ዕቅድ ከክንውን የተስማሙለት ግቢ ጉባኤ

በዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

ጊዜው ከዛሬ አስር ዓመት በፊት ሲሆን በወቅቱ የነበሩ ተማሪዎቹ ሰፊ የሆነ መርሐ ግብር እና የመሰበሰቢያ አዳራሽ ስለሌላቸው መርሐ ግብራቸውን ፀሐይና ዝናብ እየተፈራረቁባቸው፣ ዛሬ አዳራሹ ተሠርቶ ከሚገኝበት ቦታ በነበሩ ዛፎች ጥላ ሥር ያካሒዱ ነበር፡፡ ይህን የተቀደሰ ተግባር በደብረ ማርቆስ ከተማ የሚገኘው የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት ያበረታታ፤ ይደግፍ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ሲፈቅድ፤ የተማሪዎቹና የማእከሉ ጥረት ተሳክቶ ተቋሙ ከተመሠረተ ከስድስት ወር በኋላ የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ተብሎ፣ በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት መዋቅር ውስጥ ታቅፎ የካቲት ፲፮ ቀን ፲፱፻፺፱ ዓ.ም አገልግሎቱን በተጠናከረ መንገድ ጀመረ፡፡ በምሥረታው ዕለት በተቋሙ ከሚገኙ ፯፻፷ ተማሪዎች መካከል ፭፻፴፮ ተማሪዎች ተገኝተዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በ፳፻፣ በ፳፻፩ እና በ፳፻፪ ዓ.ም ተማሪዎችን የመቀበል ዐቅሙ እያሳዳደገ በመሔዱ፣ ግቢ ጉባኤውም አገልግሎቱን አሰፋ፤ በተለይ የቴክኖሎጂ ተማሪዎችን ተቋሙ ሲቀበል የግቢ ጉባኤው አገልግሎት ይበልጥ እየጎለበት መጣ፡፡ Read more