የመንፈስ ልዕልና

በዲ/ን አሻግሬ አምጤ
ግንቦት 2፣2003ዓ.ም

ልዕልና ከተለመደ ነገር ላቅ ማለትን፣ ሰው ሊሠራው ከሚችለው በላይ መስራትን ያመለክታል፡፡ በአስተሳሰብ ምጥቀት፣ በሚፈጸም ጀብዱ ይገለጻል፡፡ ጥብዓት፣ በመንፈሳዊ ቆራጥነት፣ ወኔ፣ በተፋፋመ አካላዊ  ሆነ መንፈሳዊ ጦርነት ለመግባት መጨከን የልዕልና መገለጫዎች ናቸው፡፡ “በሞት ጥላ መካከል እንኳን ባልፍ ክፉን አልፈራም አንተ ከእኔ ጋር ነህና” እንዳለ መዝሙረኛው፡፡

 

ልዕልና ያለፈውን እየረሱ ወደፊት ሊደርሱበት የሚሹትን ለመናፈቅ ይዳርጋል፡፡ በፈተና ተወልውሎ እንደ ወርቅ ጠርቶ ይገኛል፡፡ ለእኔ ብኲርናዬ ምኔ ናት በማለት የተናገረው ብኲርና ልዕልና መሆኗን ባለመረዳቱ ነው፡፡

ሥጋዊ ፈቃድ የጠየቀውን ሁሉ አለመተግበር፣ በስሜት የተፈጠረን ሁሉ ለማስተናገድ አለመሞከር በተቃራኒው መንፈስ በሥጋ ላይ ማሰልጠን ወይም ሥጋን ለመንፈስ ማስገዛት የልዕልና ተግባር ነው፡፡ የሰሙትን ምሥጢር መጠበቅ፣ የተቀበሉትን አደራ መወጣትም እንዲሁ ቃልን መጠበቅ፣ ታምኖ መሰማራት፣ አደራን መመለስ ለሁሉ አይቻለውም፡፡ ልዕልና በፈተና መጽናትን፣ እንደወርቅ መቅለጥን፣ ሌላው እየበላ ጦም ማደርን፣ ሌላው እየዘነጠ በድህነት መማቀቅን ሊያስከትል ይችላል፡፡ የሚያልፈውን በማያልፈው አሸንፈው፣ ጊዜያዊውን በዘለዓለማዊው ተቆጣጥረው የተጋረጠባቸውን ያሸንፉታል ለልዕልና የታጩቱ፡፡

ሰው ለልዕልና የሚታጨው የፈተናን የክብር ምንጭነት አምኖ ሲቀበል ነው፡፡ አደራ ለመቀበል መብቃት፣ አደራም ለመስጠት ሰውን ማመን ልዕልና አይደለም ትላላችሁ? “መተማመን ከሌለ አደራ ሰጪም አደራ ተቀባይም አይኖርም” እንዲሉ አበው፡፡ ይህ ብቻም አይደል “አደራ ጥብቅ ሰማይ ሩቅ” በማለት ታምኖ መገኘትና አደራን መወጣትን ከሰማይ ርቀት ጋር ያነጻጽሩታል፡፡ እኒህ የተጠቀሱት የልዕልናና የአደራ ጥብቅነት ማሳያዎች ምግባርን ከሃይማኖት አዋሕደው፣ ፍቅረ እግዚአብሔርንና አክብሮተ ሰብእን አጣምረው እንዲኖሩ ኅሊናን ገርተው፣ ጊዜያዊ የሥጋ ፍላጎትን ተቆጣጥረው ይኖራሉ፡፡

 

አደራን ለተወጣ ማኅበረሰቡ የሚያቀርብለት ሙገሳ፣ ውዳሴ፣ ሞራላዊ ሽልማት ለልዕልና ያበቃል፡፡ ሌሎች አደራውን ተወጥቶ ክብር የተቸረው ከደረሰበት ለመድረስ አርአያነቱን ይከተላሉ፡፡ እውነትን ከሐሰት የማያቀላቅል፣ የገባውን ቃል የማይከዳ ይከበራል፡፡ እንዲፈራ የሚያደርገው የመንፈስ ልዕልናው ነው፡፡

 

አደራ የመተማመን፣ የጽኑ ፍቅር ውጤት በመሆኑ አደራ የሚሰጠው ለሚታመን ሰው ነው፡፡ በመተማመን የሚተገበረው አደራ የማያልፍ ዘለዓለማዊ ክብር ያጎናጽፋል፡፡

 

ክብሩ ምድራዊም ሰማያዊም ሊሆን ይችላል፡፡ “የምትጸድቅን ነፍስ ጎረቤት ያውቃታል” የሚለው ብሂል ለዚህ ትንታኔ ድጋፍ ይሆናል፡፡ አደራን ሳይወጡ ከመቅረት ይልቅ ሞትን መምረጥና ክብርን ተክሎ ማለፍ መብለጡን ሐዲስ ዓለማየሁ በማይጨው ጦርነት ጊዜ ተመልክተውት በኅሊናቸው ታትሞ የቀረን ክስተት እንዲህ ይተርኩታል፡፡

 

“ጌትየው በጽኑ ቆስለው በጣዕር ውስጥ እንዳሉ እሷ ስታስታምማቸው እንደማይተርፉ ተረድተውት ኖሮ አንቺና ተስፋው ከሞት ተርፋችሁ ሀገራችሁ ለመግባት የበቃችሁ እንደሆነ መሳሪያዬንና አባቴ ሲሞቱ ለመታሰቢያቸው የሰጡኝን ዳዊቴን ለልጄ ለንጋቱ እንድታደርሱልኝ አደራ፡፡ እንግዲህ ያች ሰው ሁሉ ነፍሷን እንድታተርፍ ያን ያህል ሲማጠናት ዐይኗ ዕያየ በቦንብ ተቃጥላ የሞተች የወዳጇን የአደራ ኑዛዜ ለመፈጸም ኖሯል፤ ምን አይነት እስከ ሞት የሚያደርስ ታማኝነት ነው ምን አይነት ሀያል ፍቅር ቢሆን ነው? ለሃይማኖቷ ብላ፣ እንዲያ ተቃጥላ ሞተች፡፡” አለ ሰውየው፡፡ /ሐዲስ፣ 1985፣86ዓ.ም/


በዚያ ፍጥረተ ዓለም በፍርሃት በሚናጥበት፣ ሳር ቅጠሉ፣ ሰው አራዊቱ በሚያረግድበት ሰዓት አደራ መስጠትም ሆነ መቀበል አስቸጋሪ ነበር፡፡ ልጄ ሆይ ሰው ሁን ያለው እንዲህ ላለው ሰዓት ይሆን እንዴ? አደራ ሰጭው የሴትየዋን ፍቅርና ታማኝነት መዝነውታል፡፡ አደራ የተሰጣቸው ሁለት ነገሮች ጠመንጃና ዳዊት ናቸው፡፡ ሁለቱም ከጠላት መጠበቂያ ናቸው፡፡ አንዱ አፍአዊ ሌላው መንፈሳዊ ጠላትን ለመውጋት ያገለግላሉ፡፡ አንደኛው ባህር ተሻግሮ የመጣን ጠላት ለመቆጣጠር፣ ሌላኛው ከርስት መንግሥተ ሰማያት ከሚነጥል ጠላት ጋር ለመዋጋት ጋሻ ጦር የሚሆን ነው፡፡

 

ሴትየዋ በዚያች ቀውጢ ሰዓት የተሰጣትን አደራ ለመፈጸም ተነስታለች፡፡ ታማኝነት፣ አደራና ታላቅ ፍቅር በአንድ በኩል ሞት በሌላ በኩል ትይዩ ሆነው ቀርበዋል፡፡ ሞትን ፈርተው ማፈግፈግ ታማኝነትን ያፈርሳል፣ ታላቅ ፍቅርን ያቀዘቅዛል፣ አደራ በላም ያደርጋል፡፡ ከሁለቱ መምረጥ ስለነበረበት ሞትን ተጋፍጦ ታማኝነትን ማስመስከር ደምቆ ታያት፡፡ ቃልን አጥሮ፣ አደራን በልቶ በቁም ከመሞት ሥጋዊ ዕረፍትን ተቀብሎ ስምን ከመቃብር በላይ ማዋልን መረጠች፡፡ ሞትን ተገዳድረው የወጡት ታማኝነት፣ ሀያል ፍቅርና አደራ የሃይማኖትና የማተብ መገለጫዎች ሆኑ የሴቷ የፍቅር መስዋዕትነት ሀያል ፍቅር እኮ ሞኝም እብድም፣ ሃይማኖተኛም ሁሉንም ያደርጋል ተባለበት፡፡ በምድራዊ አደራ ብላ የፈጸመችው የሃይማኖትና የማኅተብ መገለጫ ሆነ፡፡ ሴትየዋ በዚህ ሰማዕትነቷ ከጊዜያዊ የጭን ገረድነት ወደ ዘለዓለማዊ የፍቅር ተምሳሌትነት ተቀየረች፡፡ ያለውን የሰጠ ይመሰገናል፤ ራሱን የሰጠ ደግሞ ተከብሮ ይኖራልና፡፡ የተሰጣትን አደራ ለመወጣት ያንን መስዋዕትነት ባትከፍል በደራሲው ምናብ ገድሏ ታትሞ ባልቀረ ነበር፡፡

 

የአደራን ጥብቅነት በተመለከተ ሁለት ነጥቦችን በመጨመር ሀሳቤን ላጠቃልል፡፡ ከዛሬ ዐስራ ዐራት ዓመት በፊት በአንድ ወረዳ ውስጥ የመጀመሪያ ደረጃ መምህር ሆኜ ሥሠራ በአደራ ጠባቂነታቸው ሀገር ስለ መሰከረላቸው የትምህርት ቤት ጥበቃ ባልደረባዬ አጫውቶኛል፡፡ እኒህ ሰው የሰው ገንዘብ እንደማይነኩና አደራ እንደሚጠብቁ የሚያውቅ አንድ መምህር ከቦታው ሲቀየር የተረፈችውን ዐራት ቁና ገብስ የሚያደርስበት ያጣል፡፡ ለሌላ እንዳይሰጠው ከማን ለማን ያደላል፡፡ ይዞት እንዳይሄድ የዐስራ ሁለት ሰዓት የእግር መንገድ ከሌላው ጓዙ በተጨማሪ ዐራት ቁና ገብስ መያዝ ሊጠበቅበት ነው፡፡ አማራጭ ሲያጣ የሰው ገንዘብ እንደማይነኩ ለሚታወቁት የጥበቃ ሠራተኛ አደራ ብሎ ይሰጣቸዋል፡፡ ይህን ያደረገው ስቀር ይጠቀሙበታል ብሎ በማሰብ ነው፡፡ ታሪኩን የነገረኝ ባልደረባዬ ተመድቦ ይሄዳል፡፡ አንድ ቀን ለዝክር ቤታቸው ሄዶ ጠላ እየጠጡ ሲጫወቱ ተንጠልጥሎ ጠቀርሻ የጠጣ ነገር ይመለከትና ምንነቱን ይጠይቃቸዋል፡፡ ምን እባክህ ያ እገሌ የሚባል ሰው አደራ አስቀምጦብኝ ይኸው ተንጠልጥሎ ቀረ ይሉታል፡፡ ባልንጀራዬም በዚህ ዘመን እንዲህ ያለ ሰው በማየቱ ተገርሞ በዓመቱ እኔ ካለሁበት ትምህርት ቤት ተቀይሮ ሲመጣ አጫውቶኛል፡፡

 

ቃሌን አጥፌና አደራዬን በልቼ ከችግሬ ላልወጣ ለምን ከፈጣሪዬ እጣላለሁ በማለት ይመስለኛል የሰውየው ጥንቃቄና ታማኝነት ስንቶቻችን ለማይሞላ ሆድ፣ ለማይረካ ፍላጎት ያውም ለነገ ለማይተርፍ ነገር አደራችንን በልተን ከፈጣሪ የተጣላን፤ ሰውም የታዘበን፡፡ 60 ዓመት በፈጣሪያቸው ረድኤት የኖሩ አባት በአንድ እለት ለምሳ ቋጥሯት የነበረችውን አገልግል የዛሬን ይብሉልኝ ብሎ በለመናቸው ጊዜ ዛሬ ያንተን አገኘሁ ብዬ በልቼ 60 ዓመት ከመገበኝ ፈጣሪዬ ልለይ እንዳሉት አባት ማለት ነው፡፡ ላይሞላ፣ ቀዳዳ ላይደፈን፣  ችግር ከልኩ ላያልፍ፣ አምላክ ያለው ላይቀር፣ እኛም ከተፈቀደልን ደረጃ ከፍ ላንል ስንቱን አደራ ኑሮ በላነው?

 

የጽሑፌ ማጠቃለያ የአለቃ ለማ ኃይሉ እና የአለቃ ተጠምቀ ታሪክ ነው፡፡ በትምህርት የኖሩት ሊቁ አለቃ ለማ ዋድላ ድላንታ ቅኔ ሲማሩ ኖረው ዐባይን ተሻግረው በዘመኑ የቅኔና የመጻሕፍት ማስመስከሪያ ከነበሩት መጀመሪያ ሞጣ ጊዮርጊስ ቀጥሎም ዲማ ጊዮርጊስ ይመጣሉ፡፡ ዲማ ጊዮርጊስም ከአለቃ ተጠምቀ ጋር ይገናኛሉ፡፡ አለቃ ተጠምቀ ዐይነስውር ናቸው፡፡ ብሉይ ኪዳንን ከነ አለቃ ለምለም በ6 ወር የወጡ ተጠምቀና ደቀመዝሙሩ አለቃ ለማ ወደ አዲስ አበባ ለመምጣት ይነሳሉ፡፡ ዘመኑ በኢትዮጵያ ታሪክ ክፉ ቀን የተባለው፣ ሰውም ከብቱም ያለቀበት እናት የልጇን ሥጋ ሳይቀር የበላችበት አስቸጋሪ ዘመን ነበር፡፡ በዚህ ዘመን ከዲማ መምህራቸውን እየመሩ ደብረ ሊባኖስ፣ ደብረ ብርሃን፣ ከዚያም አንኮበር መጨረሻም አዲስ አበባ መካነ ሥላሴ በማለት አብረዋቸው ኖረዋል፡፡ በወቅቱ ርሃቡ ከመጽናቱ የተነሣ የሚበላ ጠፍቶ በሦስት ቀንም፣ በአራት ቀንም የሚቀመስ ሲገኝ አብረው እየቀመሱ ምግባቸውን ቃለ እግዚአብሔር አድርገው ክፉውን ቀን አሳልፈዋል፡፡ በጊዜው ወጣት የነበሩት አለቃ ለማ በልቼ ወደ ማድርበት ልሂድ ሳይሉ ከመምህራቸው ጋር ተናንቀው ቀኗን አሳለፏት፡፡ በሚያልፍ ቀን፣ በሚያልፍ ችግር የቀለም አባታቸውን አልለወጧቸውም፡፡ እንዲያውም ለዚህ ደረጃ ያደረሰኝ ከእሳቸው ያገኘሁት በረከት ነው ይላሉ፡፡ ይህን የመንፈስ ልዕልና የሚያገኙና ሲያገኙትም የበረከት ምንጭነቱን ተረድተው የሚገጥማቸውን ጊዜያዊ ፈተና የሚወጡ ምንኛ የተባረኩ ናቸው!

/ምንጭ፡-

  • ሐዲስ ዓለማየሁ ትዝታ፣ 1985ዓ.ም፣ ሜጋ አሳታሚ ድርጅት፣
  • መጽሐፈ ትዝታ ዘአለቃ ለማ ኃይሉ ወልደ ታሪክ 1959ዓ.ም፣
  • ዲ/ን ያረጋል አበጋዝ፣ ከበረሃውያን ሕይወትና አንደበት ጥር 2003ዓ.ም፣
  • ባሕሩ ዘውዴ ዘመናዊ የኢትዮጵያ ታሪክ አ.አ.ዩኒቨርሲቲ 1989ዓ.ም፡፡/

“አዲስ ልብና አዲስ መንፈስ ለእናንተ አድርጉ” /ሕዝ 18፥31/

በማሞ አየነው

የሰው ልጅ ለሥጋዊና መንፈሳዊ እንቅስቃሴው አመች በሆነ መልኩ እግዚአብሔር ለሚያፈራርቃቸው ዘመናት ቀመር ሲያወጣ ኖሯል፡፡ ጊዜያትንም ከደቂቃ ሽራፊ እስከ ሺህ ዘመናት ድረስ ከፋፍሎ ይጠቀማል፡፡ በዚህ የጊዜ ቀመርም ትናንትን ያስረጃል፤ ዛሬን ደግሞ አዲስ ያደርጋል፡፡ በጊዜ ዑደትም ብዙ ሺህ አዲስ ዓመታት አልፈው ብዙ ሺህ አዲስ ዓመታት መጥተዋል፡፡ የዘመናት መፈራረቅ ሰው የእግዚአብሔርን ሥራ እንዲያደንቅ፣ መግቦቱንም እንዳይረሳ ያደርጋል፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ቃል ኪዳኑን እንዳልረሳ፣ ፍጥረቱን እንዳልዘነጋ ያመለክታል፡፡

 

 

ቅዱስ ዳዊት «የሰው ሁሉ ዓይን  አንተን ተስፋ ያደርጋል፡፡ ምግባቸውንም በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ» እንዳለ፣ወራትን እያፈራረቀ፣ በዝናብ እያበቀለ፣በፀሐይ እያበሰለ ለፍጥረታት ምግባቸውን ይሰጣል።/መዝ 144፥15/ እግዚአብሔር አምላክ ዓመታት አያረጁበትም፣ አይለወጡበትም «አንተ ግን ያው አንተ ነህ ዓመቶችህም ከቶ አያልቁም» እንዲል /መዝ 101፥27/፡፡ ስለዚህም ዓመታት የሚቀያየሩት የሚያልቁትና የሚጀምሩትም ለሰው ልጆች ብቻ ነው፡፡ አዲስ ዓመት የክረምትን መውጣትና የመከርን መድረስ የዝናሙን ማለፍ ተከትሎ የሚከበር የአዲስ ተስፋ እና ብስራት በዓል ነው፡፡ ይህን አስመልክቶ ጠቢቡ ሰሎሞን እንዲህ ብሏል፡፡ «እነሆ ክረምት አለፈ ዝናቡም አልፎ ሄደ፡፡ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፣ የዜማም ጊዜ ደረሰ፣ የቁርዬውም ቃል በምድራችን ተሰማ፣ በለሱ ጎመራ ወይኖችም አበቡ፣ መዐዛቸውንም ሰጡ» /መኃ 2፥11/፡፡ በአዲስ ዓመት ዓመታት ብቻ ሳይሆኑ ምድርም ገጽታዋን ትለውጣለች፡፡ የደረቁ ዛፎችና የደረቀችው መሬት አረንጓዴ ይለብሳሉ፤  አዝርእትና እፅዋት በአበባ ለዘር ለፍሬ ይደርሳሉ፡፡ ይህም በዓሉን እጅግ ደማቅና ተወዳጅ ያደርገዋል፡፡ መግቦቱን እንድናከብር እና ቃል ኪዳኑንም እንዳንረሳ እግዚአብሔር አምላክ አዝዞናልና፡፡

ስለዚህም ነው ቅድስት ቤተክርስቲያን በዓሉን በድምቀት የምታከብረው ምዕመናንንም እንዲያከብሩት የምታስተምረው፡፡ ነገር ግን አሁን አሁን እየታየ ባለው የአከባበር ሁኔታ የበዓሉን መንፈስ ፍፁም ሥጋዊ እንዲሆን ግብረ እግዚአብሔርን ፤ መግቦተ እግዚአብሔርን ከማሰብ ይልቅ የሥጋን ነገር ብቻ እያሰብን እንድናከብር የሚያስገድዱ ነገሮች ይስተዋላሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ አዲስ ዓመትን እንዴት ማክበር እንዳለብን የሚነገረን ነገር አለ፡፡ በክርስትና መስመር ያለ ሰው እነዚህን ጠቃሚ ነጥቦች በማየት ራሱን እንዴት ማስተካከል እንዳለበት፣ አዲሱን ዓመት እንዴት መቀበል እንዳለበት ይገልጻል፡፡ መጽሐፍ ከሚያስተምረን ብዙ ቁም ነገሮች የተወሰኑትን እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 

1.“አዲሱን ሰው ልበሱ” /ኤፌ 4 ፥22/


የዓመታት መቀያየር በእኛ ክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ ለውጥ ካላመጣ በድሮው አሮጌ ሰውነታችን አዲሱን ዓመት ከተቀበልን ዛሬ ከትናንት በምን ይሻላል? ድሮ የነበሩንን የኃጢአት ልምዶች ዛሬ ማስወገድ ካልቻልን አዲስ ዓመት መጣ ማለት ረቡ ምንድን ነው? አዲስ ዓመት ሲመጣ በአእምሯችን ልናመላልሰው የሚገባው ነገር የመንፈሳዊ ሕይወታችን መለወጥ መሻሻልና ማደግ ነው፡፡ እነዚህን ሃሣቦች ተግባራዊ ለማድረግ አሮጌውን እኛነታችንን አውልቀን አዲሱን ሰው መልበስ ያስፈልጋል፡፡ «አሮጌውን ሰው ከሥራው ጋር ገፍፋችሁታልና፤ የፈጠረውንም ምሳሌ እንዲመስል እውቀትን ለማግኘት የሚታደሰውን አዲሱን ሰው ለብሳችሁታልና» እንዲል ቅዱስ ጳውሎስ /ቆላ 3፥10/። አሮጌውን ሰው ከነ አሮጌ ሥራው ስንገፈውና አዲሱን ሰው ስንለብስ ነው ዓመቱን አዲስ የምናደርገው አሮጌው ሰው በምክንያትና በሰበብ አስባቦች የተሞላ ነው፡፡ ጊዜ ለሰጠው አምላክ እንኳን ጊዜ የሚሰጠው በድርድርና በቅድመ ሁኔታ ነው፡፡ አሮጌው ሰው ስለንስሐ ሲነገረው “ከልጅነቴ ጀምሮ ሕግጋቱን ጠብቄያለሁ” ይላል፡፡ ስለ ሥጋወደሙ በተነገረው ጊዜ “ይህ የሚያስጨንቅ ንግግር ነው ማን ሊሰማው ይችላል»/ዮሐ 6፥60/ ይላል፡፡ ወደ እግዚአብሔር ቤት እንዳይገሰግስ «አባቴ ሞቷል እቀብር ዘንድ ፍቀድልኝ»/ሉቃ 9፥59/ ብሎ ራሱን በምክንያቶች ይከባል፡፡ ይህ ከእግዚአብሔር ጋር ያለያየን አሮጌው ሰውነታችን በአዲስ ሊቀየር ይገባዋል፡፡ አሮጌው ሰውነታችን ነፍሳችን እንድትጠማ ምክንያት ሆኗል፡፡ «እንጨትና ውኃ በሌለበት በምድረ በዳ ነፍሴ አንተን ተጠማች» እንዲል /መዝ 62፥1/ ስለዚህም ነፍሳችን ከጥሟ ትረካ ዘንድ በቃለ እግዚአብሔርም ትረሰርስ ዘንድ አዲሱን ሰው እንልበስ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም «ፊተኛ ኑሯችሁን እያሰባችሁ እንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዱ። በአእምሯችሁ መንፈስ ታደሱ፤ ለእውነትም ለሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ።» እንዲል /ኤፌ 4፥22-24/፡፡

 

2.“አሮጌው እርሾ አስወግዱ” /1ቆሮ 5፥7/


ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው «ጽድቃችሁ ከጻፎችና ከፈሪሳዊያን ካልበለጠ ወደ እግዚአብሔር መንግስት አትገቡም።» ብሎ አስተምሮ ነበር፡፡ ከጻፎችና ከፈሪሳዊያን እኩይ ግብር አንዱና ዋነኛው ደግሞ በሁለት ቢላዋ የመብላት ልምዳቸው ነው፡፡ የሙሴን ሕግ እንፈጽማለን እናስፈጽማለን ይላሉ፤ በሌላ በኩል ይሄንኑ ሕግ ራሳቸው ሲጥሱ እንመለከታለን፡፡ ጽድቅና ኃጢአትን በአንድ ሰውነታቸው ሊፈጸሙ የሚሞክሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ ጽድቃችን ይህን ከመሰለ ሁኔታ እንዲለይም ጌታችን አስተምሮናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በመልእክቱ እንዲህ ይለናል፤ «እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ….። ስለዚህ በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም፡፡» /1ቆሮ 5፥7/፡፡ እርሾ ለሊጥ አስፈላጊ የሚሆነው ሊጡን እስከሚያቦካ ድረስ ብቻ፡፡ ሊጡን ካቦካ በኋላ አሮጌው እርሾ ይወገዳል፡፡ ካለያ ሊጡን ሆምጣጣና ጣዕም የለሽ ያደርገዋል፡፡ ሊጡ ቂጣ መሆን የሚችለውም አሮጌው እርሾ ከተወገደ በኋላ ነው፡፡
በክርስትና ሕይወታችንም ጽድቅና ኃጢአት እየተፈራረቁ ሊያስቸግሩን ይችላሉ፡፡ በአዲስ የንስሐ ሕይወት እንኖር ዘንድ ቀድሞ የነበረውና ከጽድቃችን ጋር የተቀላቀለው እኩይ ግብር ሊወገድ ይገባል፡፡ ይህ ካልሆነ ጽድቃችን ከፈሪሳውያን በምን ተሻለ? በዓልንም በቅንነትና በእውነት ቂጣ የምናከብረው አሮጌውን እርሾ ስናስወግድ ነው፡፡ በቂጣ የተመሰለው ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ለሰው ምግብ መሆን የሚችለው ከአዲሱ ማንነታችን /ከአዲሱ ሊጥ/ ጋር አብሮ የተቀላቀለው አሮጌ እርሾ ማለትም ጽድቅን ከኃጢያት አደባልቆ የሚሄደው ሰውነታችን ይህን ግብሩን እርግፍ አድርጐ መተው አለበት።

 

3.“አዲስ ልብና መንፈስም ለእናንተ አድርጉ” /ሕዝ 18፥31/


በመንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ ትልቁ ፈተና ያለንን ነገር ጠብቆ መቆየት መቻል ነው፡፡ መንፈሳዊ ዝለት የሚፈጠረውም መንፈሳዊ እንቅስቃሴያችን ተደጋጋሚና ዕድገት የሌለው መሆን ሲጀምር  ነው፡፡ መንፈሳዊ ዕድገት የሚያሳይ ሰው ለመንፈስ ዝለት አይጋለጥም፡፡ በአዲስ ልብና በአዲስ መንፈስ ሕይወቱን የሚመራ ክርስቲያን አይሰለችም፣ ለእሱ ክርስትና ሁሌም አዲስ ነው፤ አንዴ የሚፈጽሙትና የሚጨርሱት ሳይሆን የዕድሜ ልክ ሕይወት ነው፡፡ ስለዚህም ክርስትና በአዲስ ልብና በአዲስ መንፈስ የሚኖር አዲስ ሕይወት፣ የድሮውን እየረሱ ነገን ለመያዝ የሚደረግ የተስፋ ሕይወት ነው፡፡ « ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፏል፤ እነሆ ሁሉም አዲስ ሆኗል፡፡»  እንዲል ቅዱስ ጳውሎስ። /2ቆሮ 5፥17/ አዲስ ዓመትንም አዲስ የምናደርገው አዲስ ልብና አዲስ መንፈስ ስንይዝ ብቻ ነው፡፡ የለውጥ መጀመሪያ የልቦና መለወጥ ነውና፡፡ በስሜት የሚመጣ ለውጥ ዘላቂነት የለውም፡፡ ትንሽ ነፋስ ሲነፍስ መወዛወዝ ይጀምራል፡፡ ለዚህም ነው ነብዩ የድሮው እኛነታችንን እንድናስወግድ አዲስ ልብና አዲስ መንፈስም እንዲኖረን የሚመክረን «አዲስ ልብና አዲስ መንፈስም ለእናንተ አድርጉ፤ የእስራኤል ቤት ሆይ ስለምን ትሞታላችሁ? የሟቹን ሞት አልፈቅድምና´ /ሕዝ 18፥31/።

 

በአጠቃላይ አዲስ ዓመትን ለአዲስ ክርስቲያናዊ ሕይወት መነሻ አድርገን ብናከብር በዓሉን እውነተኛ የአዲስ ዓመት በዓል ያደርገዋል፡፡ «ካመንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደኛ ቀርቦአል፡፡ እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ» እንዲል ሐዋርያው ያለፉትን የባከኑ ዓመታት ለማስተካከል የብርሃን ጋሻ ጦር በመልበስ የጨለማን ሥራ ማስወገድ አስፈላጊ ነው፡፡/ሮሜ 13፥12-44/ በልብስና በቤት በመኪና ብቻ ሳይሆን በልባችን መታደስ መለወጥ የሚገባን ልዩ ጊዜ ቢኖር ይኼው አዲስ ዓመት ነው።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

መንፈሳዊ ተጋድሎ

በዲ/ን አሉላ መብራቱ

1.    መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት ምን ማለት ነው?

መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት – አንድ ሰው የሚያምንበትን እምነት፣ የሚመራበትን ሕግ፣ የሚያልመውን ተስፋ እና የሚወደውን ነገር ተከትሎ ከግቡ ለመድረስ ማድረግ ያለበትን በማድረግ÷ ማድረግ የሌለበትን በመተው በነፃ ፈቃዱ ወስኖ፥ በሙሉ ልቡናው፥ በሙሉ ኃይሉ የሚያደርገው የውስጥና የውጭ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ፥ ጥረትና ትግል ነው፡፡
 

ሀ. ከፈቃደ ሥጋ ጋር የሚደረግ ውጊያ ነው፡፡

ሰው በዚህ ዓለም በተሰጠው ዘመኑ ራሱን ለፈጣሪው ለማስገዛት ከራሱ ጋር ብርቱ ተጋድሎ ማድረግ ግድ ይለዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሥጋ በመንፈስ ላይ መንፈስም በሥጋ ላይ ይመኛል፤ እነዚህም እርስ በርሳቸው ይቀዋወማሉ፡፡ ስለዚህም የምትወዱትን ልታደርጉ አትችሉም›› ብሎ የገለጸው ይህንን በሰው ሕይወት ውስጥ ያለውን የማያቋርጥ ጦርነት ነው፡፡ (ገላ 5፥12) ታላቁ አባት ኢዮብም ‹‹በምድር ላይ የሰው ሕይወት ብርቱ ሰልፍ አይደለምን ?›› በማለት ሰው ጽኑ ጦርነት የሚካሄድበት የጦር ሜዳ መሆኑን ገልጿአል፡፡ ይህም ጦርነት በተወሰነ ጊዜ ተነሥቶ የሚጠፋ ሳይሆን በሰው ዘመን ሁሉ የሚኖርና የዕድሜ ልክ ትግል ነው፡፡ ይህን የሥጋና የነፍስ ጦርነት በነፍስ አሸናፊነት ማጠናቀቅና ፈቃደ ሥጋን ድል አድርጎ ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ይገባል፡፡

ይህ ሲባል ግን ሥጋ ርኵስ ነው፤ ሥጋ መጥፋትና መወገድ አለበት ማለት አይደለም፡፡ ሥጋ በራሱ ርኵስ አይደለምና፤ ምክንያቱም ሥጋ የተፈጠረው በራሱ በእግዚአብሔር ነው፡፡ አምላካችን ደግሞ ርኵስ ነገር አይፈጥርም፡፡ ሰውን (ሰው የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ውጤት ነው) ከፈጠረ በኋላ ‹‹ያደረገውን ሁሉ አየ እነሆም እጅግ መልካም ነበረ፡፡›› ተብሏል፡፡ (ዘፍ1፥31) ሥጋ ርኵስ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር ወልድ (ቃል) ‹‹ሥጋ ሆነ›› ባልተባለ ነበር፡፡ (ዮሐ 1፥14) አዳምና ሔዋን ከኃጢአት በንጽሕና ይኖሩ ነበር፡፡ ‹‹አዳምና ሚስቱ ሁለቱም ዕራቁታቸውን ነበሩ፣ አይተፋፈሩም ነበር›› እንዲል (ዘፍ 2፥25)  ህፃናት፣ ልጆች  ሰውነት አላቸው ነገር ግን የኃጢአት ምኞት የላቸውም፡፡

ስለዚህ ፈቃደ ሥጋን መዋጋት ማለት ሥጋን ማጥፋት ወይም ደግሞ ተፈጥሮአዊና ንጹህ የሆነ የሥጋን ፈቃድ ማስወገድ ማለት ሳይሆን፣ ኃጢአትን በማየት፣ በመስማት፣  በመለማመድ ያደገውን÷ ወደ ኃጢአት ያዘነበለውን ፈቃዳችንን መጐሰም/መግራት ማለት ነው፡፡ ይህ ፈቃድ (ኃጢአት) ሥጋን በመጠቀም ይሠራል÷ ሥጋን ከነፍስ ቁጥጥር ውጭ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡

የሰው ሥጋዊ ባሕርዩ ምግብ ሲያጣ ይራባል፣ ይደክማል፣ ሥራ መሥራት ይሳነዋል፡፡ ሲሰጡት ደግሞ ኃጢአትን ተለማምዷልና ሌላ ፈቃድ በማምጣት ጠላት ሆኖ ይፈትነዋል፡፡ ‹‹ያዕቆብ በላ፣ ጠገበ፣ ወፈረ፣ ደነደነ፣ ሰባ፣ የፈጠረውንም እግዚአብሔርን ተወ፣ የመድኃኒቱንም አምላክ ናቀ፡፡ (ዘዳ 32፥15)

ሰውነት የሚፈልገውን ሁሉ እንደ ልቡ ካገኘና ያለ ገደብ የሚቀለብ ከሆነ ወደ ኃጢአት ለመገስገስ የተዘጋጀ መርከብ ነው፡፡ ሰውነት በተመቸውና ፈቃዱን ለመፈጸም ኃይል ባገኘ ጊዜ ነፍስ እየደከመች ትሄዳለች፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሰውነት ፈጽሞ ከደከመና ከዛለ ሥራ መሥራት ያስቸግራል፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ‹‹ሰውነቴን እየጎሰምሁ አስገዛዋለሁ›› እንዳለ፡፡ በአግባቡ ሊያዝና ሊገራ ይገባዋል፡፡ (1ኛ ቆሮ 9፥27) በአጠቃላይ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ወንድሞች ሆይ ዕዳ አለብን እንደ ሥጋ ፈቃድ ግን እንኖር ዘንድ ለሥጋ አይደለም፡፡ እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፤ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ›› እንዳለ ከፈቃደ ሥጋ ጋር በመጋደል ፈቃደ ሥጋችንን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ይገባናል፡፡

ለ. ከርኵሳን መናፍስት ጋር የሚደረግ ጦርነት ነው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር እንጂ›› እንዳለ መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት ሰው ከሰው ጋር በመጣላት የሚያደርገው ትግል ሳይሆን ጥንተ ጠላታችን ከተባለው በእባብ ወይም በዘንዶ ከተመሰለው ዲያብሎስና ከእርሱ ጋር ካሉት ሠራዊቱና መልእክተኞቹ ጋር የሚደረግ ጦርነት ነው፡፡ (ኤፌ 6፥12)

ከአዳምና ከሔዋን ከልጃቸውም ከቃየን ጀምሮ ሰይጣን የሰው ልጆችን ዘወትር ይዋጋል፤ ከዘላለም የሞት ፍርድ ሥር ሊጥል ይሠራል፡፡ በዚህም ውጊያው ከነቢያት ፤ከሐዋርያት ፤ የእግዚአብሔር መንፈስ ካደረባቸው ሰዎች እንኳ ሳይቀር ብዙዎችን ጥሏል፡፡

ዛሬም በገዛ ባሕርያችን የሚገኘውን ፈቃደ ሥጋ በመጠቀም፣ የራሱን በመጨመርና የተለያዩ ፈተናዎችን በማቀናበር ይዋጋናል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና›› በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት፡፡›› እንዳለ ጠላት ዲያብሎስ ክርስቲያኖችን በኃጢአትና ሞት ሊውጥ ዘወትር ይተጋል፡፡ ማንም ሰው ደግሞ ከዚህ ፈተናና ውጊያ ሊያመልጥ አይችልም፤ ስለዚህ ሐዋርያት ‹‹በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት››፣ ‹‹የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ፡፡›› እንዳሉን የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ለብሰን ልንዋጋው ይገባል፡፡ (1ኛ ጴጥ 5፥8-9፣ኤፌ 6፥11)

ሐ. የሚመጣውን ዓለም ደስታ ተስፋ እያደረጉ ብቻ በዚህ ዓለም ሕይወት ከደስታ ውጪ መሆን ማለት አይደለም፡፡

ደስታ በራሷ የቤተ ክርስቲያን መገለጫ የሆነች፤ ከእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የተሰጠች፤ ንጹሕ ፈርጥ ነች፡፡ (ገላ 5፥22)

እውነት ነው፤ በዚህ ዓለም ስንኖር መከራ አለብን፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀሉን ተሸክመን እንድንከተለው አዞናል፡፡ እያንዳንዱ ክርስቲያን በዚህ ምድር ላይ እስካለ ድረስ ከጨለማው ዓለም ገዢ ከዲያብሎስና ከሠራዊቱ የሚመጣ ልዩ ልዩ ፈተናና ከሥጋችንም ባሕርይ ከሚገኘው ክፉ ምኞትና ርኵሰት ሥራ እንዲሁም ከሌሎቹ የኃጢአትና የፈተና ዓይነቶች ጋር በማያቋርጥ እልህ አስጨራሽ በሆነ ትግል ውስጥ መኖሩ የግድ ነው፡፡ መከራና ስቃይ፣ ትግልና ጦርነት የሌለበት በዘለዓለማዊ ደስታ ብቻ የሚኖርበት ሕይወት በሚመጣው ዓለም የሚገኝ ነው፡፡

በዚህ ምድር በጉዞ ላይ ያለችው ቤተ ክርስቲያን ጉዞዋን ጨርሳ ድል ከነሱት አባላቷ ጋር አንድ እስክትሆን ድረስ መከራው፣ እንቅፋቱ፣ መሰደዱ፣ መራቡ፣ መጠማቱ የግድ ነው፡፡ ‹‹ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል፡፡›› እንዲል (ሐዋ 14፥22)

ይህ ሲባል ግን በዚህ ዓለም የሚኖሩ ክርስቲያኖች ከደስታ የተራቆቱ ዘወትር በኅዘንና በስቃይ ብቻ የሚኖሩ ናቸው ማለት አይደለም፡፡ ክርስቲያኖች የሚለዩትና ዘወትር ለመለየት ጥረት የሚያደርጉት የውሸት ከሆነው ኃጢአት (ዝሙት፣ ርኩሰት፣ መዳራት፣ ጣዖትን ማምለክ፣ ምዋርት፣ ጥል፣ ክርክር፣ ቅንአት፣ ቁጣ፣ አድመኝነት፣ መለየት፣ መናፍቅነት፣ ምቀኝነት፣ መግደል፣ ስካር፣ ዘፋኝነት፣ ይህንም የሚመስል) ከሚገኘው ደስታ እንጂ ከእውነተኛውና ከሰማያዊው ደስታ አይደለም፡፡

መንፈሳዊ ተጋድሎ በመንፈስ ቅዱስ አነሳሽነትና ረድኤት መንፈስ ቅዱስ መሪና አስተማሪ፣ የሚያነቃቃና የሚያጽናና፣ የሚያርምና የሚገሥጽ፣ የሚረዳና የሚያጸና፣ በመሆን ስለ ክርስቶስ በክርስቶስ ጸጋ የሚከናወን በመሆኑ መከራንና ስቃይን በሚያስረሳ እውነተኛ ደስታና ሰላም የተሞላ ሕይወት ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ ሲላስ ስለ ክርስቶስ በማስተማራቸው ምክንያት ገዢዎች ልብሳቸውን ገፈው በበትር እንዲመቱ አዘዙ በበትር ከመቷቸውም በኋላ በወኅኒ ቤት ጣሏቸው እነርሱ ግን ከጀርባቸው ደም እየፈሰሰ በመንፈቀ ሌሊት እንኳን እግዚአብሔርን በመዝሙር ያመሰግኑ ነበር፡፡ እውነተኛውና ሰማያዊው ደስታ በልቡናቸው ሞልቶ ነበርና፡፡ (ሐዋ 16፥22-25)

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሐዋርያት እንዲህ ይለናል ‹‹ ሐዋርያትንም ወደ እነርሱ ጠርተው ገረፏቸው  በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቷቸው፡፡ እነርሱም ስለ ስሙ ይናቁ ዘንድ የተገባቸው ሆነው ስለተቆጠሩ ከሸንጎው ፊት ደስ እያላቸው ወጡ፡፡››(ሐዋ 5፥40-41)

ቅዱስ ዮሐንስ ካሲያን የተባለው አባት በተጋድሎ በግብጽ በረሃ ውስጥ ይኖሩ ስለነበሩት መነኰሳት ሲናገር ‹‹ እነዚህ ምድራዊ መላእክት ናቸው፤ የግብጽን በረሀዎች በደስታ ወደ ተሞላ መዝሙርና እግዚአብሔርን የማመስገኛ ገነትነት ለውጠዋልና››  ብሏል፡፡

በአጠቃላይ መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት ከተድላ ሥጋ፣ በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ በመሸሽ ሰማያዊና እውነተኘ በሆነ ሰላምና ደስታ ውስጥ መኖር ይህንንም ለማግኘት መጋደል ማለት ነው፡፡

2.    መንፈሳዊ ተጋድሎ ዓላማው ምንድነው?

ሀ. የድል አክሊል (የዘለዓለም ሕይወት) ለመቀበል

እግዚአብሔር አምላካችን ሰዎች ነፃ ፈቃዳቸውን ተጠቅመው ከአምላካቸው ጋር መኖር ከመረጡ ሊሰጣቸው ያዘጋጀው ከመነገርና ከመታሰብ በላይ የሆነ የዘለዓለም  ሕይወት አለ፡፡ የሰው ልጅ ሕሊናዊ ነፃ ፈቃዱ ደግሞ ከአዳምና ከሔዋን ውድቀት በኋላ በየጊዜው እየደከመና ወደ ኃጢአት እያዘነበለ መጥቷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ዘንድ ከብሮ ባየ ጊዜ ከአባቶቻችን ጀምሮ ዘወትር የሚቀና ክፉ ጠላትም (ዲያብሎስ) አለን፤ ባገኘው አጋጣሚ ስንፍናችንንና ድካማችንን እየተከተለ እነዚህንም በመጠቀም ዘወትር ከአምላካችን ሊለየን እንደሚተጋም ከላይ ተመልክተናል፡፡

ሽልማት፣ አክሊል የሚሰጠው ደግሞ ማሸነፍ ለሚችል ጎበዝ ሰው ነው፡፡ ሰነፍና ቸልተኛ ሰው ግን ሊሸለም አይገባውም አንድ ሰው ጎበዝ ወይም ሰነፍ መሆኑ የሚታወቀው ደግሞ በፊቱ ያጋጠመውን ውድድር ወይም ፈተናና መከራ ማሸነፍና ማለፍ ሲችል ብቻ ነው፡፡

ስለዚህ የመንፈሳዊ ተጋድሎ ዓላማ በገዛ ባሕርያችን ያለን መጥፎ የኃጢአት ዝንባሌና ጠላታችን ዲያብሎስ የሚያመጣብንን ፈተናና ሽንገላ ከእግዚአብሔር ርዳታና ቸርነት ጋር ሕሊናን በማንቃት፣ ራስን በመግዛትና ጠንክሮ በመጋደል አምላካችን ያዘጋጀልንን የድል አክሊል የዘላለም ሕይወትን መቀበል ነው፡፡ ‹‹ የተጠራህለትን የዘለዓለም ሕይወት ትቀበል ዘንድ መልካሙን የሃይማኖት ገድል ተጋደል›› አንዲል (1ኛ ጢሞ 6፥12) ሐዋርያቅ ቅዱስ ጳውሎስ ብዙ መከራዎችን አልፎ ገድሉን በድል አድራጊነት ሲፈጽም ‹‹ መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫዬን ጨርሻለሁ፤ ሃይማኖቴንም ጠብቄያለሁ፤ ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፤ ይህም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያስረክባል፤ ደግሞም መገለጡን ለሚወዱ ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም፡፡›› ብሏል ( 2ኛ ጢሞ 4፥7-8)

ለ. ለመንፈሳዊ እድገት

ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ለፍሬ የሚበቃው የድል አክሊልን መቀዳጀት የምንችለው የማያቋርጥ (የማይቆም) መንፈሳዊ ዕድገት ሲኖረን ነው፡፡ በጥምቀት ያገኘነው አዲሱ ሕይወታችን ዘወትር ማደግ ይኖርበታል፡፡ ክርስቲያናዊ ሕይወታችን በዛፍ ተክል ይመሰላል፡፡ ከችግኝ ማፍላት ጀምሮ ፍሬ እስከሚያፈራለት ጊዜ ድረስ ያለው ድካም ቀላል አይደለም፡፡ የዛፉ ችግኝ እንዲያበቅል፣ እንዲለመልም፣ አንዲያብብና እንዲያፈራ አትክልተኛው ያልተቆጠበ ጥረት ማድረግ ይኖርበታል፤ በየጊዜው ውሃ ማጠጣት፣ ማረምና መኰትኰት፣ ፀረ ዕፅዋትና ፀረ ሕይወት የሆኑ በሽታዎችን መከላከል ያስፈልጋል፡፡ እንደዚሁ ክርስቲያናዊ ሕይወታችን አድጎ ለፍሬ እስኪበቃ ድረስ ዕለተ ዕለት ጠንክረን በትዕግሥት መሥራት በመንፈሳዊ ተጋድሎ መጽናት ይገባል፡፡ የመንፈሳዊ ተጋድሎም ዓላማው መንፈሳዊ ሕይወታችንን የሚያቀጭጩ  ከጸጋ እግዚአብሔርም የሚያራቁቱ ኃጢአትና የዲያብሎስ ፈተናን በመቃወም መንፈሳዊ ምግቦችንም በመመገብ አዲሱ ሕይወታችንን ማሳደግ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

‹‹በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ዝቅ አደረገ፡፡›› ፊልጵስዩስ 2፡6

                                                   በማሞ አየነው
 
እነሆ የጨለማው ዘመን አለፈ፡፡ በጨለማ ይኖሩ የነበሩ ሕዝቦችም ብርሃን አዩ፡፡ መላእክትና ኖሎት /እረኞች/ በአንድነት እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ እርቅ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ተደረገ፡፡ የሰው ምኞትም ተፈፀመ፡፡ ሰላም፣ ፍቅር፣ ተስፋ በምድር ሰፈነ፡፡ እነዚህ ሁሉ በክርስቶስ የልደት ገፀ በረከት የተገኙ ናቸው፡፡ ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ በምድር የሚኖሩ ሰዎች በቀቢጸ ተስፋ፣ ሰላም በማጣት ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጭ ሆነው ለብዙ ሺህ ዓመታት ኖረዋል፡፡ የነቢያት ጾም ጸሎት፣ የካህናት መሥዋዕት ምድርን ከኃጢአት ሊያነጻ አልቻለም፡፡ ምድርን ከኃጢአት የሚያነጻት ወልደ እግዚአብሔር ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ በመሆኑ እነሆ አምላክ ሰው ሆነ፡፡ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ›› ዮሐ 1፡29  በማለት ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡ ስለዚህም ነው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በፍፁም ትህትና የሰውን ልጅ ሥጋ ለብሶ ሰው መሆንን የመረጠው፡፡

 በጌታችን ልደት ያገኘናቸውን በረከት እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

             1.ልጅነትን አግኝተናል፡፡

የሰው ልጅ የተፈጠረው በአርአያ እግዚአብሔር ሲሆን የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ስሙን ይቀድስ ክብሩን ይወርስ ዘንድ ነው፡፡ ነገር ግን የምኞት ፈረስ ከልጅነት ይልቅ አምላክነት እንዲመርጥ ገፋፋው፡፡ ስለዚህም ልጅነቱን በፈቃዱ አጣ፡፡ ምንም አንኳን የሰው ልጆች ልጅነታቸውን ቢጥሉ እግዚአብሔር አምላክ ግን አባትነቱን አልተወም፡፡ በነቢያት እያደረ መምህራንን እያስነሳ ዳግመኛ ልጆቹ እንዲሆኑ መክሯል፣ አስመክሯል፣ ‹‹እናት ልጇን እንደምታጽናና እንዲሁ እኔም አጽናናችኋለሁ›› ኢሳ 66:13 በማለት አባትነቱን ተናግሯል፡፡ ይህን ያጣነውን ልጅነት ሊያስመልስልን ወልደ እግዚአብሔር ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍፁም ሰው ሆነ፡፡ ባርነታችን ወደ ልጅነት፣ ባዕድነታችን ወደ ወራሽነት ተለወጠ፡፡ ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንደ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ›› ገላ 4፡7 በማለት አዲስ የታሪክ ምዕራፍ በልደቱ እንዳገኘን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ገልጧል፡፡ በክርስቶስ ልደት ማመን ከልደቱም በረከት መካፈል ልጅነትን የሚያሰጥ ታላቅ ምስጢር ነው፡፡ መጽሐፍም ‹‹የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፤የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም፤ ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው›› ዮሐ 1፡11 በማለት ልጅነታችንን ፍንትው አድርጎ ያሳያል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ልጆቹም ስለሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮህ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ›› ገላ 4:6 በማለት ልጅነታችንን እንዳገኘን ያረጋግጣል፡፡

        2.   ነጻነታችን አግኝተናል፡፡

ሰው ነጻ መሆኑ የሚታወቀው ፈቅዶ በመረጠው ነገር ያለምንም ከልካይ መኖር ሲችል ነው፡፡ ከውድቀቱ በኋላ የሰው ልጅ ያጣው ታላቅ ነገር ቢኖር ነጻ ፈቃዱን ነበር፡፡ ጽድቅን መርጦ በጽድቅ መንገድ ቢጓዝ እንኳ መንግሥቱን ለመውረስ አይችልም ነበር፡፡ ነቢያትም አምርረው ሲያለቅሱ የነበረው ‹‹ጽድቃችን የመርገም ጨርቅ ሆነ›› በማለት ነበር፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ይህን ነጻነታችንን አስመልሶልናል፡፡ ‹‹በነጻነት ልንኖር ክርስቶስ ነጻ አወጣን›› ገላ 5፡1 እንዳለ፡፡ የጌታን ልደት መላእክቱ ለኖሎቱ ሲያበስሩም እንዲህ ብለዋል፡፡ ‹‹ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ›› ሉቃ 2፡14፡፡ ከእስር የተለቀቀ ሰው ነጻ እንደሆነ ሁሉ የሰው ልጅም ለሺህ ዘመናት በዲያብሎስ ግዞት ይኖር ስለነበር በልደቱ ከዚህ እስር በመላቀቁ ነጻነቱን አግኝቷል፡፡

      3.    ሰላማችን ተመልሷል ተስፋችን ተሳክቷል፡፡

በቀደመው ዘመን ከልደተ ክርስቶስ በፊት ሰው ሰላሙን አጥቶ ይኖር ነበር፡፡ ‹‹ የሰላምን መንገድ አያውቁም… መንገዳቸውን አጣመዋል፤ የሚሄዱባትም ሁሉ ሰላምን አያውቁም›› ኢሳ 59፡7 በማለት ሰላም አንዳልነበረ አስረድቷል፡፡ ልደት እውነተኛ ሰላማችንን ያገኘንባት፣ ተስፋችንም የተረጋገጠበት ልዩ ቀን ናት፡፡ ከእግዚአብሔር ፈቃድ በመውጣት ያጣነው ሰላም በልደቱ ተመልሷል፡፡ ሰላምን የሚያድል እርሱ ስለሆነም ‹‹ሰላሜን እሰጣችኋለሁ›› ብሏል፡፡ ለብዙ ዘመናት ሰላምን ብንነፈግም እውነተኛ ሰላምን ያገኘነው በክርስቶስ ልደት ነው፡፡ ‹‹ሰላም በምድር ሆነ›› ብለው መላእክት የዘመሩትም በልደቱ ነው፡፡በልደት ካገኘናቸው ገጸ በረከቶች በተጨማሪ ሌሎች ለሕይወታችን ጠቃሚ የሆኑ መልእክቶችንም አግኝተናል፡፡ በክርስቲያናዊ ሕይወታችን ምሳሌ የሆነ ዐቢይ ቁም ነገሮችንም በልደቱ ገብይተናል፡፡

             ሀ. ትህትና

እግዚአብሔር አምላክ ‹‹እኔ የዋህ በልቤም ትሁት ነኝ›› በማለት ትህትና የባህርይ ገንዘቡ እንደሆነ አስረድቷል፡፡ በልደቱም ወልደ እግዚአብሔር ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለማመን በሚከብድ ፍፁም ትህትና ራሱን ዝቅ አድርጎ ለሰዎች ተገልጧል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያዕቆብ ‹‹በትረ መንግሥት ከይሁዳ አይጠፋም›› ዘፍ 40:9 የሚለው የትንቢት ቃል ተፈጻሚ እንዲሆን ከይሁዳ ወገን ቢወለድም ቅሉ ከይሁዳ ግዛትም ታናሽ በሆነችው ቤተልሔም እንደተወለደ መጻሕፍት ይነግረናል፡፡ ‹‹አንቺም ቤተልሔም ኤፍራታ ሆይ አንቺ ከይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ›› ሚክ 5:2፣ ሉቃ 1:5 ማቴ 1:1 ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከታናሿ ቤተልሔም ለመወለድ የመረጠው በበረት ግርግም ውስጥ ነው፡፡ ሁሉ የእርሱ የሆነ አምላክ ምንም እንደሌለው የሆነው የትህትናን ልዕልና ሊገልጽልን ፈልጎ ነው፡፡ ፍፁም የሆነ ትህትና መገለጫው ያለንን ነገር እንደሌለን መቁጠርና  መተው ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስም ያደረገው ይህንኑ ነው፡፡ ባለፀጋ ሳለ ደሀ ሆነ ፤ ሁሉ የሞላለት ሳለ ማደሪያ ስፍራ አጥቶ በበረት (ግርግም)ተወለደ፡፡ ይህንን ትህትናውን በጥምቀቱ ገልጿል፤ ወደ ፈጠረው ዮሐንስ ሄደ ‹‹እንግዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናል›› በማለት ጽድቅ ለፍፁም ትህትና የሚደረግ ሕይወት እደሆነ አስረድቶናል፤ ማቴ 3:14፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ትህትና እንዲህ በማለት ገልጾታል፡፡ ‹‹የባሪያውን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ዝቅ አደረገ›› ፊሊ 2:6  ‹‹ስለ ሰው ሁሉ ሞትን ይቀምስ ዘንድ ከመላእክት ይልቅ በጥቂት አነሰ›› ዕብ 2፡9 ‹‹ስለዚህ የሕዝቡን ኃጢአት ለማስተሰረይ….በነገር ሁሉ ወንድሞቹን ሊመስል ተገባው›› ዕብ 2፡17 ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመጀመሪያው እስከ ፍጻሜው ያደረጋቸው ነገሮች በሙሉ በትህትና የተደረጉ ናቸው፡፡ ወደ ምድር ሲመጣ ፍፁም ትህትና ባላት በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አድሮ መጣ፡፡ ሲወለድ በቤተልሔም በበረት ግርግም፣ ሲጠመቅ ባገልጋዩ በዮሐንስ እጅ፣ ወደ መስቀል ሲወጣም በፈጠራቸው ፍጡራን እጅ መሆንን ስንመለከት እውነትም እግዚአብሔር የትህትና ባለቤትና የትሁታን ወዳድ መሆኑን እንረዳለን፡፡

            ለ. ፍቅር

እግዚአብሔር ሰውን ለምን ወደደው; ብለን ብንጠይቅ መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠን መልስ ቀላልና ግልፅ ነው፡፡ ‹‹…እንዲሁ…›› ዮሐ 3:16፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውን ለመውደድ /ለማፍቀር/ ምክንያት የለውም፡፡ ኃጢአተኛና ጻድቅ፣ ንጹሕና ቆሻሻ፣ ምሁርና ያልተማረ፣ የሚል መመዘኛም በአምላክ ዘንድ የለም፡፡ እግዚአብሔር እንዲወደን ሰው መሆናችን ብቻ በቂ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሰውን ከማፍቀሩ የተነሳ ዓለምን እንዲያድን አንድያ ልጁን ወደ ዓለም ላከው፡፡ በልደትም የምናየው ይህን የአምላካችንን ልዩ ፍቅር ነው፡፡ ቀድሞ በነቢያት ‹‹በዘላለም ፍቅር ወድጃችኋለሁ›› ኤር 31:3 በማለት ፍቅሩን ገልጦ ነበር፡፡  ይህን ፍቅሩን ደግሞ በልደቱ በይበልጥ ገለጠው፡፡ ሰውን ለመውደድ ምክንያት የምናበዛ ሰዎች ስንቶች ነን? ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በልደቱ ያሳየንን ግሩም ፍቅር ለእህት ለወንድሞቻችን በማሳየት ክርስቶስን በግብር ልንመስለው ይገባል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር ወርዶ በበረት ግርግም የተወለደው እስከ መስቀል ሞትም የደረሰው ለሰው ልጅ ባለው ፍፁም ፍቅር መሆኑን መገንዘብ ያደረገውን የትህትና ስራ መመልከት የልደትን መንፈሳዊ ምስጢር እንድንረዳ ያደርገናል፡፡ ካለዚያ ልደትን ለመታሠቢያነት ብቻ ከማክበር የዘለለ ፋይዳ አይኖረውም፡፡ በእግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረ ሰውን ፍፁም በሆነ ፍቅር መውደድ ከባድ ቢሆንም እንኳ የማይቻል ነገር ግን አይደለም! ሰውን መውደድ ቀስ በቀስ እየዳበረ እስከ ፍጽምና የሚያደርስ መንፈሳዊ ሀብት ነው፡፡ በፍቅር ላይ ያልተመሠረተ መንፈሳዊ ሱታፌ፤ መንፈሳዊ ሕይወት መጨረሻው አያምርም፡፡ በፍቅር ላይ የተመሠረተ ሕይወት ‹‹በሁሉ ይጸናል›› 1ኛ ቆሮ 13:7 የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደትም የፍቅር የመጨረሻው ማሳያ መሆኑን መገንዘብ ሕይወታችንን በዚህ መነጸርነት እንድናይ ያግዘናል፡፡

                  ሐ. ተስፋን መፈጸም፡-

እስራኤል ዘሥጋ የመሲሑን መምጣት በተስፋ ሲጠብቁ ቢቆዩም የክርስቶስን ሰው ሆኖ መምጣት ለመቀበል ዳተኞች ነበሩ፡፡ መጽሐፍም ‹‹የገዛ ወገኖቹ አልተቀበሉትም›› ዮሐ 1:7 ይላል፡፡ ነቢያት በሙሉ እግዚአብሔር የሰው ዘር ማዳኑን በተስፋ ሲጠብቁ ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ተስፋውን ሊፈጽም አንድያ ልጁን ወደ ምድር ላከ፡፡ ተስፋችንም ተፈጸመ፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ‹‹ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ›› ገላ 4:4 ይላል፡፡ ነቢያት ይህን ቀን በተስፋ ሲጠብቁ እንደነበር በትንቢታቸው ገልጸዋል፡፡ ኢሳ 7:14 ፣ ኢሳ 9:6 ፡፡ አምላካችን ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ የሰጠን ነገር ቢኖር ተስፋን ነው ‹‹እነሆ አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ፡፡›› ዘፍ 3:22 በማለት ሰው ሆኖ ወደ ምድር እንደሚመጣ ተስፋን ሰጠን፡፡ ይህንም ተስፋ ይዘን ለሺህ ዘመናት በጉጉት ጠበቅን ነቢዩ አንደተናገረው አምላክ ጻሕቀ ልቡናችን ፈጸመልን፡፡ ‹‹ሣሩ ይደርቃል አበባውም ይረግፋል፤ የአምላካችን ቃል ግን ለዘላለም ጸንታ ትኖራለች›› ኢሳ 40:80 ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው የገባውን ቃል አስታውሶ ወደ ምድር እንደመጣ ሁሉ በእርሱ ስም የሚጠሩ ክርስቲያኖችም የገቡትን ቃል፣ የሰጡትን ተስፋ በመፈጸም አምላካቸውን መምሰል ይገባቸዋል፡፡ የተሰጣቸውን ሥራ በጊዜ የማይጨርሱ፣ ጉባኤ የሚያስተጓጉሉ፣ ሰው ቀጥረው ሲያረፍዱ እንኳ ቅንጣት የማይሰማቸው ክርስቲያኖች ካሉ በእውነትም በልደት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረንን ቀጠሮ የማክበር ቃልን የመጠበቅ አሰረ ፍኖት የዘነጉ መሆናቸውን መረዳት አለባቸው፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት የሚያስተላልፈው ዐቢይ መልእክትም ይህን  ነው፡፡ ‹‹ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም›› እንደተባለ በቃላችን የምንገኝ፣ ባልነው የምንጸና ተአማኒ መሆን ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል፡፡

ባጠቃላይ በልደቱ ያገኘናቸውን ሀብታት በመጠበቅ፣ የተማርናቸውን ትምህርቶች በመፈጸም እውነተኛ የልደት በዓል ተካፋዮች መሆን ይገባናል፡፡ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ሰማያውያን መላእክት ከምድራውያን እረኞች ጋር በአንድ ላይ እንዳመሰገኑ እኛም በዝማሬና በምስጋና በፍፁም ደስታ ልናመሰግን ይገባል፡፡

                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በጎ ያልሆኑ ተጽእኖዎች በክርስትናችን

በማሞ አየነው
 
በተደጋጋሚ ከሚያጋጥሙኝ ክስተቶች አንዱ ይህ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከምተዋወቀው አንድ ልጅ ጋር ቁጭ ብለን እየተጨዋወትን ነው፡፡ ልጁን የማውቀው ሰ/ት/ቤት ውስጥ ታታሪ አገልጋይ በነበረበት ጊዜ ነበር፡፡ አሁን ከመንፈሳዊ አገልግሎቱ ራሱን አግልሏል፡፡ እንደድሮው ስለመንፈሳዊ ሕይወቱ የሚያወያየው ለአገልግሎት የሚጋብዘው፣ ሲደክም የሚያበረታው፣ ሲሰለች መንፈሱን የሚያድስለት፣ ጓደኛ የለውም፡፡
 
ከሚሳተፍባት አጥቢያ  ሰ/ት/ቤት መራቁን እንደ ትልቅ ምክንያት እያነሳ በተደጋጋሚ ነገረኝ ምክንያቱ አልተዋጠልኝም፤የራቀው ከአንድ አካባቢ እንጂ ቤተ ክርስቲያንና ሰ/ት/ቤት አሁን ካለበት አካባቢ እንዳለ አውቃለው፤ ከተለያየን በኋላ ስለጉዳዩ በደንብ አሰብኩበት፡፡ ይህ ችግር የብዙ ሰዎች ችግር እንደሆነ በተደጋጋሚ እናያለን፤ ራስን ከሚያገኛቸው ሁኔታዎች ጋር አስማምቶ ክርስቲያናዊ ሕይወትን በጊዜና በቦታ የመገደብ፣ ራስን ከሚያገኛቸው ሁኔታዎች ጋር አስማምቶ ክርስቲያናዊ ሕይወትንና አገልግሎትን የማስኬድ ችግር የብዙዎች ችግር ነው፡፡ ይህም አንድ ነገር እንዳለ ያመላክተናል።ይህም ክርስትናችን የቆመበት መሠረት በነፋስና በጎርፍ ተጠራርጎ ለመውደቅ ቅርብ መሆኑን ነው። ለዚህ ነው ጥቃቅን ምክንያቶች ግዙፍ የሚመስለንን ግን ያልሆነውን ክርስትናችንን አደጋ ላይ የሚጥሉት የሁሉም ነገር መነሻ መሠረቱ ነውና፡፡ ክርስትናም የራሱ መሠረት አለው፡፡ እስኪ በተረጋጋ መንፈስ ክርስትናችን የተገነባበትን እንመርምር፡፡ በክርስቲያናዊ ሕይወታችን ውስጥ ልብ ልንላቸው የሚገቡ ነገር ግን እንደዋዛ የምናያቸውን ነጥቦችን እንደሚከተለው እንመለከታለን፡-

ሀ.  በሌሎች ጫንቃ ያረፈ ክርስትና ነው ያለዎት?

ሁሌም ልብ ልንለው ከሚገቡ ነጥቦች አንዱ ክርስትናችን ማንን ተስፋ እንዳደረገና በማንስ ላይ ተስፋውን እንደጣለ መረዳት ነው፡፡ የብዙዎቻችንን መንፈሳዊ አይን ሸፍኖ ዋናውን ነጥብ እንዳናይና የሚያደርጉ ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ በአካባቢያዊና በአጥቢያ ላይ የተመሠረተ የአገልግሎተ ፍቅር፣ በማኅበራት ትክሻ ላይ የተንጠላጠለ ሱታፌ፣ ከጓደኝነትና ከመላመድ የመነጨ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ዋናውን የክርስትና ዓላማ  እንዳንረዳ ከሚያደርጉን መሰናክሎች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ እነዚህ ነጥቦች ለክርስትናችን እንደ ግብዓት የሚታዩ እንጂ የአገልግሎታችንና የክርስቲያናዊ ሕይወታችን መሠረቶች ሊሆኑ አይገባም፡፡ ልብ ብሎ ራስን መመርመር የሚገባም ለዚሁ ነው፡፡
ግድግዳና ጣሪያ ብቻ ለቤት መሠረት ሊሆኑ እንደማይችሉ ሁሉ በሰው በማኅበር መሠባሰብ ላይ የተመሠረተ ክርስትናም ዘላቂነት የለውም፡፡ ብዙዎች ከሚያገለግሉበት አጥቢያ ሲርቁ፤ በክርስትና ከሚያውቋቸው ጓደኞቻቸው ሲለዩ ከቤተክርስቲን ለመራቅ ያስባሉ፡፡ ክርስትና እዚያና እዚህ ብቻ ያለ ይመስላቸዋል፤ ክርስቲያናዊ ሕይወት የእነ እገሌ ተሰጥዖ  ብቻ አድርገው ይወስዳሉ፤ ቀስ በቀስም ተስፋ የመቁረጥና የብቸኝነት ስሜት በልባችን ሰርጾ ይገባል፡፡ ከለመድነው አሰራርና አካሄድ የተለወጠ ነገር ባየን ቁጥር እየበረገግንና እየራቅን እንመጣለን። ስለዚህ በድሮው ክርስትናችን መቀጠል ይከብደናል፡፡ ዴማስ ከለመደው ከተማና ሁኔታ የተለየ ሁኔታ ስለገጠመው ነበር በተሰሎንቄ ተስቦ የቀረው /2ኛ ጢሞ/ ብዙዎች የተሰናከሉት የሰው ልጆችን ኑሮ በማየታቸውና ከለመዱት የአኗኗር ዘየ የተለየ ነገር ስለገጠማቸውና ስለተሸነፉለትም ነበር። /ኩፋ 6፥9 ዘፍ 6፥1/  የያዕቆብ ልጅ ዲናም ከክብር ያነሰችው የለመደችውን የአህዛብ አኗኗር መቋቋም አቅቷት ነበር፡፡ ዘፍ 34፥1 የብዙዎቻችንም ክርስትና እንዲሁ ለፈተና የተጋለጠ ነው፡፡ አካባቢን ከመለወጥ ይልቅ እኛው ተለውጠን ክርስትናችን ደብዛው የጠፋብን ብዙዎች ነን፡፡ የማኅበረ እስጢፋኖስ መበታተን ክርስትናን የበለጠ እንዲስፋፋ አደረገ እንጂ ክርስትናቸውን አላጠፋባቸውም፡፡ በጊዜና በቦታ ሳይወሰኑ አሐቲ የሆነችውን ቤተክርስቲያን ማገልገል የቤተክርስቲያንን የአገልግሎት ሁኔታ የመረዳትና የክርስትናንም ውል የመያዝ ምልክት ነው፡፡ ከመንፈሳዊ ሩጫችን ጎን ለጎን ልናስተውለውና ልንረዳው የሚገባን ቢኖር እያገለገልኩና እየሮጥኩ ያለሁት ከራሴ በሚመነጭ መንፈሳዊ ግፊት ነው ወይስ በስብሰባ ድምቀት ልምድ ስለሆነብኝ? ወይንም ከሰ/ት/ቤት ልጆች መራቅ ስላልፈለግሁ ነው የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ ነው፡፡

ለ. ከአፍአዊ አገልግሎትና ምስጢራት ከመሳተፍ የቱን ያስቀድማሉ?

በሚገባ አስተውለንና አጢነን ከሆነ ብዙ ጊዜ መንፈሳዊ ሩጫ ውስጥ የገቡ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ምስጢራት መሳተፍ ያቆማሉ፡፡ ከኪዳን፣ ከቅዳሴ፣ ከሥጋ ወደሙ የራቁ ነገር ግን ሩጫ የሚያበዙ፣ መረጋጋት የማይታይባቸው፣ በአፍአ (በውጭ) ያሉ ብዙ ጓደኞች አሉን፡፡ መንፈሳዊ በሆነ ኃይልና ዕውቀት ከማገልገል ይልቅ በስጋ ድካም ማገልገል የበለጠ ውጤት የሚስገኝ ስለሚመስላቸው ቅዳሴና ኪዳን ለነሱ ቦታ የላቸውም፤ እንደዚህ ዓይነት አገልጋዮች ይህን ከመሰለው እንቅስቃሴ ሲለዩ የክርስትና መስመር የተበጠሰ ይመስላቸዋል፡፡ የዚህ ሁሉ እንቅስቃሴ ዓላማ ሰውን ምስጢራት ወደ ማሳተፍ ማምጣት መሆኑን ይዘነጉታል፡፡
የማርታና የማርያምም ታሪክ የሚያስተላልፍልን መልእክት ይህንን ነው፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን መስማት የሚቻለው ከቅዳሴው ምስጢር መሳተፍ ስንችል ነው፡፡ በቅዳሴ ቃለ እግዚአብሔርን ሰምተን ብቻ አንበተንም፤ ለሥጋ ወደሙ ያዘጋጀናል፡፡ ዋናው የክርስትና ግብም ይህን ምስጢር መሳተፍ ነው።   ጌታችንም ሐዋርያትን ካስተማረና አእምሮአቸውን ካዘጋጀ በኋላ በመጨረሳ ሰዓት የተናገራቸው  ታላቅ ነገር ቢኖር ምስጢራትን እንዲፈጽሙ ማድረግ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው በምሴተ ሐሙስ ሥጋውና ደሙን ያቀበላቸው፡፡ማቴ 26፥26 መንፈሳዊ አገልግሎት ላይ ያለን ሰዎችም ልናስተውለው የሚገባን ታላቅ ምስጢርም ይህ ነው፡፡ ዕውቀትን ከማጎልበት፣ ለሌሎች መዳን ደፋ ቀና ከማለት በተጨማሪ ምስጢራትን መሳተፍና መፈፀም ይገባናል፡፡ በምስጢራት መሳተፍ ያልለመደ አገልጋይ ክርስትና ሰ/ት/ቤት፣ ማኅበራት ጋር፣ ከጓደኞቹ ዘንድ ብቻ ያለ ስለሚመስለው ከነዚህ ሲርቅ ክርስትናው ከገደል አፋፍ ላይ ይቆማል፡፡ ከምንም ነገር በላይ በምስጢራት መሳተፍ መልመድ ከቤተክርስቲያን እንዳንርቅ የሚያስተሳስረን ሕቡር ገመድ ነው፡፡ ይህን የለመደ ሰው የትም ሄደ የት ከምስጢሩ አይርቅም፡፡ ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ማስተካከል የሚገባንም ከዚህ መሠረታዊ ነጥብ ጋር ነው፡፡

ሐ. እውን ሕይወትዎን እየመሩ ያሉት ለሰው ወይስ ለእግዚአብሔር?

ህገ እግዚአብሔርን እየፈጸ ምን ያለነው በእውነተኛ የእግዚአብሔር ፍቅር ተመክረን ነው ወይስ ከመንጋው ላለመለየትና ከነቀፌታ ለመራቅ ብለን ነው? ቤተ እግዚአብሔር የምንሄደው፣ የምናስቀድሰው፣ የምናገለግለው፣ … ከሰው ምላሽን ጠብቀን ከሆነ ጽድቃችን ከፈሪሳዊያን በምን ይለያል? ፈሪሳውያንና ጸሐፍት ህጉን የሚፈጽሙት ለጽድቅ ብለው ሳይሆን የሙሴን ህግ ይፈጽማሉ ለመባል ብቻ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን ‹‹ ጽድቃችው ከፈሪሳውያን ጽድቅ ካልበለጠ ….›› ብሎ ያስተማረ፡፡ እያንዳንዱ የሕይወታችን ጥቃቅን ነገር መመርመር ያለብንም ያደርጋሉ ይፈጽማሉ ለመባል ሳይሆን የጌታ ፍቅር ገብቶንና ደስ እያለን በፍጹም ተመስጦ መሆን ይገባል፡፡ ፍፁም በሆነ ፈቃድ ያለተርእዮ ህግን መፈጸም ግን ጽድቃችንን ከሰው ተጽእኖ የጸዳ ያደርገዋል፡፡ ጌታም በወንጌሉ ‹‹ ቀኝህ የሚያደርገውን ግራህ አይመልከት›› ያለው ለታይታና ለሆይ ሆይታ ተብሎ ጽድቅን መፈጸም እንደማይገባን ሲያስረዳን ነው፡፡ በዚህ መነሻነት ጽድቅን አለመፈጸም ከጓደኛ ሲለዩ’ ከሚያውቁት ማኅበረሰብ ሲወጡ ክርስትናችንን ፈተና ላይ ይጥላቸዋል፡፡ ህግ የተሰጠ ከእግዚአብሔር ስለሆነ መፈጸም ያለበት ስለእግዚአብሔርና ለእግዚአብሔር ተብሎ ብቻ ነው፡፡ መጽሐፍም ‹‹ የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ›› ይላል ለሰው’ ለጓደኛ’ለማህበረሰብ  ብሎ ህግን መፈጸም የእግዚአብሔርን ለሌላ እንደመስጠት ይቆጠራል። ነገሮችን ለእግዚአብሔር ብሎ መፈጸም ክርስትናችን በጊዜ፣ በቦታና በሁኔታ እንዳይወሰን ያደርጋል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር የሌለበት  ቦታ፣ ጊዜና ሁኔታ የለምና ነው፡፡ ስለዚህም የትም ሆን የት ከእግዚአብሔር እቅፍ መውጣት አንፈልግም፡፡ ከእግዚአብሔር መራቅ ለሰከንዶች እንኳን ሳናቋርጥ ከምንወስደው አየር እንደመለየት ነው፤ አየር ለመውሰድ ጊዜና ቦታን እንደማንመርጥ ሁሉ ከእግዚአብሔር ከአገልግሎት ላለመራቅም ጊዜና ቦታ መምረጥ አይገባም፡፡
ከላይ የተጠቀሱትን ነጥቦች በማስተዋል ክርስትናችንን በጎ ካልሆነ ተጽእኖ ማጽዳት አስፈላጊ ከመሆኑም በላይ መንፈሳዊ ሕይወታችን በጊዜና በቦታ እንዳይወሰን ለማድረግ ጠቃሚ ነው፡፡ እነዚህን ሀሳቦች እናስተውል ዘንድ አስተውለንም እንተገብራቸው ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ልቦናችንን ያነቃቃል!!  አሜን።
                                                            
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሐዘን ሲገጥመን ምን እናድርግ? / 2ቆሮ 5÷1-5 /

ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ
 
የምንወደው ሰው በሞት ከእኛ ሲለይ በእጅጉ እናዝናለን፤ እናለቅሳለንም፡፡ በርግጥም ማልቀስ በአግባቡ ከሆነ ጠቃሚና አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ በመሪር ሐዘን የተቆጣውን ሰውነታችንን የሚያስተነፍስ መፍትሔ፤ዕንባ፡፡ የውስጥ ሰውነቱ ፈሳሽ ነገር ቋጥሮበት ወይም በእግርና በእጁ ላይ መግል የቋጠረ የቁስል ጥዝጣዜ ዕረፍት የነሣው ሰው የቋጠረውን ፈሳሽ ወይም የሚጠዘጥዘውን መግል ሲያፈሱለት ደስ እንደሚለውና ዕረፍት እንደሚሰማው በሐዘን ውስጡ የተጎዳ ሰውነትም ዕንባ ሲያፈስ ዕረፍት ማግኘቱ አይቀሬ ነው፡፡

እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ዕንባ እንዲኖረው አድርጎ የፈጠረውም ዕንባ ጠቃሚና አስፈላጊ በመሆኑ ነው፡፡ እስከ አሁን በምናውቀው እንኳ ሦስት ከፍተኛ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡

የመጀመሪያው ጠቀሜታው ዕንባ በሰው ልጅ ታሪክ ከተጀመረበት ጊዜ አንሥቶ ያለው ነው፡፡ ዕንባ የተጀመረው በአዳምና በሔዋን ነው፡፡ ያለቀሱትም አትብሉ የተባሉትን ዕፀ በለስ በልተው እግዚአብሔርን በመበደላቸው   ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ ዕንባ የተጀመረው በንስሐ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ከዚያ በፊት በሰውነታቸው ያልነበረ ነገር ተፈጠረ ማለት አይደለም፡፡ በሩካቤ መተዋወቃቸውን /የተዋወቁበትን ጊዜ/ ይዘን በዚያ ጊዜ የመራቢያ ብልታቸው ተገኘ እንደማንለው ዕንባውም እንዲሁ ነው፡፡ በቀሌምንጦስ «አልቦቱ ካልዕ ሕሊና ለአዳም ዘእንበለ ብካይ ላዕለ ኃጢአቱ፤ ለአዳም ስለ ኃጢአቱ ከማልቀስ /ኃጢአቱን እያሰበ ከማልቀስ/ በቀር ሌላ አሳብ /ግዳጅ/ አልነበረውም» ተብሎ እንደተጻፈ ዕንባ የተጀመረው በዚህ ነው፡፡ ስለዚህ የዕንባ ቀዳሚ ጠቀሜታ ሰውን በንስሐ ከእግዚአብሔር ጋር ማስታረቅ ነው ማለት ነው፡፡ ይህም በመጽሐፍ ቅዱስ ተደጋግሞ ተመዝግቧል፡፡ «ወበአንብዕየ አርሐስኩ ምስካብዬ፤ በዕንባዬም መኝታዬን አርሳለሁ» የሚለው ቅዱስ ዳዊት የንስሐ ዕንባውን፣ የጸሎት ዕንባውን ነው፡፡ /መዝ 6÷6/ ጌታችንም በወንጌል «ብፁዓን እለ ይላህው ይእዜ እስመ እሙንቱ ይትፌስሑ፤ ዛሬ የሚያዝኑና የሚያለቅሱ የተመሰገኑ ናቸው፣ መጽናናትን ያገኛሉና» /ማቴ 5÷4/ ሲል ያስተማረው የሚገባው ለቅሶ ወይም ዕንባና ሐዘን የንስሐ መሆኑን ያስረዳናል፡፡ በሌላም ቦታ «እናንተ አሁን የምትስቁ ወዮላችሁ፣ ታዘናላችሁና፣ ታለቅሱማላችሁ» /ሉቃ 6÷25/ ሲል ያስጠነቀቀን ጠቃሚውን ዕንባና ሐዘን ለማስተማር ነው፡፡ መፍቀሬ ጥበብ ሰሎሞንም «ከሳቅ ሐዘን ይሻላል፣ ከፊት ኀዘን የተነሣ ደስ ይሰኛልና፤ የጠቢባን ልብ በልቅሶ ቤት [በንስሐ] ነው፤ የሰነፎች ልብ ግን በደስታ ቤት [ኃጢአት በሚፈጸምበት ቦታ] ነው» በማለት የንስሐ ዕንባን መፈለግ ጠቢብነት እንደሆነ ይነግረናል፡፡ከዚህም በላይ በቅድስና ሕይወት የሚኖሩ ቅዱሳን በዐሥሩ መዓርጋት ሲሸጋገሩ አራተኛው መዓርግ አንብዕ ይባላል፡፡ ይህም ፊታቸው ሳይከፋውና ሰውነታቸው ሳይሰቀቅ ዕንባን ከዓይናቸው ማፍሰስ ነው፡፡ ስለዚህ ዕንባ ይህን የመሰለ ጠቀሜታ ያለው በመንፈሳዊነትም የብቃት ደረጃ ሆኖ እናገኘዋለን ማለት ነው፡፡

ሁለተኛው ጠቀሜታው ደግሞ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ማንኛውም ሰው በዓይኑ ላይ ሁልጊዜም ስስ የሆነች የዕንባ ሽፋን አለችው፡፡ ሳይንስም ጭምር እንደ ተረጋገጠው ዓይንን በከፍተኛ ደረጃ ከሚጠብቁት ነገሮች አንዷና ዋናዋ ይህች ዕንባ ናት፡፡ ስለዚህ በነፋስ፣ በፀሐይ፣ ጨረርና በመሳሰለው ከፍተኛ ጉዳት እንዳይደርስበት ይህች ዕንባ ትከላከልለታለች፡፡ በነፋስና በሙቀት ደርቃ እንዳታልቅም እግዚአብሔር በጥበብ እንድንጠቀምባት አድርጓል፡፡ ማንኛውም ሰው ዓይኑን ጭፍን አድርጎ ሲከፍተው በዓይኑ ላይ የነበረችውን ስስ የዕንባ ሽፋን ገፍቶ ወደ አፍንጫ በሚያወርደው ቀዳዳ ያስወግድና አዲስ ዕንባ ይተካል፡፡ በዚህ መንገድ በየደቂቃው ወይም ዓይናችንን ጭፍን ግልጥ ባደረግን ቁጥር ይህችን የዕንባ ሽፋን በአዲስ መልክ     ስለምንቀይር ዓይናችንን በረቂቅ መንገድ እንጠብቃለን፡፡ የሀገራችን ሰው «የዓይን አምላክ» የሚለው ለዓይን ይህን የመሰለ ሰፊ የጥበቃ መንገዶችን እግዚአብሔር ስለፈጠረልን ነው፡፡ በመጽሐፍም «ዕቀበኒ እግዚኦ   ከመ ብንተ ዓይን፤ አቤቱ እንደ ዓይን ብሌን ጠብቀኝ» የሚል ቃል ተጽፏል፡፡ ስለዚህ ዕንባ ዓይንን እንዲህ አድርጎ ለመጠበቅ ጠቃሚ ነው ማለት ነው፡፡

ሦስተኛው ጠቀሜታው ደግሞ ሐዘንን ማስወገጃ ማስተንፈሻ የሐዘን ማቅለያ መሆኑ ነው፡፡ ከዛሬው የጽሑፋችን ዓላማ ጋር የሚገናኘውም ይኽኛው ነው፡፡ የመጀመሪያው  አባታችን አዳም የመጀመሪያ ልጁ አቤል በሞተ ጊዜ እጅግ ተጨንቆ ሰውነቱ ሁሉ አባብጦ ተነፋፍቶም እንደነበር ትውፊቱን የመዘገቡ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ በመጀመሪያ ሞት ከዚያ በፊት አይታወቅምና ምን ማድረግ እንደነበረባቸው እንኳን አዳምና ሔዋን አያውቁም ነበር፡፡ ዳግመኛም በዚያ ጊዜ     የመጀመሪያዎቹ ሰዎች በምድር ላይ እነርሱ ብቻ ናቸውና የሚያጽናናቸውም ሆነ የሚመክራቸው ሰው ማንም አልነበረም፡፡ በዚህ ምክንያት አዳም ሰውነቱ በሐዘን ተዋጠ፤ ተጨነቀ፤ ሰውነቱም ተቆጣ፤ ታመመም፡፡ በዚህ ጊዜ መላእክት ወደ አዳም መጥተው እንዲያለቅስ አሳዩት፤ አስተማሩት፡፡ እርሱም ሲያለቅስ ውጥረቱ በረደ፤ የተቆጣ አካሉ ተመለሰ፤ ሰውነቱም ዕረፍት አገኘ፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በሐዘን የሚገጥመንን የሰውነት መታመምና ከባድ ጭንቀት በዕንባ መገላገሉን ይዘን ይኸው እስከ አሁን ዘልቀናል፤ ወደፊትም እንቀጥላለን፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አልዓዛርን ከተቀበረ ከአራት ቀናት በኋላ ከሞት ሊያስነሣው ሲሔድ በእኅቶቹ ቤት እንደደረሰ መጀመሪያ አልቅሶለታል፡፡ /ዮሐ 11/፡፡ ይህም በሞት ለተለየን ሰው በሐዘን ጊዜ ማልቀስ ተገቢ መሆኑን ይህንም በማድረጋችን ኃጢአት እንደማንሠራ ያስረዳናል፡፡ ጌታ ቸር አምላክ፣ ሰውንም ወዳጅ ነውና ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ከሞት እንደሚያስነሣው እያወቀ እኅቶቹን ሲያገኛቸው መጀመሪያ ሐዘናቸውን በልቅሶ ተካፈለ፡፡ ከዚያም እነርሱን አጽናንቶ ሞቶ የተቀበረውን ከሞት አሥነሥቶ ከመቃብር አውጥቶታል፡፡ በዚህም እጅግ ብዙና ሰፊ ትምህርቶችን አስተምሮናል፡፡

ለክርስቲያኖች በሐዘን ጊዜ ማድረግ ስለሚገባቸውና ስለማይገባቸው ነገሮች መሠረታዊ የሆኑት የትምህርት መነሻዎች ከላይ የጠቀስናቸው እነዚህን የመሰሉት በቅዱሳት መጻሕፍት የተገለጡት ታሪኮች ናቸው፡፡ ምንም እንኳን በሞት ለተለየን ቤተሰባችን የተሰማንን ሐዘን በለቅሶና በዕንባ መገላገል ተገቢ ቢሆንም ለእነዚህም ጊዜና መጠን አላቸው፡፡

በጊዜ ያልተወሰነ በመጠን ያልተገደበ ከሆነ እንኳን ሐዘን፣ ለቅሶና ዕንባ ቀርቶ ደስታና ጨዋታም በእጅጉ ጎጂ ነው፡፡ ቀደም ብለን እንደገለጽነው ሐዘንን በዕንባ መገላገል ጠቃሚና እግዚአብሔር የፈቀደው ቢሆንም   ከመጠኑ ሲያልፍ ደግሞ ከጥቅሙ በተቃራኒ በእጅጉ ይጎዳል፡፡ በበጋ የደረቀች መሬትን ለማርጠብ፣ ለማለስለስና እህሉንና ሣሩን ለማብቀል የክረምት ዝናም አስፈላጊና ጠቃሚ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከመጠን በላይ ከወረደ ግን እርሻውን አጣጥቦ በመውሰድ፣ የበቀለውን አዝመራ በማጥፋት ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል፡፡ ለቅሶና ዕንባም እንዲሁ ነው፡፡ ዓይንን ለመጠበቅና ሰውነታችን በሐዘን እንዳይጎዳ ለመከለካል የተፈጠረውን ዕንባ ስናበዛው ዓይናችንን ለማጥፋት፣ ሰውነታችንም ጎርፍ እንደበላው መሬት ሸርሸሮ ለማይድን በሽታ    ያበቃዋል፡፡ ስለዚህ ልክና መጠኑን ጠብቆ በጊዜ ተወስኖ የሚፈጸም ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም «እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የሆነ ኀዘን ጸጸት የሌለበትን፣ ወደ መዳንም የሚያደርሰውን ንስሐ ያደርጋልና፡፡ የዓለም ሐዘን ግን ሞትን ያመጣል፡፡» /2ቆሮ 7÷10/ የሚለን ለዚህ ነው፡፡

አንድ ሰው ከቤተሰብ አንዱ በተለየው ጊዜ የሚያደርገው ነገር በመጠንና በሥርዓት ካልሆነ እንኳን ሥጋውን ነፍሱንም ጨምሮ ይጎዳዋል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ በሐዘናቸው ምክንያት እግዚአብሔርን ያሳዘኑ እርሱም   ያዘነባቸው ሰዎች አሉ፤ እንዲሁም ደግሞ በሐዘናቸው እግዚአብሔርን ደስ ያሰኙ ሰዎች አሉ፡፡ በወንጌል እንደተጻፈው የሰማዩን ቤት የማያስቡ፤ በጎ የሠሩ ሰዎች በሰማይ ከእግዚአብሔር የሚቀበሉትን በጎ ዋጋ ረስተው የሰውን ሞት ተስፋ እንደሌለው እንደ እንስሳ እና እንደ አራዊት ሞት ወይም ተቆርጦ እሳት በልቶት አመድ እንደሚሆን ካለበለዚያም ወድቆ በስብሶ አፈር ሆኖ እንደሚቀር እንደ ዛፍ እንደ ቅጠል ቆጥረው መሪር ሐዘን የሚያዝኑ ሰዎች ሰነፎች ናቸው፤ እግዚአብሔርን ያሳዝናሉ፤ እግዚአብሔርም ያዝንባቸዋል፡፡ «ሙታናቸውን ይቀብሩ ዘንድ ሙታንን ተዋቸው» ብሎ ጌታ በወንጌል የተናገረላቸው ሰዎች የሰውን ክብር እና የእግዚአብሔርን ኃይል ለማያውቁ ሰዎች ነው፡፡ እንደዚህ ያሉት ሰዎች «ሙታን» የተባሉት በምድር ላይ በሕይወት እየኖሩ ነው፡፡ ሙታን የተባሉት የሞተ ሰው ሥጋው ምንም ሊያውቅ እንደማይችል እነዚህም እየኖሩ የማያውቁና የማያስታውሱ ስለሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ክርስቲያን ትንሣኤ  እንደሌለን በሰማይ በአባታችን ቤትም ክብርና ጸጋ እንደማይጠብቀን አድርጎ የሚያዝንና የሚያለቅስ ከሆነ እግዚአብሔርን የሚያሳዝን እንደተጻፈውም ቆሞ የሚሔድ ነገር ግን የሞተ ይሆናል፡፡

በተጠቀሰው መንገድ እግዚአብሔርን ያሣዘኑ ሰዎች እንዳሉ ሁሉ እግዚአብሔርን ያስደሰቱትም ደግሞ አሉ፡፡ ከእነዚህ አንዱና ዋናው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተገለጸው ዳዊት ልጁ በታመመ ጊዜ በእጅጉ አዝኖ ነበር፡፡ ከሞተ በኋላ ግን ያደረገው ብዙዎችን አስገርሟል፤ አርአያነቱም ታላቅ ነው፡፡ ታሪኩን የሚነግረን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡፡ «እግዚአብሔርም የኦርዮ ሚስት ለዳዊት የወለደችውን ሕፃን ቀሰፈ፣ እጅግም ታምሞ ነበር፡፡ ዳዊትም ስለ ሕፃኑ እግዚአብሔርን ለመነ፤ ዳዊትም ጾመ፣ ገብቶም በመሬት ላይ ተኛ፡፡ የቤቱም ሸማግሌዎች ተነሥተው ከምድር ያነሡት ዘንድ በአጠገቡ ቆሙ፤ እርሱ ግን እንቢ አለ፣ ከእነርሱም ጋር እንጀራ አልበላም፡፡ በሰባተኛውም ቀን ሕፃኑ ሞተ፡፡ የዳዊትም ባሪያዎች ሕፃኑ በሕይወት ሳለ ብንነግረው አልሰማንም፤ ይልቁንስ ሕፃኑ እንደሞተ ብንነግረው እንዴት ይሆን ?» በነፍሱ ክፉ ያደርጋል ብለው ሕፃኑ እንደሞተ ይነግሩት ዘንድ ፈሩ፡፡ ዳዊትም ባሪያዎቹ በሹክሹክታ ሲነጋገሩ ባየ ጊዜ ዳዊት ሕፃኑ እንደሞተ አወቀ፤ ዳዊትም ባሪያዎቹን ሕፃኑ ሞቶአልን? አላቸው፡፡ እነርሱም፡- ሞቶአል አሉት፡፡ ዳዊትም ከምድር ተነሥቶ ታጠበ፣ ተቀባም፣ ልብሱንም ለወጠ፤ ወደ እግዚአብሔርም ቤት ገብቶ ሰገደ፡፡ ወደ ቤቱም መጣ፣ እንጀራ አምጡልኝ አለ፤ በፊቱም አቀረቡለት፣ በላም፡፡ ባሪያዎቹም፡- ይኽ ያደረግኸው ነገር ምንድር ነው? በሕይወት ሳለ ስለ ሕፃኑ ጾምህና አለቀስህ፤ ከሞተ በኋላ ግን ተነሥተህ እንጀራ በላህ አሉት፡፡ እርሱም፡- ሕፃኑ ሕያው ሳለ እግዚአብሔርም ይምረኝ፣ ሕፃኑም በሕይወት ይኖር እንደሆነ ማን ያውቃል? ብዬ ጾምሁ፤ አለቀስሁም፡፡ አሁን ግን ሞቶአል፤ የምጾመው ስለምንድር ነው? በውኑ  እንግዲህ እመልሰው ዘንድ ይቻለኛልን?  እኔ ወደ እርሱ እሔዳለሁ እንጂ  እርሱ ወደ እኔ አይመለስም አለ፡፡» /2ሳሙ 12÷15-23/፡፡ በዚህ ታሪክ ውስጥ ንጉሡ ዳዊት ልጁን ምን ያህል ይወደው እንደነበር፤ ከዙፋኑ ወርዶ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ፤ ማቅ ለብሶ አመድ ነስነሶ በጾምና በጸሎት እንደ ተጋደለ እንመለከታለን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከሞተ በኋላ በሰማይ የሚደረገውን ስለሚያውቅ «እኔ ወደ እርሱ እሔዳለሁ እንጂ እርሱ ወደ እኔ አይመጣም» በማለት በሰማይ ቤት ያለውን ጽኑ እምነት፤ ሞተ ማለትም ወደ እግዚአብሔር ሔደ ማለት እንጂ ሌላ ማለት ስላልሆነ ወደ ቤተ እግዚአብሔር ሔዶ ሰግዶ፤ እግዚአብሔርንም አመስግኖ እንደተመለሰ ይነግረናል፡፡

በመጽሐፈ ኢዮብ የተጻፈውን ስንመለከት ደግሞ በሐዘን ጊዜ እግዚአብሔርን እንዴት ማስደሰት እንደሚቻል እንረዳለን፡፡ ኢዮብ በአንድ ቀን ዐሥር ልጆቹ ሞተውበታል፤ በዚያው ቀንም ሊቆጠር የማይችል ሀብትና ንብረቱን አጥቷል፤ እርሱ ግን «እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔር ነሣ» አለ እንጂ አላማረረም፤ ሐዘኑንም በቅጡና በሥርዓቱ ተወጥቶታል፡፡ በዚህ ምድር ያለን ሰዎች ለሰው የማይቀረው ሞት አንዱ ቤተሰባችን ሲጠራው ከእኛ መካከልም በሞት ሲወሰድ ተመልክተን ይሆናል፡፡ እንደ ኢዮብ ግን ዐሥር ልጆቹ በአንድ ቅጽበት ያጣ ሰው የለም፡፡ በዚህም ከእግዚአብሔር እጥፍ ድርብ ዋጋ አገኘበት እንጂ አልተጎዳበትም፡፡ እንዲያውም ከቀደሙት የበለጡ ልጆች፣ ከቀድሞው ዕጥፍ ድርብ የሆነ ሀብት ተሰጥቶት፤ እንደተረገመ የቆጠሩት ሰዎች ሁሉ አፈሩ፤ እርሱ ግን በማጣቱም በማግኘቱም ጊዜ፤ በሐዘኑም በደስታውም ጊዜ እግዚአብሔርን ደስ አሰኘው፤ ተባረከበትም፡፡ ታዲያ የሕይወታችን እውነታ እንዲህ ሆኖ ሳለ አንዳንዶቻችን ያለ መጠን የምናዝነው፣ የምንፈተነው እና የምንጨነቀው ለምንድን ነው ? እንደ ኢዮብ እንደ ዳዊት ለመሆንስ ለምን ተሳነን ? ብለን ልንጠይቅ እንችላለን፤ ተገቢም ነው፡፡

የዚህን መልስ በአግባቡ ከተረዳን እኛም እንደ ሌሎቹ ብርቱዎች የማንሆንበት ምክንያት አይኖረንም፡፡ ለጥያቄያችን መልስ የሚሆነውንም ቅዱስ መጽሐፍ ስለመዘገበልን ከዚህ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

«ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈረስ፣ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘለዓለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንፃ እንዳለን እናውቃለንና፡፡ በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፣ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም፡፡ በእውነትም የሚሞተው በሕይወት ይዋጥ ዘንድ ልንለብስ እንጂ ልንገፈፍ የማንወድ ስለሆነ፣ በድንኳኑ ያለን እኛ ከብዶን እንቃትታለን፡፡ ነገር ግን ለዚሁ የሠራን እግዚአብሔር ነው፣ እርሱም የመንፈሱን መያዣ ሰጠን፡፡» /2ቆሮ 5÷1-5/ በዚህ ጥቅስ ውስጥ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እጅግ እምቅ የሆኑ መሠረታዊ ነገሮችን አስቀምጦልናል፡፡እነዚህን በአግባቡ ከተረዳን ብዙ ጥያቄዎቻችን በአግባቡ ይመለሳሉ፡፡ ስለዚህ ፍሬ አሳቦችን በቅደም ተከተል እንመለከታቸዋለን፡፡ ለዚህ ጽሑፍ በሦስት ብቻ ከፍለን እንመለከታቸዋለን፡፡

ይቆየን
ምንጭ፡ሐመር ኅዳር 2003 ዓ.ም

ክርስቲያናዊ ሕይወትና ምግባር (ሦስተኛ መጽሐፍ)

በሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ
 
አንድ ሰው የሚያንበትን እምነት ፣ የሚመራበትን ሕግ ፣ የሚያልመውን ተስፋና የሚወደውን ነገር ተከትሎ ከግቡ ለማድረስ ማድረግ ያለበትን በማድረግ ማድረግ የሌለበትን በመተው በነፃ ፈቃዱ ወስኖ በሙሉ ልቦናው በሙሉ ኃይሉ የሚያደርገው የውስጥና የውጭ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ፣ ጥረትና ትግል ነው፡፡

ክርስቲያናዊ ሕይወትና ምግባር (ሁለተኛ መጽሐፍ)

በሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ
 
ሕገ እግዚአብሔርን መፈጸም ማለት ለአሥሩ ቃላት መታዘዝ ነው፡፡ አሥሩ ቃላት ደግሞ በፍቅር ትእዛዛት ይጠቃለላል፡፡

ክርስቲያናዊ ሕይወትና ምግባር (አንደኛ መጽሐፍ)

በሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ
 
ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ፍፁም የሚሆነው የዘልማዱን አኗኗር ትተን ከክርስቶስ ጋር አንድ ሁነን በእርሱ ቅዱስ መንፈስ ሱታፌ ኑሮን በእርሱና ስለ እርሱ ለእርሱ ብለን የምንሆነውና የምናደርገው የዘውትር ጥረትና መንፈሳዊ ተጋድሎ ነው፡፡ ክርስቲያናዊ ሕይወት ማለትም ትርጉሙ ይኸው ነው፡፡ ክርስቲያናዊ ምግባርም ወይም በጎ አድራጎት በዚሁ ትርጉም ውስጥ ቢጠቃለልም በተለየ መንገድ በክርስቶስ ሁነን ለሌሎች የምናደርገውን የፍቅር ሥራ ውጤት ይመለከታል፡፡ ክርስቲያን መሆን ማለት ከልዩ ልዩ አለማዊና ሥጋዊ ነገሮች ተለይቶ በአንድ ልብ ተወስኖ ራስን ለክርስቶስ ብቻ አስገዝቶ በእርሱ ቅዱስ መንፈስ ተመርቶ ለቃሉ እየታዘዙ በመኖር በስሙ መከራውን በመታገሥ እስከ መጨረሻው በታማኝነት መጽናት ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ነው ክርስቲያናዊ ሕይወታቺንና ምግባራችን በሌላ እንግዳ ሕግና መመሪያ ሳይሆን በራሱ በክርስቶስና በክርስቶስ ቅዱስ መንፈስ መሆን እንዳለበት የምንመሰክረው፡፡ እኛ ክርስቲያን መስለን ለመታት ሳይሆን ሆነን በመገነትና መሆናቺንንም በመንፈሳዊ ተጋድሎ በተግባር ስንገለጸው ነው፡፡ እንግዲህ ክርስቲያን መሆን ወይም አለመሆን እዚህ ላይ ነው ጥያቄው፡፡