ዘወረደ

ትዕግሥት ሳዝነው

ከፍጥረት አልቆ በክብር ቢያበጀው፣

አዳም ክብር ሽቶ ክብሩን አቆሸሸው፣

ምንም ሳያጎድል ሁሉን ለእርሱ ሰጥቶ፣

ይቀመጥባት ዘንድ ገነትን ርስት አድርጎ፣

በውስጧ ያሉትን ፍጥረታትን ገዝቶ፣

አምላኩ ሲሾመው ጌታዋ አድርጎ፡፡

አንድ ሕግ ነበረ ለአምላክ ቃል የገባው፣

ከዛፎቹ ሁሉ አንዷን ዛፍ እንዲተው፣

እንዲህ ሲል አዘዘው፡፡

ክፉ እና ደጉን ከምታሳውቀው፡፣

ሞትን እንዳትሞት ከዚ’ች ዛፍ አትብላ፣

ከእርሷ በበላህ ቀን ትሞታለህና፣

ክብሩን ያላወቀ ማዕረጉን የረሣ፡፡

በተሰጠው ፍጥረት አዳም ተታለለ፣

ትእዛዝ እና ሕጉን የአምላኩን ቃል ጣሰ፡፡

 ዕፀ በለስ በልቶ አምላክ ይሆን ዘንድ፣

 በፍጥረት በእባብ ተታለለ ሳይወድ፣

በበላትም ቅፅበት ቆርጦ እንደወሰዳት፣

ክብርና ማዕረጉን አጥቶ ወረደ ከገነት፣

ሞትንም ሊቀምሳት መጣ ወደ መሬት፣

ትእዛዙን ተላልፎ አዳም ቢበድልም፣

ሕግን በመሻሩ በአዳም በደል ቢያዝንም፡፡

ንስሓን ሊሰጠው ይቅር ሊለው ወ’ዶ፣

ከሰማዩ ክብር ከዙፋኑ ወርዶ፣

ከፈጠረው ፍጥረት ከማርያም ተወልዶ፡፡

እርሱ በመውረዱ አዳም እንዲወጣ፣

አምላክ ሰው ሆነ ከእነክብሩ መጣ፣

አዳም የሻውን የአምላክነት ፀጋ፣

በአምላክ ሰው መሆን ከአምላኩ ተጠጋ፡፡

 የአዳም በደል ሊፍቅ የአዳም ቁስል ሊሽር፣

 አምላክ እንዲወርድ ቢያስገድደው ፍቅር፣

 እሱ ባላጠፋው ባልሠራው ኃጢያት፣

 በጅራፍ ተገርፎ በመስቀል ቢሰቅሉት፣

 አምላክ ነፍሱን ሰጥቶ የእርሱን ነፍስ አዳናት፡፡

 እኛም የአዳም ልጆች  ፍቅሩ ያልገባን፣

 አምላክ ይቅር ሲለን እኛ እየበደልን፣

ንስሓን ቢሰጠን በኃጢአት መኖር መርጠን፣

በዘር በጥላቻ በክፋታችን ደምቀን፣

ከተሰጠን ክብር ጌትነትም ወረድን፡፡

ወንድሙን ሊገድል ወዳጁን ሊከዳ፣

ሰው ከንቱ ሰው መና ይደክማል በጓዳ፡፡

ከተሰጠው ፍቅር ከተሰጠው ሕይወት፣

የክፋት አባቱ ዲያቢሎስ በልጦበት፣

 የዘር ጣዖት ሠርቶ ኖረ ሲሰግድለት፣

 ይህን በደል ዐይቶ ልቡናዬ ቢያዝን፣

 አምላክ ውረድና ቅጣን እንዳልለው፣

 እኔም ሰው ነኝና እንዳልቀጣ ፈራው፣

 ቂም በቀል ትዕቢት መለያየት ስመኝ፣

 በኃጢያት በክፋት በበደል ስጎበኝ፣

 አምላክ ዛሬም ውረድ ከበደሌ እጠበኝ፡፡

 የተሰጠኝ ፍቅር መጻሕፍትን ጥፎ፣

 ሐዋርያትን ሹሞ ሕግና ሥርዓትን፣

 ቀኖናን አትሞ ፃድቃን ሰማዕታትን፣

 መምህራንን ጠርቶ ትእዛዙን ሠራልን፡፡

 በደሙ አትሞ ከሕጉ የወጡት በግራው ሲቆሙ፣

 በሕጉ የፀኑት በቀኙ ሊቆሙ፣

ያኔ ሠርቶልናል ከሰማያት ወርዶ፣

ከፈጠራት ፍጥረት ከድንግል ተወልዶ።

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *