‹‹እግዚአብሔርን መፍራት›› (መዝ. ፴፫፥፲፩)

ነቢዩ ዳዊት ‹‹ልጆቼ ሆይ ኑ፥ ስሙኝ፤ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራቹሁ ዘንድ›› ያለን ሰው አምላኩ እግዚአብሔርን በመፍራት ሊኖር እንደሚገባ ሲገልጽ ነው፡፡ በዚሁ መዝሙር ላይ ‹‹ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎ ዘመንንም ለማየት የሚወድድ ማን ነው?? አንደበትህን ከክፉ ከልክል፥ ከንፈሮችህም ሽንገላን እንዳይናገሩ። ከክፉ ሽሽ፥ መልካምንም አድርግ፤ ሰላምን ሻት፥ ተከተላትም። የእግዚአብሔር ዐይኖች ወደ ጻድቃኑ፥ ጆሮዎቹም ወደ ልመናቸው ናቸውና›› ብሏል፤ ይህም እኛ ከፈጣሪያችን ጋር እንኖር ዘንድ ማድረግ የሚገባንን ሁሉ እንድንፈጽም ነው። (መዝ. ፴፫፥፲፩-፲፭)

‹‹እግዚአብሔር ብርሃን ነው፤ ጨለማም በእርሱ ዘንድ ጥቂትስ እንኳ የለም›› (፩ዮሐ. ፩፥፭)

ፀሐይ በቀን፣ ጨረቃም በጨለማ ለምድር ብርሃን እንደሆኑ ሁሉ አምላካችን እግዚአብሔር በአማኞቹ ልብ ያበራል፤ ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ ‹‹እግዚአብሔር ብርሃን ነው፤ ጨለማም በእርሱ ዘንድ ጥቂትስ እንኳ የለም›› ሲል እንደተናረው በእርሱ ዘንድ ጨለማ የለም፤ ሁሌም ብርሃን ነው፡፡ ‹‹ከእንግዲህም ወዲህ ሌሊት አይኖርም፤ የመብራት ብርሃን፥ ወይም የፀሐይ ብርሃን አያስፈልጋቸውም፤ እግዚአብሔር ያበራላቸዋልና፤ ለዘለዓለምም እስከ ዘለዓለም ይነግሣሉ›› እንደተባለው ያ ብርሃን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ነው፡፡ (ራእ. ፳፪፥፭)

የእመቤታችን በዓለ ዕርገት

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያረገችበት ዕለት ነሐሴ ዐሥራ ስድስት ቀን በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራልና እኛም ስለዕርገቷ እንዲህ እንዘክራለን፤…

በዓለ ደብረ ታቦር

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን፣ ክብረ መንግሥቱን መግለጡን በማሰብ በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በዓሉ በድምቀት ይከበራል፡፡ ይህ በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ዘንድ ‹ቡሄ› በመባል ይታወቃል፡፡ ቡሄ ማለት ‹ገላጣ› ማለት ነው፡፡ በአገራችን ክረምቱ፣ ጭጋጉ፣ ደመናው ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታይበት በዚሁ በዓል አካባቢ ስለ ሆነ በዓሉ ‹ቡሄ› ተብሎ ይጠራል፡፡ በዓለ ደብረ ታቦር ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት፤ ብርሃን የታየበትና ድምፀ መለኮቱ የተሰማበ  ዕለት ስለ ሆነ ‹የብርሃን› ወይም ‹የቡሄ› በዓል ይባላል፡፡

‹‹ፈለሰት ማርያም እምዘይበሊ ኀበኢይበሊ›› ቅዱስ ያሬድ

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዚህ ዓለም ፷፬ ዓመታትን በሕይወተ ሥጋ ከቆየች በኋላ ሥጋዋ በምድር እንዲቆይ የአምላክ ፈቃድ አልበነረም፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእናቱን ተድላ ነፍሷን እንጂ ተድላ ሥጋዋን አይወድምና ከጌቴሴማኒ ሥጋዋ ተነጥቆ በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር እስከ ነሐሴ ዐሥራ ስድስት ቀን ለሁለት መቶ አምስት ቀናት እንድትቆይ ፈቃዱ አደረገ፡፡ እርሱ ሞትን በሥልጣኑ እንዳሸነፈ ሁሉ በልጇ መለኮታዊ ኃይል ሞትን አሸንፋ ተነስታለች፡፡

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም

በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የረጅም ዘመን ሐዋርያዊ ጉዞ ላይ በጎ ተፅዕኖ ካላቸው የአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አባቶች መካከል አንዱ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ ይህ አባት ምንም እንኳን በቋንቋ ውሱንነትና በቦታ ርቀት በርካቶች ሥራዎቹና ጽሑፎቹ የታወቁለት ባይሆንም ሕይወቱን በብሕትውና የመራ የትርጓሜ መጻሕፍትን፣ የቅኔ፣ የግጥምና የወግ ጽሑፍ በማዘጋጀት የኖረ ባለ በጎ ገድል አባት ነው፡፡

‹‹በበለስ ዛፍ ሥር አየሁህ›› (ዮሐ.፩፥፶፩)

እግዚአብሔር ሁላችንንም ከበለስ በታች ያውቀናል፡፡ እግዚአብሔር ዝም የሚለው ስለማያውቀን አይደለም፡፡ ናትናኤልን እያወቀው ተንኮል የሌለበት የእስራኤል ሰው እንደሆነ ተናገረ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ በገሊላ ባሕር እንዳስተማረው ትምህርት ሊሰሙ፣ ሊማሩ፣ ሊለወጡ ባለመቻላቸውም ‹‹ኮራዚ ወዮልሽ! ቤተ ሳይዳ ወዮልሽ! በእናንተ የተደረገው ተአምራት በጢሮስና በሲዶና ተደርጎ ቢሆን ቀድሞ ማቅ ለብሰው አመድም ነስንሰው በተቀመጡ ንስሓም በገቡ ነበር፡፡ ነገር ግን ጢሮስና ሲዶና ከእናንተ ይልቅ በፍርድ ቀን ይቅርታን ያገኛሉ፡፡ አንቺም ቅፍርናሆም እስከ ሰማይ ድረስ ከፍ ከፍ ብትዪ እስከ ሲኦል ትወርጃለሽ›› ብሎ ጌታችን ተናገሯል፡፡ (ሉቃ.፲፥፲፫-፲፭)

‹‹የይቅርታ ልብ ይኑረን››

የሰው ልጅ ወደ አምላኩ እግዚአብሔር ይመለስ ዘንድ የይቅርታ ልብ ሊኖረው ይገባል፡፡ አዳም ይቅርታ ባይጠይቅ እና ከእግዚአብሔር ይቅርታን ባያገኝ ኖሮ የዘለዓለም ቅጣት ይፈረድበት ነበር፡፡ ሆኖም ከሚኖርባት ገነት ወደ መሬት በመምጣት ቅጣት ተቀብሏል፡፡ አዳም ዕንባ ሲያልቅበት ደም፣ ደም ሲያልቅበት እዥ እያነባ ‹‹በድያለሁ ይቅር በለኝ›› ብሎ ፈጣሪን ይቅርታ በመጠየቁ ድኅነትን አግኝቷል፡፡ ይቅርታ ሰውን እንደገና ወደጥንት ክብሩ የመለሰ ትልቅ ጸጋ ነው፡፡ ያለ ይቅርታ ዓለም ለኃጢአት ስርየትም ሆነ ቸርነት የበቃ አይሆንም፡፡

‹‹እንደተማራችሁት በሃይማኖት ጽኑ›› (ቆላ. ፪፥፯)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ ሃይማኖታቸውን እንዲያጸኑ ታስተምራለችና ስለሃይማኖታችን ልንኖር ይገባል፤ ሃይማኖት የእግዚአብሔርን ህልውና ማወቅ ለእርሱ መታመን ነውና ምእመናን ሁሉ በሃይማኖት መጽናት አለብን፡፡ ይህም በሕይወታችን የሚመጣብንን መከራ እና ፈተና ሁሉ በትዕግሥት እንድናልፍ ይረዳናል። ቅዱስ ጳውሎስ አስቀድሞ ለቆላስይስ ምእመናን ማስተማሩን በማስታወስ እኛ ክርስቲያኖች በቅድሚያ የተማርነውን ትምህርት አጽንተን በሃይማኖት እንድንቆይ ነግሮናልና።

‹‹ለእግዚአብሔርም የመዓዛ ሽታ የሚሆንን መባንና መሥዋዕትን አድርጎ ስለ እናንተ ራሱን አሳልፎ እንደሰጠ ክርስቶስ በፍቅር ተመላለሱ›› (ኤፌ. ፭፥፪)

የእግዚአብሔር ልጆች እንሆን ዘንድ አምላኮተ እግዚአብሔርን መፈጸም ይጠበቅብናል፡፡ በመጽሐፍም አባቶቻችን በብሉይ ኪዳን ፍየል፣ በግ፣ ወይፈን፣ ርግብን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር ሲያቀርቡ እሳት ከሰማይ ወርዳ መሥዋዕቱን ትበላላቸው እንደነበር ይገልጻል፡፡ መሥዋዕታቸውንም እሳት መብላቱ እግዚአብሔር ለመቀበሉ ማረጋገጫ ነበረች፡፡ እነርሱም በዚህ ከእግዚአብሔር ጋር ታርቀው ይኖሩ ነበር፡፡ ቅዱስ አባታችን ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን ሲተረጉም ‹‹መሥዋዕት ማለት አንተ ሰው ዛሬ በግ፣ ፍየል፣ ወይፈን ወይም ርግብ የምታርድ አይምሰልህ፤ ራሱን ሠውቷልና፡፡ ከአንተ የሚፈልገው መሥዋዕት ምንድነው ካልከኝ ራስህን መሥዋዕት አድርገህ ማቀረብ ነው፤ ክህነት የማያስፈልጋት መሥዋዕት ማለት ይህች ናት›› ብሏል፡፡ መሥዋዕት የሚቀርብበት መረብረቢያው፣ መጸፍጸፊያው፣ ድንጋዩ፣ ጉልቻው፣ እንጨቱ፣ እና ማገዶው ደግሞ ምሕረትና ርኅራኄ ነው፡፡ ፍቅር፣ ትዕግሥት፣ ትሕትና፣ የዋህነት እና ንጽሕና የመሥዋዕት መረብረቢያዎች ናቸው፡፡ ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት እና ቸርነት መሥዋዕት ሲሆኑ የሚቀርቡበት ምድጃ ትዕግሥትና ትሕትና ነው፡፡  (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)