“መራሔ ፍኖት” መንፈሳዊ ጉዞ ለግቢ ጉባኤያት ተዘጋጀ

መጋቢት 25 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማእከል አስተባባሪነት በ60 ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሥር ለሚገኙ 5000 /አምስት ሺህ/ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች  “መራሔ ፍኖት” /መንገድ መሪ/ የተሰኘ መንፈሳዊ ጉዞ ወደ ሱሉልታ ደብረ ምሕረት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በዕለተ ሆሣዕና ሚያዚያ 20 ቀን 2005 ዓ.ም. መዘጋጀቱን የአዲስ አበባ ማእከል ዋና ጸሐፊ አቶ ካሳሁን ኃይሌ ገለጹ፡፡

የጉዞውን መሠረታዊ ዓላማ አስመልከቶ አቶ ካሳሁን ኃይሌ ሲገልጹ “በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚገኙ ግቢ ጉባኤያት የአንድነት መንፈስ እንዲኖራቸው ለማድረግ፤ እንዲሁም በግቢ ጉባኤያት የማይሳተፉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆችን በግቢ ጉባኤያት ውስጥ የሚሰጠውን መንፈሳዊ ትምህርት እንዲማሩ ለማነሳሳት ታስቦ የተዘጋጀ መርሐ ግብር ነው” ብለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን በዋነኛነት ተማሪዎች በቀለም ትምህርታቸው፤ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውና አገልግሎታቸው እንዴት ስኬታማ መሆን ይችላሉ? በሚል ርዕስ ከዚህ በፊት በግቢ ጉባኤት ውስጥ በመማርና በማገልገል ላይ የነበሩ ወንድሞችና እኅቶች ተሞክሯቸውን ያካፍላሉ፡፡ እንዲሁም ተማሪዎች ለሚያቀርቧቸው በቀለም ትምህርታቸውና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚያጋጥሟቸውን ፈተናዎችና ተያያዥነት ያላቸው ጥያቄዎቻቸው በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምላሽ ይሰጥባቸዋል፡፡

በዚህም መሠረት ተማሪዎች ያሏቸውን ጥያቄዎች እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ በኢሜይል አድራሻ Mfenot2005@gmail.com ፤ በስልክ  09 11 89 89 90 / 09 11 36 16 92 መላክ እንደሚችሉ  አቶ ካሳሁን ኃይሌ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም የቲኬት ሽያጩ በሁሉም ግቢ ጉባኤያት ሥራ አስፈጻሚዎች፤ በማኅበረ ቅዱሳን ንዋያተ ቅድሳት መሸጫ ሱቆችና መዝሙር ቤቶች እንዲሁም በአዲስ አበባ ማእከል ጽሕፈት ቤት ውስጥ ማግኘት እንደሚቻል አስታውቀዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የሚተላለፈው ቴሌቪዥን ዝግጅት የሰዓት ለውጥ ተደረገ

መጋቢት 25 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ሬድዮና ቴሌቪዥን ዝግጅት ክፍል እየተዘጋጀ በNilesat/EBS የሚቀርበው የ30 ደቂቃ መርሐ ግብር በየሳምንቱ እሑድ ከጧቱ 3፡30-4፡00 ሲተላለፍ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ሆኖም ሰዓቱ በቅዳሴ መጠናቀቂያ ላይ ይተላለፍ ስለነበር ለመከታተል አስቻጋሪ እንደሆነ ለክፍሉ ከሚደርሱት መልእክቶች ለመረዳት ተችሏል፡፡

በዚህም መሠረት ከፊታችን እሑድ ከመጋቢት 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በየሳምንቱ እሑድ ከቀኑ 5፡30-6፡00 ሰዓት የሚተላለፍ መሆኑንና የተላለፉ መርሐ ግብሮችን eotc.tv ላይ እንዲሁም በyoutube ላይ Mahibere kidusan Tv Program ብሎ በመፈለግ ማግኘት እንደሚቻል የሬድዮና ቴሌቪዥን ክፍሉ አስተባባሪ የሆኑት ዲ/ን ሄኖክ ኀይሌ ገልጸዋል፡፡

“ተማሪ በሞተ በሰባት ዓመቱ ተምሮ ይመጣል ትላለች እናቱ”

ይህ ሥነ ቃል ከሞቀ ከደመቀ ቤቱ የላመ የጣመን ትቶ የነገው ካህን፣ መምህር፣ ሊቅ የመሆን ህልሙን ለማሳካት ቃለ እግዚአብሔር ፍለጋ የተሰደደው ተማሪ በረሃብ፣ በእርዛት፣ በሽታን መቋቋም ተስኖት ወደ ቤቱ አለመመለሱን ፤ወጥቶ መቅረቱን የተማሪውን መከራ ለማዘከር በሰፊው በማኅበረሰቡ ዘንድ የተነገረ ቃል ነው።



ተማሪው በተማሪ ቤት ምንም ዓይነት የምግብ፣ የመጠለያ፣ የአልባሳት የመሳሰለውን ድጋፍ አያገኝም።

ጥሬ ቆርጥሞ፣ ኮቸሮ አኮችሮ በአንድ እራፊ ጨርቅ ተጠቅልሎ፤ ማደሪያ ሳያምረው በሳር ጎጆ ተጠግቶ የመማርያ አዳራሽ ሳይኖረው በዛፍ ጥላ ሥር ትምህርቱን በትጋት በንቃት ይከታተላል።

ተማሪው ከምግብ እጥረት የተነሳ ሰውነቱ ቀጥኖና አጥሮ በዳፍንት በሽታ በማታ ማየት እየተሳነው የትምህርት ቤቱን ኑሮ በመከራ ይገፋል።

ተማሪው በቂ ንፁሕ የመጠጥ ውኃ ፣ የመጸዳጃ ቤት ካለማግኘቱ የተነሣ ለልዩ ልዩ ተላላፊ በሽታዎች ይጋለጣል። በዚህም ሰውነቱ በምግብ እጥረት የተጎዳ በመሆኑ በሽታን መቋቋም ስለማይችል ለሞት በቀላሉ ይጋለጣል። 

ብዙዎችም ከትምህርት ቤት ያተረፉት በሽታ በዕድሜአቸው ሙሉ በአገልግሎታቸው ሲያውካቸው ይገኛል። 

ዛሬ በዓለም ብሎም በኢትዮጵያ በግልና በአካባቢ ንጽሕና ጉድለት የሚመጡ በሽታዎችን ለመቀነስና የተሻለ ዓለምን ለመፍጠር የሚረባረቡ አካላት ቢኖሩም የአብነት ተማሪዎች ግን ዛሬም የችግሩ ተጠቂዎች እንደሆኑ ይገኛሉ።

በተማሪ ቤት ጎልቶ የሚታየውን ችግር በተለየም ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የበሽታ ዓይነት ከግልና ከአካባቢ ንጽሕና ጉድለት፤ ከንጹሕ ውኃ መጠጥ አለማግኘት፤ ከምግብ እጥረት ጋር ተደምሮ የሚመጣ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን የጤና እክል ለመታደግ 12 ሺህ ተማሪዎችን ተጠቃሚ ሚያደርግ መርሐ ግብር ነድፎ የሁሉንም ተሳትፎ እየጋበዘ ይገኛል። የመርሐግብሩ ሥያሜ ተማሪ በሞተ……..የሚል መሪ ቃል እዲኖረው ተደርጓል። ምክንያቱም እውቀትን ለመሻት መራራውን ሞት የተጎነጩ ሊቃውንትን ለማዘከርና አሁን ያሉትን ተማሪዎች ሕይወት ለመታድግ ገላጭ ቃል ሆኖ በመገኘቱ ነው።

• የመርሐ ግብሩ አስፈላጊነት

  • የግልና የአካባቢን ንጽሕና መጠበቅ አምላካዊ ትዕዛዝ መሆኑን ለማስገንዘብና ተፈጻሚ ለማድረግ (ኦሪት ዘዳግም 23፣13) 
  • በአብነት ትምህርት ቤት በግልና በጋራ የንጽሕና አጠባበቅ ችግር የሚፈጠረውን የሕመምና የሞት አደጋ ለመቀነስ 
  • ተማሪዎቹ ትምህርታቸው ላይ እንዲያተኩሩ በማድረግ ምቹ የሆነ የመማርና የማስተማር ሁኔታ መፍጠር
  • በአብነት ትምህርት ቤቶች ዙሪያ ያለውን ዝቅተኛ የጤናና የንጹሕ መጠጥ ውኃ ተደራሽነት ትኩረት እንዲያገኝ ማድረግ 
  • የአብነት ተማሪው ስለጤና አጠባበቅ ምንነት ተረድቶ እርሱም ለኅበረተሰቡ እውቀቱን እንዲያስፋፋ ለማገዝ 

• ከእርሶ ምን ይጠበቃል

  • ፕሮግራሙ እውን እንዲሆን የሙያ የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ እንዲያደርጉ ተጋብዘዋል።
  • ፕሮግራሙን ተግባራዊ ለማድረግ 
  • 200 ግራም የሆነ 12,000 የልብስ ሳሙና 
  • 10 ባለ 3,000 ሊትር የውኃ ማጠራቀሚያ የፕላስቲክ ታንከር 
  • የውኃ ማከሚያ ኬሚካሎች
  • ለውኃ መጠጫ፣ ለማብሰያ፣ ለመመገቢያ የሚሆኑ የተለያዩ መጠን ያላቸው ቁሳቁስ
  • ለገላና ለልብስ ማጠቢያ የሚያገለግሉ ቁሳቁሶችን 
  • የግል ንጽሕና መጠበቂያ የሚያገለግሉ (መርፌ፣ ምላጭ)
  • በ10 ትምህርት ቤቶች የጋራ መጸዳጃ ቤት ሥራ እንዲሁም 
  • የጤና አጠባበቅ ሥልጠና 

የድጋፍ ማሰባሰቢያ 
ጊዜ፦ ከመጋቢት 21 እስከ ሚያዝያ 11 ቀን 2005 ዓም 
ቦታ፦ በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ
ለበለጠ መረጃ ስልክ፦ 0911 751529 / 0913 102621

ምኲራብ

መጋቢት 18ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊትደስታ

የዐብይ ጾም ሦስተኛው ሰንበት ምኲራብ ይባላል፡፡ ይህም ምኲራብ ከክርስቶስ ልደት በፊት እግዚአብሔርን ለማመስገን የእግዚአብሔር አማኞች ለጸሎት የሚሰባሰቡበት ቤት ስም ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙ ጊዜ ወደ ምኲራባቸው በመግባት ሰዎችን አስተምሯል፡፡ ሰዎች የእግዚአብሔር መመስገኛ የሆነውን ምኲራብ ገበያ አድርገውት ስላገኘም “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል ተብሎ ተጽፏል እናንተ ግን የሌባና የቀማኛ ዋሻ አደረጋችሁት” /ማቴ.21፥12-13/ በማለት ገሥጾ በዚያ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን ሁሉ በትኗቸዋል፡፡ ይህንን ምክንያት በማድረግ ሦስተኛው የዐብይ ጾም ሳምንት ምኩራብ በሚል ሰያሜ ይጠራል፡፡ በምኲራብ ገብቶ እንዳስተማረ የሚያሳስብ ዕለት የሚነበበው የወንጌል ክፍልም ዮሐ.12 እስከ ፍጻሜው ያለው ነው፡፡

ቅድመታሪክ
ስለምኲራብ /ሲናጎግ/
ምኲራብ ማለት የአይሁድ የጸሎት ቤት ማለት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን የአይሁድ አምልኮ በኢየሩሳሌም በነበረው ቤተ መቅደስና እንደ ሥርዓቱ የተመሠረተ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በዚሁ መቀጠል አልቻለም፡፡ ምክንያቱም ሃይማኖት የሚያጠፋ ቤተ መቅደስ የሚያፈርስና የሚያቃጥል አረማዊ ንጉሥ ተነሣ፡፡ 

አረማዊው ንጉሥ ናቡከደነጾር ቤተ መቅደሱን አፍርሶ ሕዝበ እስራኤልን ወደ ባቢሎን አፍልሶ ስለነበር ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አይሁዶች በሚገኙባቸው ሥፍራዎች ሁሉ ለጸሎትና በማኅበር ለማመስገን ቤቶችን ሊሠሩ እንደጀመሩ ይነገርላቸዋል ሕዝ.11፥16፡፡

በምኩራቦችም የብሉይ ኪዳን ማምለኪያ አምልኮታቸውን ይፈጽሙ ስለነበረና ምኲራቦቻቸውም ብዙ ስለ ነበሩ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋዌ ምስጢር ተገልጾ በተዋሕዶ ከብሮ ወደ ዓለም በመጣ ጊዜም ተከታዮቹን ሐዋርያትን እየላከ በምኲራቦቻቸው ያስተምራቸው ነበር፡፡ /ማቴ.4፥23፣ ሐዋ.6፥9፣ 13፥5፣ 14፥1፣ 17፥16-18/፡፡ በብሉይ ኪዳን ታሪክና ለአይሁዳውያን ሕግ አሥር የሚያህሉ ወንዶች በአንድ ማኅበር ቢገኙ ምኲራብ ለመሥራት ይፈቀድላቸዋል፡፡ እንዲሁም በሚያንጹት ምኲራብ ውስጥ ሕግና ነቢያት የተጻፈባቸው የብር ጥቅልሎች /Scroll/ በአንድ ሳጥን ወይም ማኅደር ውስጥ ይቀመጣሉ፡፡ /ፅላትበታቦት፣ ዳዊት በማኅደር እንደሚቀመጥ/ ማለትነው፡፡ ምኲራብ እንደ ደብተራ ኦሪት ሁሉ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚፈጽምበት ሕንፃ ነው፡፡

የ ቆሙ መቃብሮች

መጋቢት 16 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ስምዓኮነ መላክ

ሰዎች ሲሞቱ ወይም ነፍሳቸው ከሥጋቸው ሲለይ በክብር የሚያርፍበት ቦታ መቃብር ይባላል፡፡ መቃብር የሚላው ቃል የጎደጎደ ምድር ተብሎ ይተረጎማል፡፡ መዝ.14፥4፣ ኢሳ.22፥16 ሲዖልንም መቃብር ሲል ይገኛል፡፡ መትሕተ ታሕቲት ናትና፡፡

በማን ጊዜ እንደተጀመረ ባይታወቅም የሚቀበሩት በርስትነት በያዙት ቦታ ነበር ዘፍ.13፡፡ ያ ልማድ ሆኖልን ዛሬም በአዲስ ኪዳን የምንኖር ክርስቲያኖች እንደ አባቶቻችን ሁሉ በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ እንቀበራለን፡፡ ስለምን ቢሉ ሥጋውን ደሙን የበላንበትና የጠጣንበት ብቸኛዋ ርስታችን በምድር ቤተ ክርስቲያናችን ናትና ነው፡፡

የቀደመው ርስት በዋጋ ይገዛ ነበር የዛሬዋ የምእመናን ርስት ቤተ ክርስቲያን ዋጋዋ የክርስቶስ ደም ነውና ደሙ በነጠበበት ቦታ ብቻ ስትሠራ ትኖራለች የምእመናን መቃብር በጌታ ደም የተገዛ እንጂ በሰቅል በተመዘነ ወርቅ የተገዛ አይደለም፡፡ ይህም የጌታ ደም ከሁሉ በላይ የከበረ እንደሆነ የምእመናንም መቃብር የከበረ መሆኑን ያመለክታል፡፡

ለዛሬው ግን መቃብርን ያነሣነው ከአቤል ሞት ጀምሮ እስከ ጌታ ዳግም ምፅአት የማያቋርጥ ታሪክ ያለውን ጀግና ባለ ታሪክ መቃብርን ታሪኩን ለትውልድ ልናስተዋውቅለት ሳይሆን መምህራችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለቆሙ መቃብሮች የተናገረውን ቃል ማስታወስ ስለሚገባ ነው፡፡

መድኀኔ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ስብከት በጀመረ በመጨረሻው ዓመት በመቅደስ ተገኝቶ ለሕዝቡና ለደቀመዛሙርቱ ተናገረ፡- “ታላቅ ሸክም ማሰር ሰለሚችሉት መሸከም ግን ስለማይወዱት ስለ ጻፎችና ፈሪሳውያን ነበር የተናገረው፡፡

ለብዙዎች ብዙውን ኀጢአታቸውን በፍቅር የሸፈነው ጌታ ስለ ወንጀለኞች ሲጠየቅ ዝም የሚለው አምላክ ዮሐ.8፥11፣ ሉቃ.7፥47 በቤተ መቅደሱ አደባባይ በተሰበሰበው ሕዝብ መካከል የእነዚህን ታላላቅ የኦሪት አገልጋዮች በደል መዘርዘር ጀመረ፡፡ ተመክሮ ያልተመለሰን ሰው በአደባባይ ሊወቅሱት ይገባልና ጌታ በቅዱስ ወንጌል እንደተናገረው “ቢሰማህ ብቻውን አድርገህ ብቻህን ሆነህ ምከረው ባይሰማህ ካንተ ጋር ሁለት ሆናችሁ ምከረው….. እነርሱንም ባይሰማ ለቤተ ክርስቲያን ንገራት” ማቴ.18፥15-17 ብሎ በእግዚአብሔር ጉባኤ ላይም የማይገባ ነገርን አድርገዋልና መገሰጽ ስለሚገባቸው በታላቅ ቃል ገሰጻቸው 1ቆሮ.5፥5 በመጽሐፍ ቃልህ እውነት ነው ተብሎ የተነገረለት መምህር ነውና ዮሐ.17፥17 እነርሱን ከውስጥ እስከ ውጭ ሊገልጹ በሚችሉ የተግሣፅ ቃላት ገሰፃቸው፡፡

በዘመኑ የነበሩ መምህራን አባቶቻቸው በሠሩት ኀጢአት የተጸጸቱ ለመመሰል አባቶቻቸው የገደሏቸው የነቢያትን መቃብር በኖራ እየለሰኑ ይሠሩና ያሠሩ ነበርና ያንኑ የሠሩትን ልስን መቃብር እየተመለከተ “የተለሰነ መቃብር የምትመስሉ” ሲል ተናገራቸው ይህ መቃብር ቢከፍቱት ለአፍንጫ የሚከረፋ ለዐይንም የሚከፋ ነገር አይታጣበትም፡፡ ሥጋው ተልከስክሶ አጥንቱ ተከስክሶ፣ እዡ ፈሶ ሲታይ ከውጭ የተለሰነ ውበቱን ያጠፋዋል፡፡  አብረውት እንዳይኖሩ ያስገድዳል በዚህ ረጅም ዕድሜው እንደላዩ ሁሉ ውስጡ አምሮ አያውቅም፡፡

ዘመኑን ሁሉ ሕይወት በሌላቸው ነገሮች የተሞላ ሆኖ ይኖራል እንጂ፡፡ ከዕለታት ባንዱ ስንኳን ንጹህ ነገር ክርስቶስን ቢያገኝ በሥጋ የሞተው በመንፈስ ግን ሕያው የሆነው ጌታ በትንሣኤ አሸንፎት ይዞ ማስቀረትም አይቻለው ብሎ ባዶውን ቀርቶ ይሄው እስከዛሬ ያለ ክርስቶስ ይኖራል፡፡ በእውነት ክርስቶስ በመቃብር መስሎ የተናገረበት ነገሩ ምን ይመስላችኋል? ለጊዜው የሚያመለክተው በዚያ ዘመን እስከ ክርስቶስ ወደ መቃብር መውረድ ድረስ በሰው ልጆች ላይ ሙስና መቃብር በሥጋቸው ወደ ሲዖል መውረድ በነፍሳቸው የግድ የነበረባቸው መሆኑን ያመላክታል፡፡

በዘመኑ ባለ ጊዜ ሆኖ ሞት ውጦ መቃብር ተረግጦ የማስቀረት ኀይል ነበረውና፡፡ ያንን የሚገልጽ ሲሆን ፍጻሜው ግን ከውጭ ለሰው መልካም መስለው ስለሚታዩት ከውስጥ ግን ለእግዚአብሔር የሚመች በጎ ተግባር የሌላቸው ሰዎች እንዲገሰጹበት የተጻፈ ነው፡፡

ከውጭ ሲያዩአቸው ይጸልያሉ ይጾማሉ በጾምና በጸሎት ብዛት በገድልና በትሩፋት ጠውልገው ይታያሉ ስመ እግዚአብሔርን ጠርተው ይምላሉ ሐሰቱን እውነት ያስመስላሉ በልባቸው የሌላውን የእግዚአብሔር ቃል አንሥተው ሲናገሩ በቂሳርያ ከተመሰገነው ጴጥሮስ ይበልጣሉ ዝምነታን በማያውቀው አንደበታቸውም ደግመውና ደጋግመው ስሙን ሲጠሩ ከጳውሎስ በላይ ሰባኪ ይመስላሉ ከውስጣቸው ግን እንዲህ አይደሉም፡፡ አመጽንና ሽንገላን ተሞልተዋል፡፡ በክፉ ምኞታቸውና አስቀያሚ በሆነው መሸታቸው የገዛ ነፍሳቸውን ገለው የገዛ ሥጋቸውን መቃብር አድርገው ቀብረዋል፡፡

በወይንና በአረቂ አልሰከሩም እንጂ በኀጢአት ሰክረው ወድቀዋል፡፡ ከመብልና ከመጠጥ እንጂ ክፉ ተግባራቸውን ከመተው የማይከለክሉ ይልቁንም በሞተ ሥራ የተሞሉ የቆሙ መቃብሮች ሆነዋል ስለዚህም መቃብር ውስጥ ያሉ ሙታንን ስንኳን የማይጠላ ጌታ ለተለሰኑ መቃብሮችም በቤተ መቅደሱ አደባባይ ቆሞ አሳምረው የለሰኑአቸው ልስን መቃብሮችን አሻግሮ እየተመለከተ ሁሉም ወደ መዳን የሚደርሱበትን ሕያው መልእክቱን አስተላለፉ፡፡

ወንድሜ ሆይ! አንተስ እንዳምን ነህ? ከውስጥህስ ምን ይገኛል? እግዚአበሔር አንተን ክርስቲያን አድርጎ ሐዋርያት ከሰበሰቧት አንዲት ማኅበር አባል ሲያደርግህ ምን ዓይነት ዓላማ እንደነበረው ታውቃለህ? ጨለማውን ዓለም ካንተ በሚወጣው የመንፈስ ቅዱስ ብርሃን ሊሞላው፣ ሕይወት አልጫ ለሆነችባቸው ማጣጫ ሊያደርግህ ማቴ.5፥12-13 በአሕዛብ መካከል ስሙን አሸክሞ ሊልክህ ሐዋ.9፥5 ዓላማ ስላለው ነው፡፡

የታመሙትንና በአጋንንት ተይዘው የሚሰቃዩትንም የሚፈውሳቸው ለምጻሞችን የሚያነጻቸው የረከሱትን የሚቀድሳቸው አንተን መሣሪያ አድርጎ እንደሆነ ታውቃለህ? አንተ ግን ለዚህ ዓላማ የተጠራህ መሆንህን የረሳህ ትመስላለህ፡፡ በአለባበስህና በከንፈርህ ብቻ እግዚአብሔርን ታመልካለህ ቀን ቆጥረህ ደማቅ በሆኑ የዓመትና የወር በዓላት ብቻ ለእግዚአብሔር ትዘምራለህ በሌላው ቀን ግን ትጠፋለህ ቃሉን ታውቃለህ እንደ ቃሉ መኖር ግን ተስኖሃል ከውጭ እንጂ ከውስጥ የሚታይ ነገር የሌለህ መጥፎ ሰው ሆነሃል፡፡ በክፉ መሻትህ እየወጋህ ሕያዊት ነፍስህን ገለህ የቆመ መቃብር ሆነሃታል፡፡

የማይታይ የተሰወረ የማይገለጥ የተከደነ አለ ይመስልሀልን? ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመት ቆይታ በኋላ ተከድኖ ይኖር የነበረ መቃብር መገለጡን በጌታ ደም ድብቅ ምሥጢሩን ከረጅም ዓመታት በኋላ ማጣቱን እንዳትረሳ ማቴ.27፥57 አንተ ሆይ! ሳይነግሩት የሰውን ማንነቱን የሚያውቅ ጌታ አንተንስ ቢገልጥህ? ዮሐ.2፥25 ከላይ የተለሰነ ኖራህን ቢያነሳብህስ? የቆመው መቃብርነትህ በጌታ ቃል የሞተውን ሳይሆን ሕያው የሆነ አልዓዛርን የሚያስገኝ ይመስልሃል? ብታምን የልቡናህን ትንሣኤ ዛሬ ታየ ዛሬም የተለሰነው መቃብር በር ላይ ቆሞ ይጣራል በውስጥህ ያሉት ሙታን አካሎችህ ዛሬ ድምጹን የሚሰሙበት ጊዜ ደርሷል እርሱም አሁን ነው ዮሐ.5፥25፡፡

የሚያሳዝነው ነገር ተዘግቶ ተለስኖ መቀመጡ ነው እንጂ የተከፈተ መቃብርማ ለብዙዎች የሚያስገርም ምስጢር ተገኝቶበታል እኮ! ሉቃ.24፥12 መላእክቱ የከበቡት የጌታ ደቀ መዛሙርት የጎበኙት ያ ቅዱስ መቃብር ባዶም ቢሆን ለመጀመሪያ ጊዜ ትንሣኤውን የሰበከ እርሱ ነበር፡፡

ወንድሜ ሆይ! የቆመ መቃብር ብትሆንም ለእግዚአብሔር ቃል የተከፈተ ልብ ካለህ እውነት እልሃለሁ ስላንተ ወዳንተ ወደመቃብሩ መላእክቱን ያዝልሀል ለደቀ መዛሙርቱ ሳይቀር የሚደንቅ ጥበብን ይገልጥብሃል ለጌታችን ቃል የተከፈተ ልብህ ዝቅ ብለው ቢያዩትስ የጌታ ልብስ ብቻ እንጂ ሌላ ምን ይገኝበታል፡፡ ከእውቀት፣ ከጥበብህ ከቅድስና የተለየሁ ባዶ ሰው ነኝ ብለህ ብታምን እንኳን እግዚአብሔር ባዶነትህን ለምስክርነት ይሻዋልና ከላይህ ላይ ያለ ልስንህን አስወግደው፡፡

አለበለዚያ የክፉዎች አጋንንት ማደሪያ መሆንህን አትርሳው፡፡ ማቴ.8፥28 ከዚያ በፊት ግን አሁን ዕድል አለህ፡፡ እንደውጪ ሁሉ ውስጠኛውንም የመቃብር ክፍል ማጽዳት ትችላለህ፡፡ አንተ እኮ! ዕድለኛ ነህ፡፡ የአባትህ ድምጹ እስከመቃብር ድረስ ዘልቆ ይሰማል ቅዱስ የሆነው ደሙ በመቃብር ያሉትን ሳይቀር መቃብራቸውን ከፍቶ ይቀድሳል እንዳትረሳ! ይሄ ዕድል ላንተም ተሰጥቶሃል፡፡ ደግሞም አንድ ነገር አለ እግዚአብሔር ለሕዝቡ የገባው ቃል ኪዳን አለ መቃብሩን ከፍቶ ለሞቱ አጥንቶች ሕይወትን ሰጥቶ የሚያኖርበት ጊዜ አለ ይሄ ቃል ኪዳን ላንተም የተገባ ቃል ኪዳን ነውና አትፍራ ምን አልባትም ይሄ ቃል ኪዳን ላንተም የተገባ ተስፋ አትቁረጥ፡፡

በዙሪያህ ሆነው ከመቃብሩ ደጃፍ ድንጋዩን ማን ያንከባልልናል የሚሉም ይኖራሉ ድንጋዩ ታላቅ ቢሆንም ጊዜው ሲደርስ እግዚአብሔር መላኩን ልኮ አንተ ባልጠበቅከው ሰዓት ሊያነሣው እንደሚችል አትጠራጠር፡፡ መቃብር ብዙ ኀያላንን ይዞ ማስቀረቱ የተገለጠ ነው፡፡ እነ ዳዊት እነሶምሶን፣ ዮፍታሔ፣ ጌዴዎን ሌሎችም ኀያላን መቃብር ያድራሉ ደራሲዎቹ የደረሱላቸው ተራኪዎቹ የተረኩላቸው ዜመኞቹም ያዜሙላቸው ጀግኖች ሁሉም ከመቃብር አላመለጡም ምድራዊ ፍጥረት ሥጋዊ ደማዊ ሰውነት ሁሉም የመቃብር ምርኮኞች ሆነዋል፡፡

አንተ ሆይ! ባንተም ውስጥ ስንት ኀያላን የእግዚአብሔር ቃላት ተቀብረው ቀርተዋል መሰለህ? እነ አባ ጳውሊ ከዓለም ወጥተው የኮበለሉባቸው እነ አባ እንጦንስ ሥርዓተ መላእክትን የተላመዱባቸው ይሄ ግዙፍ ዓለም የተከናወነባቸው እነዚያ ሰባሪ ቃላቶች አንተ ዘንድ ሲደርሱ ግን ሳይሠሩ ቀብረህ አስቀርተሃቸዋል፡፡

እውነት እልሃለሁ አዲስ ሆነህ የምትሠራው በቅዱስ ቃሉ ነውና ቃሉን ጠብቅ ብታምንም ባትምንም በክፋት ብትሆን ሳትወድ በግድ “መቃብር ሆይ ይዞ ማስቀረትህ ወዴት አለ?” ሆሴ.13፥14፣ 1ቆሮ15፥55 ተብለህ መጣልህ አይቀርምና ይህ የፈጣሪህ ድምጽ ወዳንተ ባደረበት ቅጽበት ወዲህ በፈቃድህ ንስሓ ግባ ይሄ ጊዜ ለሌላ ለምንም የተመደበ አይደለም የንስሓ ብቻ ነው፡፡

“እነሆ መቃብራችሁን እከፍታለሁ ከመቃብራችሁም አወጣችኋለሁ ወደ እስራኤል ምድርም አገባችኋለሁ መቃብራችሁን በከፈትሁ ጊዜ ከመቃብራችሁም ባወጣኋችሁ ጊዜ እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ታውቃላችሁ” ሕዝ.37፥12-13፡፡

ቅድስት

መጋቢት 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

በአባ አሥራተ ማርያም ደስታ

የማቴ.6፥16-24 ምንባብ በአንድምታ ትርጓሜ
ቁ.16. በምትጾሙበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትሁኑ፡፡ እነዚያ ፊታቸውን አጠውልገው ግንባራቸውን ቋጥረው ሰውነታቸውን ለውጠው ይታያሉና፡፡ እንደ ጾሙ ሰው ያውቅላቸው ዘንድ የወዲህኛውን ውዳሴ ከንቱ አገኙ የወዲያኛውን ዋጋቸውን አጡት ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ፡፡ 

ቁ.17. እናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ ራሳችሁን ተቀቡ ፊታችሁን ታጠቡ የተቀባ የታጠበ እንዳይታወቅበት አይታወቅባችሁ ሲል ነው፡፡ ይህስ በጌታ ጾም ምን ውዳሴ ከንቱ አለበት ይኸውስ በከተማ ነው በገዳም ቢሉ በከተማ ነው እንጂ በገዳምማ ምን ውዳሴ ከንቱ አለበት ይህም ሊታወቅ ዳንኤል እኔ ዳንኤል ሦስት ሳምንት ሙሉ ሳዝን ማለፊያ እንጀራ አልበላሁም ሥጋና ጠጅም በአፌ አልገባም ዘይትም አልተቀባሁም ብሏል፡፡ እናንተስ ራሳችሁን ተቀቡ /ፍቅርን ያዙ/ ፊታችሁን ታጠቡ፣ ንጽሐናን ገንዘብ አድርጉ ወይም ትሕትናን ያዙ፣ በንስሓ እንባ ታጠቡ፡፡

ቁ.18. እንደ ጾማችሁ ሰው እንዳያውቅባችሁ ሁሉን መርምሮ ከሚያውቅ ከሰማያዊ አባታችሁ በቀር ነው እንጂ ተሠውራችሁ ስትጾሙ ተሰውሮ የሚያያችሁ ሰማያዊ አባታችሁ በጻድቃን በመላእክት በኀጥአን በአጋንንት መካከል ዋጋችሁን ይሰጣችኋል፡፡

በእንተ ምጽዋት
ቁ.19. እህሉን ነዳያን ከሚበሉት ብለው አኑረውት ነቀዝ ቢበላው፣ ልብሱን ነዳያን ከሚለብሱት ብለው አኑረውት ብል ቢበላው ወይም ነቀዝ ቢያበላሸው ምቀኝነት ነውና ዳግመኛ ለክፉ ቀን ይሆነኛል ብሎ ማኖር እግዚአብሔርን ከዳተኛ ማድረግ ነው፡፡ በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ አይመግበኝም ማለት ነውና አንድም ምንም እጅ እግር ባያወጡለት ገንዘብ ማኖር ጣዖት ማኖር ነውና ኅልፈት ጥፋት ያለበትን ምድራዊ ድልብ አታድልቡ፣ ብል የሚበላውን ነቀዝ የሚያበላሸውን ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው የሚወስዱትን ከሚወስዱበት ቦታ አታድልቡ፡፡

ቁ.20. ኅልፈት ጥፋት የሌለበትን ሰማያዊ ድልብን አድልቡ እንጂ፡፡ ብል የማይበላውን ነቀዝ የማያበላሸውን ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው የማይወስዱትን ከማይወስዱበት ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ፡፡

ገንዘባችሁ ካለበት ዘንድ ልቡናችሁ ከዚያ ይኖራልና አንድም ውዳሴ ከንቱ ያለበትን ምጽዋት አትመጽውቱ አጋንንት በውዳሴ ከንቱ የሚያስቀሩባችሁን ሳይሆን የማያስቀሩባችሁን ምጽዋት መጽውታችሁ፣ ምጽዋታችሁ ካለበት ልቡናችሁ ከዚያ ይኖራልና፡፡

ቁ.22. የሥጋህ ፋና ዓይንህ ነው ማለት የሥራህ መከናወኛ ዐይንህ ነው፡፡ ዓይንህ ብሩህ የሆነ እንደሆነ አካልህ ሁሉ ብሩህ ይሆናል ዐይንህ የቀና እንደሆነ ሥራህ ሁሉ የቀና ይሆናል፡፡

ቁ.23. ዐይንህ የሚታመም የሆነ እንደሆነ አካልህ ሁሉ ጨለማ ይሆናል ማለት ዐይንህ ግን ያልቀና እንደሆነ ሥራህ ሁሉ ያልቀና ይሆናል፡፡ ባንተ ያለ ብርሃን ጨለማ ከሆነ ጨለማህ እንደምን ይሆን? በተፈጥሮ የተሰጠህ ዓይንህ የታመመ ከሆነ ጨለማ እንደምን ይጸናብህ ይሆን የታመመው ዓይንህ እንደምን ያይልሃል?

ቁ.24. አንድ ባሪያ ለሁለት ጌታ መገዛት አይቻለውም፡፡ ከፍለን መጽውተን ከፍለን ብንኖር ምነዋ ትሉኝ እንደሆነ ይህም ባይሆን ማለት እገዛለሁም ቢል አንዱን ይወዳል ሌላውን ይጠላል፣ ላንዱ ይታዘዛል ለሌላው አይታዘዝም እንጂ፡፡ እንደዚህም ሁሉ እናንተም ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ /መታዘዝ/ መገዛት አይቻላችሁም፡፡

ቁ.25. ስለዚህ ነገር ለነፍሳችን ምን እንበላለን ምን እንጠጣለን ለሥጋችን ምን እንለብሳለን ብላችሁ አታስቡ መብል መጠጥን ለነፍስ ሰጥቶ ተናገረ የበሉት የጠጡት ደም ይሆናል፡፡ በዚህ ምክንያት ነፍስ ከሥጋ ተዋሕዳ ትኖራለችና፣ ልብስን ለሥጋ ሰጥቶ ተናገረ ምንም የምታፍር ነፍስ ብትሆን አጊጦ ከብሮ የሚታይ ሥጋ ነውና ነፍስን እምኀበ አልቦ አምጥቼ ሥጋን ከአራቱ ባሕርያት አዋሕጄ የፈጠርኋችሁ ለእናንተ ምግብ ልብስ እንደምን እነሳችኋለሁ ለማለት እንዲህ አለ፡፡

ቁ.26. ከፍለን መጽውተን ከፍለን ካላኖርን ምን እንመገባለን ትሉኝ እንደሆነ ዘር መከር የሌላቸውን በጎታ፣ በጎተራ፣ በሪቅ የማይሰበስቡትን ሰማያዊ አባታችሁ የሚመግባቸው አዕዋፍን እዩ ማለት አዕዋፍን አብነት አድርጉ ከተፈጥሮተ አዕዋፍማ ተፈጥሮተ ሰብእ አይበልጥምን? ለኒያ ምግብ የሰጠ ለእናንተ ይነሣችኋልን?

ዘወረደ

መጋቢት 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

በአባ አሥራተ ማርያም ደስታ

የዮሐ.3፥10-21  ምንባብ በአንድምታ ትርጓሜ

ቁ.11. ራሱን ከዮሐንስ አግብቶ፡፡ ያየነውን፣ የሰማነውን እናስተምራለን ብዬ እንድናስተምር በእውነት እነግርሃለሁ፡፡ ምስክርነታችንን ግን አትቀበሉም፡፡

ቁ.12. ምድራዊ ልደታችሁን ስነግራችሁ ብነግራችሁ ያልተቀበላችሁኝ ሰማያዊ ልደታችሁን ብነግራችሁ እንደምን ትቀበሉኛላችሁ፡፡ ለዚህ ምክንያት አለው በጥምቀት፣ በንፍሐት ይሰጣል፡፡ ለዚያ ግን ንቃሕ ዘትነውም ባለው ነው፡፡ ምክንያት የለውምና፡፡  

ቁ.13. ወደ ሰማይ የወጣ የለም፣ ወደ ሰማይ የወጣው ከሰማይ የወረደው ክርስቶስ ነው እንጂ፡፡ ይህንስ ለምን ይሻዋል ቢሉ የወጣውም የወረደውም አንድ አካል አንድ ባሕርይ ነው ለማለት ሰማያዊ ሀብትን ሰማያዊ ዕውቀትን ገንዘብ ያደረገ የለም፣ ሰማያዊ ሀብትን ሰማያዊ እውቀት ገንዘብ ያደረገ ከሰማይ የወረደው ክርስቶስ ነው እንጂ፡፡

ቁ.14. ሙሴ እባብ በምድረ በዳ እንደ ሰቀለ እንዲሁ የሰው ልጅ ክርስቶስ ይሰቀል ዘንድ አለው፡፡ ጌታ መሰቀሉ ስለምን ነው ቢሉ ትንቢቱ ምሳሌው ሊደርስ ሊፈጸም፡፡ ጌታ እስራኤልን መና ከደመና አውርዶ ውኃ ከጭንጫ አፍልቆ ቢመግባቸው ከዚህ ምድሩ ብቅ ሰማዩ ዝቅ ቢልለት፣ ከደጋ ላይ ቢሆንለት የወርጭ ሰደቃ እያበጀ ውኃውን እያረጋ መና መገብኳችሁ ይላል እንጂ ይክልኑ እግዚአብሔር ሠርዓ ማዕድ በገዳም ቆላ ቢሆንማ ባልተቻለውም ነበር ብለዋል፡፡ ጌታም የርሱን ከሃሊነት የነርሳቸውን ሐሰት ለመግለጥ ሙሴን አውርዶሙ ቆላተ ሐራሴቦን አለው፡፡ ነቅዐ ማይ የሌለበት በረሐ ነው፡፡ ይዟቸው ወርዷል መናም ዘንሞላቸዋል፣ ውኃውም ፈልቆላቸዋል፡፡ ነገር ግን ነዘር የሚባል እባብ እየነከሰ ይፈጃቸው ጀመር፡፡ ሙሴን ከኛ ስሕተት ኃጢአት አይታጣምና ወደ እግዚአብሔር አመልክትልን አማልደን አሉት፡፡ ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክትላቸው ድሩቶን ብርት /ነሐስ/ አርዌ /እባብ/ አስመስለህ ሠርተህ ከሚገናኙበት አደባባይ ከእንጨት ላይ ስቀልላቸው ያልጸናባቸው መልኩን አይተው የጸናባቸው ድምጹን ብቻ ሰምተው ይዳኑ አለው እንዳዘዘው አደረገው፡፡ ያልጸናባቸው መልኩን አይተው የጸናባቸው ድምጹን ብቻ ሰምተው ድነዋል፡፡ አርዌ ምድር የዲያብሎስ፤ አርዌ ብርት የጌታ ምሳሌ፤ በአርዌ ምድር መርዝ እንዳለበት በዲያብሎስም ፍዳ ኃጢአት አለበት፡፡ በአርዌ ብርት መርዝ እንደሌለበት በጌታም ፍዳ ኀጢአት የለበትም፡፡ ጽሩይ እንደሆነ ጌታም ጽሩየ ባሕርይ/ በባሕርዩ ንጹሕ/ ነው፡፡ አርዌ ብርት በአርዌ ምድር አምሳል መስቀሉ፣ ጌታም በአርአያ እኩያን ለመስቀሉ ምሳሌ፡፡ ተቅለቈ ምስለ ጊጉያን ከክፉዎች ተቆጠርኩ እንዲል፡፡ ይህንም ሊቁ ከመ ይደምረነ ምስለ ነፍስ ጻድቃን ከጻድቃን ነፍስ ይደምረን ዘንድ ብሎ ተርጉሞታል፡፡ መልኩን አይተው ድምጹን ሰምተው የዳኑ በአካል ያዩ ከቃሉ ሰምተው ያመኑ የዳኑ ድምጹን ብቻ ሰምተው የዳኑ ከርሱ በኋላ በተነሡ መምህራን ሰምተው ያመኑ የዳኑ የምእመናን ምሳሌ፡፡

ቁ.15. በእርሱ ያመነ ሁሉ እንዳይጎዳ ለዘለዓለም ይድን ዘንድ እንጂ፡፡ አይጎዳም ይድናል እንጂ፡፡

ቁ.16. አንድ ልጁን ለሁሉ ቤዛ አድርጎ እስከ መስጠት ደርሶ እግዚአብሔር ዓለሙን ወዶታልና፡፡ በእርሱ ያመነ ሁሉ እንዳይጎዳ የዘላለም ደኅንነት ያገኝ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ በርሱ ያመነ ሁሉ አይጎዳም የዘላለም ደኅንነት ያገኛል እንጂ፡፡

ቁ.17. እግዚአብሔር በዓለሙ ሊፈርድበት ልጁን ወደዚህ ዓለም አልሰደደውም፡፡ እርሱ ስለካሠለት ያድነው ዘንድ እንጂ አስቀድሞ ያልተፈረደበት ሆኖ ሊፈርድበት አልሰደደውም፡፡ ተፈርዶበታልና ከተፈረደበት ፍርድ ሊያድነው ነው እንጂ፡፡ በሥጋው ሊፈርድበት አልላከውምና ተኀደገ ለከ ኀጢአትከ ተኀደገ ለኪ ኀጢአተኪ እያለ ሥርየተ ኀጢአትን ሊሰጥ ነው እንጂ፡፡

ቁ.18. በእርሱ ያመነ አይፈረድበትም፡፡ በእርሱ ባላመነ ግን ፈጽሞ ይፈረድበታል፡፡ በአንድ በእግዚአብሔር ልጅ አላመነምና፡፡

ቁ.19. ፍርዱም ይህ ነው ብርሃን ክርስቶስ ወደ ዓለም መጥቶአልና፡፡ ሰውም ከብርሃን ጨለማን፣ ከዕውቀት ድንቁርናን ከክርስቶስ ሰይጣንን፣ ከወንጌል ኦሪትን ወዷልና እስመ እኩይ ምግባሩ፡፡

ቁ.20. ምግባሩ ክፉ የሆነ ሰው ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና ወደ ብርሃን አይመጣም ሥራው እንዳይገለጥበት ሥራው ክፉ ስለሆነ ሥራው በጎ የሆነ ሰው ግን ወደ ብርሃን ይመጣል፡፡ ሥራው ይገለጥ ዘንደ ስለ እግዚአብሔር ብሎ ይሠራዋልና ሥራቸው ክፉ የሆነ ጸሐፍት ፈሪሳውያን፣ አይሁድ፣ አሕዛብ ጌታን ይጠላሉ በጌታ አያምኑም ሥራቸው እንዳይገለጥ ሥራቸው ክፉ ስለሆነ ሥራቸው በጎ የሆነ ሐዋርያት፣ አይሁድ አሕዛብ ግን በጌታ ያምናሉ ሥራቸው ይገለጥ ዘንድ ሥራቸው በጎ ስለሆነ፡፡

በሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ጉዳይ ውይይት ተደረገ

በዳዊት ደስታ

መጋቢት 9 ቀን 2005 ዓ.ም.

ሰማዕቱ የአቡነ  ጴጥሮስ ሐውልት

 

የሰማዕቱ የአቡነ  ጴጥሮስ ሐውልት የቴክኒክ ጥናት ኮሚቴ ሐውልቱ ያለምንም ጉዳት እንዴት መነሣት እዳለበት ከባለ ድርሻ  አካላት ጋር ውይይት አደረገ፡፡

 

የቴከኒክ ጥናት ኮሚቴው የካቲት ፲፫ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስብሰባ አዳራሽ ለግማሽ ቀን ባካሔደው ውይይት ሐውልቱ ተነሥቶ ወደ ሥራ ከመገባቱ በፊት በሚያስፈልጉ ጉዳዮች ላይ በስፋት መክሯል፡፡

 

ሐውልቱ ከቦታው ተነሥቶ የመንገድ ግንባታው ከተጠናቀቀ በኋላ እንዴት ወደ ነበረበት መመለስ እነዳለበት ኮሚቴው ከወዲሁ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን የቴክኒክ  ጥናት ኮሚቴው የፕሮጀክቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ በኃይሉ ስንታየሁ አስታውቀዋል፡፡

 

የሰማዕቱ የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት በጊዜያዊነት የሚነሣበት ምክንያት በዐደባባይ ላይ የቀላል ባቡር መስመር ዝርጋታ ስለሚካሔድ ጉዳት እንዳይደርስበት በሚል እንደሆነ በሐውልቱ  አነሣስ የቴክክ ጥናት ኮሚቴ የፕሮጀክቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ በኃይሉ ስንታየሁ ስለ አዲስ አበባ ባቡር ፕሮጀክት አሠራር አጠቃላይ ገለጻ አድርገዋል፡፡

 

በውይይቱ መርሐ ግብሩ ላይም ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡ ሲሆን የመጀመሪያው “የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ታሪካዊ ዳራና ሐውልቱ የሚገኝበት ሁኔታ” በሚል ርእስ ጥናት ያቀረቡት በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ዳይሬክቶሬት ጊዜያዊ አስተባባሪ አቶ ኃይሉ ዘለቀ ናቸው፡፡

 

እንዲሁም የቴክኒክ ጥናት ኮሚቴው ሰብሳቢና ከፍተኛ የማይንቀሳቀስ ቅርስ ጥገና ባለሙያ አቶ በየነ ደሜ “ የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት አነሣሥ” በሚል ርእስ ጥናታዊ ጽሑፍ አቅርበዋል፡፡

 

በቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ የተለያዩ ጥያቄዎችና አስተያየቲች ከተሳታፊዎቹ የቀረበ ሲሆን ፤ በተለይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው የተገኙት መ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል “ እስካሁን ተነሥቶ ያልተመለሰ ሐውልት ስላለ ማነው የሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልትን በባለቤትነት የሚያስመልሰው ፤ ቤተ ክርስቲያን ለእኒህ ቅዱስ አባት የመጨረሻ ክብር ሰጥታ አክብራለችና ሐውልቱ ሲመለስ እንደቀድሞ ስለመከበሩ ምን ዋስትና አለው ” ሲሉ ስጋታቸውን ገልጠዋል፡፡

 

ሌላው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ጥናት  ምርምር መምህር ዶክተር ሐሰን ሰይድ “ ወደፊት የባቡር ንቅናቄ ስለሚኖር በሐውልቱ ላይ የሚያመጣውን አደጋ ከወዲሁ አብሮ ማጤን ያስፈልጋል” ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

ለተነሡት ጥያቄዎችና አስተያየቶች ከጥናት አቅራቢዎቹ  በቂ ምላሽና ማብራሪያዎች ተሰጥቶባቸዋል፡፡

 

በጊዜያዊነት የሚነሣው የሰማዕቱ የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት የባቡር ሀዲዱ ዝርጋታ ተጠናቆአስኪያልቅ ድረስ በብሔራዊ ሙዚየም እንደሚቀመጥ ተጠቁሟል፡፡ሐውልቱ መቼ እንደሚመለስ ፣ የአወሳሰዱ ሒደትና የሚያስፈልጉ ግብአቶችን እንዲሁም ወጪዎችን በሚመለከት የቅርስ ባለአደራ ባለሥልጣንና የአዲስ አበባ አስተዳደር እንደሚፈራረሙ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

በውይይቱ መርሐ ግብር ላይ የተለያዩ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ባለሥልጣናት ፣ የቤተ ክርስቲያንና የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ተወካዮች፣ የዩኒቨርስቲ ምሁራንና ተጋባዥ  እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

ምንጭ፡-  ስምዐ ጽድቅ  ፳ኛ ዓመት ቁጥር ፲፪  ከመጋቢት ፩ -፲፭ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም.

 

የዲላ ዮኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ የተመሠረተበትን አስራ ስድስተኛ ዓመቱን አከበረ

መጋቢት 6 ቀን 2005 ዓ.ም.


በዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

በማኅበረ ቅዱሳን በዲላ ወረዳ ማእከል ሥር የሚገኘው የዲላ ዮኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ የተመሠረተበትን ዐሥራ ስድስተኛ ዓመቱን በዋለሜ ደብረ ሰላም ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን በደመቀ ሁኔታ አከበረ፡፡

ግቢ ጉባኤው ከየካቲት 29 ቀን እስከ መጋቢት 1 ቀን 2005 ዓ.ም የተመሠረተበትን በዓል ሲያከብር በማኅበረ ቅዱሳን የአዋሣ ማእከል ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላልፏል፡፡ ማእከሉ በወከለው በአቶ ታደሰ ፈንታ በኩል ባስተላለፈው መልእክት “ዛሬ የምሥረታ በዓላችሁን የምታከብሩ ተማሪዎች ከመደበኛው ትምህርታችሁ ጎን ለጎን መንፈሳዊ ተግባራችሁን አጠናክራችሁ እንድትቀጥሉ ጥሪያችንን በማቅረብ ነው” በማለት የእንኳን አደረሳችሁ መልእክቱን አስተላልፏል፡፡

 

አያይዞውም “የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች በዕድሜ ዘመናችሁ ሁሉ በሥርዓተ አምልኮ መጽናት፣ በግቢ ቆይታችሁ በምታገኙት መንፈሳዊ ዕውቀት በመደገፍ ሀገራችሁንና ቤተ ክርስቲያናችሁን ማገልገል፣ ማኅበራችሁ ማኅበረ ቅዱሳን አሁን በመስጠት ላይ ያለውን አገልግሎት በማጠናከርና ከማኅበሩ ጎን በመሆን ለቤተ ክርስቲያን ያላችሁን ታማኝነት ትወጡ ዘንድ እናሳስባችኋለን” ብሏል፡፡

የዲላ ዮኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ ተማሪ ገብሬ ወርቁ ስለግቢው ምሥረታ በዓል አከባበር ሲናገር “የዘንድሮን ምሥረታ በዓል ግቢ ጉባኤው ሲያከብር ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን የምትጠብቅባቸውን መንፈሳዊ አገልግሎት በብቃት እንዲወጡ ለማስቻል በማሰብ ነው” ብሏል፡፡

 

የዲላ ዋለሜ ደብረ ሰላም ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መላከ ሰላም አምሳሉ ሣለ በምሥረታ በዓሉ ላይ በመገኘት አባታዊ ምክራቸውን የለገሱ ሲሆን መላከ ሰላም አምሳሉ በምክራቸው “የዲላ ዮኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ በዚህ ደብር መኖሩ በቤተ ክርስቲያኒቱ የወንጌል አገልግሎት ላይ ከፍተኛ መንፈሳዊ አስተዋጽኦ አድርጓል፤ በመሆኑም የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የምሥረታ በዓላችሁን ስታከብሩ መንፈሳዊ አገልግሎታችሁን ወደ ፊትም አጠናክራችሁ ለመቀጠል በማሰብ መሆን አለበት” ሲሉ መክረዋል፡፡

በምስረታ በዓሉ ላይ በተጋባዥ መምህራንና መዘምራን፣ በተመራቂ ተማሪዎች እና በግቢ ጉባኤው ተማሪዎች ስብከቶች፣ መዝሙሮችና ልዮ ልዮ መንፈሳዊ መርሐ ግብራት ቀርበዋል፡፡ እንዲሁም ከሠላሳ በላይ የሚሆኑ የግቢው ተመራቂ ተማሪዎች በምስረታ በዓሉ ላይ በመገኘት ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ልምዳቸውንና ተሞክሯቸውን አካፍለዋል፡፡

አቶ ፍፁም ኩራባቸው የ2001 ዓ.ም የዲላ ዮኒቨርስቲ ተመረቂ ሲሆን በምሥረታ በዓሉ ላይ በመገኘቱ የፈጠረበትን ስሜት ሲናገር “በምሥረታ በዓሉ ላይ በመገኘት ሳከብር ቀድሞ በግቢ ውስጥ የነበረኝን መንፈሳዊ አገልግሎት በማስታወስ ወደ ፊት በበለጠ ለማገልገል የሚያስችለኝን መንፈሳዊ ስንቅ የምንሰንቅበትና ለግቢ ተማሪዎች ከወንድሞቻችን ጋር በመሆን ተሞክሯችንን የምናስተላልፍበት ልዮ ጊዜ በመሆኑ በጣም ደስተኛ ነኝ” ሲል ተናግሯል፡፡

በተያያዘም በምሥረታ በዓሉ ላይ የግቢ ጉባኤው የአዳራሽ አሠሪ ኮሚቴ ግቢ ጉባኤው በ600 ካሬ ሜትር ላይ እየሠራ ያለው አዳራሽ እየተፋጠነ እንደሆነ ገልጸል፡፡ የአዳራሽ አሠሪ ኮሚቴው በተወካያቸው በተማሪ ፍርዴ ጥላሁን በኩል ባቀረበው ሪፖርት “ተማሪዎች ቃለ እግዚአብሔር የሚማሩበትን አዳራሽን ለመሥራት እስከ አሁን አንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ብር እንደፈጀና በቀጣይ ሊሠሩ ስላሰቧቸው የበር፣ የመስኮት፣ የኮርኒስ እንዲሁም የማጠቃለያ ሥራ የዕርዳታ ጥሪ” አቅርበዋል፡፡

የዲላ ዮኒቨርስቲ ግቢ ጉባኤ በተማሪዎች ከፍተኛ ትጋትና በአካባቢው ምእመናን ተነሳሽነት የዋለሜ ደብረ ሰላም ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያንን አንጾ ቅዳሴ ቤቱን በ1994 ዓ.ም እንዲከበር ማድረጉ የሚታወስ ነው፡፡ 

 

ቅዱስነታቸው የመጀመሪያ እንኳን አደረሳችሁ መልእክታቸውን አስተላለፉ

የካቲት 28 ቀን 2005ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

abune mathias1ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የአብይ ጾምን በማስመልከት የካቲት 29 ቀን 2005 ዓ.ም. የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላለፉ፡፡

 

ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት መልእክት “ለእግዚአብሔር ሕግ መገዛት እስከተቻለ ድረስ ክፉውንና በጎውን ለይቶ ማወቅ ስለማያዳግት በተቻለ መጠን ከፊታችን ሰኞ መጋቢት 2 ቀን 2005 ዓ.ም. በሚጀመረው በታላቁ ጾማችን በዓብይ ጾም ወራት ጎጂ ከሆኑ ተግባራት ሁሉ መራቅ አለብን፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን የማዳን ሥራ ከመጀመሩ በፊት ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት በመጾም ድኅነተ ነፍስ እንዳስገኘልን ሁሉ እኛም ፈለጉን ተከትለን ጾም በመጾም ጥንካሬን አግኝተን ረቂቅ የሆነውን የዲያብሎስ ፈተና ማሸነፍ በሚያስችለን ቀጥተኛ መንገድ ለመጓዝ ቅድመ ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅብናል” ብለዋል፡፡

የጾም ዋና ዓላማው ለእግዚአብሔር ቃል በሙሉ ኃይል ለመታዘዝ መዘጋጀት እንደሆነ የገለጹት ቅዱስ ፓትርያርኩ በጾም ወራት ሊፈጸሙ ይገባቸዋል ያሏቸውንም ሲጠቅሱ “ተግባራችን ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ ሊሆን የሚችለው ርኅራኄን፤ ቸርነትን፤ ምጽዋትን፤ ፍቅርን፤ ስምምነትን፤ ትሕትናን፤ መረዳዳትን፤ መተዛዘንን ገንዘብ አድርገን የጾምን እንደሆነ ነው፡፡ በጾም ወራት ልንፈጽማቸው የሚገቡን የትሩፋት ሥራዎች ብዙዎች ቢሆኑም በተለይ መሠረታዊ የሆነ የኑሮ ፍላጎት ላልተሟላላቸው ወገኖቻችን ማለትም ልብስ ለሌላቸው ልብስ በማልበስ፤ የምግብ እጥረት ላጋጠማቸው የሚቻለንን በመለገስ፤ ማረፊያ ለሌላቸው መጠለያዎችን በመቀለስ ወገኖቻችንን መርዳት ያስፈልጋል” በማለት መልእክት አስተላልፈዋል፡፡