ጠቅላይ ቤተ ክህነት ደብሩ በ‹‹አጥማቂው›› ላይ የጣለውን እገዳ አጸና

በምሥራቅ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያን ቅጽር ግቢ ‹‹ሲያጠምቅ›› በነበረው ግለሰብ ላይ ያሳለፈውን የእግድ ውሳኔ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አጸናው፡፡ ከደብሩ ሰበካ ጉባኤ ያገኘውን የእግድ ደብዳቤ መሠረት በማድረግ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በቁጥር 9474/756/2005 በቀን 08/09/05 ያወጣው ደብዳቤ ‹‹መ/ር ግርማ ወንድሙ ሰባኬ ወንጌልና አጥማቂ ነኝ፤ የማዳን ፈውስ አለኝ በማለት በሕገ ወጥ መንገድ እስከ አሁን ድረስ በደብሩ እያጠመቀ›› እንደሚገኝ ይገልጻል፡፡

memher girma
በማከልም ቅዱስ ሲኖዶስ በሕገ ወጥ መንገድ የማዳን ፈውስ አለኝ በማለት በየደብሩ ቅጥር ግቢ በማሰባሰብ የሚያጠምቁትን በተመለከተ ያሳለፈውን የእግድ ውሳኔ በመጥቀስ፤ ‹‹መምህር ግርማ ወንድሙ በደብረ ሰላም ቅዱስ እሰጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ ውስጥ የሚፈጽሙት የማጥመቅ ሥርዓትና የወንጌል አገልግሎት ሕገ ወጥ መኾኑን›› በአጽንዖት በመግለጽ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት በግለሰቡ ላይ ያሳለፈውን ውሳኔ እንዳጸናው ይገልጻል፡፡ በተጨማሪም ከእግዱ ጋር በተያያዘ ሕዝበ ክርስቲያኑ የፀጥታ ችግር እንዳይገጥመው የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ጥብቅ ክትትል በማድረግ ውሳኔውን ተግባራዊ እንዲያደርግ አሳስቧል፡፡ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ ለውሳኔው ተግባራዊነት አስፈላጊ ትብብር እንዲያደርጉ ለሚመለከታቸው የመንግሥት የፀጥታ አካላት ጥሪ አድርጓል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ እና የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት እግዱን ያስተላለፈበት ደብዳቤዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

 betekihent girma

 

 

ማእከላት ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡ ተጠየቀ

ሚያዚያ 22 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

የማኅበረ ቅዱሳን ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ክፍል ማእከላት ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡ የክፍሉ ሓላፊ አቶ የሸዋስ ማሞ አስታወቁ፡፡

በአዲስ አበባ ለሁለት ቀናት ለሀገር ውስጥ ማእከላት ስለ ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎትና አሠራር ዙሪያ ሚያዝያ 12 እና 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በተሰጠበት ወቅት ነበር ማእከላት አገልግሎቱን አጠናክረው መቀጠል የሚገባቸው መሆኑን የተገለጸው፡፡

ማእከላት የሒሳብ ክፍል አሠራራቸውንና የኦዲትና ኢንስፔክሽን ክፍሎቻቸውን ይበልጥ  አጠናክረውና በሰው ኃይል አደራጅተው አገልግሎታቸውን መቀጠል እንዳለባቸው በሥልጠናው ላይ ተገልጿል፡፡

ለማእከላት በርካታ ሥልጠናዎችና የግንዛቤ ማስጨበጫ ዝግጅት እየተደረገ ሲሆን የማእከላቱ የግንዛቤ መጠን መጠነኛ ለውጦችን ማምጣት መቻሉን አቶ የሸዋስ ገልጸው ማእከላቱ ለኦዲትና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ትኩረት እንዲሰጡና ክፍሉንም በባለሙያ እንዲያጠናክሩ ጥሪያቸውን ያቀረቡት፡፡ የአገልግሎት ክፍሉ እና የሒሳብ ክፍሉ መጠናከር የጎላ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውና ለማእከላት ወጥ የሆነ የሒሳብ አያያዝ ሥርዓትም አዎንታዊ ተጽዕኖ ሊኖረው እንደሚችል አስገንዝበዋል፡፡

የአገልግሎት ክፍሉ የማኅበሩን ስልታዊ ዕቅድ ከማስፈጸም አኳያ የተለያዩ ድጋፎችን ለማእከላት የሚያደርግ መሆኑና በዕቅዱም ዘመን የራሱን የአገልግሎት ስልት ዘርግቶ እንደሚሠራ ነው ከሓላፊው ገለጻ የተረዳነው፡፡ ሚያዝያ 12 እና 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በተሰጠው ሥልጠና በሀገር ውስጥ ከሚገኙ ማእከላት ተወካዮች በሥልጠናው መሳተፋቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚማሩ አባላት መንፈሳዋ ጉዞ አካሄዱ

ሚያዚያ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊት ደስ

የማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል “መራሔ ፍኖት” በሚል መሪ ቃል በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እየተማሩ ላሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆች መንፈሳዊ ጉዞ ወደ ሱሉልታ ደብረ ምሕረት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሚያዚያ 20 ቀን 2005 ዓ.ም. አካሄደ፡፡

የጉዞውን ዓላማ አስመልክቶ አስተባባሪ የሆነው ሸዋለም ተክሉ ከዚህ ቀደም በግቢ ሲማሩ የነበሩ ተሞክሮአቸውን የሚያካፍሉበት፣ ተማሪዎች መንፈሳዊም ሆነ በሚማሩት ትምህርታቸው ያለባቸውን ጥያቄ የሚመለስበትና የክርስትና ሃይማኖት ተከታይ ሆነው ወደ ግቢ የማይመጡትን ተማሪዎችን በግቢ እየመጡ እንዲማሩ ለማድረግ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም ይህ የግቢ ጉባኤ አንድነት መርሐ ግብር ለአራተኛ ጊዜ የተካሄደ ሲሆን ከጉዞው የሚጠበቀው ውጤት በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የዛሉ የመንፈስ ብርታት የሚያገኙበት፣ የግቢያት የአባላት ቁጥር ወደተሻለ እድገት እንዲመጣ ለማድረግ ነው ሲሉ አስተባባሪው ተናገረዋል፡፡

በዕለቱ በግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና በዘማርያም መዝሙር ቀርቢል፣ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲሆን ግቢያቱ በተለያየ ርዕሰ ጉዳይ የተጠየቁ ጥያቄች ምላሽ ተሰጥተውባቸዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ ሲሳተፉ ያገኘናቸው ወጣት ዮዲት ተገኔ የሮያል ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ተማሪ ስትሆን በዚህ ጉዞ ለመጀመሪያ ጊዜዬ ነው የተጓዝኩት፡፡ ጉዞው ትልቅ ነገር አስተምሮኛል፡፡ የሌሎችን ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ጋር አስተዋውቆኛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ላይ እየተሠራ ያለውን ተግባር እንዳይ አድርጎኛል በማለት ገልጻለች፡፡

ሌላው የ5 ኪሎ ግቢ ጉባኤ ተማሪ የሆነው ናትናኤል ስዮም በጉዞው በመሳተፌ በውስጤ ይመላለስ የነበሩብኝ ጥያቄዎች ተመልሰውልኛል፡፡ እንደዚህ አይነት መርሐ ግብሮች ወጣቱን የሚያንፁ ስለሆነ ማኅበሩ አጠናክሮ ሊሠራበት የሚገባ ተግባር ነው፡፡ ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡ በጉዞው ላይ ከ60 በላይ ከሚሆኑ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የመጡ ከሁለት ሺህ በላይ ተጓዦች ተሳትፈዋል፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ ከማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ጋር ልዩ ቃለ መጠይቅ አደረጉ

ሚያዚያ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.


 abune matyas 17

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ከማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ጋር በዓለ ትንሣኤን ምክንያት በማድረግ ልዩ ቃለ መጠይቅ አደረጉ፡፡ በዚህ አንድ ሰዓት የፈጀ ቃለ መጠይቅ ላይ ቅዱስነታቸው ስለ ልጅነት ጊዜያቸው ፣ በትምህርት ቤት ሳሉ ስለነበሯቸው ገጠመኞች ፣ ስለ ምንኩስና ሕይወት፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስላሉ ልዩ ልዩ አስተዳደራዊና ችግሮች እና በተሠጣቸው ሓላፊነት ምን ሊሠሩ እንዳሰቡ ፣ ስለ ቅድስት ሀገር የርስት ጉዳይ ከግብፅ ቤተ ክርስቲያን ጋር ለመሥራት ስለታሰበው መፍትሔ እና ስለ ዕርቀ ሰላሙ ጉዳይ ሰፋ ያለ ማብራሪያ የሠጡ ሲሆን ሙሉ ቃለ መጠይቁ በማኅበሩ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ከበዓለ ትንሣኤ ጀምሮ እንደሚቀርብ የማኅበሩ ሬድዮና ቴሌቪዥን ክፍል አስተባባሪ ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ገልጸዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን በኢቢኤስ ቴሌቪዥን መርሐ ግብር ከተጀመረበት የካቲት ፲፮ ፳፻፭ ጀምሮ እስከ በዓለ ትንሣኤ ድረስ ዐሥር ልዩ ልዩ መርሐ ግብራትን ያስተላለፈ ሲሆን የተጀመረበትን ሰዓት በማስተካከልም መርሐ ግብሩ ዘወትር እሑድ ከ5፡30 – 6፡00 ሰዓት ድረስ ሆኗል፡፡ የተላለፉ ዝግጅቶችም በኢንተርኔት http:// eotc.tv ላይ በማንኛውም ሰዓት መከታተል ይቻላል፡፡ ዝግጅቶቹን በመመልከት በስልክና በኢንተርኔት አድራሻዎቻችን ገንቢ አስተያየቶቻችሁን የሠጣችሁን ምዕመናንን እያመሰገንን ለበለጠ ሥራ ረድኤተ እግዚአብሔር እንዳይለየን ጸልዩልን ሲሉ የክፍሉ አስተባባሪ ገልጸዋል፡፡  

ሠራተኛ ጉባኤያት በቤተ ክርስቲያን ትልቅ ድርሻ እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ

ሚያዚያ 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

sera 2 1የማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል የሠራተኛ ጉባኤ የአንድነት መርሐ ግብር ሚያዚያ 13 ቀን 2005 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተካሄደው መርሐ ግብር ሠራተኛ ጉባኤያት በቤተ ክርስቲያን ትልቅ ድርሻ እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ፡፡

የመርሐ ግብሩን ዓላማ አስመልክቶ የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል ሓላፊ የሆኑት ኀይለ ማርያም መድኅን “በአዲስ አበባ ማእከል ሥር ሆነው የሚማሩ 22 የሚደርሱ የሠራተኛ ጉባኤያት ለቤተ ክርስቲያን እውቀታቸውን፣ ገንዘባቸውን፣ ጊዜያቸውን ሊያበረክቱ የሚያስችላቸውን ነገር ማስጨበጥና በተደራጀ ሁኔታ ቤተ ክርስቲያንን በአቅም ማገልገል የሚችሉበትን ሁኔታ ለመፍጠር ነው” በማለት ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም እንደዚህ ዓይነት መርሐ ግብር ሲዘጋጅ የመጀመሪያ ጊዜ በመሆኑ ወደፊት የተለያዩ የሠራተኛ ጉባኤያትን በአንድነት ለማጠናከር በቤተ ክርስቲያን ከዚህ ቀደም ከሚሠሩት የተሻለ ሥራ እንዲሠሩ ለማድረግ የታሰበ ነው በማለት ሓላፊው ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ “የቤተ ክርስቲያን ተልዕኮና ዓላማ እና የልጆቿ ድርሻ” በሚል ጥናታዊ ጽሑፍ፣ ትምህርተ ወንጌልና መዝሙር ቀርቧል፡፡ በቀረበው ጥናታዊ ጽሑፍsera 2 2 አስተያየትና ጥያቄዎች ቀርበው ከጥናት አቅራቢው ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ሲሳተፉ ያገኘናቸው አቶ ተስፋዬ አሻግሬ “በዛሬዋ ቀን በመገኘቴ ትልቅ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ ምክንያቱም በርካታ መሥሪያ ቤቶች ጉባኤ ያካሂዳሉ፡፡ ከመማር ባለፈ ምንም ድርሻ እንዳለን እንኳ አናውቅም ነበር፡፡ ዛሬ ግን ቤተ ክርስቲያናችን ከኛ ከልጆቿ ብዙ ነገር እንደምትጠብቅና መሥራት እንደምንችል አውቄበታለው” በማለት ገልጸዋል፡፡

በዕለቱ በተደረገው መርሐ ግብር ከአምስት መቶ በላይ የሆኑ በተለያየ መሥሪያ ቤት የሚሠሩ የሠራተኛ ጉባኤ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡

ለአብነት ተማሪዎች በጤና አጠባበቅ ላይ ያተኮረ ሥልጠና ተሰጠ

ሚያዚያ 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

healthበማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከጎንደር ማእከል ጋር በመተባበር በጎንደር ውስጥ ከሚገኙ አብነት ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ ተማሪዎች በግልና በአካባቢ ንጽህና አጠባበቅ ላይ ያተኮረና አንድ ቀን የወሰደ ስልጠና በደብረ ኀይል ወደብረ ጥበብ በዓት ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አዳራሽ  ሚያዚያ 12 ቀን 2005 ዓ.ም. ተሰጠ፡፡

“ጤና ሀብት ነው” በሚል መሪ ቃል የተሰጠውን ሥልጠና በማስመልከት በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የአብነት ትምህርት ቤቶች ክትትል ክፍል ምክትል ኃላፊና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ሊቀ ዲያቆን መሐሪ መዘምር የሥልጠናውን ዓላማ አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ “በአብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የጤና ችግሮች ይታያሉ፡፡ ይህንንም መነሻ በማድረግ 25 ሺህ ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮጀክት በመቅረጽ የጤና አጠባበቅ ትምህርት ለአብነት ትምህርት ተማሪዎች ለመስጠት አቅደን ወደ ትግበራ በመሸጋገር ላይ እንገኛለን፡፡ ጎንደር ከተማ ውስጥ እስከ 2000 ተማሪዎች ይገኛሉ ተብሎ ስለሚገመት ለሁሉም ሥልጠና ለመስጠት ስለሚያዳግት ከየአብነት ትምህርት ቤቱ ለተውጣጡ 200 ተማሪዎች ሥልጠናውን እየሰጠን እንገኛለን፡፡ ተማሪዎቹም በአብነት ትምህርት ቤቶቻቸው ውስጥ ለሚገኙ ጓደኞቻቸው የአቻ ለአቻ ሥልጠና እንዲሰጡ እናደርጋለን፡፡” ብለዋል፡፡

በጎንደር ማኅበረ ቅዱሳን ማእከል የአብነት ትምህርት ቤቶቹን የጤና አጠባበቅ ሁኔታ የሚከታተልና የሚቆጣጠር ኮሚቴ እንደሚዋቀር የተገለጸ ሲሆን የግልና የአካባቢ ንጽህና ለመጠበቅ የሚረዱ ቁሳቁሶች እደላና አጠቃሙን ለማሳየት በየአብነት ትምህርት ቤቶቹ የሙከራ ሥራ እንደሚሠራ ሊቀ ዲያቆን መሐሪ መዘምር ገልጸዋል፡፡

ከመንበረ ፀሐይ ቁስቋም ማርያም ገዳም የቅኔ ጉባኤ ቤት ተማሪ የሆኑት መሪ ጌታ ዮሴፍ ታረቀኝ ስለ ሥልጠናው ጠቀሜታ ሲገልጹ “አብሮ ስላደገብን ቀሸሽ ብለን ስለምንታይ ለተለያዩ በሽታዎች ስንጋለጥ ኖረናል፡፡ ንጽሕናችንን መጠበቅ የሚጠቅመው ራሳችንን ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን እየሰጠን ያለውን ስልጠና ወስጄ ለተማሪዎች በቅኔ ነገራ ወቅትም ሆነ አመቺ በሆነ ስዓት ለማስተማር ተዘጋጅቻለሁ” ብለዋል፡፡

ስልጠናው የግልና የአካባቢ ንጽሕና አጠባበቅ፤ የውኃ አያያዝና አጠቃቀም፤ የምግብ አያዝና አጠቃቀም፤ የበሽታ መንስኤዎች፤ የበሽታ መተላለፊያ መንገዶች፤ ተላላፊ በሽታዎችን መከላከል፤ ወባ፤ የግርሻ በሽታ፤ . . . የሚሉ ርዕሶችን ያካተተ ሲሆን ለሃያ አምስት ሺህ ተማሪዎች በአራት ዓመታት ውስጥ ተጠቃሚ ለማድረግ እስከ አንድ ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅ ተገልጧል፡፡  

ኒቆዲሞስ

ሚያዚያ 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

እግዚአብሔር “ጾምን ቀድሱ ጉባኤውንም ዐውጁ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ሰብስቡ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ በጽዮን መለከት ንፉ ጾምንም ቀድሱ” በማለት ዐውጀን መጾም ያለብንን ጾም እንድንፆም በነብዩ ኢዩኤል ነግሮናል፡፡ ኢዩ.1፥14፣ 2፥15

እግዚአብሔር ሙሴን በእሥራኤል ልጆች ዘንድ ከሰውም ከእንስሳም ማኅፀንን የሚከፍት በኲርን ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ በማለቱ /ዘጸ.13፥12 ከሰው፣ ከዕለታትት ተለይተው የተቀደሱ ነበሩ፡፡ አጽዋማትም በዐዋጅ ተለይተው ይጾማሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥም፡- የዐብይ ጾም ይገኛል፡፡

ዐብይ ጾም ዐብይነቱ ነብያት፣ ሐዋርያት፣ ቅዱሳን የጾሙት ጾም ሳይሆን የጠፋውን የሰውን ልጅ ለመፈለግ፣ የሞተውን አዳምን ለማስነሣት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደዚህ ዓለም የመጣው ወልደ አብ ወልደ ማርያም በመብል የተጀመረውን የሞት መንገድ ለማጥፋት በጾም ስለጀመረው ነው፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ያደረጋቸውን የድኅነት ጉዞና ድንቅ ድንቅ ተአምራት ዋጋ የተከፈለባቸው በመሆናቸው አባቶቻችን በሠሩልን ሥርዓት መሰረት በዐብይ ጾም ወራት ዘወረደ ብለን ጀምረን ትንሣኤ ብለን አስከምናከብርበት ድረስ ያሉትን ሰንበታት ለሰው ልጆች የተከፈለልንን ዋጋ እያሰብን እንማረዋለን፣ አንዘምራለን፣ እንጸልያለን፡፡ ከነዚህ ሰንበታት በ7ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ደግሞ ኒቆዲሞስ ተብሎ ተሰይሞ ይከበራል፡፡

ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ በነበረው በኒቆዲሞስ የተሰየመ ሰንበት ነው፡፡ የአይሁድ አለቆች አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ምልክት አሳየን” እያሉ ይፈታተኑት ነበር፡፡ ስለሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ ቢነግራቸው አልገባቸውም፡፡ ሲያስተምር ብዙዎች ያምኑ ነበር፡፡ ለአይሁድ አለቆች ግን ጭንቅ ነበር፤ የታመሙ ሲፈወሱ ሕጋችን ተሻረ ይሉ ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ ተአምራትና ትምህርት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ወቅት ከአይሁድ አለቆች አንዱ ኒቆዲሞስ በቀን እንዳያደርገው አይሁድን ፈርቶ አንድም ጊዜ አላደርሰው ብሎ እንደ አይሁድ አለቆች ኢየሱስን መቃወሙን ትቶ በሌሊት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሄደ፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍስ የታመሙትን በቃሉ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ፤ ኒቆዲሞስ ሰምቶና ተመልክቶ “መምህር ነኝ” ብሎ በመምህርነቱ ሳይኮራ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ፡፡ በልቦናው የተሳለውን እውነትን የመፈለግ ስሜት አንግቦ ጌታው መምህሩ ዘንድ በሌሊት ገሠገሠ ዮሐ.3÷1

ደርሶም ምስክርነቱን እንዲህ ሲል መስጠት ጀመረ “መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና” ዮሐ.9÷24፣ የሐዋ.ሥራ 10÷38 በማለት መመስከር ሲጀምር ጎዶሎን የሚሞላ፡፡ አላዋቂነት በአዋቂነት የሚለውጥ፡፡ ከምድራዊ እውቀት ወደ ሰማያዊ ምስጢር የሚያሸጋግር አምላክ፡፡ “ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” ዮሐ.3÷6 1ጴጥ.1÷23 በማለት የአይሁድ መምህር ለሆነው ኒቆዲሞስ ቢያስተምረው ስለዳግመኛ መወለድ ከመጽሐፍ ቢያገኘውም ምስጢሩ አልተገለጠለትምና “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” በማለት ጥያቄ አቅርቧል፡፡

“እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዝአበሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ኤፌ.5÷26 ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡ በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቢያስረዳው ምስጢሩ ከአቅሙ በላይ የሆነበት ኒቆዲሞስ እንደምን ይቻላል? በማለት ጠይቋል፡፡ አበ ብዙኀን አብርሃም ከአምላኩ ሞገስን አግኝቶ፤  የሰዶምና ገሞራ ጥፋት እንዳይደርስ እያማለደ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር እንደ ነበረ፤ ኒቆዲሞስም አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምስጢር አምላኩን የመጠየቅ ዕድል በማግኘቱ ሲጠይቅ፣ ኢየሱስ ክርስቶስም “አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ ግን ይህን ነገር አታውቅምን? በምድር ያለውን ስንነግራቸው ካላመናችሁ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም ….፡፡ሙሴ ምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀላል፡፡ ያመኑበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ እንዲኖር እንጂ እንዲጠፉ አይደለም…..” ዮሐ.3÷14፡፡ እያለ ለድኅነተ ዓለም እንደ መጣ ሰው በመብል፣ አምላኩን ከድቶ ልጅነቱን ትቶ ከእግዚአብሔር ቢለይም የሰው ልጅ ያጣውን ልጅነት ለመመለስ ስመ ግብርና ሀብተ ወልድን ለመስጠት መምጣቱን አስረዳው፡፡ “ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ፡፡ አመከርከኒ ወኢተረከ በዓመፃ በላዕሌየ፡፡ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው፡፡ ልቤን ፈተንከው በሌሊትም ጎበኘኸኝ ፈተንከኝም ምንም አላገኘህብኝም፡፡ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው” መዝ.16÷3 እንዳለ ቅዱስ ዳዊት ምስጢረ ሥጋዌን የድኅነት ምስጢር ገልጾለታል፡፡

በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምስጢሩ የተገለጸለት ኒቆዲሞስ ፍርሃት ርቆለት ቀድሞ በአደባባይ ሄዶ መማርን የፈራ ምስጢሩ ሲገለጽለት አይሁድ በሰቀሉት ዕለት ሳይፈራ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበር በቃ “ወአልቦ ፍርሃት ውስተ ተፋቅሮትነ፡፡ ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል ማቴ.27÷58፣ 1ዮሐ.4÷18 እንዲል፡፡

ያመነ የተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ ያልተጠመቀ ይፈረድበታል ማር.16÷16፡፡ ባለው አማናዊ ቃል ኪዳን መሠረት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አምላክነቱ አምነን  ለመንግሥቱ ዜጋ እንድንሆን ለኒቆዲሞስ ምስጢሩን ጥበቡን የገለጸ አምላክ ለኛም ይግለጽልን፡፡

የኔታ ይቆዩን የገዳማት ዐውደ ርእይ በፓሪስ ከተማ

ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ደረጄ ግርማ

 

gedamat 11የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የፈረንሳይ ግንኙነት ጣቢያ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶችን የሚያስተዋውቅ ዐውደ ርእይ ማዘጋጀቱን ገለጠ።

 

ዐውደ ርእዩም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና ለሀገር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ፣ በተለይም ጥንታዊ ገዳማት ትናንትና ዛሬ እንዲሁም የአብነት ትምህርት ቤቶችን ነባራዊ ሁኔታ የሚዳስስ፤ እየተደረጉ ያሉ ድጋፎችን የሚጠቁም እንዲሁም ከሕዝበ ክርስቲያኑ የሚጠበቀውን ድርሻ የሚያመላክት ዐውደ ርእይ ይቀርባል።

ከዚህም በተጨማሪ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስኮላርሸፕ፤ የላይ ቤት ትርጓሜ ፕሮጀክት እንዲሁም የቅዱስ ያሬድ 1500 ዓመት መታሰቢያ የሚያመላክቱ ጹሑፎች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል፡፡ ዐውደ ርእዩም ሚያዚያ ፲፰ ቀን ፳፻፭ ዓም ለፓሪስ እና አካባቢ ምእመናን እንደሚቀርብ ተገልጿል። ከፓሪስ ደብረ ም/ቅ/ማርያም ሰበካ ጉባኤ ጋር በመተባበር ሚያዚያ ፲፱ ቀን ፳፻፭ ዓም ልዩ የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር የተዘጋጀ ሲሆን በዕለቱም በገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ውይይት እንደሚካሄድ ከዝግጅቱ አስተባባሪ ኮሚቴ የደረሰን መረጃ አመልክቷል። ለዚህ ዝግጅት አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ የማኅበረ ቅዱሳን ቅዱሳት መካናትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አንድ ልዑክ እንዲሚልክ ለማወቅ ተችሏል።

 
በአውሮፓ የምትገኙ ሁላችሁም በዝግጅቱ እንድትታደሙ የተጋበዛችሁ ሲሆን በርቀት ያላችሁ ለመርሐ ግብሩ ስኬት በጸሎት እንድታግዟቸው አስተባባሪ ኮሚቴው ጥሪውን አስተላልፏል።

ከየማእከላቱ ለተውጣጡ ተጠሪዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተሰጠ

ሚያዚያ 9 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

seletena 2 2በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከየማዕከላቱ ለተውጣጡ 38 የክፍል ተጠሪዎች ከሚያዝያ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. በዋናው ማእከል የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተካሄደ፡፡

የሥልጠናውን ዓላማ አስመልክቶ የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲ/ን አእምሮ ይሄይስ “የማኅበሩን ስልታዊ ዕቅድ ተጠሪዎቹ ግንዛቤ ኖሮአቸው በቀጣይ በየማእከላቱ የሚሠሩትን ሥራ በተግባር ላይ እንዲያውሉ ለማስቻል  ነው” ብለዋል፡፡

አያይዘውም ሥልጠናው በዚህ ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደ ሲሆን፣ በቀጣይም  በገዳማት ላይ የሚሠራውን የልማት ሥራ በጋለ ሆኖ ከታሰበበት ለማድረስ ያግዛል ሲሉ ሓላፊው ገልጸዋል፡፡

ከሥልጠናው ተሳታፊዎች መካከል የደሴ ማእከል የቅዱስት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ተጠሪ ወ/ት ስንታየው እሸቱ በሥልጠናው የተለያዩ ግንዛቤዎችን አግኝቻለሁ፡፡ በተለይ የአብነት ትምህርት ቤት ላይ የምንሠራቸውን ሥራ እንዴት ማጠናከርና ገቢ ማሰባሰብ እንዳለብን፣ ፕሮጀክት እንደምንቀርጽና እንደምንተገብር ተንዝቤያለሁ፡፡

ሌላው ከአሰበ ተፈሪ ማእከል የመጣው አቶ ብርሃኑ እንዳለ በሀገራችን በሚገኙአብያተ ክርስቲያናት የአገልጋይ እጥረት ይስተዋላል፡፡ ከዚህ አንጻር የአብነት ትምህርት ቤቶች ተተኪ አገልጋይ የሚፈራባቸው በመሆኑ ብዙ ሊሠራ እንደሚገባ የሚያመለክትና ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡

ለሦስት ቀን በተካሄደው መርሐ ግብር ሉላዊነት እና የቤተ ክርስቲያን የማእከላት ድርሻ ምን መምሰል አለበት፣ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስኮላር ሺፕ ፕሮግራም አፈጻጸም ማእከላት ድርሻቸው ምን መሆን አለበት፣ ቤተ ክርስቲያን ለልማት ያላት ምቹነትና ተግዳሮቶች፣ የሀብት ምንነት የፕሮጀክት ሠነድ ዝግጅት፣ የንግድ ዕቅድ ዝግጅት (ለገዳማት፣ አብያተ ክርስቲያናት፣ አብነት ት/ቤት ተማሪዎች) በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሥልጠናና ውይይት ተደርጓል፡፡

በመርሐ ግብሩም ላይ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊን ጨምሮ ከሁሉም ማእከላት የተውጣጡ 38 የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ተጠሪዎች ተሳትፈዋል፡፡