይ አምስት ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና መጠናቀቁን አስታወቀ
አዲስ አበባ ማእከል 26 ለሚሆኑ የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ለተከታታይ አምስት ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና መጠናቀቁን አስታወቀ
ሚያዝያ ፳፮/፳፻፲፰ ዓ.ም
በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ስብከተ ወንጌልና መንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች አገልግሎት ዋና ክፍል ከተለያዩ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለተውጣጡ 26 የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ለአምስት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ማእከል አስታውቋል።
በሥልጠናው 26 የሚሆኑ የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ አብዛኞቹ የአቡነ ሀብተ ማርያም የአብነት ትምህርት ቤት ተማሪዎች መሆናቸውን በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል የስብከተ ወንጌልና መንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች ክፍል ኀላፊ አቶ አዘዘ ፀሐዩ ገልጸዋል።
የሥልጠናው ዋና ዓላማ በአብነት ትምህርት ቤት የሚገኙ ደቀ መዛሙርት ብቁ እና ንቁ መሪ አገልጋይ ሁነው እንዲወጡ ማድረግ መሆኑን የገለጹት ኀላፊው በዚህ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ ንቁ ተሳትፎ ያላቸው መሪ ይሆናሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ በማንሳት ሥልጠናው ለነገዋ ቤተ ክርስቲያን ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው ተናግረዋል።
በተጨማሪም ለአብነት ተማሪዎቹ የመጽሐፍ ስጦታ የተበረከተላቸው ሲሆን ነገ ላይ ካህናትና ጳጳሳት ሁነው በቤተ መቅደስ ውስጥ የሚያገለግሉ በመሆኑ ትኩረት ተሰጥቶ ሥልጠናው ሲሰጥ መቆየቱን ገልጸው በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል።
ከዚህ ባሻገር አብነት ትምህርት ቤቶቹ የአልባሳት፣ የመጠለያና የምግብ ችግር ያለባቸው በመሆኑ ማኅበሩ በተለያዩ ጊዜያት ድጋፍ እንደሚያደርግ ያነሱ ሲሆን ዘላቂ መፍትሔ እስኪመጣ ድረስ ምእመናን በተለይም ለዕለት ጉርስ እና ለዓመት ልብሳቸው የሚሆን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
ዘገባው የአዲስ አበባ ማእከል ነው
👇👇👇👇👇👇👇
የማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ ሚዲያ አውታሮች ይቀላቀሉ
ቴሌግራም፡- http://t.me/mkpublicrelation
የማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት፡- http://www.facebook.com/eotcmkidusan/
ድረገጽ፡- http://www.eotcmk.org
ዩ ቲዩብ፡- http://www.youtube.com/user/EOTCMK
:- https://www.youtube.com/@-zemawetibebzmk7905










