በጎቹና ፍየሎቹ

የ”እናስተውል” 1ኛና መለሰተኛ 2ኛ ደረጃ የሕዝብ ትምህርት ቤት ለስምንተኛ ክፍል ተማሪዎች የተዘጋጀ የመጀመሪያው መንፈቅ ዓመት የአማርኛ ትምህርት ፈተና
በዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ
 

ለፈተናው የተሰጠ ሰዓት ፡- 0፡05    
የተማሪው ሙሉ ስም:_________________ ቁጥር:______                            

   

የሚከተለውን ምንባብ በጥንቃቄ አንብቡ
በጎቹና ፍየሎቹ
 
ከዕለታት በአንዱ ቀን በአንድ ሀገር ትልቅ የበጎች በረት ነበረ፡፡ በዚህ የበጎች በረት ውስጥ ብዙ በጎች ይኖሩ ነበር፡፡ ይህ የበጎች በረት ለረዥም ዓመት የቆየ እና ብዙ ታሪክ ያለው በረት ሲሆን በጎቹ ሁሉ ግን የሚኖሩበትን በረት ጥንታዊነት እና ታሪክ በሚገባ የሚያውቁ አይደሉም፡፡ በቅርብ ጊዜ ከሚወለዱት በጎች መካከል ለመስማት ፈቃደኞች ያልሆኑ አሉ እንጂ በረቱን እስከ ዛሬ ድረስ ጠብቆ ለማቆየት ብዙ በጎች ከሚያገሳ አንበሳ ጋር ጭምር ተታግለው ብዙ ድል አድርገዋል፡፡ ብዙ በጎችም ለዚሁ በረት መቆየት ሲሉ አንገታቸውን እስከመስጠት ድረስ ደርሰው ነበር፡፡ ከአሁኑ በጎች ውስጥ ግን አንዳንዶቹ እንኳን ራሳቸውን መሥዋዕት አድርገው ሊሰጡ የቀድሞዎቹ በጎች የፈጸሙትን ገድል እንኳን ለማመን ይከብዳቸዋል ፤ ለመስማትም ይሰለቻሉ፡፡
   
በዚህ በረት ውስጥ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ አንድ ችግር ተፈጥሯል፡፡ የችግሩ መነሻ አንዳንድ ፍየሎች በጎች መስለው ከመንጋው መቀላቀላቸው ነው፡፡ እነዚህ ፍየሎች ምንም እንኳን ሥራቸው ፣ ድምፃቸው ፣ አኗኗራቸው ሁሉ ፍየል መሆናቸውን የሚመሰክር ቢሆንም ከበጎቹ በረት ረዥም ጊዜ የቆዩ በመሆናቸው ብዙ በጎችን ግራ ያጋባ ነው፡፡ አንዳንዶቹ አስተዋይና የበግን ጠባይ ከፍየል ለይተው የሚያውቁ በጎች ‹‹ኸረ እነዚህ ፍየሎች ናቸው ፣ ድምፃቸው ፣ አነጋገራቸውና አኗኗራቸው ያስታውቃል!›› እያሉ ሲሟገቱ ከጥቂቶች በቀር የሚሰማቸው አላገኙም፡፡
 
አንዳንዶቹ በጎች ‹‹ምን ችግር አለው ፤ አነጋገራቸው እንደ በግ ባይሆንስ? እስከ መቼ እንደ በግ ብቻ እንናገራለን!›› እያሉ ከመቃወማቸውም በላይ በግ የመሰሉትን ፍየሎች ለመምሰል እነርሱም የፍየሎችን አኗኗር ለመኮረጅ ሞከሩ፡፡ የሚያሳዝነው ግን እውነተኛዎቹ በጎች በግ በመሆናቸው ፍየሎቹን ለመምሰል ያደረጉት ጥረት አልተሳካላቸውም፡፡ ሌሎቹ የዋሃን በጎች ደግሞ ምን ችግር አለው? ‹‹የምንመገበው አንድ ዓይነት ምግብ እስከሆነ ድረስ አንድ እኮ ነን!›› ብለው መከራከር ጀመሩ፡፡ ‹‹ኸረ ከመቼ ወዲህ ነው ፍየሎች አንድ የሆንነው?›› ብለው የተቃወሙ በጎች ደግሞ በእነዚህ በፍየሎች በተታለሉ በጎች ጥርስ ውስጥ ገቡ ‹‹አክራሪ ፣ ጽንፈኛና ወግ አጥባቂ በጎች››  የሚል ስያሜም ወጣላቸው፡፡
 
ይህንን ትርምስ አስቀድሞም ይፈልጉት የነበሩት በግ መሳይ ፍየሎችም ጉዳዩን ማራገብ ጀመሩ፡፡ ‹‹እኛ ለበረታችን ያልሆነው ነገር የለም ፤ እኛ ታማኝ በጎች ነን ፤ ይህቺ በረት ድሮ እንዲህ እንዲህ ነበረች›› ብለው የበረቲቱ መብት ተቆርቋሪዎች ሆኑ፡፡ ይባስ ብለው ድሮ በረቷ የፍየሎች መንጋ እንደነበረች ፣ የምትተዳደረውም በፍየሎች ሕግ እንደነበረ ፤ ከጥቂት ምዕተ ዓመታት ወዲህ በተነሡ በጎች በረቲቱ እንደተበላሸች መወትወት ጀመሩ፡፡ ምንም የማያውቁት በጎች ደነገጡ፡፡ ‹‹ወይኔ በረታችን! ለካ በችግር ላይ ነሽ?›› ብለው በረቲቱን የፍየል በረት ለማድረግ ቆርጠው ተነሡ፡፡ ስለበግነት የሚያነሣን በግ ባገኙት መንገድ ማንቋሸሽም ጀመሩ፡፡
በዚህ መካከል ሌላ ክስተት ተፈጠረ ፤ አንዳንድ ከበጎች ጋር ተቀላቅለው የነበሩ ፍየሎች በይፋ በረቱን ለቅቀው እንደወጡ ተሰማ፡፡ ከወጡ በኋላ ‹‹እውነቱን ተረድተን በግ ከመሆን ፍየል መሆን ይሻላል ብለን ተፀፅተናል ፤ ይህንን እውነት ካወቅን ትንሽ ቆይተናል›› ብለው በአደባባይ ተንሰቅስቀው አለቀሱ፡፡ ሁሉን አይተነዋል ፤ ከእኛ ወዲያ በግነት ለኀሣር አሉ፡፡ በረቱ ውስጥም እያሉ ወሳኝ በጎች እንደነበሩና የበረቱን ጓዳ ጠንቅቀው የሚያውቁ ሊቃውንት እንደሆኑም በዘዴ ጠቆሙ፡፡ አንዳንዶቹም ‹‹የበረቱ ጓዳ›› የሚል መጽሐፍ አዘጋጅተው በተኑ፡፡ ተረባርበው የገዙት በጎቹ ሲሆኑ መልስ ከመስጠት ይልቅ ብዙዎቹ በጎች ተሸማቅቀው ‹‹ጉድ ፣ ጉድ ለካ ይሄ ሁሉ ጉድ አለ?›› ብለው ተንሾካሾኩ፡፡
በዚህ ጊዜ በጎች አሁንም ለሁለት ተከፈሉ፡፡ አስቀድመው ሲቃወሙአቸው የነበሩት በጎች ብዙም ሳይደነቁ ‹‹ከመጀመሪያውስ መች በጎች ነበሩና ነው ፍየል ሆንን የሚሉት ፤ በጎች አለመሆናቸው ይታወቅ ዘንድ ከእኛ ዘንድ ወጡ ፤ በጎች ቢሆኑ ኖሮ ከእኛ ዘንድ ጸንተው በኖሩ ነበር፡፡›› ብለው አስረዱ፡፡ አንዳንድ የዋሃን በጎች ግን ‹‹በግ እገሌ ፍየል ከሆነማ ምን ተረፈን? እንደርሱ ያለ በግ ከየት ይገኛል? ፍየሎችን ያሳፈራቸው እርሱ አልነበረም እንዴ! አይ ይህቺ በረት ምን ቀራት ከእንግዲህ…›› እያሉ ራሳቸውን ነቀነቁ፡፡ ‹‹ከእንግዲህ ትልቅ ነው ብዬ በግ አልከተልም!›› የሚሉም አልጠፉም ይህን ሲሰሙ አስተዋዮቹ በጎች ‹‹አስቀድሞስ በግ በእረኛ እንጂ በግ በበግ ሲመራ የት አይታችኋል ፤ በሉ ይኼ ትምህርት ይሁናችሁ›› አሏቸው፡፡ከዚህ በተጨማሪ “በግ መስለው የሚኖሩ ፍየሎች አሉ” የሚለው የበጎች አቤቱታ አዝማሚያው ያሰጋቸው አንዳንድ በግ መሰል ፍየሎች የበጎችን ልቅሶ ቀምተው ‘ኧረ ፍየሎች በዙ!’ እያሉ ማስመሰል ጀመሩ።
 
ሌላው አሳሳቢ ጉዳይ ደግሞ ትክክለኛው የበጎች በረት የት እንደሆነ ባለማወቅ በጎች ሆነው ሳለ ከፍየሎች መንጋ ጋር የሚንከራተቱ በጎች ጉዳይ ነው፡፡ ወደ ትክክለኛው በረት እንዳይመጡ በበጎቹ በረት አካባቢ የሚታየው ትርምስ የበጎች በረት መሆኑን ስለሸፈነባቸው ተቸገሩ ፣ የብዙዎቹ በጎች ሕይወት ደግሞ የበግ ስለማይመስል የበረቱን በጎ ምስል እንዳይታይ አድርጎታል፡፡ ከፍየል ሌላ የጅብ ፣ የዕባብ ፣ የውሻ ወዘተ ጠባይ የሚያሳዩ በጎች ቁጥር መብዛቱም እነዚህሰ የጠፉ በጎች እንዳይመለሱ እንቅፋት ሆነባቸው፡፡ እረኛው ደግሞ ‹‹ከዚህ በረት ያልሆኑ ሌሎች ብዙ በጎች አሉኝ›› ብሏል፡፡ ከዚህ በረት ውስጥ ያሉ ፍየሎች እንዳሉ ሁሉ ከበረቱ ውጪ ያሉ በጎችም ብዙዎች ናቸው፡፡ ምንም እንኳን እነዚህ የጠፉ በጎች በፍየሎች መካከል ቢሆኑም የበጎች በረት ነገር ሲነሣ ግን በቀላሉ የሚነኩ ፣ልባቸው በቶሎ የሚሰበር ፣ ዕንባ የሚቀድማቸው ናቸው፡፡ የእነዚህ በጎች ጉዳይ እጅግ አሳሳቢ ሆነ፡፡ ‹‹ኸረ ብዙ በጎች እየወጡ ነው!›› እያሉ የሚጮኹም አልታጡም፡፡ አንዳንድ በጎች ደግሞ ለበረቱ የተቆረቆሩ መስሎአቸው ‹‹ይውጡ ፤ ኖረውም አይጠቅሙም! ይላሉ›› እረኛው ግን በጎቹን በበረቱ ለመሰብሰብ ብዙ እንደተሰቃየ ታላላቅ በጎች ታሪክ ጠቅሰው ይናገራሉ፡፡
 
በዚህ ሁሉ መካከል በረቱ እየፈረሰ ነው፡፡ በጎችም እየኮበለሉ ነው፡፡ ፍየሎችም ሌት ተቀን በረቱን የፍየል መንጋ መስፈሪያ ለማድረግ እየተጉ ነው፡፡ ተስፋ የሚጣልባቸው በጎችም ግማሾቹ ወጣ ብለው ሣር ሲግጡ ውኃ ሲጠጡ ፣ ግማሾቹም በዋዛ በተራ እሰጥ አገባ ተጠምደው ፣ ግማሾቹ በፍየሎች ላለመጠመድ ሲሉ የበረቱን ነገር ወደ ጎን ተዉት፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ እንኳን በረቱን ገብተው ሊታደጉ ሌሎች ትንሽ ሲፍጨረጨሩ ሲያዩ ‹‹አዬ የዚህ በረት ነገር በቀላሉ የሚፈታ እንዳይመስላችሁ… ለማንኛውም መፍጨርጨር ጥሩ ነው!›› ‹‹ይኼን ሠራን ብላችሁ ነው? ወይ አለመብሰል!›› ይሏቸው ጀመር፡፡ ነገር ግን በጎቹ ምንም ባያውቁ በበረቱ ማደጋቸው በራሱ ከመብሰል አልፎ ካልተጠቀሙበት ለማረርም የሚበቃ ጊዜ ነበር፡፡ ይሁንና የጥቂቶቹ በጎች ጥረት ውጤቱ ቶሎ እንዳይታይ ደግሞ ምንም እንኳን ፍየሎች ባይሆኑም እንደ በግ ግን መኖር ያቃታቸው ደካሞች በመሆናቸው አቅም አጠራቸው፡፡ በጎችም ሆነው ፍየሎችን እንዴት እናጥቃ በሚለው ጉዳይ መስማማት አቅቷቸው ሥራውን ሳይጀምሩ የጨረሱ ታካቾችም አሉ፡፡ አንዳንድ በጎች መፍትሔ ለማግኘት “ወደ አንበሳ ሔደን አቤት እንበል” ይላሉ። ሌሎች ብጎች ደግሞ ‘አንበሳ ብዙ አንበሳዊ ጉዳዮች አሉበት ደግሞም አንበሳ የሚፈርደው በጎችንና ፍየሎችን በእኩል ዓይን ተመልክቶ ነው ሲሉ ይሞግታሉ።
 
የበረቱ ችግር እየከፋ ፣ የፍየሎቹ አካሔድም እየተስፋፋ ቢመጣም አሁንም ግን ዝምታው ሰፍኗል፡፡ ስለ ፍየሎች ጉዳይ እንዲነሣባቸው የማይፈልጉ በጎችም ተፈጥረዋል፡፡ ‹‹ኸረ ፍየሎች እንዲህ እያደረጉ ነው›› የሚል በግ ሲገኝም ‹‹መዓት አታውራ!›› ተብሎ ይገሠፅ ጀመር፡፡ በዕድሜ የገፉ በጎች ደግሞ ‹‹ይህንን ሳላይ በሞትኩ!›› ብለው ያዝኑ ጀመር፡፡ በእርግጥም በዕድሜ የገፉት በጎች ከመቼውም በላይ የተናቁት አሁን ነው፡፡
 
ፍየሎችን ‹ፍየሎች ናቸው› ብሎ መጥራትም በበጎች ዘንድ ጥላቻን የሚያተርፍ ሆነ፡፡ አንዳንድ በጎች ደግሞ መፍትሔ ያመጡ መስሎአቸው ቢንቀሳቀሱም ፍየልን ፍየል ከማለት ውጪ የበግነትንና የፍየልነትን ልዩነት በሚገባ ማስረዳት ተሳናቸው፡፡ በረቱ የፍየል እንጂ የበግ አልመስል አለ፡፡ አንዳንድ በጎች ጆሮአቸውን ማመን እስኪያቅታቸው የፍየሎች ድምፅ ከበረቱ መሰማቱ እየተለመደ እየተለመደ መጣ፡፡ የሚያስፈራው አዲስ የሚወለዱ ግልገሎች ከልጅነታቸው ጀምሮ ሲሰሙ የሚያድጉት የፍየሎችን ድምፅ በመሆኑ ስለ በግነት እና የበግ ድምፅ ምንም ሳያውቁ የሚያድጉ መሆናቸው ነው፡፡ አንዳንድ በበረቱ ያደጉ በጎች ጭንቀቱን አልቻሉትም፡፡ ‹‹ጆሮዬ ነው ወይስ … እውነት የበረታችን አኗኗር እንደዚህ ነበረ ፤ እውነት ይህቺ በረት ከፍየሎች ጋር አንድ ነበረች? የተሳሳትኩት እኔ ነኝ ወይስ ሌላው?››የሚሉም ነበሩ፡፡ ለማን አቤት እንደሚሉ ጨነቃቸው፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ለእረኛው አመለከቱ፡፡ በጎ ስላደረጉ በጎች መነገሩ ነውር ሆነ፡፡ ፍየሎቹ ስለ እረኛው ብቻ ነው መነገር ያለበት ባዮች ሆኑ፡፡ ስለ እረኛም ግን ስሙን እየጠሩ ከመፎከር በቀር ፍሬ ያለው ነገር አይወጣቸውም፡፡ በዚህ ከቀጠለ ቀስ በቀስ በግ የመሆንና ፍየል የመሆን ልዩነት ጠፍቶ በረቱ መፍረሱ እንደማይቀር አንዳንድ በጎች ይናገራሉ፡፡ 
 

በምንባቡ መሠረት የሚከተሉትን ጥያቄዎች መልሱ

1.    ለበረቱ መበጥበጥ ምክንያት የሆኑት እነማን ነበሩ?
2.    በግ መስለው የተቀላቀሉት ፍየሎች በምን ይታወቃሉ? (መለያ ጠባያቸው)
3.    አንዳንድ የዋሃን በጎች የተሳሳቱት በምን በምን ነበር?
4.    በግ ነበርን ብለው የወጡት ፍየሎች መውጣት የማያስደንቀው ለምንድን ነው?
5.    ጥሩ ጥሩ በጎች ለምን የበረቱን ችግር ለመፍታት አልቻሉም?
6.    ፍየሎችን ‹ፍየሎች› ብሎ መጥራት ለምን ነውር ሆነ?
7.    ለበረቱ መልካም ነገርን የሚመኙ በጎች ለምን ተባብረው መሥራት አልቻሉም?
8.    ከበረቱ ውጪ ያሉት በጎች ለምን ወደ በረቱ ለመመለስ አልቻሉም?
9.    በጎች መመራት ያለባቸው በሌላ በጎች ነው ወይስ በእረኛ?
10.     የበረቱን ችግር ለመፍታት ምን መደረግ አለበት (ከጓደኞቻችሁ ጋር ተወያዩበት)

ማሳሰቢያ ፡- ተማሪዎች ይህን ፈተና ከተፈተናችሁ በኋላ የበጎቹንና የፍየሎቹን ገጸባሕርያት እያነሣችሁ አንዳችሁ ለአንዳችሁ ስም እየሰጣችሁ እርስ በእርስ እንድትነቃቀፉ አልተፈቀደላችሁም! የጎበዝ ተማሪ መለያ በረቱ ሰላም የሚሆንበትን መፍትሔ መጠቆም ነው፡፡
                                             መልካም ፈተና
ምንጭ፡ሐመር የካቲት 2003 ዓ.ም. 

ነፍስና ሥጋ የውል ስምምነት ተፈራረሙ

በመ/ርት ጸደቀወርቅ አሥራት
ነፍስና ሥጋ እንደከዚህ በፊቱ ለሚጠብቃቸው ከባድ የሥራ ኃላፊነትና አለመግባባት የውል ስምምነት ተፈራረሙ። የውል ስምምነቱን የተፈራረሙት በቀጣዩ ሣምንት የሚገባውን የዐቢይ ፆም ምክንያት በማድረግ ነው።
 
በውሉ ሥነ ሥርዐት ላይ ነፍስ እንደገለጸችው ከዚህ በፊት በአጽዋማት ጊዜ በመካከላቸው የሚፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት ውሉ ጠቃሚነቱ የጎላ ነው።

ባለፉት ዓመታት ሥጋ የአጽዋማትን ወቅት ጠብቆ ነፍስ ተገቢውን ድርሻ እንዳትወጣ እንቅፋት እየሆነ ችግር ሲፈጥር መቆየቱን ገልጸው ስምምነቱ በመካከላችው ሰላም እንዲሰፍን ምክንያት ይሆናል ያሉን በስምምነቱ ሥነ ሥርዐት ላይ የተገኙት የነፍስ አባት ናቸው።

ከፊርማው ሥነ ሥርዐት በኋላ ባነጋገርነው ወቅት ስምምነቱን ተቀብሎ የነፍስን ሥራ ሳይቃወም ሊገዛላት መዘጋጀቱን ሥጋም ቢሆን አልሸሸገም።

በሥነ ሥርዐቱ ላይ የተገኙት ሌሎች ምዕመናንም ሥጋን በቃልህ ያጽናህ እያሉ ከስብሰባው አዳራሽ ሲወጡ እንደተሰሙ “ሪፖርተራችን” ዘግቦልናል።

ትንሣኤ ግዕዝ

 

/ርት ፀደቀ ወርቅ አስራት

የጥንቱ ውበቱ

ጭራሽ ተዘንግቶ፣

ለብዙ ዘመናት

የሚያስታውስ አጥቶ፣

ተዳክሞ ቢያገኙት

ግዕዝ አንቀላፍቶ፣ 

«ሞተ ሞተ» ብለው

አዋጅ አስነገሩ፣

በርቀት እያዩ

ቀርበው ሳያጣሩ፡፡

ታዲያ ይሄን ጊዜ…..

አዋጁን የሰሙት

ቀርበው ወገኖቹ፣

ፍፁም እያነቡ

ግዕዝ….. ግዕዝ ቢሉ

አብዝተው ቢጣሩ፣

በቅፅበት ተነሣ፣

ትንሣኤን አግኝቶ

ለወዳጆቹ ጥሪ

ምላሽ ሊሰጥ ሽቶ፡፡


ከታሪክ አንድ ገጽ

እንደዚህ ሆነ፡፡
በአንዲት መንደር ውስጥ አንድ ሰው ነበረ፡፡ አንደበቱ ከጸሎት እጁ ከምጽዋት ልቡ ከጠዋሐት ተለይቶ የማያውቅ፤ ሰው ተጣላ ማን ያስታርቅ፣ ልጅ አገባ ማን ይመርቅ ቢባል በመጀመሪያ የሚጠራው እርሱ ነው፡፡

ለሽማግሌዎች መኩሪያ ለታዳጊዎች አርአያ መሆንን የሚያነሣ የለም፡፡ ኃጢአትን ሊሠራት ቀርቶ ስሟን ያውቃታል ብሎ የሚገምት የመንደሩ ነዋሪ ከማግኘት አንድ ቀን ሰይጣን ሊመለስ ይችላል ብሎ ተስፋ የሚያደርግ ማግኘት ይቀላል፡፡
ለብዙዎች መለወጥ፣ ለብዙዎች ለጽድቅ መመረጥ፣ ለብዙዎች ከዓለም መመለስ፣ ለብዙዎች ዓለምን ጥሎ መመንኮስ አንድም መሪ ያለያም አበረታች መካሪ እርሱ ነው፡፡
የተናገረው ከልቡና ያስተማረው ከኅሊና ጠብ ሲል ልብ ያደርሳል ኩላሊት ያድሳል፡፡
ያለ ሠርክ ሰዓት እህል የማይቀምስ ያለ ተርታ ነገር ነጠቅ መንጠቅ ያለ የማይለብስ መሆኑን በአካባቢው ሐይቅ ስለሌለ የባሕር ዓሦች ካልሆኑ በቀር የማይመሰክር ፍጥረት አለ ማለቱ ይቸግራል፡፡

ትዳሩን አክባሪ ባለቤቱን አፍቃሪ በመሆኑ ከአብርሃምና ከሣራ ቀጥሎ ለሰርግ ምርቃት እርሱና ባለቤቱ ሳይጠሩ አይውሉም፡፡ አንድ ቀን ከቤተክርስቲያን መልስ ወደ ቤቱ በማምራት ላይ እያለ ዓይኑን ዓይኑ አንድ የማይወራውን ነገር ተመለከተ፡፡ አንድ አገር ያስቸገር መናፍቅ ከርሱ ቤት ግቢ ወጣ፡፡ ለምን?

 
ባለቤቱን አግኝቶ እስኪጠይቃት ነፍሱ የቸኮለችውን ያህል የመኪና እሽቅድድም ተወዳዳሪዎች ቸኩለው አያውቅም፡፡ ገባ፤
‹‹ ይኸ ሰውየ እንዴት መጣ?››
‹‹ ረጋ በልና አስረዳሃለሁ፡፡››
‹‹ ለመናፍቅ ምን እርጋታ ያስፈልገዋል››
‹‹ እኮ ረጋ በል››
‹‹ ለምን ታረሳሽኛለሽ?››
‹‹ ምኑን?›› የሆነ ነገር ብልጭ አለበት፡፡ ሰይጣን እሳት ጫረና ቤንዚን ለቀቀበት፡፡
‹‹ምን ሊሰራ መጣ?››
‹‹ለምን ትቆጣለህ?›› ሰይጣን እሳቱን እፍ በማለት ላይ ነው፡፡
እርስዋ ራስዋ ሰይጣን መስላ ታየችው፡፡ ደክሞታል፡፡ ተናዷል፡፡ ዝሏል፡፡ አእምሮው ዕረፍትን ብቻ ነበር የሚሻው፡፡ ውሳኔ ለመስጠት፤ ነገር ለማመዛዘን ዐቅሙም አልነበረውም፤ ብቻ ሳይሆን ዐቅሙ እንደሌለውም አላወቀም፡፡ አደርጎት የማያውቀውን ዓይኑን አጉረጠረጠና ገፈተራት፡፡ ወደ ኋላ ተንደረደረችና አንገትዋ ኮመዲኖው ጠርዝ ላይ አረፈ፡፡ በስተመጨረሻም መሬት ላይ ተኛች፡፡ ላንዴም ለመጨረሻም፡፡
ነቃ፣ ነቃና አያት፤ ያደረገውን ለማስታወስ ሞከረ፡፡ እርሱ ወይስ ሌላ ሰው? ምንድን ነው የፈጸመው? ሚስቱን ገደላት ማለት ነው? ገዳይ-ወንጀለኛ-ጨዋ-ሰላማዊ-አርአያ-ምሁር- መምህር-ገዳይ-ወንጀለኛ፡፡
ጮኸ – ከማለት ይልቅ የጩኸቱ ደምጽ ፈነዳ ማለቱ ይቀላል፡፡ አካባቢው በሰው ተጥለቀለቀ፡፡
 
እርሱ ያለቅሳል፡፡ ሰውም ያለቅሳል፡፡ አለቃቀሳቸው ግን ለየቅል ነበር፡፡ አንዱ ‹‹ክፉ ተናግራው መልአክ ቀስፏት ነው፡፡ ይላል፡፡ አንዱ ደግሞ ‹‹ የጻድቅ ሰው ዕንባ፡፡ ድሮም የማይናገር ሰው ዕንባው ሰይፉ ነው፡፡›› ሌላው ‹‹ አሁንኮ ወይ እማታለሁ ወይም እገላለሁ ብላ ይሆናል፡፡ ይቺ ሰው መሳይ በሸንጎ የርሱ ደግነት ክፋቷን ሸፍኖላት ዛሬ እግዜር አጋለጣት፡፡›› እርሱ ይገላል ቀርቶ ዝንብ ያባርራል ብሎ የጠረጠረ የለም፡፡ ወንጀሉ ሁሉ የርስዋ ሆነ፡፡
እርሱ ግን የደም ዕንባ አለቀሰ፡፡ የሰዎችን ንግግር በሰማ ቁጥር ዕንባው ይጨምር ነበር፡፡ ‹‹እኔ ነኝ እኔ ነኝ እኔ ነኝ›› አለ ድምፁን ከፍ አድርጎ፡፡
‹‹አይ የዋህ ሰው፡፡ ከባቴ አበሳ አይደል፡፡ ስሟ በክፉ እንዳይነሳ ብሎእኮ ነው›› ይላል አንዱ፡፡
‹‹ስላዘንኩባት ነው ማለቱኮነው›› ቀጠለ ሌላው፡፡ ሊያምነው ቀርቶ ሊሰማው የወደደ የለም፡፡ ሰው የሚናገርለት እና እርሱ የሆነው እየተጋጨበት ኅሊናው ዞረ፡፡ ማን ይመነው፡፡
ለያዥ ለገራዥ ቢያስቸግርም በሽማግሌ ጥረት ሊቀመጥ ቻለ፡፡ ‹‹አይዞህ አንተ አልገደልካት እግዜር መታት እንጂ›› ይሉታል ሽማሎች ሰብሰብ ብሎው፡፡ ያ ለርሱ መርፌ ነው ልብ የሚወጋ፡፡
‹‹እንዲያው እግዚአብሔርን ማመስገን አለብህ፡፡ ፊትህ ላይ ተአምሩን ሲያሳህ›› ሲሉት ደግሞ የተወጋው ልቡ መድማት ጀመረ፡፡
‹‹እኔ አይደለሁም እንዴ አለና መጠራጠር ያዘ፡፡›› አሰበው /ድርጊቱን ሁሉ አሰበው/ ነው እርሱ ነው እኔ ነኝ፡፡ እኔ ነኝ ገዳይዋ- ተንሰቀሰቀ፡፡
‹‹ወይ ግሩም ጻድቃን የወንድማቸው ኃጢአት ከሚገለጥ የራሳቸው ኃጢአት ቢገለጥ የተባለው ደረሰ።›› አሉ አንዲት ወይዘሮ፡፡
‹‹የነ አባ እንጦንስ ታሪክ ሲደገም በዓይናችን አየንኮ›› ሌላዋ ተቀበሉ፡፡
ማን ይመነው፡፡ የልቡን ማን ይወቅ፡፡ እሳት እየከመሩበት መሆኑን ማን ይረዳ፡፡
ጊዜያት ነጎዱ፡፡ ሰው ሁሉ ሊረሳው ጀመረ ጉዳዩን፡፡ እርሱ ግን የሚንተገተግ እሳት ሆኖበታል፡፡
በመጨረሻ እንዲህ ወሰነ፡፡ ለአንድ ለሚወደው ጓደኛው ሊነግረው፡፡ ሐሳብ ቢከፍልልኝ ምክር ቢለግሰኝ ብሎ፡፡
ያደረገውን፡፡ የሆነውን ሁሉ ነገረው፡፡ እየማለ እየተገዘተ የጓደኛው ፊት ሲለዋወጥ ታየው ነጣ- ከዚያ ቀላ መጨረሻ ላይ ጠቆረ፡፡ ‹‹ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ….ለካ አንድ ሰው የለም ባገሩ፡፡ አንተ ስናምንህ ስናከብርህ- ለካ አውሬ ኑረሃል…›› ሰቀጠጠው፡፡ እናም ሸሸው ‹‹ ለኔም ፈራሁህ ››
‹‹እኔኮ የነገርኩህ… ›› አላስጨረሰውም ‹‹ዝም በል!››
ልቡ  ሌላ ነገር ፀነሰ፡፡ የነገርኩት እንዲቀልድብኝ አይደለምኮ አለና ‹‹ባይሆን ነገሩን በልብህ ያዘው›› ሲል ለመነው፡፡
‹‹ገና በአደባባይ ትሰቀላለህ›› ሲል መለሰለት፡፡
ብልጭ አለበት- ሰይጣን እሳት ጫረ፡፡ ዓይኑ ዘወር ዘወር አለ ክትክታ አነሣና ሠነዘረ፡፡ ተጥመልምሎ ወደቀ፡፡ ትኩር  ብሎ ሲያየው ነፍሱ ሸሽታዋለች፡፡ እያለቀሰ፡ ደረቱን እየደቃ ወጣ፡፡ ከቤቱ ብቻ ሳይሆን ከመንደሩ ወጣ፡፡ ወደ በረሃው ሰው ወደ ሌለበት ዘለቀ፡፡ ልክ መንገዱን ሲጨርስ አንድ ሽማግሌ አገኘ፡፡
‹‹ እንደምን ዋሉ አባቴ ››
‹‹እግዚአብሔር ይመስገን ይኼ ደም ምንድነው ልጄ››ልብሱን አሳዩት ደነገጠ፡፡
‹‹እይውልዎት›› አለና ታሪኩን መናገር ሲጀምር ደነገጡና አፈገፈጉ፡፡
‹‹ ዘወር በል አንተ ሰይጣን፡፡!››
‹‹ ይምከሩኝ አባቴ ምን ላድርግ እባክዎ አያውግዙኝ››
‹‹ ዘወር በል ዲያብሎስ እኔንም እንዳትጨምረኝ››
‹‹እኔ እኮ ከቁስሌ ትፈውሰኝ ብዬ እንጂ በቁስሌ ላይ እንጨት የሚሰሰድማ መች አጣሁ፡፡›› አለና ክትክታውን አነሣ እኒያ ሽማግሌ ወደቁ፡፡
ሰው ሁሉ አውሬ መሰለው፡፡ ልቡ እየደነደነ መጣ፡፡ ‹‹ታዲያ ምን ይሁን›› አለው ሰይጤ ‹‹አንተ የመጀመሪያው አይደለህ ››
‹‹ ካሁን በኋላ ማንም ቁስሌን ሊነካ አይችልም ›› አለና በፍጥነት በረሃውን ማቋረጥ ጀመረ፡፡ ማዶ ማዶ ነው አንድ አረጋዊ ካህን ደበሏቸውን ለብሰው ዛፍ ሥር ተቀምጠው ጸሎት ያደርሳሉ፡፡
‹‹ለመጨረሻ ጊዜ›› አለ ‹‹ለርሳቸው ነግሬ መፍትሔ ካልሰጡኝ፤ በቁስሌ ላይ ዘይት መጨመር ትተው ኮምጣጤ ከደፉብኝ የሰው ልጅ ሁሉ ጠላቴ ነው ማለት ነው።›› ወሰነ፡፡
ቀና ብለው አዩት፡፡ ያስፈራል ፡፡ ልብሱ ደም ነክቶታል፡፡
‹‹ ምን ሆንክ ልጄ?›› አሉና ከመቀመጫቸው ተነሡ፡፡ ሠይጣን አንድ ርምጃ አፈገፈገ፡፡
‹‹ ተቀመጥ ደክሞሃል›› ድንጋዩን ለቀቁለት፡፡ ሰይጣን ተናደደ፡፡
‹‹ ምን ሆነሃል?››
በዕንባ ጀምሮ በዕንባ ጨረሰው፡፡
‹‹በተሰቀለው ክርስቶስ ዛሬ ጓደኛ አገኘሁ፡፡›› ዕልል አሉ፡፡
ሰይጣን ፈረጠጠና ዛፍ ሥር ተሸጉጦ ማየት ቀጠለ።
በመገረም ተመለከታቸው፡፡ ‹‹ይገርምሀል፡፡ ሚስቴን ገድዬ፤ ልጆቼን አርጄ፣ የሰው ሀብት ዘርፌ፣ ስንት ልጃገረዶች አባልጌ፣ ሰው መቀመጫ ሲነሳኝ ጻድቅ መስዬ እዚህ ተቀምጫለሁ፡፡ ያንተማ ምን አላት፡፡ በኔ አይነትኮ ያንተ በጥቂት ቀኖና ትሻራለች፡፡››
የፊቱ ጥቁረት ቀነሰ
ክትክታው ከእጁ ወደቀ፡፡
‹‹ በል አሁን ካንድ ሁለት ይሻላል፡፡ ሰው እንደሆነ ቂመኛ ነው ይቅር አይለንም፡፡ እግዚአብሔር ግን መሐሪ ነው፡፡ በዚህ ከቀጠልን እኛ ራሳችን ከሰይጣን መብለጣችን ነው፡፡ ስለዚህ ገደል እንቆፍርና እዚያ ውስጥ ገብተን ንስሐ እንግባ፡፡›› አሉት፡፡ ፈነደቀ፡፡ ዘሎ ተነሣና ዐቀፋቸው፡፡ እናም በዚያው ክትክታ መቆፈር ጀመረ፡፡ እጅግ አድካሚ ሥራ ነው፡፡ አባ ጸሎተ እግዝእትነ ማርያም ይደግማሉ፡፡ ቀና ብሎ አየና እርሱም ጸሎቱን ቀጠለ፡፡
ቀን-ሳምንት-ወር-ሁለት- ሦስት- ወር ፈጀ ቁፋሮው፡፡
ቅጠል ይበላሉ፡፡ አብረው ስለጥንቱ እያወሩ፡፡ ከዚያ ደግሞ ስለ እግዚአብሔር መሐሪነት ያስተምሩታል ዐረፍ ሲሉ፡፡ ይቆዩና ደግሞ ይቆፍራሉ፡፡
በሰው ቁመት ልክ ገደሉ ተቆፈረ፡፡
እንዴት እንግባ፡፡
‹‹አንተ እዚያው ቆየኝ ዕቃውን ሰብስቤ ምግባችንን ይዤ እኔ መጣሁ፡፡›› ተስማማ፡፡
በገመዱ ተንጠልጥለው አባ ወጡ፡፡እላይ ከደረሱ በኋላ ገመዱን ሳቡት፡፡ ደነገጠና ቀና ብሎ አያቸው፡፡
‹‹ ልጄ አሉት አባ›› የነገርኩህ ታሪክ ውሸት ነው፡፡ ‹‹ አንተ እንዳይሰማህ ብዬ ነው ከአሁን በኋላ ምግብህን አመጣልሃለሁ እየሰገድህ፣ እየጾምክ ጸልይ፡፡ እግዚአብሔር ይምራል››  አሉት፡፡ ተናደደ ክትክታው አጠገቡ የለም፡፡ ከግራ ገደል ከቀኝ ገደል አለቀሰ፡፡ አነባ፡፡
‹‹ዕንባ የኃጢአት ክምር ትንዳለች ›› አሉ አባ፡፡
ምንም አማራጭ የለም፡፡ ጸሎቱን ጀመረ፡፡
አባም በዘጠኝ ሰዓት ምግቡን አስበው ያመጡ ነበር፡፡
ከሰባት ዓመት በኋላ አባ ምግቡን ሊያደርሱለት ሲሄዱ ክንፍ አውጥቶ ሲበር አዩት፡፡
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፦  ሐመር 7ኛ ዓመት ቁጥር 3 ሰኔ/ሐምሌ 1991 ዓ.ም.

በሕይወት ያለ ማስታወሻ ለገና ሥጦታ

የዘመነ ማቴዎስ 4ኛ ወር የመጨረሻውን ቀን በሚመስጥ የሕይወት ትምህርት በመማር አሳለፍኩት፡፡ ጠዋት ከጓደኛዬ ጋር ቁርስ አድርገን እርሱ ሊወስደኝ ካሰበው ሥጦታ መስጫ ቦታ ሄድን፡፡ይህ የስጦታ መለዋወጫ ቦታ ለእነርሱ ልማድ ነው፡፡ በዓል በመጣ ቁጥር የሚሄድበት የውዴታ ግዴታ የሆነበት ልማድ በእርግጥ ሲጀምረው ጥልቅ ደስታና እርካታ የተሞላ ነበር።

እኔ ከጉዟችን መልስ በድርጊቱ ተደምሜያለሁ፣ እርሱ በዓመት ሦስቴ ለበዓላት በመሄድ ገንዘብ ያደረገው ልማድ!! ይህ የልደት በዓል በጠዋቱ መልካም የሕይወት ተሞክሮ እያስተማረኝ እንደሆነ መረዳቴ የዘመኑን መልካም ጅማሮ እንድወደው አስገደደኝ ገና ሦስት ሩብ ዓመታት ይቀራሉና!!

‹ታምሜ ጠይቃችሁኛል?…… ተርቤ አብልታችሁኛል?› የሚሉት የክርስቶስ የወንጌል ቃላት ለእርሱ የሕይወት ልምምድ መሠረቶች ነበሩ፡፡ እንዴት ልፈጽመው ከሚል በጎ መሻት የመነጨ ልምድ፣ እናም ወሮታ የማይከፈልበት ብድር ከማይመለስበት፣ ይሉኝታ ከሌለበት፣ ከሥጋዊ የራስ ጥቅም አድልዎ የነጻ ዕረፍት፣ ጥልቅ ደስታና የሕይወት እርካታ ያገኝ ዘንድ በበዓላት በሆስፒታል የተኙ ህመምተኞችን ቤት ያፈራውን በመያዝ ‹እንኳን አደረሳችሁ…..እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን፤ እግዚአብሔር ይማራችሁ! በማለት ይጠይቃቸዋል፡፡ ከቤተሐኪም ገብቶ የሚጠይቃቸው፣ የሚያጫውታቸውና የሚያጐርሳቸው በአጠገባቸው አስታማሚ(ጠያቂ) የሌላቸውን ብቸኛ ህመምተኞች ናቸው፡፡ ይደርስላቸዋል፣ ከጐናቸው!!

አዎ! ማንም ህመምተኛ ድኖ ሲነሣ ውለታ ለመክፈል አይጨነቅም በውለታ አልታሰረምና፡፡ አያውቃቸውም አያውቁትም ቀድሞ እንዲሁ ነበር ዛሬም እንደዛው ወደፊትም እንዲያው ሊሆን ይችላል፡፡ እናም የማያውቁትን በመጠየቃቸው ብድር የማይመልሱትን እርሱም ለነገ ብድራት የማያስቀምጠውን ግን ህመምተኛ ጠያቂን ፈላጊ የሆነን ሰው እንደው ደርሶ ‹እንኳን አደረሰህ› ብሎ የፈጣሪን ምሕረት ለምኖ መጽናናትን መፍጠር እርግጥ ምን ያህል ዋጋ ያለው ደስታ ይኖረው ይሆን… ወዘተርፈ፡፡

የዓውደ ዓመት በዓል ይሄን ያህል ደስታ ይፈጥር ይሆንን? እርግጥ በቤተሰብ መሀል ለሚኖር ሰው ደስታው፣ ጨዋታው፣ ሁካታው፣ መጠያየቁ፣ መልካም ምኞቱ ደስታ ሊፈጥሩ ይተጋገዙለት ይሆናል ይሄን ቢጨምርበት ግን ደስታው ሊያገኘው ከሚታገለው እጥፍ ሲበዛለት ሲበረክትለት ወደ እርካታ ሲመራው በሕይወቱ ሊማር እንደሚችል አምናለሁ፡፡ ምናልባትም የምንጠይቀው አንዱ ህመምተኛ የሕይወትን ቃል ሊያሰማን ምክንያት ቢሆንስ? ኑ እንውረድ በዓርአያችን እንደምሳሌያችን ሰውን እንፍጠር ያለው ለዚህ ይሆን እንዴ?!
ይህ ነው የገና ሥጦታ የተሰጠኝ፣ የሕይወት ትምህርታዊ ገጸ በረከት! ማስተዋሉን ላደለው መልካም ትምህርት ነበር ግሩም!!

/ በዕለት ውሎ መመዝገቢዬ ለጽሑፍ በሚሆን መልክ የተቀዳ
በኤርምያስ ትዕዛዝ  ዘሐብታም
መስከረም 1 2001 ዓ.ም /

ይህን ያውቁ ኖሯል?

የመነኮሳት ሕይወት

ምንም እንኳን የድንግልናና የምናኔ ኑሮ ቀደም ብሎ የተጀመረ ቢሆንም የምንኩስና መሥራችና አባት ቅዱስ እንጦንስ ነው፡፡ አባ እንጦንስ ግብፅ ውስጥ በምትገኝ ቆማ በምትባል ቦታ በ251 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ወላጆቹ ሀብታሞችና ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ከወላጆቹ ዕረፍት በኋላ የነበረውን ሀብት ለድሆች መጽውቶ መንኩሶ ብዙ ዓመት በብሕትውና ኖረ፡፡

በዚያን ጊዜ ብዙ ታምራትን ስለሠራ ሕዝቡ ግማሹ እሱን አይቶ ለማድነቅ የቀረው ደግሞ በእርሱ ጸሎት ለመፈወስ ወደነበረበት ቦታ ይጐርፍ ነበር፡፡ እርሱም በ356 ዓ.ም ዐረፈ፡፡

አባ ጳኩሚስ የተባለ ሌላው አባት በላይኛው ግብፅ ውስጥ ብዙ ገዳማትን በመሥራት የምንኩስናን ሕግና ሥርዓት በመወሰን ስለምንኩስና መስፋፋት ብዙ ደክሟል /290-347 ዓ.ም/፡፡ አንድ ቀን ወደ ዱር እንጨት ፍለጋ ሔዶ ሳለ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸለትና እንደ አባቶቻችን ሐዋርያት የአንድነትን ማኅበር ለመሥራት መነኮሳትን እንዲሰበስብ አዘዘው፡፡ ብዙ አማኞች እየናፈቁት ማግኘት ያልቻሉትን ገዳማዊ ሕይወት ያገኙ ዘንድ ገዳም ለመመሥረት የሚስችለውንና የሚያስተዳድርበትን በነሐስ ላይ የተቀረጸ ሕግ ሰጠው፡፡ አባ ጳኩሚስም ከመልአኩ በተሰጠው ሕግ መሠረት የሚተዳደር ገዳም አቋቋመ፡፡ ይኸውም መነኮሳቱ ጠዋትና ማታ አብረው እንዲፀልዩ በአንድነት እንዲሠሩ ገቢና ወጪያቸው አንድ ላይ እንዲሆን በአንድነት እንዲመገቡ፣ ልብሳቸው አንድ አይነት እንዲሆንና እነዚህን የመሳሰሉትን ደንቦች አወጣላቸው፡፡ በዚህ መሠረት መነኮሳቱ የዕለት ምግባቸውን የሚያገኙት እየሠሩ ነበር፡፡ ከሴቶችም የምንኩስናን ሕይወት የጀመረች የአባ ጳኩሚስ እህት ማርያም ናት፡፡

ከዚህ በኋላ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ጀምሮ ምንኩስና በግሪክ፣ በሮም፣ በሶሪያና በሌሎችም ሀገሮችም እየተስፋፋ ሄደ፡፡

የምንኩስናን ሕይወት ወደ ኢትዮጵያ ያመጡ በ5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በጉባዔ ኬልቄዶን /በሃይማኖት ስደት/ ምክንያት ከቁስጥንጥንያ፣ ከግብፅ፣ ከሶርያ፣ ከሮም፣ ከአንጾኪያ ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ዘጠኙ ቅዱሳን መነኮሳት ናቸው፡፡ ምንኩስና ከተመሠረተ ጀምሮ በየጊዜው ሕዝቡ ታላላቆችም ሳይቀሩ ወደ ገዳማቱ እየሄዱ ይመነኩሱ ነበር፡፡

ነገር ግን ከ9ኛው መቶ ዘመን ጀምሮ በማኅበር ከሚኖሩት መነኮሳት መካከል ጥቂቶቹ ቀስ በቀስ ለብቻ በተለየ ቤት መኖር እያንዳንዱ መነኩሴ ለብቻ በፈለገበት ጊዜ መብላትና መተኛት ስለጀመረ በየገዳማቱ የመነኮሳቱ ኑሮ በማኅበር የሚኖሩትና ለብቻቸው የሚኖሩት ለሁለት ተከፈሉ፡፡

የድንግልና መሠረቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ስለ መንግሥተ ሰማያት ሰውነታቸውን ጃንደረባ ያደረጉ አሉና፤ መፈጸም የሚችል ግን ይፈጽም» ሲል የተናገረው የሕግ ቃል ነው፡፡ ማቴ. 19፡12

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

/ምንጭ፦ ‘የዛሬዋ ኢትዮጵያ በመጽሐፍ ቅዱስ’ በዲ/ን አሐዱ አስረስ፣ ነሐሴ 1992 ዓ.ም/