‹‹ለራስህ እና ለትምህርትህ ተጠንቀቅ›› (፩ኛ ጢሞ. ፬ ፥፲፮)

በአሁኑ ወቅት በአንድም በሌላ አንዳንድ የይዘት፣ የትርጉም፣ የፍቺ ግድፈቶች ከዛ የባሰም የዶግማ ችግር ያለባቸው ለቤተክርስቲያን ትምህርት ስጋት የሆኑ ከስንዴ መሐል የተቀላቀሉ ጥቂት እንክርዳድ የተቀላቀለባቸው መጻሕፍት በቤተ ክርስቲያን ስም እየወጡ ነው፡፡ ስለዚህ እንክርዳዱን ከስንዴው ለቅሞ መለየትና ማረም ያስፈልጋል፡፡

የአዳዲስ ፊዳላት፣ አዳዲስ ቁጥሮች፣ አፈጣጠር ሂደትና አስፈላጊነት

ሚያዚያ 20/2004 ዓ.ም.

ሠዓሊ አምሳሉ ገብረ ኪዳን አርጋው

ኢትዮጵያ ያሏትን መንፈሳዊና ቁሳዊ የታሪክ ዕሴቶች በማበርከት በኩል የቤተክርስቲያናችን ሊቃውንት ድርሻ ታላቅ መሆኑ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ ከእነዚህ ዕሴቶቻችን መካከል ደግሞ በዓለም አቀፍ ደረጃ ስሟን የሚያስጠራና እንደ አፍሪካዊነታችን ብቸኛ ባለቤት እንድንሰኝ የሚያደርጉን ፊደላትና ቁጥሮች ናቸው፡፡ ይህን የሊቃውንቱን አርአያነት ያለው ተግባር ተከትለን የበለጠ ማርቀቅና ሃይማኖት ብቻ ሳይሆን በፍልስፍናና በፈጠራ ሥራውም ችግር ፈቺ በመሆን መራመድ እንዳለብን እናስባለን፡፡ ይህንን አስተሳሰብ ተከትሎ ወንድማችን አምሳሉ ‹‹የኢትዮጵያ ቁጥሮችና ፊደላት በየምክንያቱ ወደጎን እየተተዉ የእኛ ባልሆኑ እኛነታችንንም በሚያስረሱ ሌሎች ፊደላትና ቁጥሮች የመገልገል ዝንባሌ እየታዩ መምጣታቸው ያሳስበኛል በማለት አንድ አስተዋጽኦ ለሀገር ማበርከት አለብኝ ብሏል፡፡ እርሱ እንደሚለው የኢትዮጵያ ፊደላት እና ቁጥሮች በየትኛውም ቋንቋና አሠራር ውስጥ ውጤታማ ናቸው፡፡ አሉ የሚባሉ ውስንነቶችንም መቅረፍ የሚያስችል ዕምቅ አቅም አላቸው ይህንን አቅም እንዲኖራቸው አድርገው ሊቃውንቱ ቀምረው አልፈዋል፡፡ ስለዘህ ጥያቄ ሲነሣባቸው በፈጠራ አዳብረን ለትውልዱ እንዲመጥኑ አድርጎ አቅማቸውን መግለጽ ይቻላል ለዚህም የራሴን ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ ስለዚህ የፈጠራ ረቂቄን አቅርቤ ሊቃውንትና የማኅበረ ቅዱሳን መካነ ድር አንባብያን የማኅበሩን መካነ ድርና የሐመር መጽሔትን ተጠቅመው እንዲተቹት፤ በዚህ ላይ ተመሥርቶም በዚሁ ረገድ የቤተክርስቲያን ሊቃውንትና የትውልዱ መነሣሣት እንዲፈጠር እሻለሁ›› ብሏል፡፡ እኛም እርሱ እንደ ቤተክርስቲያን ልጅነቱ ያሳየውን የፈጠራ ረቂቅ በማቅረብ ሊቃውንቱና አንባብያን ሁሉ አስተያየት በመስጠት እንዲወያዩበት የእርሱን ሐሳብ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤ መልካም ንባብ፡፡

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም (ክፍል አራት)

በዲ/ን ዮሐንስ ልሳነወርቅ

ከክፍል ሦስት የቀጠለ

  7. የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም (The interpretation of Scripture)

(ግንቦት 19/2003 ዓ.ም)

ለቅዱስ ኤፍሬም ስለ እግዚአብሔር የሰው ልጅ እውቀት ቀዳሚ ምንጩ በመጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ራሱ  ስለ ራሱ እንዲባል  የፈቀደውን ነው። የእግዚአብሔር ስሞችና በቅዱስ መጽሐፍ ያሉ የተለያዩ ዓይነቶችና ምሳሌዎች በእግዚአብሔርና በሰውነት መካከል መገናኛ ነጥብን ይፈጥራሉ፤እግዚአብሔር በፈጣሪ ትሕትናው የሰው ልጅ ሊረዳው ወደ ሚችለው ደረጃ ራሱን ዝቅ አደረገ። በሰው ልጅ በኩል በእግዚአብሔር የተሰጠውን ራሱን ወደማወቅ ወደሚወስደው መንገድ የመቅረብ ዕድል ለመጠቀም ከተፈለገ ሁለት ነገሮች አስፈላጊ ናቸው፤በመጀመሪያ ደረጃ ቀድመን እንደተማርነው በመጽሐፍ ቅዱስ ፈጽሞ ለእግዚአብሔር የተጠቀመባቸው ስሞችንና ስእላዊ አገላለጾችን ጥሬ ትርጉም በመውሰድ ያልተገባን ስህተት  ልንፈጽም አይገባም፤በሁለተኛ ደረጃም የአንባቢው ዝንባሌ የመቀበልና ቀናነት መሆን አለበት። ቅዱስ መጽሐፍን በተሳሳተ ዝንባሌ ወይም በራሱ ግንዛቤ የሚቀርብ ከሆነ ከመጽሐፍ ቅዱስ ስለ እግዚአብሔር ምንም ዓይነት እውቀት ለማግኘት ይሳነዋል ብቻ ሳይሆን ወደ ኃጢአትም ሊገባ ይችላል።

ቅዱስ መጽሐፍ አፍአዊ(ውጫዊ) እና ውሳጣዊ(ውስጣዊ) ትርጉሞች አሉት ሊባል ይችላል ፤ አፍአዊው እኛ ታሪካዊ እውነታ እያልን የምንጠራውን ይመለከታል፤ውሳጣዊው መንፈሳዊ እውነታን ይመለከታል። በሥግው ክርስቶስ ልክ ሰውነትም ፈጣሪነትም እንዳሉ ሁለቱም እንዲሁ በአንድነት ይኖራሉ። ፡ቅዱስ ኤፍሬም በእግዚአብሔር ሁለት ሥጋዌዎች ፡መጀመሪያ ስሙን በሰው ቋንቋ በቅዱሳት መጻሕፍት ሲያስቀምጥ ቀጥሎም ሥጋን ሲዋሐድ የሚያስተውለው ትይዩነት ቅዱስ መጽሐፍን በመረዳቱ ላይና በትርጓሜውም ላይ እምነት እንደሚያስፈልግ የሚያይበትን ጠቃሚ የብርሃን ፍንጣቂ ይልካል። ከእምነት ውጭ የናዝሬቱ ኢየሱስ ታሪካዊ ምልክት ብቻ ሆኖ ይቀራል፤ ሰውነቱ ለሚያየው ሁሉ የሚታየው ነው።የክርስቶስ ፈጣሪነት የሚስተዋለው ተመልካቹ በውሳጣዊ የእምነት ዓይን ሲያይ ብቻ ነው። ለቅዱስ መጽሐፍም እንዲሁ፡ውሳጣዊ የእምነት ዓይን በሌለበት የሚታየው ሁሉ አባቶች ፊደል ብለው የሚጠሩት ውጫዊው፣ታሪካዊው የቅዱሳት መጻሕፍት ትርጉም ነው።

ይህ  ትምህርታዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቅነት ነው፤ያ የትምህርት መስክ ባለፈው ክፍለ ዘመን እንደ ማደጉ ፣ስለዚህ ይህ ታሪካዊ እይታ በጣም ትኩረት የሚሰጥበት ትርጉም ሆኗል።ለቅዱስ ኤፍሬም ግና ይህ እይታ በቂ አይደለም ፤ታሪካዊ እውነታን ብቻ የሚመለከት እንደመሆኑ ፣የእምነት ዓይን ብቻ ከታሪካዊው ሰው ኢየሱስ  ወደ ሥግው ክርስቶስ መሄድ እንደሚችል ሁሉ በቅዱስ መጽሐፍም ውሳጣዊ ትርጉሙን ለመመርመር ወደ ውስጥ መዝለቅ የሚችለው የእምነት ዐይን ብቻ ነው።

ቅዱሳት መጻሕፍቱ እንደመስታወት ተቀምጠዋል

ዓይኑ ብሩህ የሆነዉም በዚያ ውስጥ የእውነትን ምስል ያያል።(Faith 67:8)

እንደ መንፈሳዊ ትምህርት አዋቂነቱ ቅዱስ ኤፍሬም በቀዳሚነት አግባብነት ባለው አመለካከትና በዚህ ውሳጣዊው የእምነት ዓይን ብቻ ሊታይ የሚችል ውሳጣዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም መመልከትን ይወዳል ። እንዲያዉም ቅዱሳት መጻሕፍት ስለ እግዚአብሔር የሚሉትን ውጫዊ ዓረፍተ ነገሮችን ከመመልከት ማቆምና ጥሬ ትርጉማቸውን መውሰድ ሁለቱም እኩል አደገኞች እንደሆኑ በአጽንኦት ይገልጻል፤ ስለ እግዚአብሔር ማንነት ወደ ተሳሳተ አረዳድ ስለሚወስድ፤በተመሳሳይ ጊዜም በአጠቃላይ በትሕትና በሰው ቋንቋ እንዲነገር  ለፈቀደ ለራሱ ለእግዚአብሔር የምሥጋና አልባ ንግግር ምልክትና  ስለ እግዚአብሔር ትሕትና በአግባቡ አለመረዳት ነው።

አንድ ሰው የእግዚአብሔርን ኃይል ለመግለጽ በተቀመጡ በስእላዊ አገላለጾች ላይ ብቻ

አትኩሮቱን የሚያደርግ ከሆነ

እግዚአብሔር ለራሱ ለሰው ልጅ  ጥቅም ራሱን በሰወረባቸው

በእነዚያ ስእላዊ አገላለጾች አማካይነት

ያንን ኃይል በማይገባ መልኩ ይወክለዋል፤አይረዳዉምም

እንዲሁም ለዚያ ክብር አይገባም

ምንም እንኳ ከእርሱ ጋር የጋራ ነገር ባይኖረውም

ማንነቱን ወደ ሰው ልጅ ደረጃ ያወረደ

ሰውነትን ወደ ራሱ መውደድ ያመጣ ዘንድ

 እርሱ ራሱን በሰው ልጅ መውደድ ውስጥ ሰወረ(Paradise 11:6)

ቅዱስ ኤፍሬም በቅዱሳት መጻሕፍት ውጫዊ ትርጉም ላይ ምንም ፍላጎት እንደሌለው ወይም ምንም ጥቅም እንደማይገኝበት አድርጎ እንደሚረዳ ልናስብ አይገባም። ይኽ ውጫዊው ትርጓሜ የክርስቶስ ሰውነት ያህል አገልግሎት አለው።የመጽሐፍ ቅዱስ ውጫዊው ታሪካዊ ትርጉምና ውስጣዊው መንፈሳዊ ትርጉም እጅግ እንደተሳሰሩና እንደ ተያያዙ በሰው ልጅ ውስጥ እንደ ሥጋና ነፍስ፣በክርስቶስ ውስጥም እንደ ሰውነትና ፈጣሪነት ናቸው።ለቅዱስ ኤፍሬም ጠቃሚ የሆነው የእነዚህ ሁሉ ጥንዶችን ግንኙነትና መስተጋብር መረዳት ነው። በየትኛዉም መንገድ ዙሪያ ቢሆንም የአንዱን ጥቅም በመካድ በሌላኛው ላይ ብቻ ትኩረት ማድረግ አደገኛና የተሳሳተ ነው።ስለዚህ ከአይሁድ ጋር የነበረው የቅዱስ ኤፍሬም ጥል ፡አይሁድ እነደ እርሱ አባባል በክርስቶስ ወደ ማመን ይመራቸው የነበረውን ወደ ውስጥ ጠልቀው ማየትን መቃወማቸው፡የኢየሱስ ሰውነትን ብቻ ማየታቸው እንዲሁም የቅዱሳት መጻሕፍት ውጫዊ ትርጓሜ ብቻ ማየታቸው ነው።

አይሁድ ህጉን ማጥናትንና ምክንያት መፈለግን

ባለመቻላቸው አፍረዋል

ይልቁን ከቃላቱ ድምጾች ራሳቸውን ካለ  ምንም መረዳት ውስጥ በመዝጋት

የትእዛዛቱን ትርጉም ቀላቀሉ

እውነተኛዉንና ትክክለኛውን

የመጽሐፍ ቅዱስን ትርጓሜ ሊያዩበት

የሚችሉበትን አስተሳሰብ ለማግኘት

አልደከሙምና (Heresies 50:4)

ቅዱስ ኤፍሬም በውጫዊ ታሪካዊና ውስጣዊ መንፈሳዊ የቅዱሳት መጻሕፍት እይታዎች መካከል መሠረታዊ ልዩነት እንዳለ በውል የተረዳ ነው። የመጀመሪያው(ታሪካዊው) በፍጥረት ክልል ውስጥ ያለው ውሱን ነው፤ትርጓሜዎች ቢያንስ በክልስ ሀሳብ ደረጃ ሊወሰኑና ጠቅላይ ሊሆኑ ይችላሉ። በሌላ በኩል መንፈሳዊ ትርጓሜ በተለዩ ህጎች ውስጥ የሚሠራ ነው፤እንዲሁም በዋናነት ሰፊ ነው፤ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞችም ውሱን አይደሉም። እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ ያስቀመጣቸው ስሞች በተፈጥሮና በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በሁሉም ስፍራ የሚገኙት ምሳሌዎችና ዓይነቶች ለእውነት እንደ መስኮቶች ወይም ትናንሽ ቀዳዳዎች ናቸው። እንዲያዉም በመጀመሪያ ደረጃ በእነዚህ ትናንሽ ቀዳዳዎች ለማየት መሠረታዊው ቅድመ ሁኔታ የእምነት ዓይን ነው፤ አንዴ ከመጀመሪያ መኖሩ ከተረጋገጠ ግና ይኽ የእምነት ዓይን ከተለያዩ ሰዎች ጋር በተለያዩ መንገዶች ይሠራል፤ወይም እንዲያዉም በአንድ ሰው ውስጥ በተለያዩ መንገዶች ግና በተለያዩ ጊዜያት ይሠራል። ውሳጣዊ ዓይኑ የጠፋበት ሰው ወደ መጽሐፍ ቅዱስ መመልከት አይችልም፤ ውስጣዊ ዐይኑ የሚያበራና ግልጽ የሆነ ግና ትልቅን ጉዳይ ያስተውላል። "ማንኛዉም ሰው ከትህትናው መጠን ጋር በተያያዘ መልኩ ከሁሉም የበለጠውን  እርሱን (እግዚአብሔርን) ይረዳል።”(Nativity 4:200)  

የእምነት ዓይን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በትኩረት ይመለከት ዘንድ እንዲህ ዓይነቱ  የእውነት ወይም መንፈሳዊ እውነታ ትልቅ ሀብት ቢሆንም  ማንም ግለ ሰብእ ሁሉንም ነገር የመረዳት ችሎታ የለዉም።ስለዚህም ውሳጣዊው ዓይን ይሆናሉ ብሎ የሚያስተውላቸው ትርጓሜዎች ወሰን የለሽ ናቸው።

ለመጽሐፍ ቅዱስ ቃላት አንድ ትርጉም ብቻ ቢኖር ኖሮ የመጀመሪያው ተርጓሚ ትርጉሙን ያገኘው ነበር፤ሌሎች አድማጮችም የመፈለግን ድካምና የማግኘትን ደስታ ባልተጋሩ ነበር። ይልቁን እያንዳንዷ የጌታችን ቃል የራሷ መልክ አላት፤እያንዳንዷ መልክም የራሷ አካል አላት፤ እያንዳንዷም አካል የራሷ መለያ አላት።እያንዳንዱም ሰው እንደየዓቅሙ ይረዳል ፤በተሰጠው መጠንም ይተረጉማል። (Commentary on the Diatessaron 7:22)

አንዱ ትርጉም ትክክል ሌላው ስህተት  የሚሆንበት አይደለም(ሁልጊዜ በታሪካዊ እይታ ሊሆን እንደሚችለው) ይልቁን ለአንድ ግለሰብ በተወሰነ ጊዜ ትርጉም ያለው እስከሆነ ድረስ የተገባ ትርጓሜ ነው።ስህተት የሚፈጠረው አንድ ሰው የራሱ መንፈሳዊ ትርጓሜ ብቻ ትክክል እንደሆነ ሲናገርና የአንድ ምንባብ ውጫዊና ውስጣዊ ትርጓሜዎች አይገናኙም ብሎ ሲያስብ ብቻ ነው።ይኽ በዋናነት ያ ጉዳይ አይደለም ሁለቱም የትርጓሜ ዓይነቶች ፡ታሪካዊው በአፍአዊው ስሜትና መንፈሳዊው በውሳጣዊው ስሜት በማተኮሩ በሁለት ፈጽሞ በተለያዩ የእውነታ አገላለጽ ወይም እውነታ ዙሪያ ያጠነጥናሉ፤ እንዲሁም አንደኛው እውነታ ሌላኛውን አያጠፋዉም ፤ሁለቱም አገላለጾች በአንድነት ጎን ለጎን በጋራ ሊኖሩ ይችላሉ።

ግልጽ ለሆኑ ምክንያቶች ቅዱስ ኤፍሬም ስለ ታሪካዊ ትርጓሜ የሚያትተው አልፎ አልፎ ብቻ ነው፤በዚህ ደረጃ ሲናገርም እሱ ሊለው የሚገባው እጅግ አርኪ አይደለም፤እጅግ በጣም ውስብስብ በሆኑት፣ባለፈው ዘመን ባደጉት የታሪካዊ ትርጓሜ ስልቶች ሲመዘን። ግን የእርሱ ዋና ጉዳይ ውስጣዊ፣መንፈሳዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም በሆነበት ቦታ ሁሉ(ይኽም የእርሱ የሁል ጊዜ ጉዳይ ነው) በዚያ የእርሱ ምልከታዎች አሁንም ቢሆን ጥልቅ እይታ ያላቸው በመሆኑ አስተዋይ ዘመናዊ አንባቢዎችን መማረክ ይችላሉ።

በዚህ ክፍል የቅዱስ ኤፍሬም መጽሐፍ ቅዱስን የመረዳት ምንነትና ትርጉም የመሰለኝን እየለየሁ ነው፤እንዲሁም እርሱ ራሱ በቀጥታ እንዲናገር ሊፈቀድለት አሁን ጊዜው ነው።

በዚህ ምንባብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥቅዱስ ኤፍሬም  ስለ ውሳጣዊ ትርጓሜዎች መብዛት ለክርስቶስ በመናገር ይጀምራል።

በአንተ(እግዚአብሔር) አንድ  አባባል ውስጥ የሚፈለገውን ስፋት ሁሉ መረዳት የሚችል ማን ነው? ከእርሱ ከምንወስደው በራቀ መልኩ ከእርሱ ብዙ እንተዋለንና ፤የተጠሙ ሰዎች ከምንጭ እንደሚጠጡት ። የእርሱ (እግዚአብሔር) እይታዎች ከእርሱ ከሚማሩት እይታዎች እጅግ የበዙ ናቸውና።እግዚአብሔር እያንዳንዱ ከቃሉ የሚማር እርሱ የፈለገውን አቅጣጫ እንዲያይ በሚያስችል መልኩ ቃሉን በብዙ ውበቶች ገልጾአል።እንዲሁም እግዚአብሔር እያንዳንዳችን በእርሱ በየትኛዉም አቅጣጫ ላይ በመመሰጥ ባዕለጸጋ እንሆን ዘንድ በቃሉ ውስጥ ሁሉንንም የስጦታ ዓይነቶችን ሰውሮአል።የእግዚአብሔር ቃል የሕይወት ዛፍ ነውና በሁሉም አቅጣጫ ላንተ የተባረኩ ፍሬዎችን የሚሰጥ ፤እርሱ በምድረ በዳ እንደተሰነጠቀው ዐለት ነው ፤በሁሉም አቅጣጫ ለእያንዳንዱ መንፈሳዊ መጠጥ የሆነው።እነርሱ የመንፈስን መብል በሉ፤የመንፈስንም መጠጥ ጠጡ።

ማንኛዉም መጽሐፍ ቅዱስን የሚመለከት ሰው ከመጽሐፍ ቅዱስ ሀብቶች ሁሉ ያገኘውን አንዱን ብቸኛ ያለ አድርጎ ሊወስድ አይገባውም፤ይልቁንም እርሱ ራሱ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉት ከብዙ ሀብቶች መካከል ያገኘውን አንዱን ብቻ መፈለግ እንደቻለ ሊያስተውል ይገባል።

እንዲሁም አንባቢው እርሱን ሀብታም ስላደረገው መጽሐፍ ቅዱስ  ምሥጢር ያለቀበት ደሀ አድርጎ ሊያስብ አይገባም።ይልቁንም አንባቢው ተጨማሪዎችን ማግኘት ካልቻለ የመጽሐፍ ቅዱስን ጥልቀት ያመሥግን።እርካታ ስላገኘህ ተደሰት ፤የሆነ ነገር ስለቀረብህ አትዘን።የተጠማ ሰው ስለጠጣ ያመሠግናል፤ምንጩን በመጠጣት ሊያደርቀው አለመቻሉን በማረጋገጡ አያዝንም።ምንጩ ያንተን ጥማት ይቁረጥ ያንተ ጥማት ምንጩን  አያድርቅ!ምንጩ ሳይቀንስ ጥማትህ ቢቆረጥ በተጠማህ ጊዜ እንደገና ትጠጣለህ፤ነገር ግን አንዴ ከረካህ በኋላ ምንጩ ደርቆ ቢሆን ኖሮ በምንጩ ላይ ያገኘኸው ድል ያንተን ጉዳት ባረጋገጠ ነበር።ስለወሰድከው ምስጋናን ስጥ እንዲሁም በዝቶ ስለተረፈው አታጉረምርም።አንተ ለራስህ የወሰድከው የራስህ ድርሻ ነው፤የተረፈው አሁንም ያንተ ውርስ ሊሆን ይችላል።( Commentary on the Diatessaron 1:18-19)

ይቆየን

 

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም (ክፍል ሦስት)

ዲ/ን ዮሐንስ ልሳነወርቅ

ግንቦት 4፣ 2003ዓ.ም

ከክፍል ሁለት የቀጠለ

5.የሥጋ(ሰውነት) ክብር (The value of the Body)

ቅዱስ ኤፍሬም የሥጋን ክብር ለመንቀፍ  ከሚሹ ከተወሰኑ የቀድሞ የክርስትና ልማዶች መገለጫ ከሆኑት ከፕላቶናዊ ወይም ከምንታዌ ዝንባሌዎች  ፣  በእጅጉ የራቀ ነው። ለቀና አመለካከቱ መነሻው ነጥብ ሥጋ ከእግዚአብሔር ፍጥረታት መካከል ስለሆነ ሊጠላ አይገባዉም የሚል እውነታ ነው፤ በየትኛዉም መንገድ  ክፉ ተደርጎ ከሚታሰበው አስተሳሰብ  የራቀ ይሁን። ግና በተጨማሪ ቅዱስ ኤፍሬም ሦስት ጠቃሚ ግንዛቤዎች አሉት።

የመጀመሪያው የራሱ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሥክርነት ነው። 1ቆሮ.619 ላይ ያለውን በመተርጎምሰውነታችሁ ከእናንተ ጋር የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደሆነ አታውቁምን?” ቅዱስ ኤፍሬም እግዚአብሔር ራሱ ሰውነትን ለቅድስት ሥላሴ ማደሪያ በማድረግ የሰጠውን ክብር ይጠቁማል።(የቅ/ኤፍሬም አንድምታ በቅ/ጳውሎስ መልእክታት ላይ ገጽ 62) በኋላም 2ቆሮ.5 ያለውን ሲተረጉም እንዲህ ይላልሰውነታችን ለእግዚአብሔር መንፈስ ማደሪያነት የተገባ እንደሆነ ሁሉ በመጨረሻም ለዘለአለማዊ ክብር የተገባ አድርጎታል።”(የቅ/ኤፍሬም አንድምታ በቅ/ጳውሎስ መልእክታት ላይ ገጽ 96) የሰው ሰውነት በጽዮን ተራራ የነበረውን ቤተ መቅደስ በመተካት አዲሱ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆነ ቅዱስ ኤፍሬም በማንኛዉም ቦታ ይናገራል። (Heresies 42:4)

 

ሁለተኛም እግዚአብሔር ሥጋን የመዋሐዱ እውነታ ስለ ሥጋ ርኩሰት ወይም ለሥጋ አይገባም የምንለው ምንም ነገር እንደሌለ ያመለክታል።(Nativity 9:2) በመጨረሻም ቅዱስ ቁርባን ለቅዱስ ኤፍሬም ስለ ሥጋ ክብር ተመሳሳይ መረጃን ይሰጠዋል። በሚከተለው ጽሑፍ በቅዱስ ቊርባን እያመኑ ነገር ግን  ሰውነትን ርኩስ አድርገው የሚቆጥሩት የክርስቲያን ቡድንን ይሞግታል።

ጌታ ሥጋን እንደ ርኩስ፣ የተጠላና ስሑት

አድርጎ ወቅሶ ቢሆን ኖሮ

ስለዚህ የድሳነት ሕብስቱ ጽዋውም ለእነዚህ መናፍቃን

የተጠላና ርኩስ መሆን አለበት፤

ራሱን በሕብስቱ ውስጥ የሰወረ ሆኖ እያለ

ያ ሕብስት ከዚያ ደካማ ሰውነት ጋር የተዛመደ መሆኑን እያየ

ክርስቶስ ሰውነትን እንዴት ሊንቅ ይችላል።

እንዲሁም እርሱ በማይናገር ሕብስት ተደስቶ ከነበረ

በሚናገርና አመክንዮን ገንዘብ ባደረገ በሰውነትማ

ምን ያህል እጅግ ይደሰት ይሆን!(Heresies 47:2)

እግዚአብሔር የተቀደሰውን ምሥጢር ሥጋዉንና ደሙን በሰው ሰውነት እንዲመገቡት በመፍቀዱ በትክክል ተመሳሳይ ነገር ተጠቁሟል።

ሰውነት ከክፉ ነገር የተገኘ ቢሆን ኖሮ

እግዚአብሔር  ምሥጢራቱን  በሰውነት ላይ ባላሳደረ ነበር።(Heresies 43:3)

ስለዚህም በቅዱስ ኤፍሬም ዓይን ሥጋና ነፍስ እኩል አስፈላጊነት አላቸው፤ የሚጫወቱት የተለያየ ሚና አላቸው።

ሥጋ ላንተ ምሥጋናን ያቀርባል

ምክንያቱም ላንተ መኖሪያ ይሆን ዘንድ ፈጥረኸዋልና፤

ነፍስ አንተን ታመልካለች

ምክንያቱም በመምጣትህ ለሙሽሪትነት አጭተሃታልና። (Heresies 17:5)

ሰውነት የሰርግ ቤትን ሲሆን ሙሽሪት ነፍስ ግን ሰማያዊ ሙሽራን ትገናኛለች።

6.በመንፈሳዊ ትምህርት ጥያቄን ለመጠየቅ የሚያስፈልጉ ቅድመ ሁኔታዎች (The prerequisities for Theological Enquiry)

መንፈሳዊ ትምህርት እንደሌሎች ማናቸውም የህሊና ጥያቄዎች ጥያቄ በሚያቀርበው ሰው ባለው የህሊና ዝንባሌ መሠረት ሦስት የተለያዩ  መልኮች ሊኖረው ይችላል።

በመጀመሪያ ደረጃ ህሊና የጥያቄውን አካል ለመጫንና ለመቆጣጠር ሊፈልግ ይችላል። እንዲህ ዓይነቱ ዝንባሌ ከፍራንሲስ ባኮን ዘመን ጀምሮ በብዛት ለሳይንሳዊና ሌላ ጥያቄ መገለጫ ሆኗል። በትክክልም ይሁን በስህተት ቅዱስ ኤፍሬም ይኽ በዘመኑ ለነበሩ ብዙ የኑፋቄ አሳቢዎች እንደ ዋና ዝንባሌ እንደሆነ አስተውሏል፤በተለይ በመንፈሳዊ ትምህርት መስክ ውስጥ እንዲህ ዓይነት የህሊና ኩራት ለእርሱ ተቀባይነት የሌለው ነው።

ለሁለተኛው አቀራረብ በአጀማመሩ እጅግ ተቀባይነት ያለው ይመስላል፤በአሁኑ ዘመን የመንፈሳዊ ትምህርት ጥያቄ መለያ የሆነ መልክ አለው። እዚህ ላይ ህሊና በተቻለ መጠን ከተጽእኖ ነጻ በሆነ መልኩና ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ የጥያቄውን አካል ለማጥናት ይዘጋጃል። በብዙ አቅጣጫዎች ፍሬያማ የሆነ አቀራረብ ነው፤እንዲሁም ይኽ አቀራረብ ቅዱስ ኤፍሬም የሞከረው መሆኑን ያመለክታል።ግና …

 

ወደ ትምህርትህ መልሰኝ ከኋላ ልቆም ፈልጌ ነበር

ግና እጅግ ደሀ ወደ መሆን እንደመጣሁ አየሁ

ነፍስ ካንተ ጋር ከመነጋገር በቀር

ሌላ ምንም ጥቅም አታገኝምና። (Faith 32:1)

የቅዱስ ኤፍሬም የሆነው ሦስተኛው አቀራረብ ታማኝነት ነው፤ከሁሉም በላይ ለፍቅርና ለአድናቆት የሚደረግ ታማኝነት። ነገር ግን ሁለተኛው አቀራረብ ከህሊና ወደ ተጠያቂው አካል የሚደረግ የአንድ አቅጣጫ እንቅስቃሴ ነው ፤ይኽ ሦስተኛው አቀራረብ በሁለት አቅጣጫ የሆነና ቀጣይነት ያለው ሱታፌ ነው።

ስለ ፈጣሪ እውነተኛነት የሰው እውቀትሊያድግ የሚችለው በእንዲህ ዓይነት የፍቅር መስትጋብር ብቻ ነው።

 

በዚሁ መዝሙር ላይ ቅዱስ ኤፍሬም እንዲህ በማለት ይቀጥላል።

አንተን በማሰብ በተመሰጥኩ ጊዜ

ካንተ ፍጹም ዋጋን አገኛለሁ

ስላንተ ባሰብኩበት በየትኛዉም አቅጣጫ

ካንተ ምንጭ ይፈስሳል

እኔ ምንጩን ልይዝበት የምችልበት ምንም መንገድ የለም

ጌታ  ያንተ ምንጭ ስላንተበማሰብ ከማይጠማ ሰው የተሰወረ ነው

አንተን ለማይቀበል ሰው ያንተ ዋጋ ባዶ ይመስለዋል

ፍቅር ያንተ ሰማያዊ ግምጃ ቤት ባለቤት ነው። (Faith 32:2-3)

ስለዚህ እግዚአብሔርንና ስለእኛ የተፈጠረውን ዓለም የምንረዳበት መንገድ በእኛ መሠረታዊ ዝንባሌና አቀራረብ የተደገፈ ነው፤ከእኛ ከራሳችን እነደተለዩ የጥያቄ አካላት የምንረዳቸው እንደሆነ (እነርሱን ለመጫን መሞከር እንችላለን ወይም በአማካይ ከእኛ ጋር እንዳሉ መረዳትእንችላለን) ወይም ራሳችንን ሊቀየር በማይችል መልኩ በጥያቄያችን አካል ላይ እንደተሳተፍን ማየታችን እንዲሁም በምሥጢሩ ለመሳተፍ ፈቃደኞች መሆናችን ይደገፋል። ቅዱስ ኤፍሬም ይኽ የመጨረሻው መንገድ ብቸኛው በእውነት ተቀባይነት ያለው መንገድ ብቻ ሳይሆን የትኛውም የእግዚአብሔር እውቀት ሊሻበት የሚችል ብቸኛው መንገድ እንደሆነ አይጠራጠርም።

ከዚህ ከመነሻው የታማኝነትና ሱታፌ ዝንባሌ ጋር እኩል ጠቀሜታ ያለው የመደነቅና የመገረም ስሜት ነው።እንዲህ ዓይነቱ የመደነቅ ሰሜት በቅዱስ ኤፍሬም በየትኛዉም ጽሑፎች ላይ የሚገኝ ነው።እንዲህ በማለት ይናገራል፤”በሕይወት በሚያጋጥሙ ቀላል ነገሮች አስተሳሰባችን አድናቂ እንዲሆን ያደረገ እርሱ(እግዚአብሔር) ምስጉን ነው።”(Faith 43) ግና ከሁሉም በላይ ተደናቂ የሆነው  ሰውን በመውደድ በእግዚአብሔር ከፍተኛ መገለጥ እርሱ ራሱ ከሥጋ ጋር በተዋሐደ ጊዜ  ነው።(Fast 3:6, Heresies 35:7) የእግዚአብሔር ወደ ትቢያ መውረድ (መምጣት)  የሚያስደንቅ ነው።(Faith 46:11)

መደነቅ ወደ ፍቅርና ወደ ምሥጋና ያደርሳል፤እንዲሁም በፍቅራችን መጠን በማመሥገን በኩል መለኪያ የሌለውን ሕይወት እናገኛለን።(Nisibis 50:5) እንዲያዉም ባለማመስገን መኖር ሙት ሆኖ እነደ መኖር ነው።

 

በምኖርበት ጊዜ ምሥጋናን አቀርባለሁ

እኔ ህልውና እንደሌለኝም አይደለም

በሕይወት ዘመኔ ምሥጋናን አቀርባለሁ

በሕያዋን መካከል እንደሞተ ሰውም አልሆንም

ሥራ ፈትቶ የሚቆም ሰው ሁለት ጊዜ የሞተ ነው

ፍሬ ማስገኘት የተሳናት ምድርም የሚያዘጋጃትን ትከዳዋለች። (Nisibis 50:1)

እንዲሁም ያለ ፍቅር እውነት ሊደረስበት አይችልም።

እውነትና ፍቅር ሊለያዩ የማይችሉ ክንፎች ናቸው

እውነት ያለ ፍቅር መብረር እንደማይችል ሁሉ

እንዲሁም ፍቅር ያለ እውነት ወደ ላይ ሊወነጨፍ አይችልም

የስምምነት ቀንበራቸው አንድ ነው።(Faith 20:12)

የዚህ ግጥም ክፍል ሦስተኛ ስንኝ ለቅዱስ ኤፍሬም ተጨማሪ ጥቅም ወዳለው ጉዳይ ያመጣናል፤ለማንኛዉም ዓይነት መንፈሳዊ ጥያቄ መነሻው ነጥብ በሰው ህሊና የትኞቹ የመንፈሳዊ ትምህርት ክፍሎች ሊመረመሩ እንደሚችሉና የትኞቹ የመንፈሳዊ ትምህርት ክፍሎች ሊመረመሩ እንደማይችሉ ማወቅ ነው፤በሌላ አነጋገር አንድ ሰው በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለውን የነገረ ህላዌን ልዩነት የት ላይ ማስቀመጥ እነዳለበት በሚገባ ማወቅ አለበት ።ይኽም ማለት አንድ ሰው ከኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊ ትምህርት አቋቋም ካልተነሳ ከመጀመሪያው ጀምሮ ስህተትን ይሠራል፤ስህተት የሆኑ የመነሻ ግንዛቤዎችም ወደ ተጨማሪ ስህተት ብቻ ይመራሉ። ይኽም ቀድመን እንዳየነው ከተለያዩ የአርዮሳዊ አቋቋም ጋር ቅዱስ ኤፍሬም መሠረታዊ ቅራኔ ውስጥ የሚገባበት ጉዳይ ነው። በተመሳሳይ ቅዱሳት መጻሕፍት በአግባቡ ሊተረጎሙ የሚችሉት በኦርቶዶክሳዊ እምነት ብርሃን ብቻ ነው።

ሁሉን ቅዱሳት መጻሕፍትን የሚከፍቱ የዶግማ ቁልፎች

በእኔ ዓይን ፊት የሥነፍጥረትን መጽሐፍ ፣

የታቦቱን ግምጃ ቤት፣የህጉን ዘውድ ከፍተዋል

ከሌሎች መጻሕፍት ሁሉ በራቀ በትረካው  ፈጣሪን የተረዳና

ሥራዎቹንንም ያስተላለፈ ቅዱስ መጽሐፍ ነው።

ሁሉንም የእርሱ የእጅ ሥራዎችን በማስተዋል

መጽሐፍ ቅዱስ የሥራዎቹን አካላት ገልጿል ። (Paradise 6:1)

ይቆየን…

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም(ክፍል ሁለት)

ዲ/ን ዮሐንስ ልሳነወርቅ

ከክፍል አንድ የቀጠለ

በቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች ላይ በሚያጠነጥነውና የሚያበራ ዐይን በሚል ርእስ ሰባስቲያን ብሩክ ካዘጋጀው  መጽሐፍ የተገኘው እንዲህ ተተርጉሞ ቀርቦአል። መልካም ንባብ

በዚህ ክፍል ውስጥ የምናየው ፈጣሪና ፍጡር፣/የተሰወረውና የተገለጠው/ሁለቱ ጊዜያትና ነጻ ፈቃድ በሚሉት ርእሶች ስር ቅዱስ ኤፍሬም በግጥም ያቀረበውን ትምህርት ነው።የቅዱስ ኤፍሬም መዝሙራት ከሚያጠነጥኑባቸው ርእሰ ጉዳዮች አንጻር ስያሜ ተሰጥቶአቸዋል። ለምሳሌ በእምነት ዙሪያ የጻፈውን -Faith ፣በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ የጻፈውን -Church የሚል ሲሆን ፤በዚህ ጽሑፍም እነዚህ  በእያንዳንዱ መዝሙር ስር ተጠቅሰዋል።

1. ፈጣሪ-ፍጡር (Creator-Creation)

ቅዱስ ኤፍሬም በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለዉን ልዩነት ሁልጊዜ የተረዳ ነው። በእምነት ላይ ከዘመራቸው መዝሙሮች በአንዱ(Faith 69:11) በነዌና አልአዛር (ሉቃ.16፣26) ምሳሌ የተገለጸውን ቃል በማንፀባረቅ ስለ ነገረ ህላዌ(ontology) ያለውን ክፍተት እንደ ሰፊ ልዩነት በመውሰድ ይናገራል። በዚህ ሰፊ ልዩነት ውስጥ ፍጡር ፈጣሪዉን አይደርስበትም።(Faith)ይኽም ማለት የተፈጠረ ማንነት ስለ ፈጣሪ ማንነት ምንም ማለት አይችልም።

ቀድሞ እንዳየነው በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለው ጥርት ያለ  የልዩነት ቦታ የማመልከት ጉዳይ በአራተኛው መቶ ክ/ዘመን ክርክር ነበረበት። ቅ/ኤፍሬም  ሁሉንም የመልአካዊና የቁስ አካላዊ ማንነትን በአንድ ወገን (ፍጡር) ሲያስቀምጥ የፈጣሪ ቃል ከነገረ ህላዌ ልዩነት(ontological chasm) በሩቅ አቅጣጫ በአጽነዖት ያስቀምጠዋል።

ማንኛዉም ፍጡር ይኽንን ሰፊ ልዩነት በማለፍ ፈጣሪ ጋር መድረስ እንደማይችል ከማስተዋል ጋር በተያያዘ (ቅ/ኤፍሬም ከሌሎች ብዙ አባቶች ጋር የሚጋራው ሀሳብ) በሆነ ነገር ዕውቀት ያለው መረዳት ከዕውቀቱ አካል የግድ መብለጥ አለበት የሚለው ግንዛቤ ውጤት ነው።በዚህ መረዳት መሠረት በተመሳሳይ ጊዜ  እግዚአብሔርን ማወቅም መግለጽም ይቻላል የሚል የሰው መረዳት የማይያዘውን (uncontainable) እግዚአብሔርን መያዝ ይችላል እያለ ነው። ስለዚህም የእግዚአብሔርን ማንነት ለመመርመር መሞከር እጅግ አስፈሪ እንደሆነ እንዲህ ይገልጸዋል።

           ማንኛዉም መመርመር(ላልቶ ይነበብ) የሚችል ሰው
           የሚመረምረውን(ነገር) የያዘ (contains) ይሆናል።
           ፍጹም ዕውቀት ያለውን የሚይዝ (contains) ዕውቀት
           ሁሉን ዐዋቂ ከሆነው(ከእግዚአብሔር ) ይበልጣል።
           እርሱን(እግዚአብሔርን) በአጠቃላይ መለካት እንደሚችል አረጋግጧልና።
           ስለዚህም አብንና ወልድን የሚመረምር ሰው ከእነርሱ ይበልጣል!
           አመድና ትቢያ ሲሆን ራሱን ከፍ አድርጎ

አብና ወልድ መመርመር(ጠብቆ ይነበብ) አለባቸው የሚል የራቀ ፣የተወገዘም ይሁን። (Faith 9:16)
የአምላክን መሰወር ስለመመርመርና መጠየቅ (የማይጠየቀውን) የሚሰጠው ምላሽ ማስጠንቀቂያ ቅ/ኤፍሬም   ዝንባሌው ኢ-ምሁራዊ ነው ወደሚለው ሊመራን አይገባም። ከዚህ የራቀ ነው፣ እርሱ እንደሚያየው የሰው መረዳት በተፈጥሮ ውስጥ ብዙ አቅጣጫ(scope) ያለው ሲሆን ድርሻዉም የፈጣሪን እውነታ በከፊል ለመረዳት የሚያስችሉትን ዓይነቶችንና  ምሳሌዎችን ከተፈጥሮ መፈለግ ነው። አስነቃፊ የሚሆነው መረዳቱ የነገረ ህላዌን ልዩነት ማለፍ ሲፈልግ ብቻ ነው።አግባብነት ያለው የመረዳት ጥያቄ የሚያርፍበት ቦታ እግዚአብሔር ራሱን በፍጥረት(በተገለፁ ነገሮች) በገለፀበት ላይ ነው። ስለዚህም በእምነት መዝሙሮች ላይ ቅ/ኤፍሬም ሲገልፅ                                         

                         በቤተ ክርስቲያን የመረዳት ጥያቄ አለ፤
                         የተገለጸውን መመርመር
                         መረዳቱ ያልተፈቀዱ የተሰወሩ ነገሮችን
                         የመመርመር ዝንባሌ አልነበረውም።(Faith 8:9)

ይህም ቅ/ኤፍሬም ደጋግሞ በሚጠቀማቸው የተገለጠና የተሰወረ በሚሉ ቃላት መካከል ያለውን ሚዛናዊነት(tension) ወደሚያሳየው ቀጣይ ርእስ ይወስደናል።

 

2. የተሰወረውና የተገለጠው( The Hidden and The Revealed )

ቅዱስ ኤፍሬም ስውርና ክሱት(ግልጥ) የሚሉ ቃላትን ሲጠቀም ፈጽመው ከተለያዩ ሁለት እይታዎች አንዱን ይገልጻል። አብዛኛውን ጊዜ የሰው እይታ እያልን የምንጠራውን ራሱ እንዲገለጽ ካልፈቀደ በቀር እግዚአብሔር ስውር ነው የሚለውን ይተካል። የእግዚአብሔርን መሰወር ሰው ሊረዳው  የሚችለው እግዚአብሔር በተለያዩ  ሁኔታዎች ራሱን ሲገልጽ ብቻ  ነው።ለፍጡር ህላዌ የእነዚህ እግዚአብሔር ራሱን ለእያንዳንዱ  የመግለጽ ሁነቶች ሁሉ የእግዚአብሔርን መሰወር ወደ ሙሉ መገለጥ አያደርሱትም፤ መገለጡ ሁል ጊዜ በከፊል ነው። ይኽም ማለት ይህ የሰው እይታ በዋናነት እንደየራሱ ነው። እያንዳንዱ ሰው የእግዚአብሔርን መሰወር የሚያቀርበው በተለያዩ የመገለጥ መንገዶች ነው።
የእግዚአብሔር መሰወር ወደ ሙሉነት በቀረበ ሁኔታ ለሰውነት የተገለጠው በሥጋዌ ነው ማለት አስፈላጊ አይደለም፤ያኔም እንኳን የፈጣሪነት መሰወር እንደተጠበቀ ነበር።

                       ለተሰወረው ምሥጋና የማይሰጥ ማነው፡ ከሁሉም ይልቅ የተሰወረ
                       መገለጥን ይከፍት ዘንድ ማን መጣ፡ ከሁሉም ይልቅ የተከፈተ
                       እሱ በሰውነት ላይ ተቀምጦአልና ፤ ህሊናዎች ባይዙትም
                       ሌሎች አካላትም ዳሰሱት (Faith 19:7)
                     
         ወይም ሰፋ ባለ ሁኔታ
                       ጌታ፡ ወደ መገለጥ የመጣውን መሰወርህን 
                       ትኩር ብሎ ማየት ማን ይችላል?
                       አዎ መሰወርህ ወደ መገለጥና ወደ መታወቅ መጥቶአል
                       ምሥጢራዊ ህላዌህ ያለ ገደብ ወደ መገለጥ መጥቶአል
                        የሚፈራ (የሚደነቅ) ማንነትህ ወደ ያዙት እጆች መጥቶአል።
                        ጌታ ይህ ሁሉ በአንተ ሆኖአል ፤ ምክንያቱም ሰው ስለ ሆንክ
                        አንተን ስለላከ ምስጋና ለእሱ(ለአብ)
                        እንዲህ ቢሆንም ፈጽሞ የማይፈራህ ማነው
                        ምክንያቱም ምንም እንኳ
                        ሰው መሆንህ ዳግም ልደትህ የተገለጠ ቢሆንም
                        ከአብ የተወለድከው ልደት የማይደረስበት እንደሆነ ይቀራል።
                        የሚመረምሩትን ሁሉ አስቁሞአል። (Faith 51:2-3)

ከዚህ ሰውአዊና ግላዊ እይታ ጎን ለጎን ሌላ ፈጽሞ የተለየ እይታ አለ፤ ይኽም ቅዱስ ኤፍሬም እውነት እያለ የሚጠራው የፈጣሪ እርግጠኝነት ነው። እዚህ ላይ  መነሻው የሰው እግዚአብሔርን መረዳት አይደለም፤  በራሱ ህልው የሆነ (objectively exists) ግን በተሰወረና   ግላዊ በሆነ መንገድ የሚገለጥ የእግዚአብሔር  እውነተኛ ህላዌ ነው። ከዚህ አቅጣጫ ሲታይ ዓይነቶችና ምሳሌዎች እግዚአብሔር በሚታይ  ፍጥረት  ራስን የመግለፅ ቅጽበቶች አይደሉም ፤ይልቁንም አንድ ቀን የሚገለጥን ነገር የሚያመለክት መሰወር አላቸው፤ በተፈጥሮና በቅዱሳት መጻሕፍት ምሳሌዎች የተሰወረው በክርስቶስ ሥጋዌ ተገልጦአል፤ በ(ቤ/ክ) ምስጢራት የተሰወረ በፍርድ ጊዜ በመንግሥተ ሰማያት ይገለጣል።
ቅዱስ ኤፍሬም በግጥሙ ስለ ተሰወረውና ስለ ተገለጠው ያሉትን እነዚህን ሁለት እይታዎች ድንቅ በሆነ መንገድ ያስተሳስራቸዋል። በሁለቱም ጥጎች ፡ የተሰወረና የተገለጠ ፡እንዲጠበቅ የሚያደርገው ሚዛናዊነት በእግዚአብሔር  ርሑቅነት(transcendence) ና ቅሩብነት(immanence) መካከል ካለው መሳሳብ ሌላ አይደለም።

3. ሁለቱ ጊዜያት (The Two Times)

መደበኛው ጊዜ ቀጥታዊ ነው፤ እያንዳንዱ ነጥብም በጊዜ ውስጥ በፊትንና  በኋላን ያውቃል። በሌላ በኩል ምስጢራዊ ጊዜ በፊትንና በኋላን አያውቅም ዘልዓለማዊ አሁንን ብቻ። ለምሥጢራዊ ጊዜ ጠቃሚ የሆነው  በቀጥታዊ ጊዜ ቅደም ተከተል ላይ ያለው ልዩ ቦታ ሳይሆን ይዘቱ ነው። ይኽም ማለት በታሪካዊ ጊዜ በተለያዩ ወቅቶች የሚገኙ ፣ በነገረ ድሕነታዊ ይዘታቸው አንድነት ያላቸው ድርጊቶች ፡እንደ የክርስቶስ ሰው መሆን/መጠመቅ/መሰቀል/ወደ ሲኦል መውረድ(ነፍሳትን ለማውጣት)ና ትንሣኤ ፡በምስጢራዊ ጊዜ በአንድነት ይሄዳሉ፤ሊተኮርበት የሚቻል አጠቃላይ ነገረ ድሕነታዊ ይዘታቸው  ከእነዚህ ተከታታይ  ነጥቦች በቀጥታዊ ጊዜ በማንኛዉም(በአንዱ) ላይ በማተኮር በሚለው ውጤት። ለምሳሌ ምንም እንኳ በቀጥታዊ ጊዜ የክርስቶስ ጥምቀት ከሞቱ እና ከትንሣኤው በፊት ቢሆንም በሶሪያ ትውፊት እንደራስና ለሁሉም የክርስትና ጥምቀት ምንጭ መሆኑን ወደ መረዳት እንዴት እንደመጡ ይገልጻል።

በቅዱስ ኤፍሬም መዝሙራት የምስጢራዊ ጊዜ እሳቤ ከሌሎች ሁለት ነጥቦች አንጻርም ጠቃሚ ነው።
በመጀመሪያ  ደረጃ ቅ/ኤፍሬም ክርስቶስ ወደ ሙታን ዓለም ሲኦል የመውረድ አስፈላጊነቱን ስለተረዳበት መንገድ የሚያሳይ ስለሆነ። ነገር ግን በመሬት ላይ የክርስቶስ ሥግው ሕይወት ለታሪካዊ ጊዜና ቦታ መግቢያ ነው፡ የመጀመሪያው ክ/ዘመን ፍልስጥኤም፡ ወደ ሲኦል መውረድ ከምሥጢራዊ ጊዜ እና ቦታ ጋር ብቻ የተያያዘ ነው።ይኽ የክርስቶስ ወደ ሁለቱም ኃላፊና መጪ ጊዜ መግባት ነው፤በጂኦግራፊያዊ ቦታ የተከለለም አይደለም። ስዚህም ወደ ሲኦል መውረዱ በነገረ ድሕነት ሂደት ላይ ከጌታ የምድር ቆይታው ጋር እኩል ጠቀሜታ አለው፤ በዚያም እንዲህ ባይሆን ኖሮ ሊነሳ የሚችለው ውሱንነትን (የክርስቶስ ሥራ በታሪካዊ ጊዜና ጂኦግራፊያዊ ቦታ እንደተገደበ መረዳት) ያብራራል።

የክርስቶስ ወደ ሲኦል የመውረድ ዶግማዊ ዓላማ ሥጋዌ(የክርስቶስ ሰው መሆን) ሁሉንም ታሪካዊ ጊዜንና ጂኦግራፊያዊ ቦታን እነደለወጠ(effects) በግልጽ ለማሳየት ነው። ነገር ግን ይኽን ለማግኘት በምስጢራዊ ጊዜና በምስጢራዊ ቦታ  አንጻር ሊነገር ይገባዋል፤ በዚህም መሠረት መውረዱም ታሪካዊ በሚመስልና ግጥማዊ የጥንት ታሪክ በሆነ መንገድ ብቻ ሊገለጽ ይችላል፡ ቅዱስ ኤፍሬም በንጽቢን መዝሙሮቹ ሁለተኛ አጋማሽ ላይ በታላቅ ድራማዊ ውበት እንደገለጸው።

የቅዱስ ኤፍረምን አስተሳሰብ ለመረዳት የምስጢራዊ ጊዜ እሳቤ ጠቃሚ የሆነው ሁለተኛው ነጥብ የሚያጠነጥው በታሪካዊጊዜ የክርቲያኖች የጥምቀትና ቁርባን ምስጢራት ሱታፌና በፍርድ ቀን የእነሱ ሙሉ በሙሉ እውን መሆን ነው። ምክንያቱም የመንግሥተ ሰማያት ሕይወት ለምሥጢራዊ ጊዜ የተገባ ነው። በተለያየ መጠን በምድር ላይ በታሪካዊ ጊዜ ውስጥ ባለ በእያንዳንዱ ሊተገበር ይችላል።

4. ነጻ ፈቃድ (Free will)
በቅዱስ ኤፍሬም አስተሳሰብ ውስጥ ነጻ ፈቃድ እጅግ ጠቃሚ የሆነ ሚና ይጫወታል። በዚህ ርእስ ላይ ያተኮረ መዝሙር  ጌታ፡ትንሿን አካል ነፃ ፈቃድን በመስጠት ከሌሎች ሁሉም ከተፈጠሩ ነገሮች አገዘፍክ። (Heresies 11)የሚል መልስ አለው።

ቀድሞ እንዳየነው አዳም በራሱ ነጻ ፈቃድ ትእዛዛቱን ይጠብቅ ዘንድ መርጦ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር ከፍ ባለ ሁኔታ  አዳምን ያከብረው ዘንድ በመካከለኛ ሁኔታ ፈጥሮታል ።

         
                  ፍትሓዊ የሆነው(እግዚአብሔር)፡ዘውዱን ለአዳም በከንቱ እንዲሰጠው አልወደደም
                  ምንም እንኳ በገነት ያለ ድካም ደስ ይሰኝ ዘንድ ቢፈቅድለትም
                  አዳም ቢፈልግ ሽልማቱን ማግኘት እንደሚችል እግዚአብሔር አውቆአል።
                  ፍትሓዊው ፡አዳምን ያከብረው ዘንድ ስለወደደ፤ ምንም እንኳ በልዑላዊ ሕላዌዎች ደረጃ
                  በጸጋ ታላቅ ቢሆንም ለሰው አግባብነት ላለው ለነጻ ፈቃድ አጠቃቀም
                  ክብሩ ያነሰ ነገር   አይደለም።(Paradise 12:18)   
አዳም ከገነት የተባረረው በተሳሳተ የነጻ ፈቃዱ አጠቃቀም ነው፤እንዲሁም ቅዱሳን የከበሩት በዚህ ስጦታ ትክክለኛ አጠቃቀም ነው።
                  ትእዛዛቱን ያስቀመጠ እርሱ(እግዚአብሔር) ምስጉን ነው
                  በእነዚያ(ትእዛዛቱ) ምክንያት ነጻ ፈቃድ ይከበር ዘንድ
                  ጽድቅን፣ስለነጻ ፈቃድ የሚጣሩ ምስክሮችን ያበዛ
                  እርሱ(እግዚአብሔር) ምስጉን ነው።(Heresies 11:4,end)
እርሱ ራሱን ባለ ማስከፋት ደስ እናሰኘው ዘንድ እኛን ማስገደድ በቻለ ነበር ፤ግና በምትኩ   በራሳችን ነጻ ፈቃድ በደስታወደ እርሱ እንቀርብ ዘንድ በሁሉም መንገድ ተቸገረ።(Faith 31:5)
የኖህ ትውልድ ስለ ነጻ ፈቃድ ትክክለኛ እና የተሳሳተ አጠቃቀም ለቅዱስ ኤፍሬም ቀዳሚ ምሳሌ ሆኖአል።
                   የኖህን ምሳሌ ውሰድ፤
                   በዘመኑ የነበሩትን ሁሉንንም መገሰፅ ይችላል፤
                   ፈልገው ቢሆን ኖሮ እነሱም እኩል ድል መንሳት ይችሉ ነበር፤
                   በእነሱ የነበረው የእኛ ነፃ ፈቃድ በኖህ ከነበረው ጋር አንድ ነውና።(Chrch 3:9)

የነፃ ፈቃድ ተግባር በሞራል ክልል የተገደበም አይደለም።ለተለያዩ የእግዚአብሔር ራስን የመግለፅ መንገዶች ምላሽ መስጠት ሙሉ በሙሉ እንደኛ ፍላጎት ነው።የእኛ የራሳችን ነፃ ፈቃድ የአንተ ደስታ መክፈቻ ነው።(Church 13:5)
 
ምንም እንኳ በራሳቸው ነጻ ፈቃድ ራሳቸውን ለሃጢአት ባሪያ ባደረጉት ውስጥ በግልጽ ባይታይም ነጻ ፈቃድ በእያንዳንዱ በእኩል መጠን ይገኛል።

ቅዱስ ኤፍሬም ይኽንን በሕክምናዊ ንጽጽር ይገልፀዋል።
                   የእኛ ነጻ ፈቃድ ማንነት በእያንዳንዳችን ውስጥ አንድ ዓይነት ነው።
                   የነጻ ፈቃድ ኃይል በአንዱ ውስጥ ደካማ ከሆነ በሁሉም ውስጥ ደካማ ነው
                   የነጻ ፈቃድ ኃይል በአንዱ ውስጥ ብርቱ ከሆነ በሁሉም ውስጥ አንድ  ነው።
                   የጣፋጭነት ተፈጥሮ ምንነት በጥሩ ጤንነት ላለ ለአንድ ሰው
                   ጣፋጭ ይመስለዋል።
                   ለታመመ ለሌላው ሰው ግን መራራ ይመስለዋል፤
                   ለነጻ ፈቃድም እንዲሁ
                   ከኃጢአተኞች ጋር ታማሚ ነው፤ ከጻድቃን ጋር ግን ጤነኛ ነው።
                   ማንኛዉም ሰው የጣፋጭነትን ጣዕም መቅመስ ቢፈልግ
                   በታማሚ ሰዎች አፍ ውስጥ አይቀምስም ወይም ለመቅመስ ሙከራ አያደርግም፤
                   ጣዕሞችን ለመለየት መቀመጫ የሚሆነው ጤነኛ አፍ ነው።
                   እንደገና ማንም የነጻ ፈቃድን ኃይል መለካት ቢፈልግ
                   በመጥፎ ተግባሮቻቸው በተዳደፉት ውስጥ መሞከር የለበትም
                   ንጹህ የሆነ ጤነኛ ሰው እሱን ለመቅመስ ማደሪያዉን ሊሰጥ ይገባዋል።
                   ሕመምተኛ ሰው የጣፋጭነት ጣዕም መራራ ነው ሊልህ የሚገባ ከሆነ
                   ሕመሙ ምን ያህል እንደጸና ተመልከት፤
                   ስለዚህም የደስታ ምንጭ የሆነውን ጣፋጭነትን አሳስቶአል፤
                  እንደገና ማንም የተዳደፈ ሰው የነጻ ፈቃድ ኃይል ደካማ ነው ሊልህ የሚገባ ከሆነ
                  የሰው ልጅ ገንዘብ ያደረገውን ኃብት ነጻ ፈቃድን ደሀ በማድረግ 
                  ተስፋዉን እንዴት እንደቆረጠው ተመልከት ። (Church 2:18-23)

 
ይቆየን!                                    

 

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም(ክፍል አንድ)

ዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የረጅም ዘመን ሐዋርያዊ ጉዞ ላይ በጎ ተፅዕኖ ካላቸው የአራተኛው መ/ክ/ዘመን አባቶች መካከል አንዱ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ይህ አባት ምንም እንኳን በቋንቋ ውሱንነትና በቦታ ርቀት በርካቶች ሥራዎቹና ጽሑፎቹ የታወቁለት ባይሆንም ሕይወቱን በብሕትውና የመራ የትርጓሜ መጻሕፍትን ፣የቅኔ፣ የግጥምና የወግ ጽሑፍ በማዘጋጀት የኖረ ባለ በጎ ገድል አባት ነው፡፡

የቅዱስ ኤፍሬምን ሥራዎች በማሰባሰብ በመጽሐፍ መልክ ካወጡ ሰዎች አንዱ የሆነው (ዶ/ር ሰባስትያን ብሮክ) ’the Luminous Eye’’ በሚል ርዕስ ካዘጋጀው መጻሕፍ  ውስጥ ጎላ ጎላ ያሉትን ትምህርቶች እየተረጎምን ልናቀርብ ወደድን፡፡ ይህም ክፍል አንድ መግቢያ ሆኖ የቅዱስ ኤፍሬምን ሕይወትና ሥራዎች በአጭሩ የሚቀርብበት ነው፡፡
የቅዱስ ኤፍሬም ሕይወቱ
የቅዱስ ኤፍሬም ሀገረ ውላዱ ከዋክብትን ከሚያመልኩ ሰዎች መካከል ነው፡፡ አባቱም ክርስትናን የሚጠላ ካህነ ጣዖት ነበር፡፡ አንዳንድ ምንጮች ከቅዱስ ኤፍሬም ሕይወት በመነሳት ወላጆቹ ክርስቲያኖች እንደነበሩ ዘግበዋል፡፡ የሐምሌ አስራ አምስት ስንክሳር ግን የአባቱን ካህነ ጣዖትነት ያረጋግጣል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም የተወለደው  በ306 ዓ.ም ገደማ “በሜሶፖታሚያ” ውስጥ በምትገኝ “ንጽቢን” እንደሆነ ይታመናል።(ንጽቢን   በደቡባዊ ቱርክ እና በምዕራባዊ ሶርያ መካከል የምትገኝ ቦታ ናት፡፡) ይህቺም ቦታ ከ318ቱ ሊቃውንት አንዱ የነበረው የቅዱስ ያዕቆብ ሀገረ ሰብከቱ የነበረች ናት፡፡
ይህንን ታላቅ አባታችንን የእግዚአብሔር መንፈስ አመላክቶት ወደ ቅዱስ ያዕቆብ ሄዶ ትምህርተ ክርስትናን ተምሮ የተጠመቀ ሲሆን ከወላጆቹ ጋር የኖረው እስከ አሥር ዓመቱ ብቻ ነው፡፡ በትምህርተ ክርስትና አምኖ ከተጠመቀ በኋላ ግን በቅዱስ ያዕቆብ ዘንድ በብሕትውና ተወስኖ በመማርና በማስተማር በንጽቢን ለሚገኘው መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ሓላፊ እስክመሆን ደርሶ ነበር፡፡
በ393 ዓ.ም የንጽቢን ከተማ  በወራሪዎች እጅ ስትወድቅ ቅዱስ ኤፍሬም ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር በመሆን የሮም ግዛት ወደነበረችው ኤዴሳ (ታናሽ እስያ፣ዑር) ተሰደደ፡፡ ይህቸ ቦታ ቅዱስ ኤፍሬም ከመናፍቃን ጋር የተጋደለባት፣ በቤተክርስቲያን ትምህርት ላይ ያላቸውን አብዛኞቹን የክህደት ትምህርቶች የሞገተባትና  መጻሕፍቱን ያዘጋጀባት ናት፡፡አብዛኛዎቹን ትምህርቶቹንና መጻሕፍቱን ያዘጋጀው በዚች በኤዴሳ በሚገኘው ትምህርት ቤት ነው፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከቅዱስ ያዕቆብ ጋር በመሆን በአርዮስ ምክንያት በተካሄደው  የኒቅያው ጉባኤ    ( 325 ዓ.ም ) ላይ ተገኝቷል፡፡ በዚህም የአርዮስን ክህደትና ምክንያተ ውግዘት ተገንዝቧል፡፡
ከኒቅያ ጉባኤ መልስ መንፈሰ እግዚአብሔር በራዕይ በገለፀለት መሠረት ቅዱስ ኤፍሬም ከቅዱስ ባስልዮስ (ቁጥሩ ከ318ቱ ሊቃውንት ወገን ነው) ዘንድ ለመገናኘት ወደ ቂሣርያ ሄዷል፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም የዲቁና ክህነት ሠጥቶ ከሀገረ ስብከቱ ከፍሎ እንዲያስተምር ወስኖ በእርሱ ዘንድ አኑሮታል፡፤ በዚያም ቦታ ብዙ ተአምራትን አድርጓል መጻሕፍትንም ጽፏል፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም በትውፊት እንደሚታወቀው ምንኩስናን በገቢር ገለጣት እንጂ ሥርዓተ ምንኩስናን መፈጸሙን በግልጽ የሚመለክት ማስረጃ አልተገኘም፡፡ እንዲያውም በሶርያውያን ክርስቲያኖች የሚዘወተረውን ራስን በአንድ ስፍራ ወስኖ በብሕትውናና በመምህርነት ቤተክርስቲያንን የማገልገል (Proto-monasticism) ሕይወት ይኖር እንደነበር ይታመናል፡፡ በትውፊት ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስን ለመጎብኘት ወደ ቀጰዶቅያ እንዲሁም አባ ቢሾይን ለመጎብኘት ወደ ግብጽ እንደተጓዘ የሚነገረውም ከዚህ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ፍጹም በሆነ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቱ ምሳሌ በሚሆነው ትምህርቱና የምናንኔ ሕይወቱ የሚታወቀው ቅዱስ ኤፍሬም ሐምሌ አስራ አምስት ቀን በ 370 ዓ.ም አርፏል፡፡በዚህ ሁሉ ትጋቱም ሶርያውያን ክርስቲያኖች ‹ጥዑመ ልሳን›፣ ‹መምህረ ዓለም›፣ ‹ዓምደ ቤተ ክርስቲያን› በማለት ይጠሩታል፣ያወድሱታል፣ያመሰግኑታል፡፡የቅዱስ አባታችን ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡ አሜን!

የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች
ቅዱስ ኤፍሬም እንደሌሎች የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው በርካታ ትምህርቶችንና መጻሕፍትን የጻፈና ያዘጋጃ አባት ነው፡፡ ይህንንም ስንክሳር እንዲህ ይገጸዋል፡፡

እጅግም ብዙ የሆኑ 14 ሺህ ድርሳናትንና ተግሳጻትን ደረሰ፤ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ውዳሴዋን ነው፡፡ ‹አቤቱ የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ ‘ እስከሚል ድረስ ድርሳናትን ደርሶአል፡፡ (ስንክሳር ዘሐምሌ 15 ተመልከት)
በአሁኑ ዘመን የቅዱስ ኤፍሬም መጻሕፍትና ትምህርቶች እንደሌሎቹ የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው ሥራዎች ጎልተው የታወቁ አይደሉም፡፡ ለዚህም ምክንያቶቹ ሁለት ናቸው፡፡
1. ቅዱስ ኤፍሬም አብዛኛዎቹን ትምህርቶችና መጻሕፍትን ያዘጋጀው በዘመኑ ብዙ ተጽእኖ በነበራቸው በግሪክ ወይም በላቲን ቋንቋዎች ሳይሆን በሱርስት በመሆኑ ነው፡፡ አንዳንድ ሊቃውንት ይህን እውነት እንደ መልካም ነገር ይጠቅሱታል፡፡ ወንጌል በግሪክ ከመጻፏ በፊት የተሰበከችው በሱርስት ነው( ጌታም ያስተማረው በዚሁ ቋንቋ ነው በማለት ይህም የሶርያ ክርስትና በግሪካዊው ፍልስፍና ያልተጠቃ (Little Hellenized) እንዲሆን ያደረገ ነው በማለት እንደመልካም ነገር ይጠቅሱታል።
 
2. ቅዱስ ኤፍሬም ትምህርተ ክርስትናን ከሌሎች አበው ለየት ባለ መልኩ በጥበባዊ ስልት (በግጥም፣በቅኔ፣በደብዳቤ፣በጥያቄና መልስ) በማዘጋጀቱና አብዛኞቻችን በዚህ ስልት ጠንከር ያለ ትምህርተ ክርስትና ይገኛል ብለን ስላላመንን ወይም ዝንባሌው ስለሌለን ነው፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዚህ ዘመን በርካታ መጻሕፍት የቅዱስ ኤፍሬም ናቸው እየተባሉ ሲሰራጩ እናስተውላለን። አብዛኛዎች ግን የእርሱ አይደሉም ፤በተለይ የመጀመሪያ ጽሕፈተ ቋንቋቸው ግሪክ የሆኑት።ስለዚህ መጻሕፍቱን ከመጠቀማችን በፊት የቅዱስ ኤፍሬም ድርሰቶች መሆናቸውን ማወቅ ይገባል፡፡
የቅዱስ ኤፍሬም የጽሑፍ ሥራዎች
እነዚህን ጽሑፎች ጠቅለል አድርጎ በአራት መክፈል ይቻላል፦
1. ቀጥተኛ ትርጓሜያት፡- ይህ ክፍል ከመጽሐፍ ቅዱስ አንዱን መጽሐፍ በመውሰድ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያጠቃልል ነው፡፡ ምሳሌ – የኦሪት ዘፍጥረት፣ የኦሪት ዘፀአትና የግብረ ሐዋርያት ትርጓሜያትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
2. ጥበበባዊ (Artistic) ትምህርቶች (ትርጓሜያት)፦ በግጥም ወይም በሌላ ጥበባዊ መልክ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያካትት ነው፡፡ ‹በእንተ ክርስቶስ› (በጥያቄና መልስ የቀረበው) ትምህርት ተጠቃሽ ነው፡፡ እንዲሁም ‹በነገረ ምጽአት ላይ ለፑከሊየስ የተጻፈው ደብዳቤም፡፡›
3. በቁጥር የተደረጉ ስብከቶች (Verse homilies)፦ አንድን ርዕስ በማንሳት የተሰጡ ስብከቶችን የምናገኝበት ክፍል ነው፡፡ ‹በእንተ እምነት› የተሰኘው ስብከቱ ተጠቃሽ ነው፡፡
4. የዜማ ወይም የቅዳሴ ድርሰቶች፡፡
ቅዱስ ኤፍሬምና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን
የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያዘጋጀቻቸውን አብዛኛዎችን የትርጓሜ መጻሕፍት ያጠኑ ሊቃውንት መጻሕፍቱ የኤዴሳ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት የትርጓሜ ስልትና የምስጢር ፤ የዘይቤ አንድነት እንደሚስተዋልባቸው ያስረዳሉ፡፡ ከዚያ ውጪ በውዳሴ ማርያምና በአንቀፀ ብርሃን መካከል ያለው የአንድነት ጉዳይ ከትርጓሜ መጻሕፍት ወደ ጸሎት መጻሕፍትም ሊራመድ እንደሚችል ያስገነዝባል፡፡ ለዚህ ሃሣብ መቋጫ የስርግው ሐብለ ሥላሴን ንግግር እናቅርብ፡-
‹ኤፍሬም (ሶርያዊ)› የሶርያ ተወላጅ እርሱ የደረሳቸው መጻሕፍት ወደ ግእዝ ብዙዎቹ ተመልሰዋል፡፡ በተለይ ውዳሴ ማርያም በየዕለቱ በሕዝበ ክርስቲያን የሚጸለይ ጸሎት ነው፡፡
በመጽሐፈ አክሱም እርሱና አባ ሕርያቆስ የተባለው ቅዳሴ ማርያም የደረሰው ወደ አክሱም መጥተው ማይ ከርዋህ በሚባል ስፍራ ተገናኝተው ኤፍሬም ያሬድን ውዳሴ ማርያምን ሕርያቆስን ደግሞ ቅዳሴዋን እንዳስተማረው በሰያፍ መንገድ ይገለጻል፡፡ እዚህ ላይ ዋናው ቁም ነገር ቅዱስ ያሬድ በስድ ንባብም ሆነ በግጥም መልክ የደረሳቸው ድርሰቶች የሶሪያ ቤተክርስቲያን ባህል የተከተሉ መሆናቸውና የሶርያ ቤተክርስቲያን ለኢትዮጵያ መንፈሳዊ እድገት ከፍ ያለ አስተዋጽዖ እንዳደረገች የሚያሳይ ነው፡፡
  (አማርኛና የቤተ ክርስቲያን መዝገበ ቃላት ረቂቅ ኤፍሬም የሚለውን ተመልከት)፡፡
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ይቆየን !

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም

ዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የረጅም ዘመን ሐዋርያዊ ጉዞ ላይ በጎ ተፅዕኖ ካላቸው የአራተኛው መ/ክ/ዘመን አባቶች መካከል አንዱ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ይህ አባት ምንም እንኳን በቋንቋ ውሱንነትና በቦታ ርቀት በርካቶች ሥራዎቹና ጽሑፎቹ የታወቁለት ባይሆንም ሕይወቱን በብሕትውና የመራ የትርጓሜ መጻሕፍትን ፣የቅኔ፣ የግጥምና የወግ ጽሑፍ በማዘጋጀት የኖረ ባለ በጎ ገድል አባት ነው፡፡

የቅዱስ ኤፍሬምን ሥራዎች በማሰባሰብ በመጽሐፍ መልክ ካወጡ ሰዎች አንዱ የሆነው (ዶ/ር ሰባስትያን ብሮክ) ’the Luminous Eye’’ በሚል ርዕስ ካዘጋጀው መጻሕፍ  ውስጥ ጎላ ጎላ ያሉትን ትምህርቶች እየተረጎምን ልናቀርብ ወደድን፡፡ ይህም ክፍል አንድ መግቢያ ሆኖ የቅዱስ ኤፍሬምን ሕይወትና ሥራዎች በአጭሩ የሚቀርብበት ነው፡፡

የቅዱስ ኤፍሬም ሕይወቱ

የቅዱስ ኤፍሬም ሀገረ ውላዱ ከዋክብትን ከሚያመልኩ ሰዎች መካከል ነው፡፡ አባቱም ክርስትናን የሚጠላ ካህነ ጣዖት ነበር፡፡ አንዳንድ ምንጮች ከቅዱስ ኤፍሬም ሕይወት በመነሳት ወላጆቹ ክርስቲያኖች እንደነበሩ ዘግበዋል፡፡ የሐምሌ አስራ አምስት ስንክሳር ግን የአባቱን ካህነ ጣዖትነት ያረጋግጣል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም የተወለደው  በ306 ዓ.ም ገደማ “በሜሶፖታሚያ” ውስጥ በምትገኝ “ንጽቢን” እንደሆነ ይታመናል።(ንጽቢን   በደቡባዊ ቱርክ እና በምዕራባዊ ሶርያ መካከል የምትገኝ ቦታ ናት፡፡) ይህቺም ቦታ ከ318ቱ ሊቃውንት አንዱ የነበረው የቅዱስ ያዕቆብ ሀገረ ሰብከቱ የነበረች ናት፡፡

ይህንን ታላቅ አባታችንን የእግዚአብሔር መንፈስ አመላክቶት ወደ ቅዱስ ያዕቆብ ሄዶ ትምህርተ ክርስትናን ተምሮ የተጠመቀ ሲሆን ከወላጆቹ ጋር የኖረው እስከ አሥር ዓመቱ ብቻ ነው፡፡ በትምህርተ ክርስትና አምኖ ከተጠመቀ በኋላ ግን በቅዱስ ያዕቆብ ዘንድ በብሕትውና ተወስኖ በመማርና በማስተማር በንጽቢን ለሚገኘው መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ሓላፊ እስክመሆን ደርሶ ነበር፡፡

በ393 ዓ.ም የንጽቢን ከተማ  በወራሪዎች እጅ ስትወድቅ ቅዱስ ኤፍሬም ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር በመሆን የሮም ግዛት ወደነበረችው ኤዴሳ (ታናሽ እስያ፣ዑር) ተሰደደ፡፡ ይህቸ ቦታ ቅዱስ ኤፍሬም ከመናፍቃን ጋር የተጋደለባት፣ በቤተክርስቲያን ትምህርት ላይ ያላቸውን አብዛኞቹን የክህደት ትምህርቶች የሞገተባትና  መጻሕፍቱን ያዘጋጀባት ናት፡፡አብዛኛዎቹን ትምህርቶቹንና መጻሕፍቱን ያዘጋጀው በዚች በኤዴሳ በሚገኘው ትምህርት ቤት ነው፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከቅዱስ ያዕቆብ ጋር በመሆን በአርዮስ ምክንያት በተካሄደው  የኒቅያው ጉባኤ    ( 325 ዓ.ም ) ላይ ተገኝቷል፡፡ በዚህም የአርዮስን ክህደትና ምክንያተ ውግዘት ተገንዝቧል፡፡

ከኒቅያ ጉባኤ መልስ መንፈሰ እግዚአብሔር በራዕይ በገለፀለት መሠረት ቅዱስ ኤፍሬም ከቅዱስ ባስልዮስ (ቁጥሩ ከ318ቱ ሊቃውንት ወገን ነው) ዘንድ ለመገናኘት ወደ ቂሣርያ ሄዷል፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም የዲቁና ክህነት ሠጥቶ ከሀገረ ስብከቱ ከፍሎ እንዲያስተምር ወስኖ በእርሱ ዘንድ አኑሮታል፡፤ በዚያም ቦታ ብዙ ተአምራትን አድርጓል( መጻሕፍትንም ጽፏል፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም በትውፊት እንደሚታወቀው ምንኩስናን በገቢር ገለጣት እንጂ ሥርዓተ ምንኩስናን መፈጸሙን በግልጽ የሚመለክት ማስረጃ አልተገኘም፡፡ እንዲያውም በሶርያውያን ክርስቲያኖች የሚዘወተረውን ራስን በአንድ ስፍራ ወስኖ በብሕትውናና በመምህርነት ቤተክርስቲያንን የማገልገል (Proto-monasticism) ሕይወት ይኖር እንደነበር ይታመናል፡፡ በትውፊት ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስን ለመጎብኘት ወደ ቀጰዶቅያ እንዲሁም አባ ቢሾይን ለመጎብኘት ወደ ግብጽ እንደተጓዘ የሚነገረውም ከዚህ ጋር በተያያዘ ነው፡፡

ፍጹም በሆነ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቱ ምሳሌ በሚሆነው ትምህርቱና የምናንኔ ሕይወቱ የሚታወቀው ቅዱስ ኤፍሬም ሐምሌ አስራ አምስት ቀን በ 370 ዓ.ም አርፏል፡፡በዚህ ሁሉ ትጋቱም ሶርያውያን ክርስቲያኖች ‹ጥዑመ ልሳን›፣ ‹መምህረ ዓለም›፣ ‹ዓምደ ቤተ ክርስቲያን› በማለት ይጠሩታል፣ያወድሱታል፣ያመሰግኑታል፡፡የቅዱስ አባታችን ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡ አሜን!

የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች

ቅዱስ ኤፍሬም እንደሌሎች የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው በርካታ ትምህርቶችንና መጻሕፍትን የጻፈና ያዘጋጃ አባት ነው፡፡ ይህንንም ስንክሳር እንዲህ ይገጸዋል፡፡

እጅግም ብዙ የሆኑ 14 ሺህ ድርሳናትንና ተግሳጻትን ደረሰ፤ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ውዳሴዋን ነው፡፡ ‹አቤቱ የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ ‘ እስከሚል ድረስ ድርሳናትን ደርሶአል፡፡ (ስንክሳር ዘሐምሌ 15 ተመልከት)

በአሁኑ ዘመን የቅዱስ ኤፍሬም መጻሕፍትና ትምህርቶች እንደሌሎቹ የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው ሥራዎች ጎልተው የታወቁ አይደሉም፡፡ ለዚህም ምክንያቶቹ ሁለት ናቸው፡፡

1. ቅዱስ ኤፍሬም አብዛኛዎቹን ትምህርቶችና መጻሕፍትን ያዘጋጀው በዘመኑ ብዙ ተጽእኖ በነበራቸው በግሪክ ወይም በላቲን ቋንቋዎች ሳይሆን በሱርስት በመሆኑ ነው፡፡ አንዳንድ ሊቃውንት ይህን እውነት እንደ መልካም ነገር ይጠቅሱታል፡፡ ወንጌል በግሪክ ከመጻፏ በፊት የተሰበከችው በሱርስት ነው( ጌታም ያስተማረው በዚሁ ቋንቋ ነው በማለት ይህም የሶርያ ክርስትና በግሪካዊው ፍልስፍና ያልተጠቃ (Little Hellenized) እንዲሆን ያደረገ ነው በማለት እንደመልካም ነገር ይጠቅሱታል። 

2. ቅዱስ ኤፍሬም ትምህርተ ክርስትናን ከሌሎች አበው ለየት ባለ መልኩ በጥበባዊ ስልት (በግጥም፣በቅኔ፣በደብዳቤ፣በጥያቄና መልስ) በማዘጋጀቱና አብዛኞቻችን በዚህ ስልት ጠንከር ያለ ትምህርተ ክርስትና ይገኛል ብለን ስላላመንን ወይም ዝንባሌው ስለሌለን ነው፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዚህ ዘመን በርካታ መጻሕፍት የቅዱስ ኤፍሬም ናቸው እየተባሉ ሲሰራጩ እናስተውላለን። አብዛኛዎች ግን የእርሱ አይደሉም ፤በተለይ የመጀመሪያ ጽሕፈተ ቋንቋቸው ግሪክ የሆኑት።ስለዚህ መጻሕፍቱን ከመጠቀማችን በፊት የቅዱስ ኤፍሬም ድርሰቶች መሆናቸውን ማወቅ ይገባል፡፡

የቅዱስ ኤፍሬም የጽሑፍ ሥራዎች

እነዚህን ጽሑፎች ጠቅለል አድርጎ በአራት መክፈል ይቻላል፦
1. ቀጥተኛ ትርጓሜያት፡- ይህ ክፍል ከመጽሐፍ ቅዱስ አንዱን መጽሐፍ በመውሰድ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያጠቃልል ነው፡፡ ምሳሌ – የኦሪት ዘፍጥረት፣ የኦሪት ዘፀአትና የግብረ ሐዋርያት ትርጓሜያትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
2. ጥበበባዊ (Artistic) ትምህርቶች (ትርጓሜያት)፦ በግጥም ወይም በሌላ ጥበባዊ መልክ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያካትት ነው፡፡ ‹በእንተ ክርስቶስ› (በጥያቄና መልስ የቀረበው) ትምህርት ተጠቃሽ ነው፡፡ እንዲሁም ‹በነገረ ምጽአት ላይ ለፑከሊየስ የተጻፈው ደብዳቤም፡፡›
3. በቁጥር የተደረጉ ስብከቶች (Verse homilies)፦ አንድን ርዕስ በማንሳት የተሰጡ ስብከቶችን የምናገኝበት ክፍል ነው፡፡ ‹በእንተ እምነት› የተሰኘው ስብከቱ ተጠቃሽ ነው፡፡
4. የዜማ ወይም የቅዳሴ ድርሰቶች፡፡

ቅዱስ ኤፍሬምና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያዘጋጀቻቸውን አብዛኛዎችን የትርጓሜ መጻሕፍት ያጠኑ ሊቃውንት መጻሕፍቱ የኤዴሳ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት የትርጓሜ ስልትና የምስጢር ፤ የዘይቤ አንድነት እንደሚስተዋልባቸው ያስረዳሉ፡፡ ከዚያ ውጪ በውዳሴ ማርያምና በአንቀፀ ብርሃን መካከል ያለው የአንድነት ጉዳይ ከትርጓሜ መጻሕፍት ወደ ጸሎት መጻሕፍትም ሊራመድ እንደሚችል ያስገነዝባል፡፡ ለዚህ ሃሣብ መቋጫ የስርግው ሐብለ ሥላሴን ንግግር እናቅርብ፡-

‹ኤፍሬም (ሶርያዊ)› የሶርያ ተወላጅ እርሱ የደረሳቸው መጻሕፍት ወደ ግእዝ ብዙዎቹ ተመልሰዋል፡፡ በተለይ ውዳሴ ማርያም በየዕለቱ በሕዝበ ክርስቲያን የሚጸለይ ጸሎት ነው፡፡

በመጽሐፈ አክሱም እርሱና አባ ሕርያቆስ የተባለው ቅዳሴ ማርያም የደረሰው ወደ አክሱም መጥተው ማይ ከርዋህ በሚባል ስፍራ ተገናኝተው ኤፍሬም ያሬድን ውዳሴ ማርያምን ሕርያቆስን ደግሞ ቅዳሴዋን እንዳስተማረው በሰያፍ መንገድ ይገለጻል፡፡ እዚህ ላይ ዋናው ቁም ነገር ቅዱስ ያሬድ በስድ ንባብም ሆነ በግጥም መልክ የደረሳቸው ድርሰቶች የሶሪያ ቤተክርስቲያን ባህል የተከተሉ መሆናቸውና የሶርያ ቤተክርስቲያን ለኢትዮጵያ መንፈሳዊ እድገት ከፍ ያለ አስተዋጽዖ እንዳደረገች የሚያሳይ ነው፡፡ (አማርኛና የቤተ ክርስቲያን መዝገበ ቃላት ረቂቅ ኤፍሬም የሚለውን ተመልከት)፡፡

ይቆየን !

 

የቤተክርስቲያን ፈተና እና ምዕመናን

በዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

መግቢያ

የቤተክርስቲያን ታሪክ የሚጀምረው ከዓለመ መላእክት ነው፡፡ ታዲያ ፈተና ሁሌ አብሯት የሚኖር ቤተክርስቲያን መፈተን የጀመረችው በዚሁ በዓለመ መላእክት ነበር፡፡ ዲያብሎስ ትዕቢትንና ሐሰት ከራሱ አንቅቶ መላእክትን «እኔ ፈጠርኋችሁ» በማለት ባሰማው የሐሰት አዋጅ ከሰው ልጅ ወደዚህ ምድር መምጣት ጀምሮ በብሉይ ኪዳንም በርካታ ፈተናዎች ተፈራርቀዋል፡፡

በብሉይ ኪዳን በብዙ ኅብረ ምሳሌ ከአቤል እስከ ክርስቶስ ምጽዓት ስትታሰብ የመጣች ቤተክርስቲያን በሐዲስ ኪዳን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ለማዳን በመጣ ጊዜ በአማናዊ ደሙ አጽንቶ አካለ ክርስቶስ አድርጓታል፡፡ /ኤፌ 1፥23/ ቤተክርስቲያን ለሰው ዘር ሁሉ በሰማይ ያለውን የእግዚአብሔርን መንግሥት የምታስተምር ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝበትና ወደ ሰማያዊው ርስትም የምትመራ የጽድቅ መንገድ ናት፡፡ መቼም ቢሆን ደግ ነገር ሁሉ የሚገጥመው ፈተና አይጠፋምና ቤተክርስቲያን ጉዞዋ ሁሉ በፈተና የታጠረ ነው፡፡

በዚህች አጭር ጽሑፍ ቤተክርስቲያን ፈተና በሚያጋጥማት ወቅት ምእመናን ምን ዓይነት ኑሮ መኖር፤ ምን ዓይነት አቋም መያዝ እንዳለባቸው ለማየት እንሞክራለን፡፡ ካሰብነው ለመድረስም ዋና ዋና የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጮችንና ያስከተሏቸውን ጉዳቶች ለማንሳት እንጀምራለን፡፡
1.    ዋና ዋና የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጮች
የቤተክርስቲያንን ታሪክ ስናጠና ለቤተክርስቲያን የመፈተን ምክንያት የሚሆኑ አካላትንና ድርጊቶችን ቆጥሮና ወስኖ ማስቀመጥ ወይም መገደብ ባይቻልም ጐልተው የሚታዩትን መዘርዘር ግን ይቻላል፡፡ ከእነዚህ የፈተና ምንጮች ዋነኞቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡
1.1 መናፍቃን
«የቤተክርስቲያን የውስጥ ጠላቶች በጌታ አነጋገር «ጸራዊ» በሐዋርያት አነጋገር «ቢጽ ሐሳውያን» በሊቃውንት አነጋገር «መናፍቃን» ይባላሉ፡፡ የቤተክርስቲያን ልጆች ሳይሆኑ የቤተክርስቲያን ልጆች መስለው ወይም ከቤተክርስቲያን እምነትና ትምህርት የተወሰነውን የተማሩ ፤የተወሰነውንም ተምረው ያልያዙ ጐደሎዎች ናቸው፡፡ እነርሱም እንክርዳድ ስንዴ መስሎ እንደሚያድግ በክርስቶስ ዐጸደ ወይን በቤተክርስቲያን ውስጥ የበቀሉ አሳሳቾች ናቸው፡፡ » /የቤተክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ ገጽ 48/
ብፁዕ አባታችን ከላይ እንደገለጹት እነዚህ ወገኖች ስልታቸውን በየስፍራውና በየዘመኑ እየለዋወጡ ሐመረ ኖኅ ቤተክርስቲያንን በምንፍቅና ማዕበላቸው እያንገላቷትና እያማቷት ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ወዳልተሰበኩት ሕዝብ ደርሳ ትምህርቷን እንዳታስተምር ልዩ  ልዩ የክህደት ትምህርት በመፍጠር አባቶችን ሥራ ያስፈቱ ናቸው፡፡ይልቁንም በአሁኑ ዘመን በክህደት ትምህርታቸው ብቻ ሳይቆጠቡ ቤተክርስቲያን ላይ ሁሉን አቀፍ ዘመቻ የከፈቱበት ወቅት ነው፡፡ የተቸገሩ ምእመናንን የዕለት ጉርስ የዓመት ልብስ እንሰጣለን በማለት፣ የቤተክርስቲያኒቱን የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማት እንረዳለን በማለት፣ እንዲሁም ለሆዳቸው ያደሩ ሰዎችን በመጠቀም የቤተክርስቲያን ዋነኛ የፈተና ምንጭ ሆነው ቀጥለዋል፡፡
1.2 አላውያን ነገሥታት
በቤተክርስቲያን ታሪክ ከጌታ ትንሣኤ እስከ 70 ዓ.ም ድረስ ያለው ዘመን ዘመነ ሐዋርያት ከ70 ዓ.ም እስከ 160 ዓ.ም ያለው ደግሞ ዘመነ ሐዋርያነ አበው እንዲሁም ከ16ዐ ዓ.ም እስከ 312 ዓ.ም ያለው ዘመነ ሰማዕታት  በመባል ይታወቃል፡፡
በመጀመሪያዎቹ ሁለት ክፍላተ ዘመናት የነበረው የቤተክርስቲያን አገልግሎት ከአይሁድ ጋር የተደረገ ተጋድሎ ነው፡፡ ይኸውም ምንም እንኳን የአይሁድ ማኅበረሰብ ቃል ኪዳን የተገባለት፣ ትንቢት የተነገረለት፣ በአንድ አምላክ አማኝ ቢሆንም የክርስቶስን አዳኝነትና አምላክነት ላለመቀበል በአመጽ በመግፋቱ፣ እነርሱን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመመለስና ለማቅረብ የተደረገ ጥረት ነበር፡፡
ሦስተኛው ክፍል ግን ቅዱሳን አበው ከአላውያን ነገሥታት ጋር ባደረጉት ተጋድሎ የሚዘከር ዘመነ ሰማዕታት ነው፡፡ በክርስትና ሃይማኖት ትምህርትና በመምህራኑ አማናዊ ምሳሌነት በመላው ሮም የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፍቶ ነበር፡፡ በመሆኑም ለባሮች የነጻነት ትምህርት የተሰበከላቸው ሲሆን ባለጸጋዎችም ቢያምኑ የክርስቶስ አገልጋዮች ለመሆን እንደሚበቁ ተነገራቸው፡፡ /1ቆሮ 7፥22/  የአሕዛብን የቀደመ ትዕቢትና ኩራት የእግዚአብሔር ቃል  ሲያፈራርሰው፤ የአሕዛብን የአመንዝራነት ሕይወት የክርስቲያኖች ቅድሰና አሸነፈው፡፡ በአሕዛብ ልማድ በወንዶች መካከል ሴቶች የክብር ቦታ ያልነበራቸው ሲሆን በክርስትና እኩልነትና መከባበር ታወጀ፡፡
ከዚህ በኋላ ግን ክፉዎች በክርስቲያኖች ላይ የሰውን ሥጋ ይበላሉ፤ ለቄሳር አይታዘዙም፤ ግብር አይከፍሉም፤ የሚሉ ተራና ክፉ ወሬዎችን አወሩ ፡፡ በዚህ የተነሳ እንደነ ዲዮቅልጥያኖስ ያሉ ኢአማኒያን/ከሃድያን/ ነገሥታት ስልጣናቸውን መከታ አድርገው ብዙ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት እንዲያልፉ ያደረጉበት እኩይ ተግባር ፈጸሙ፡፡ ይህም ደጉ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ መንበረ ሥልጣኑን ይዞ ለክርስቲያኖች ሠላም እስኪያወርድላቸው ድረስ የቀጠለ ጉዳይ ነበር፡፡
ቤተክርስቲያን ለምድራዊ ኑሮ ሲባል በተለያየ ሥርዓተ መንግሥት ሥር የሚኖሩ ሰዎችን ነው በሥርዓቷና እና በትውፊቷ እንዲኖሩ የምትጥረው፤ የእርሷ ድርጊት ሁሉ ከአመራራቸው ጋር የማይሄድ የሚመስላቸው ሁሉ እንደየዘመናቸው ሁኔታ መከራን አጽንተውባቸዋል፡፡ ይህም የሁል ጊዜ የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጭ ሆኖ የቀጠለ ጉዳይ ነው፡፡

1.3 የአባቶች አለመግባባት /በአባቶች መካከል አለመግባባት መከሰት/
«የክርስቶስ ፍቅር ገብቷቸው ክርስትናንና ከዚያ የሚከተሉትን ኃላፊነቶችን፣ ክህነትን እስከ ጵጵስና ድረስ «አውቃለሁ፤ እበቃለሁ» ብለው ወይም « ይገባኛል» ብለው ሹመት ፈልገውና ተካሰው ሳይሆን «እኛ አንበቃም ተውን» እያሉ፣ ነገር ግን ለመንጋው የግድ መሪ ስለሚያስፈልገው «እናንተ ለዚህ ሓላፊነት ትበቃላችሁ መንጋውን ጠብቁ» እየተባሉ አደራ ሲጣልባቸው የተሰጣቸውን ከባድ ሓላፊነት የሚጠይቀውን ዋጋ ሁሉ በመክፈል የተወጡ ብዙ ቅዱሳን አባቶች ቤተክርስቲያናችን አሏት፡፡

«በተቃራኒው ደግሞ እነዚህን ሓላፊነቶች ለራሳቸው ግላዊ ክብርና ዝና መጠቀሚያ በማድረግ የክርስቶስን ክብርና በደሙ የዋጃትን ቤተክርስቲያንን ደኅንነትና ዕድገት ሳይሆን የራሳቸውን ምድራዊና ጊዜያዊ ፍላጐት ማስፈጸሚያ መሣሪያ ያደረጉትም ብዙዎች እንደነበሩ የቤተክርስቲያን ታሪክ መስታወት ሆኖ ያሳየናል» /ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱና ትምህርቱ ገጽ 7/
ከዚህ በተጨማሪ አንዳንድ ጊዜ በአሠራርና በአመራር ምክንያት በአባቶች መካከል አለመግባባት ይፈጠራል፡፡ የአባቶች አንድነት የቤተክርስቲያን የአንድነቷ መገለጫ ነው፡፡ ይህ አንድነት በአንድም ይሁን በሌላ ምክንያት ችግር ከገጠመው የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጭ ሆኖ መቀጠሉ አይቀርም፤ ይህም በተለይ ለውጭ ጠላቶች በራችንን ወለል አድርጐ የሚከፍትላቸው ነው፡፡
1.4 የምእመናን መንፈሳዊ ሕይወት መዳከም
የክርስትና ሕይወት በየጊዜው በመጠን እየተለካ የሚያድግ ሕንጻ እግዚአብሔር ነው፡፡ ክርስትና በቤተክርስቲያን መሠረተ እምነት /ዶግማ/ በማመን በክርስቶስ ሕግና ሥርዓት መመራትና መኖር ነው፡፡
ምእመናን የቤተክርስቲያንን ድምጽ አልሰማ ብለው ሕይወታቸውን በቃለ እግዚአብሔር ከመምራት ይልቅ በሥጋዊ ፈቃድ ስሜት መመራት ከጀመሩ የቤተክርስቲያን ትልቁ አደጋዋ ነው፡፡ ይህ በሆነ ጊዜ በአባቶችና በምእመናን መካከል መደማመጥ አይኖርም፡፡ በዚህ ወቅት እግዚአብሔር ጸጋውን ይነሳል፤ የምእመናን ማኅበርም በክፉ ይታወካል፡፡
1.5 የግል ጥቅም አጋባሽ የሆኑ ግለሰቦች
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድ ወቅት ይከተሉት ለነበሩት ሰዎች አንድ መሠረታዊ ጥያቄ ጠይቋቸው ነበር፡፡ «ምን ልታዩ መጥታችኋል» /ማቴ 11፥7-1ዐ/ ምንም እንኳን  ጌታ የጠየቀው ስለ ዮሐንስ ቢሆንም እርሱን ስለመከተላቸውም የሚያመለክት ነው፡፡ በመጽሐፍ እንደምናነበው ጌታን ይከተል የነበረው ሕዝብ ሁሉ ትክክለኛና አንድ ዓላማ ብቻ የነበረው አልነበረም፡፡ ይከተሉት የነበሩትን ሰዎች በሦስት ዋና ዋና  ክፍል መመደብ ይቻላል፡፡
ሀ. ሕብስት አበርክቶ ያበላ ስለነበር ጊዜያዊ እንጀራ ለመብላት ለሆዳቸው የሚከተሉት ነበሩ
ለ. የማስተማር ጥበቡን፣ እውቀቱን ለማድነቅ እንዲሁም ዓለምን ሊያድን የመጣ ንጉሥ ምን ዓይነት እነደሚመስል መልኩን ለማየት የሚከተሉት ነበሩ
ሐ. ድውያንን ሲፈውስ ለምጻሞችን ሲያነጻ ሙታንን ሲያነሳ አይተው ከደዌ ሥጋ ብቻ ለመፈወስ የሚከተሉት ነበሩ፡፡
መ.ድውያንን ፈወሰ ለምጻሞችን አነጻ ሙታንን አነሳ እንዲሁም ከተለያዩ ሀጢአትን ከሚሠሩ ጋር ይውላል ያድራል በማለት ለክስ የሚከተሉትም ነበሩ።
እነዚህ ሁሉ ግን የጌታችን የእግር መንገድ ሥራዎች ምድራዊ ሀብት እንጅ ዋነኛ ዓላማዎች አልነበሩም፡፡ የቃሉን ትምህርት ሰምተው ተአምራቱን አይተው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣው ለአድኅኖተ ዓለምና ለእኛ አርዓያ ምሳሌ ሊሆን በመሆኑ ከአምስቱ ገበያ ሕዝብ ግን ይህን ተረድተው የተገኙት መቶ ሃያው ቤተሰብ ብቻ ናቸው፡፡
በቤተክርስቲያን ጉዞ ውስጥ እስከ ዛሬም ድረስ ለሥጋዊ ጥቅማቸው ፤ ወይም አድናቂና አጨብጫቢ ሆነው ብቻ ቤተክርስቲያን ላይ እንደ ክፉ ተባይ የተጣበቁ ግለሰቦች ነበሩ፤ አሉ፡፡ እነዚህ በቤተክርስቲያን አገልግሎት ፍላጐታቸው ሥጋዊ ጥቅማቸው ማጋበስ ብቻ ስለሆነ ከእነርሱ ጋር የማይስማማ አባት፣ ካህን፣ ዲያቆን፣ ምእመን እንዲኖር አይፈልጉም፡፡ ለዚህም ሲሉ የማያሴሩት የክፋት ሴራ ባለመኖሩ ለቤተክርስቲየን አገልግሎት ነቀርሳዎች ሆነዋል፡፡
2.    ፈተናዎች በቤተክርስቲያን ላይ ምን አደረሱ?
በቤተክርስቲያናችን በመናፍቃን፣ በአላውያን ነገስታት፣ በጥቅም አጋባሽ ግለሰቦችና በመሳሰሉት የደረሰባት በደል በዚች አጭር ጽሑፍ ዳስሶ መጨረስ ከንቱ ድካም ይሆናል፡፡ ዋና ዋናዎችን ማንሳት ግን ግድ ነው፡፡
2.1 ቤተክርስቲያንን መከፋፈል፦
በሦስቱ ጉባኤያት /ኒቅያ  ቁስጥንጥንያና ኤፌሶን/ ዶግማዋን አጽንታ፣ ክፉዎችን ለይታ፣ ጥርት ያለውን እምነት ይዛ፣ አንድነቷን ጠብቃ የተጓዘችው አንዲት ዓለም አቀፋዊት ኦርቶዶክሳዊ ቤተክርስቲያን ዛሬ ላለችበት ሁኔታ የበቃችው እነ አርዮስ በጫሩት የምንፍቅን የክህደት እሳት ነው፡፡ዛሬ ክርስቲያን በሚለው መጠሪያ የሚታወቁ ቤተ እምነቶች በዓለም እንዲፈጠሩ የሆነው ከላይ በዘረዘርናቸው ምክንያቶች ነው፡፡
የሕንድ ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያንን የአሳዛኝ ታሪክ ምሳሌ ያደረጋት የመናፍቃን ደባ ነው፡፡ የሮም ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ከኦርቶዶክሳውያኑ ጐራ ተለይታ የኖረችው  እዚህ ግባ በማይባል ፖለቲካዊ / ምድራዊ ሥልጣን/ ምክንያት በተጀመረ ጠብ ነው፡፡
ዛሬ በእኛ ቤተክርስቲያን በአገር ውስጥ አባቶችና በውጭ በሚኖሩት መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ፍጹም ክርስቲያናዊ በሆነ አኳኋን በአጭር ጊዜ ውስጥ ካልተፈታና መፍትሔ ካልተገኘ እንደ ሕንድ ቤተክርስቲያን በእኛም በየአጥቢያው ላለመከፋፈልና ጥቁር ነጥብ ስላለመከሰቱ እርግጠኛ መሆን ይከብዳል፡፡
2.2  ምዕመናን ግራ ማጋባት
ቤተክርስቲያን በአባቶች አለመግባባትና በክህደት ትምህርት በምትፈተንበት ወቅት የሚከሰተው ትልቁ ስጋት /ክስተት/ የምዕመናን ግራ መጋባት ነው፡፡ ይህ ደግሞ እነርሱን ለመቀራመት አሰፍስፈው ለሚጠብቁ የቤተክርስቲያን ጠላቶች የመንጋውን በረት ወለል አድርጐ የሚከፍት ነው፡፡ ዛሬ በአሜሪካ ባለችው ቤተክርስቲያን ከሁለቱም ወገን አይደለንም፤ገለልተኛ ነን፤ግን ጳጳስ እንፈልጋን የሚሉ አብያተ ክርስቲያናትና ምዕመናን የዚህ  ምሳሌዎች ናቸው፡፡
2.3 ጽንፈኝነት፦
በክርስትና የሕይወት ጉዞ ውስጥ እጅግ አደገኛ ከሚባሉ በሽታዎች አንዱና ዋነኛው ጽንፈኝነት ነው፡፡ ያውም ደግሞ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ «በዚህ ዓለም ያሉ ነገሮች አፈጣጠራቸውና ሕይወታቸው ከተለያዩ ነገሮች ረቂቅና ድንቅ በሆነው ጥበብ መለኮታዊ ተመጥኖ የተዘጋጀ ነው፡፡ ይህ መጠን ሲናወጥ ግን ሕይወት አደጋ ላይ ይወድቃል፡፡» /ሐመረ ተዋሕዶ 2000 ዓ.ም ገጽ 12/
«ማዕከላዊ ደረጃ የሌላቸው ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህም እግዚአብሔርና ጣዖታት፤ እውነትና ሐሰት፤ ሕይወትና ሞት ፤መንግሥተ ሰማያትና ገሃነመ እሳት፤ ክርስትናና ከክርስትና ውጭ ያሉ እምነቶችና አስተሳሰቦች.. » /ሐመረ ተዋሕዶ 2000 ዓ.ም ገጽ 13 / እነዚህ በራሳቸው ብቻ ቀዋምያን ከሆኑ ነገሮች ውጪ ያሉትን ግን በመጠን፣ መያዝ መኖር ተገቢ ነው፡፡ «መጠን ማለት» አንተም ተው አንተም ተው» ዓይነት ጉዳይ ሳይሆን ሁሉንም ነገር በራሱ አግባብና በተገቢው መጠን ማድረግና ከዚያ አለማሳለፍ ሲሆን ጽንፈኝነት ደግሞ ከዚህ ከተገቢው ልክና መጠን ማለፍ ነው፡፡» /ሐመረ ተዋሕዶ 2000 ዓ.ም ገጽ 14/
አይሁድን ከክርስትና የለያቸው ክርስቶስ ምድራዊ መንግሥትን አልመሠረተም፤ አንቀበለውም የሚል ጽንፈኛ አስተሳሰብ ነው፡፡ ወደ ክርስትና የመጡትንም ከአሕዛብ ወገን ወደ ክርስትና ከመጡት ጋር ሲያጣላቸው የነበረው « ጥምቀት ያለ ግዝረት ዋጋ የላትም» የሚለው ጽንፈኛ አስተሳሰብ ነው፡፡
ዛሬ ብዙዎችን ከቤተክርስቲያን እየለየ ያለ ይህ የጽንፈኝነት አስተሳሰብ ነው፡፡ ሰባኪ እገሌ እንዲሰብክ ካለተፈቀደለት ጉባኤ አልመጣም፤ ዲያቆን እገሌ እንዲቀድስ ካልሆነ አላስቀድስም፤ እነ እገሌ ወጥተው’ እነ እገሊት ካልተመረጡ ይህንን ማኅበር አልፍልገውም፤ እዚህ  ሰንበት ት/ቤት አልደርስም፤ ብለው የቀሩ ሰዎች በጽንፈኝነት ቀሳፊ ቀስት የተወጉ ናቸው፡፡
ቤተክርስቲያን በተፈተነች ቁጥር አንዱን ጽንፈ ይዘው በማክረርና በመወጠር ከማኅበረ ምእመናን የተለዩትን ቆጥረን አንጨርስም፡፡
ምንተ ንግበር /ምን እናድርግ/?
«ሰውን ብትታገል ብትዋጋ ታሸንፈዋለህ ወይም ያሸንፍሃል ቤተክርስቲያንን ግን ለማሸነፍ አይቻልም ቤተክርስቱያን ሁል ጊዜ ትዋጋለች ተሸንፋ ግን አታውቅም ዲያብሎስ ዝናሩን አራገፈ ቀስቱን ጨረሰ፡፡ ቤተክርስቲያንን ግን አልጎዳትም» ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን በመጥቀስ የጻፉት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የቤተክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ በተሰኘው መጽሐፋቸው ነው / የቤ.ተ. ገጽ 48/። ፈተና የቤተክርስቲያን የመኖሯ መገለጫ እንደሆነ በጽሑፋችን መግቢያ ላይ ገልጸናል፡፡ ነገር ግን ቤተክርስቲያን ፈተና በሚገጥማት ወቅት በሚነሳው ማዕበል ተከፍተን ከመርከቧ ወደ ባሕር እንዳንወርድ ምን ማድረግ ይገባናል? ጥቂት ነጥቦችን እናነሳለን፡፡
3.1 መንፈሳዊ ሕይወትን መጠበቅና ማጽናት ነው
የ አበው አባቶቻችን የተጋድሎ ገድል ስናነብ የምንረዳው ምንም እንኳን ወጥ የሆነ መንፈሳዊ ሕይወት ቢኖራቸውም ከባድ ፈተና በገጠማቸው ጊዜያት ግን የበለጠ ይበረታሉ። በርካታ ቃል ኪዳናትን የተቀበሉት በርካታ መንፈሳዊ መጻሕፍትን የጻፉት የብዙ ጸጋ ባለቤት የሆኑት በፈተና ውስጥ ነው፡፡
የምንማረው ከአባቶቻችን ነውና ቤተክርስቲያን ፈተና ላይ በምትሆን ጊዜ በጋዜጣ በሚጻፈው፣ በድረገጽ በሚለቀቀው «እንዲህ ሆነ እንዲህ ተደረገ» ወሬ ተገፍቶ እርሱን ብቻ በማውራት የራስ ሕይወትን መዘንጋት አይገባም፡፡ የሚሰሙት ዜናዎች፤ የሚፈጸሙት ድርጊቶች የግል መንፈሳዊ ሕይወትን የመሸርሸር አቅማቸው በጣም ከፍተኛ ነው፡፡ ከእኛ የሚጠበቀው የቀደመ መንፈሳዊ ሕይወታችን መጠበቅ ማጽናት እግዚአብሔር አምላክ በፈተና ውስጥ ለቤተክርስቲያን በጐ የሆነውን ሁሉ እንዲያደርግ ጉዳዩን በጸሎት መያዝ መሆን አለበት፡፡
3.2 የቤተክርስቲያንን ድምፅ ብቻ መስማት
ቤተክርስቲያናችን መሠረተ እምነታዊ /ዶግማዊ/ በሆነ ችግር የተፈተነች እንደሆነ የቤተክርስቲያን ቋሚ ምስክር የሆኑ መጻሕፍትን፣ ትውፊተ አበውን፣ የቀድሞ የቤተክርስቲያን ድንጋጌዎችን መጠየቅ፣ ማንበብ በእርሱም ብቻ መመራት ተገቢ ነው፡፡
በአባቶች መካከል አለመግባባት ተፈጥሮ ቤተክርስቲያን በተፈተነች ጊዜ ከግጭቱ ተጠቃሚም ተጐጅም ያልሆኑ በአንድም በሌላም ያልወገኑ አባቶችን ድምፅ ብቻ መስማት ተገቢ ነው፡፡ እንዲሁም ስለ ርዕሰ ጉዳዩ የቀድሞ ሥርዓትና ትውፊት እንዲሁም ትምህርት ምንድን ነው? የሚለውን ማየት ተገቢ ነው፡፡
የትኛውም ወገን’ትውልድ ቢሆን የኃይል ሚዛኑ ስለመዘነለት ብቻ የሚያራግበውን ተቀብሎ በስሜት መነዳት አያስፈልግም፡፡ የቤተክርስቲያን ድምጽ ከቅዱሳት መጻሕፍት ከትውፊትና ከቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰማ ነው፡፡ እርሱን ብቻ መስማት ተገቢ ነው፡፡
3.3 ከጽንፍ ራስን መጠበቅ ነው::
በክርስትና ሕይወት የጽንፈኝነትን አደገኛነት ከላይ በጥቂቱ ለመግለጽ ሞክረናል፡፡ የአሁኑ ዘመን ምእመናን የባሕታዊ እገሌ ተከታይ፣ የአቡነ እገሌ ደጋፊ፣ የመምህር እንትና አድናቂ፣ የዘማሪ/ዘማሪት እገሌ ቡድን እየተባባልን መታየታችን የበሽታው ምልክት ነው፡፡ መጨረሻውም መከፋፈል ነው፡፡ አሁን በቅርቡ በተጠናቀቀው የቅዱስ ሲኖደስ ስብሰባ እንኳን ብዙዎቻችን ውሳኔዎችን እንመዝን የነበረው «ማን ምን ተናገረ? የትኛው ጐራ ተሸነፈ? ማን ምን ተደረገ?» በሚሉና በሚመስሉ መስፈርቶች እንጂ ውሳኔው ለቤተክርስቲያን ጠቃሚ ነው ወይስ ሌላ? የሚል አልነበረም፡፡
በእንዲህ አይነቱ ክስተት ማንም አሸናፊ ማንም ተሸናፊ የለም፡፡ ደግ ከተሰራ ቤተክርስቲያን አሸነፈች፤ አበራች፡፡ ሸፍጥ ከተሰራ ቤተክርስቲያን ተጐዳች፤ እውነታው ይሄ ነው፡፡
ከስሜት እንራቅ፤ ከጽንፈኝነት ራሳችንን እንጠብቅ፡፡ ወገንተኝነታችን ለቤተክርስቲያን ብቻ ይሁን፡፡ ያኔ የሰውም የእግዚአብሔርም ፍስሐ ይሆናል ፡፡ አምላከ ቅዱሳን ለዚያ ድል ያብቃን፡፡አሜን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በዓለም እያሉ ከዓለም ውጪ መኖር

በዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በበሳል ትምህርቱ በመንፈሳዊ ጥብዐቱና በፍጹም መንፈሳዊ ሕይወቱ በቤተ ክርስቲያናችን የታወቀ አባት ሲሆን ኑሮውም የብህትውና ነበር። ካስተማራቸው በርካታ ትምህርቶቹ መካከል ውስጥ አንድ ክርስቲያን በምድር ሲኖር ሰማያዊውን ሕይወት እንዲኖር ነው። ይህንንም ያስተማረበትን ትምህርት እንዲህ አቅርበነዋል፡፡

“እግዚአብሔር የሚወዳችሁ እግዚአብሔርን የምትወዱ ወንድሞቼ ሆይ እነሆ ሰማያውያን ሆነናል፡፡ ዘበሰማያት የሚያሰኝ ሥጋውንና ደሙን ተቀብለናል፡፡ እንዲህ ከሆነ ከዚህ ነገር የተነሣ እንፈራ ዘንድ እንንቀጠቀጥ ዘንድ ይገባናል፡፡ ሕሊናችንም ሰማያዊውን ማሰብ ትቶ ምድራዊውን ማሰብ እንዳይሆን መሆን ይገባናል፡፡ ሰማያዊነትን የሚወድ ሰው ምድራዊውን እንዳያስብ መሆን ይገባዋልና፡፡ ምድራዊውን ነገር ማሰብ ሰማያዊውን ነገር አለማሰብ ከክፉ ሕሊና ከክፉ ፈቃድ የሚገኝ ስለሆነ፡፡ በዚህ ዓለም እየኖርን እንደሌለን መሆን ይገባናል፡፡ ሰማያዊ አነዋወርን የሚወድ ሰው በዚህ ዓለም እየኖረ እንደሌለ መሆን ይገባዋልና፡፡ በዚህ እየኖሩ እንደሌሉ መሆን ለበጎ ሕሊና ከበጎ ፈቃድ የሚገኝ ስለሆነ፡፡”

ለአምላካችን ክብር ምስጋና ይግባውና እኛ በምድር ሳለን በባለሟልነት ወደ እግዚአብሔር ከቀረብን በምድር ሳለን ፍጹማን ሆነን ሰማያውያን እንድንሆን ዛሬ ምን ያተጋናል? “የሰማይን ጌታ ካየሁት እኔ ሰማያዊ እሆናለሁና፡፡ እርሱ ጌታ አባቴና እኔ መጥተን እናድርበታለን” እንዳለ፡፡ ወንድሞች ሆይ እንዲህም ከሆነ  ራሳችንን ማኅደረ እግዚአብሔር እናደርግ ዘንድ ይገባናል፡፡
ሰማይ እጅግ ያማረች ናትና፤ በተፈጥሮዋም ፈጽማ የበራች ናትና በክረምት አትጠቁርምና መልካም አይለወጥምና ራሳችንን በሰማይ እናድርግ፡፡ ደመናትም መጥተው ከታች ቢሸፍኑዋት ከላይ የሚያበራ ብርሃን አላት፡፡ እንደዚሁ እኛም ጨለማ የማያፈራርቀው እውነተኛ ፀሐይ ጌታችንን ገንዘብ እናድርግ፡፡
አስቀድሞ እስካሁን በሰማይ እንሆን ዘንድ ይቻለናል ብዬ ተናገርሁ፡፡ ዳግመኛም ከእንግዲህ ወዲህ ከሰማይ ይልቅ ያማርን የተወደድን እንሆን ዘንድ ይቻለናል ብዬ እናገራለሁ፡፡ ፀሐይን የፈጠረ ጌታ ክብር ምስጋና ይግባውና  በውስጥ በአፍአ ቢያድረብን በእውነት ከሰማይ ይልቅ ያማርን የተወደድን እንሆናለን ብዬ እመልሳለሁ፡፡
ሰማይስ ንጽሕት ናት ብርይት ናት፡፡ በክረምት ደመና በሌሊት ጨለማ አያገኛትም፡፡ እንደዚህም ከሆነ መከራ የሚያመጣብንን፤ ቀቢጸ ተስፋ፤  ከሚያመጣብን ጠላት ተንኮል እንታገሥ ዘንድ ይገባናል፡፡
ከምድራዊ ሥራ የራቅን የተለየን እንሆን ዘንድ ይገባናል?ሰማይ ከምድር የራቀች ናት፡፡ እንደዚህም ሁሉ ሰውነታችንን ምድራዊ ነገር ከማሰብ አርቀን ሰማያዊ ነገር እናስብ ዘንድ ይገባናል፡፡ ማኅደረ እግዚአብሔር እንሁን፡፡ ትሩፋት ሠርተን ከፍጹምነት እንድረስ፡፡
ከዚህ በኋላ  እንደ ጉንዳን እንደ ትል እናያቸዋለን፡፡ይህ ዓለምና በዓለም ያለው ሃብት ሁሉ አላፊ ጠፊ እንደሆነ እንረዳለን እናያለን። ድኃውን ባለጸጋውን ብቻ አይደለም፡፡ ንጉሡንም ራስ ቢትወደዱንም ቢሆን እንዲህ አድርገን እስከማየት ድረስ ነው እንጂ፡፡ የንቀተ ያይደለ የብቃት ነውና እንዲህ አለ፡፡ ያን ጊዜ ንጉሡን ይጐዳናል አንድም ይጠቅመናል ብለን አናየውምና፡፡ ሕዝባዊውን አይጐዳንም አይጠቅመንም ብለን ለይተን አናውቅምና፡፡ ወርቁንም ብሩንም ለይተን አንድም ይጠቅመናል ብለን አናውቅምና፡፡ ከቀይ ሐር ከነጭ ሐር የተሠራውንም ልብስ ለይተን አንድም ይጠቅመናል ብለን አናውቀውምና እንደትል እናያቸዋለን፡፡
በዚያን ጊዜ ሁከት ሥጋዊ ፍርሃት ሥጋዊ የለም፡፡ በዚህ ዓለም ለሚኖር ሰው ከዚህን ያህል ማዕረግ መድረስ እንደምን ይቻለዋል የሚል ሰው ቢኖር ከዚህ ማዕረግ የደረሱ አበውን ጠቅሰን እንመልስለታለን፡፡ ንኡድ ክቡር ጳውሎስ በዚህ ዓለም ይኖር አልነበረምን፡፡ በዚህ ዓለም ሳለ ከሰማይ ደርሶ ከዚያ ተመልሶ የሰማይን አነዋወር በውኑ ይናገራል ብዬ እመልስለታለሁ፡፡ እርሱ ከሰማይ መድረሱን ለምን እናገራለሁ እግዚአብሔርን እናገኘው ዘንድ ካሰብን ፍቅሩን ክብሩን እንደሚገልጽልን እንረዳለን፡፡
እንዲህ ከሆነ የማይታየውን እንጂ የሚታየውን ዓለም አንመልከት፡፡ ጳውሎስ የሚታየውን ዓለም ይመለከት እንዳልነበረ ተረዳኽን? ወዳጄ ሆይ ከምድራዊ ግብር ሕሊናውን በለየ ጊዜ ከሁሉ በላይ እንዳደረገው ተረዳህን? ከጠፈር ብቻ ከዓለም መላእክት ብቻ አይደለም፡፡ የሉም እንጂ ያሉ ቢሆን ከሌላውም ፍጥረት በላይ እንዲያደርገው ተረዳህን?
መንግሥተ ሰማያት መግባትን ተስፋ አድርገን ግን ከትሩፋት ብንለይ በንዋመ ሀኬት /ከክፋትና ከተንኮል እንቅልፍ/ ብንያዝ ፈጽሞ ትሩፋት መሥራት አይቻለንም፡፡ መንግሥተ ሰማያትንም መውረስ አይቻለንም፡፡ እንዲህም ከሆነ ፈጽሞ ትሩፋት መሥራትን ትወዱ ዘንድ መንግሥተ ሰማያትን ትወዱ ዘንድ ወንድሞቼ ሆይ እማልዳችኋለሁ፡፡
የቅዱሱ በረከት ከሁላችን ጋር  ፀንቶ ይኑር።

/ምንጭ፡- ተግሣፅ ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወረቅ ገጽ 175-184/

ቅዱስ ሲኖዶስ

በዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ
«አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት»
kidusSinodos.jpg
በተነገረው ትንቢት በተቆጠረው ሱባዔ ጌታ በሚያውቃት ዕለት ይህች ዓለም ታልፋለች፡፡ እንደ ቅዱስ መጽሐፍ አስተምህሮ ይህ ዓለም ካለፈ በኋላ የማይጠፋ እና የማይለወጥ የዘለዓለም መኖሪያ የሆነ ሌላ ዓለም ደግሞ አለ፡፡ ያም የእግዚአብሔር መንግሥት ነው፡፡ የሰውን ልጆች ለእግዚአብሔር መንግሥት የምታበቃው እውነተኛዋ ፍኖት ደግሞ ክርስትና ናት፡፡ /ኤር 6.16/ እርሷም አንዲት ናት፡፡ የተሰጠችውም ፈጽማ አንድ ጊዜ ነው፡፡ /ይሁዳ 1-3/

ክርስትና አንድ ጌታ የሚመለክበት በአንዲት ጥምቀት ልጅነት የሚገኝበት በአንድ ተስፋ በአንድነት የሚኖርበት ሃይማኖት ነው፡፡ ይህ እምነት በየጊዜው በዓለም በሚነሱ መጤ አስተሳሰቦችና አመለካከቶች እንዳይበከል በእርሱም አምነው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚጓዙ አማንያን አንድነታቸው እንዳይፈታ በእግዚአብሔር የተሠራ ጉባዔ ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ አበው ሊቃነ ጳጳሳት ስለቤተክርስቲያን ዶግማ ቀኖና ሥርዓትና ትውፊት እንዲሁም አስተዳደር የሚመክሩበት በመንፈስ ቅዱስ የሚቃኝ ጉባዔ ነው፡፡ ይህም «ቅዱስ ሲኖዶስ ማለት ፓትርያርክ ሊቃነ ጳጳሳት ጳጳሳትና ኤጲስ  ቆጶሳት የሚያደርጉት ዓቢይ ጉባዔ ነው፡፡» ተብሎ በሕገ ቤተ ክርስቲያን የተገለፀው ነው፡፡ /ሕገ ቤተክርስቲያን አንቀጽ 2(2)/፡፡

አንዳንድ ሊቃውንት የቅዱስ ሲኖዶስን ሥርዓት አጀማመር ጌታ ከሐዋርያት ጋር ያደረጋቸው ስብሰባዎች መነሻ አድርገው ያመጣሉ፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት በመጽሐፍ ቅዱስ ተመዝግበው የሚገኙ ሦስት ጉባዔያትን አድርገዋል፡፡ የመጀመሪያው በይሁዳ ምትክ አንድ አባት መርጠው ሐዋርያ ለመሾም ያደረጉት ጉባዔ ነው፡፡/የሐዋ 1፥15-16/ ሁለተኛው ሰባቱን ዲያቆናት ለመሾም የተደረገው ጉባዔ (ሲኖዶስ) ነው፡፡ /የሐዋ 6.1-6/ የመጨረሻው ከአሕዛብና ከአይሁድ ወደ ክርስትና በመጡት መካከል የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት የተደረገው ነው፡፡/የሐዋ.15፥1/

በጉባዔ ኬልቄዶን ምክንያት የሃይማኖት መከፋፈል ከመጀመሩ በፊት የአካባቢ ሲኖዶሶች እምብዛም የተለመዱ አልነበሩም፡፡ ዛሬ በሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ተቀባይነት ያላቸው ሦስቱ ጉባዔት ብቸኞቹ ዓለም አቀፍ ጉባዔያት ናቸው፡፡ እርሱም በኒቅያ በ325 ዓ.ም በቁስጥንጥንያ በ381 ዓ.ም እንዲሁም በኤፌሶን 431 ዓ.ም የተካሔዱት ናቸው፡፡

ከዚያ በኋላ ግን ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት በየራሣቸው መንበር የአካባቢ ሲኖዶስ ማድረግ ቀጥለዋል፡፡ እነሆ የእኛም ቤተ ክርስቲያን በራሷ ሲኖዶስ መመራት ከጀመረች ከግማሽ ምእት ዓመት በላይ ሆኗል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ዋነኛ ዓላማ የቤተ ክርስቲያንን አንድነት መጠበቅ ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያን የአንድነቷ መገለጫ ነው፡፡ በየጊዜው በሚወለዱ ክስተቶች ዶግማዊ ቀኖናዋ ሥርዓቷ ትውፊቷ እንዲሁም አስተዳዳሯ እንዳይፈታ መጠበቂያ ነው፡፡ በዚህም በመሠረት እምነቷ ላይ ጥያቄ ሲነሳ ማብራሪያ መስጠት አዳዲስ አስተምህሮዎች ሲመጡ በዶግማዊ መሠረት ማረቅ ማቅናት የጾም የጾሎት ሥርዓትን መሥራት ልጆቿን የሚመሩ አበው ሊቃነ ጳጳሳትን መሾም የቅዱስ ሲኖዶስ ዋነኛ ተግባራት ናቸው፡፡

አስቀድመን እንደገለጽነው ክርስትና በማኅበር የሚኖርበት በማኅበር ወደ መንግሥተ እግዚአብሔር የሚደረግ ጉዞ ነው፡፡

ይህ ማኅበር በአንዳች ምክንያት እንዳይበተን የአንድነት መገለጫው ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡

ምዕመናን ሁል ጊዜ ሊሰሙት የሚገባው የቤተ ክርስቲያን ድምጽ ይህ የአንድነቷ መገለጫ ከሆነው ከቅዱስ ሲኖዶስ የሚወጣው ድምጽ መሆን አለበት፡፡ አንድ ክርስቲያን በአኗኗሩ ሁሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ለሚደነግጋቸው ድንጋጌዎች ተገዢ መሆን ይኖርበታል፡፡ ይህ አልተስማማኝም ይህ ጐረበጠኝ ብሎ በግልም በቡድንም መጓዝ ከሕይወት መንገድ ይለያል፡፡

እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከሆነ ቅዱስ ሲኖዶስ ፍጹምና የማይሳሳት አይደለም፡፡ ነገር ግን ሲኖዶስ ተሳሳተ ተብሎ ሌላ አቋራጭ መንገድ መከተል ደግሞ የበለጠ ለጥፋት የሚዳርግ ነው፡፡ ሲኖዶስ ቢሳሳት የሚስተካከለው በራሱ በሲኖዶሱ ሥርዓትና ደንብ ብቻ ነው፡፡

ለቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መገዛት የማኅበረ ምዕመናን አባልነት በዚህ ምድር ያላችው የእግዚአብሔር መንግሥት ነዋሪነት መገለጫ ነው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ እግዚአብሔር ሃሣቡን ፈቃዱን ለልጆቹና ለቤተ ክርስቲያን የሚያስተላልፍበት መንፈሳዊ ጉባዔ ነው፡፡
ለእስራኤል ዘሥጋ ሥለ አንድነታቸው ስለአኗኗራቸው በነሊቀነብያት ሙሴ በኩል ሥርዓትን የሠራ እግዚአብሔር በሐዲስ ኪዳን ለምንኖር ክርስቲያኖች እስራኤል ዘነፍስም ሥለ አንድነታችን ማኅበራችን እንዴት በሥርዓት ልንኖርበት እንዲገባ ሥርዓቱን የሚሠራልን በብጹአን አበው አማካኝነት ነው፡፡ በዚህም ከመንጋው ተለይቶ ላለመቅበዝበዝ የቅዱስ ሲኖዶስን ድምጽ መስማት ተገቢ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር