የጸሎት ጊዜያት

በእንዳለ ደምስስ

ክፍል አምስት

“የጽድቅን ጥሩር ልበሱ” በሚል ርእስ አራት ተከታታይ ክፍሎችን ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው ክፍል አምስት መርሐ ግብራችንም የጸሎት ጊዜያትን እንቃኛለን፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን የጸሎት ጊዜያት የታወቁ ናቸው፡፡ ጸሎትን አስመልክቶ ቅዱሳት መጻሕፍትን መሠረት አድርገን ቤተ ክርስቲያናችን የደነገገቻቸውን ሰባቱን የጸሎት ጊዜያት ከነምክንያታቸው አንደሚከተለው እንመለከታለን፡- ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ስለ እውነት ፍርድህ ሰባት ጊዜ በቀን አመሰግንሃለሁ” እንዲል(መዝ. ፻፲፰.፻፷፬)፡፡

ጸሎተ ነግህ፡-

ፀሐይ ከመውጣቱ በፊት ከእንቅልፋችን ነቅተን ከመኝታችን ተነሥተን በማለዳ የምንጸልው ጸሎት ነው፡፡ ይህም እግዚአብሔር የሌሊቱን ጨለማ አሳልፎ ብርሃኑን አብርቶልናልና ስለዚህ ማለዳ መጸለይ ለክርስቲያን ሁሉ የታዘዘ ነው፡፡ በሰላም አሳድሮ፣ ጨለማውን አሳልፎ ለብርሃን አብቅቶናልና ይህን ላደረገ እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ፣ ቀኑንም በሰላም ያውለን ዘንድ፣ ሥራችንንም ይባርክልን ዘንድ መጸለይ ለክርስቲያን የሚገባ ነው፡፡

መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት “በማለዳ ቃሌን ስማኝ፣ በማለዳ በፊትህ እቆማለሁ፣ እገለጥልሃለሁም” (መዝ.፭.፫) በማለት እንደተናገረው በማለዳ ከእንቅልፋችን ተነሥተን ልንጸልይ ይገባል፡፡

ሌላው በመጽሐፈ አክሲማሮስ እንደተገለጸው እግዚአብሔር አምላካችን አዳምን ከምድር አፈር ያበጀበትና እስትንፋስን ሰጥቶ የፈጠረው ስለሆነ፣ እኛንም ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣንን(የፈጠረንን) አምላካችንን ለማመስገን በማለዳ እንጸልያለን፡፡ (ዘፍ.፩.፳፮)፡፡

የሠለስት(ሦስት) ሰዓት ጸሎት፡-

ጠዋት በሦስት ሰዓት የምንጸልይበት ምክንያት በርካታ ቢሆኑም ጥቂቶቹን እንመለከት፡-

፩. ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤል በባቢሎን በምርኮ በነበረበት ጊዜ ዘወትር መስኮቱን በምሥራቅ አቅጣጫ ከፍቶ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ “የእልፍኙም መስኮቶች ወደ ኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ነበር፣ ቀድሞም ያደርግ እንደነበረ ከቀኑ በሦስት ሰዓት በጒልበቱ ተንበርክኮ በአምላኩ ፊት ጸለየ፣ አመሰገነም፡፡”(ዳን.፮.፲)፡፡ እኛም ቅዱሳን አባቶቻችን በሄዱበት መንገድ መጓዝ፣ ሥርዓቱንም መፈጸም ተገቢ ነውና በዚህ ሰዓት ለጸሎት በአምላካችን ፊት እንቆማለን፡፡

፪. ሌላው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በቤተ መቅደስ ሐሩንና ወርቁን አስማምታ ስትፈትል መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ወደ እርስዋ ተልኮ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና እንደምትወልድ ያበሠረበት ሰዓት ነው፡፡ “. . . መልአኩም እንዲህ አላት “ማርያም ሆይ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና አትፍሪ፡፡ እነሆ ትፀንሻለሽ፣ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ፣ እርሱም ታላቅ ነው፤ የእግዚአብሔር ልጅም ይባላል” አላት፡፡ (ሉቃ.፩.፳፮)፡፡

፫. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጲላጦስ አደባባይ የተገረፈበትንና ጲላጦስ ለካህናት አለቆችና ጸሓፊዎች፣ ለሸንጎውም ይሰቅሉት ዘንድ አሳልፎ የሰጠበትን በማሰብ ነው፡፡ ያለ በደልህ ስለ እኛ ብለህ ተከሰስህ፣ ተገረፍህ፣ አሳልፈውም ሰጡህ እያልን አምላካችን ስላደረገልን ካሳ እያሰብን እንጸልያለን፡፡ “ስቀለው፣ ስቀለው እያሉ አብዝተው ጮኹ፡፡ ጲላጦስም የሕዝቡን ፈቃድ ሊያደርግ ወድዶ በርባንን ፈታላቸው፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ገርፎ ሊሰቅሉት ሰጣቸው” እንዲል (ማቴ.፳፯.፳፮፤ማር.፲፭.፲፭)፡፡

፬. በሦስት ሰዓት ሐዋርያት በአንድነት ተሰብስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ የወረደላቸው ሰዓት ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤውን ከገለጠበት ጊዜ አንስቶ ሐዋርያት በአንድነት ሆነው እንዲጸልዩ፣ ከኢየሩሳሌምም እንዳይወጡ አስጠንቅቋቸው ዐርባውን ቀን መጽሐፈ ኪዳንን ሲያስተማራቸው ቆይቷል፡፡ በኀምሳኛውም ቀን በዕለተ እሑድ ከጠዋቱ በሦስት ሰዓት ኃይልን ይለብሱ ዘንድ፣ በጥብዓት ሆነው ይህንን ዓለም በወንጌል ያረሰርሱ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ልኮላቸዋል፣ ሰባ ሁለት ቋንቋዎችንም ገልጦላቸው ተናግረዋል፡፡ መንፈሳዊ ኃይልንም ተላብሰዋል፡፡ በዕለቱም በሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ስብከትም ሦስት ሺህ ሰዎች አምነዋል፡፡  መጽሐፍ ቅዱስ ይህንን ሲያብራራ እንዲህ ይላል፡- “ኀምሳውም ቀን በተፈጸመ ጊዜ ሁሉም በአንድነት በአንድ ቦታ ተሰብስበው ነበር፡፡ ድንገትም እንደ ዐውሎ ነፋስ ድምፅ ያለ ከሰማይ ድምፅ መጣ፣ የነበሩበትንም ቤት ሞላው፡፡ እንደ እሳት የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎችም ታዩአቸው፣ በሁሉም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ ሁሉም መንፈስ ቅዱስን ተሞሉ፣ ይናገሩ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እንደ አደላቸው መጠንም እያራሳቸው በሀገሩ ቋንቋ ይናገሩ ጀመሩ” (ሐዋ.፪.፩-፬)፡፡ ስለዚህ እኛም በሓዋርያት ያደረ መንፈስ ቅዱስ ያድርብን ዘንድ በዚህ ሰዓት እንድንጸልይ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡

ስድስት ሰዓት(ቀትር)፡-

ይህ ሰዓት ፀሐይ የሚበረታበትና አጋንንት የሚሠለጥኑበት ሰዓት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት እንዲህ እንደተናገረ “በማታና በጥዋት፣ በቀትርም እናገራለሁ፣ አስረዳለሁ፣ ቃሌንም አይሰሙኝም፣ ከእኔ ጋር ካሉት ይበዛሉና” እንዲል(መዝ.$፬.፲፯-፲፰፤መዝ.፺.፮)፡፡ ስለዚህ ለአጋንንት እንዳንንበረከክና እንዳንሸነፍ ተግተን የምንጸልይበት ሰዓት ነው፡፡

በቀትር ዲያብሎስ አባታችን አዳምን ያሳተበት ስዓት ስለሆነም በጸሎት ድል እንነሣው ዘንድ የምንበበረታበት ሰዓት ነው፡፡

እንዲሁም አይሁድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከቀኑ ስድስት ሰዓት የሰቀሉበት ጊዜ ነው፡፡ ከስድስት ሰዓት እስከ ዘጠኝ ሰዓትም ሰባት ተአምራት ተደርገዋል፡፡ በሰማይ ፀሐይ ጨለመ፣ ጨረቃ ደም ለበሰች፣ ከዋክብት ረገፉ፣ በምድር ደግሞ መቃብራት ተከፈቱ፣ ሙታን ተነሡ፣ ዓለቶች ተሰነጠቁ፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃ ለሁለት ተቀደደ፡፡ “ከዚህም በኋላ ሊሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው፣ ጌታችን ኢየሱስንም ተቀብለው ወሰዱት፡፡ መስቀሉንም ተሸክሞ በዕብራይስጥ ጎልጎታ. ወደተባለው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ወጣ፡፡ በዚያም ሰቀሉት” እንዲል(ዮሐ.፲9.፲፬)፡፡ እኛም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ሲል መገረፉን፣ መስቀል ተሸክሞ መውደቅ መነሣቱን፣ መራብ መጠማቱን፣ እንዲሁም መሰቀሉን እያሰብን በስድስት ሰዓት እንጸልያለን፡፡

ዘጠኝ ሰዓት፡-

ቅዱሳን መላእክት ለአገልግሎት የሚፋጠኑበት፣ የሰው ልጆች የሚያቀርቡትን ልመና እና  ጸሎት፣ ዕጣን ወደ እግዚአብሔር የሚያሳርጉበት ሰዓት ነው፡፡ “ሌላ መልአክም መጣ፣ በመሰዊያው ፊትም ቆመ፣ የወርቅ ጥናም ይዞ ነበር፤ በዙፋኑ ፊት ባለው በወርቁ መሰዊያም ላይ ለቅዱሳን ሁሉ ጸሎት እንዲያሳርገው ብዙ ዕጣን ተሰጠው፡፡ የዕጣኑ ጢስም ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡  (ራዕ.፲.፫)፡፡

ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ዮሐንስ ዘወትር ለጸሎት ወደ ቤተ መቅደስ ይገቡበት የነበረ ሰዓት ነው፡፡ በዚያም ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ ሽባ የነበረውን ሰው ፈውሰዋል፡፡ (ሐዋ.፫.፩)፡፡

የመቶ አለቃው ቆርኔሌዎስ በዘጠኝ ሰዓት ጸሎት ያቀርብበት የነበረ ሰዓት ነው፡፡ “በቂሳርያ ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበር ኢጣሊቄ ለሚሉት ጭፍራም የመቶ አለቃ ነበር፡፡ እርሱም  ጻድቅና ከነቤተሰቡ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነበር፣ ለሕዝቡም ብዙ ምጽዋት ይሰጥ ነበር፣ ዘወትርም ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክም በራእይ ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት በግልጥ ታየው”(ሐዋ.፲.፩-፴፪) እንዲል፡፡

በተጨማሪም የጻድቅ ሰው ጸሎት ወደ እግዚአብሔር እንደሚደርስና ዋጋ እንደሚያሰጥ ሲነግረን “የዛሬ አራት ቀን በዘጠኝ ሰዓት በቤቴ ስጸልይ ፊቱ የሚያንጸባርቅ ልብስ የለበሰ አንድ ሰው በፌቴ ቆሞ ታየኝ፡፡ እንዲህም አለኝ፡- ቆርኔሌዎስ ሆይ በእግዚአብሔር ፊት ጸሎትህ ተሰማ፣ ምጽዋትህም ታሰበልህ” እያለ ተገልጾለታል፡፡(ሐዋ.፲.፴-፴፩)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ሲል ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው የለየበት ሰዓትም በመሆኑ ይህንን እያሰብን በዚህ ሰዓት እንጸልያለን፡፡ (ማቴ.፳፯.#5-$፤ማር.፲5.፴፫-፴፬)፡፡

ሠርክ(አሥራ አንድ ሰዓት)፡-

ሰው ቀኑን ሙሉ ሲለፋ ሲደክም ውሎ በሠርክ የሠራበትን ዋጋ የሚቀበልበት ሰዓት ነው፡፡ በመልካምም ሆነ በክፉ ሥራችን ክፍያ እናገኛለን፡፡ በምግባር በሃይማኖት ጸንተን አንደበታችንን ከክፉ ነገር፣ ዐይናችንን ክፉ ከማየት ከልክለን፣ ምግባር ሃይማኖት ይዘን ለሌሎች መልካም በማድረግ፣ ለሀገር ለወገን የሚጠቅም ሥራ ሠርተን ከተገኘን፣ የበደልነውን ክሰን፣ በንስሓ ታጥበን በሃይማኖት ከጸናን “ኑ የአባቴ ቡሩካን” ተብለው ከሚጠሩት ወገን እንደመራለን፡፡ ቀን ክፉ ብንሠራ፣ ሌሎችን እየበደልንና እያስለቀስን፣ እየዋሸንና እየቀጠፍን ከዋልን እንዲሁ “አላውቃችሁም” ከሚባሉት እንቆጠራለን፡፡ ስለዚህ ሰሎሞን በምሳሌው “ልብህ በኃጠአተኞች አይቅና፣ ነገር ግን ቀኑን ሙሉ እግዚአብሔርን በመፍራት ኑር” እንዳለው እግዚአብሔርን በመፍራት መኖር ለሰው ሁሉ የሚገባ ነው፡፡

ከሥራ በኋላ የሠሩበትን ዋጋ መቀበል እንደሚያስፈልግ ሁሉ የእግዚአብሔር ቸርነት ታክሎበት በመጨረሻው ዘመንም ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዋጋችንን እንቀበላለን፡፡  የክርስቲያን ዋጋው መንግሥተ ሰማያት ናት፡፡ (ማቴ.፳.፩-፲6)፡፡

ቅዱስ ዳዊት “ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ፣ እጆቼ የሠርክ መሥዋዕትን አነሡ” በማለት እንደተናገረው በዚህ ሰዓት ጸሎት መጸለይ እንደሚገባ ቀደምት አባቶቻችንን ምሳሌ አድርገን መትጋት ከክርስቲያኖች የሚጠበቅ ነው፡፡(፻#.፪)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ያቀረበው መሥዋዕት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ያገኘበት ሰዓት ነው፡፡ ነቢዩ ለሦስት ዓመት ተኵል ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን ከለጎመ በኋላ የአክአብን ሐሰተኞች ነቢያት በጸሎቱ ድል የነሣበትና እግዚአብሔር መሥዋዕታቸውን የተጠየፈበት ነገር ግን ኤልያስ ያቀረበውን ጸሎትና መሥዋዕት የተቀበለበት ሰዓት ነው፡፡ (፩ነገ.፲፰.፴፮-#)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ መቃብር መውረዱን የምናስብበት ሰዓት ነው፡፡ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የጌታችንን ሥጋ ከመስቀል ላይ አውርደው በአዲስ መቃብር የቀበሩበትም ሰዓት ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ሰዓት በኃጢአት ምክንያት የሞት ሞት የሞትነውን እኛን ለማዳን ሲል ወደ መቃብር መውረዱን እያሰብን እንድንጸልይ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት ሠርታልናለች፡፡(ማቴ.፳፯.$፯-%6፤ ማር.፲5.ማር.#፪-#፯፤ ሉቃ.፳፬.$-$5)፡፡

ንዋም(የመኝታ ሰዓት)፡-

የሰው ልጆች በአዳም በደል ምክንያት ከእግዚአብሔር የተፈረደብንን ፍርድ ለመፈጸም በወዛችንና በላባችን፣ ወጥተን ወርደን እንበላ ዘንድ እንደክማለን፡፡ “…እሾህና አሜኬላን ታበቅልብሃለች፣ የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡ ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራህን ትበላለህ” እንዲል፡፡(ዘፍ.፫.፲፰)፡፡

ቀኑን ሙሉም ስንሠራ ስንለፋ ውለን ማታ እናርፋለን፡፡ በማረፊያችን ሰዓት ደግሞ ኦርቶዶክሳውያን በሌሎቹ ሰዓታት እንደምንጸልይ ሁሉ ወደ መኝታ ከመሄዳችን በፊት መጸለይ ተገቢ ነው፡፡ በሰላም ያዋልከን አምላካችን ሆይ እናመሰግንሃለን፣ ቀኑን በሰላም አሳልፈህልናልና ሌሊቱንም ባርከህ ቀድሰህ ታሳድረን ዘንድ ቅዱስ ፈቃድህ ይሁን እያልን ወደ መኝታ ከመሄዳችን በፊት አምላካችንን እያመስገንን፣ በደላችንንም ይቅር በለን እያልን እንጸልያለን፡፡

እንዲሁም ይህ ሰዓት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በጌቴሴማኒ ሥርዓተ ጸሎት ያስተማረበት ሰዓት ነው፡፡ (ማቴ.፳፮.፴፮)፡፡

መንፈቀ ሌሊት፡-

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በግርግም፣ በከብቶች በረት የተወለደበትን ሰዓት እያሰብን በዚህ ሰዓት እንጸልያለን፡፡ (ማቴ.፪.፩-፲፡ ሉቃ.፪.6-፲፫)፡፡ እንዲሁም በመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ የተጠመቀበት ሰዓት ስለሆነ ይህንን እያሰብን እንጸልያለን፡፡(ማቴ.፫.፲፫፤ሉቃ.፫.፳፩፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ የተነሣበትና በዕለተ ምጽአትም ጊዜው ሲደርስ ይህንን ዓለም ያሳልፍ ዘንድ በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት ሠራዊተ መላእክትን አስከትሎ የሚመጣበት ሰዓት ስለሆነ በትጋት እንጸለይ ዘንድ ታዘናል፡፡(ማቴ.፳5.6፤ዮሐ.፳.፩፤ማር.፲፫.፴፭)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “አመሰግንህ ዘንድ በእኩለ ሌሊት እነሣለሁ”(መዝ.፻፲፰.፷፪) ብሎ እንደተናገረ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ምጽአት ይህንን ዓለም ለማሳለፍ በመንፈቀ ሌሊት እንደሚመጣ እያሰብን የምንጸልበት ጊዜ ነው፡፡

ጳውሎስና ሲላስም በእስር ቤት እያሉ በዚህ ሰዓት ወደ እግዚአብሔር ይጸልዩ ነበር፡፡ “በመንፈቀ ሌሊትም ጳውሎስና ሲላስ ጸለዩ፡፡ እግዚአብሔርንም በዜማ አመሰገኑት፡፡” በማለት ቅዱስ ሉቃስ እንደገለጸው እኛም በመንፈቀ ሌሊት ልናመሰግን ይገባል፡፡(ሐዋ.፲6.፳፭)፡፡

የሰባቱ የጸሎት ጊዜያት ብዙ ምክንያት ቢኖራቸውም በአጭሩ እነዚህን ከላይ የጠቀስናቸውን በማሰብ እንጸልያለን፡፡

እግዚአብሔር ቢፈቅድ በክፍል ስድስት ዝግጅታችን ስግደትን እንመለከታለን፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡ አሜን፡፡

ይቆየን፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *