ወርኃ የካቲት
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ስድስተኛው ወር “የካቲት” ተብሎ ይታወቃል፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው ውስጥ የዚህን ወር ቃል “ከተተ” ከሚለው ግስ ከወጣው “ከቲት፣ ከቲቶት” ከሚል ንኡስ አንቀጽ የተገኘ ሲሆን በቁሙ “የወር ስም፣ ስድስተኛ ወር፣ የመከር ጫፍ (መካተቻ)፣ የበልግ መባቻ ማለት ነው” ብለው ተርጉመውታል። (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፭፻፲፭)
ሌሎችም ጸሐፍያን “የካቲት” የሚለው ቃል “ከቲት፣ ከቲቶት” ከሚል የግእዝ ንኡስ አንቀጽ የተገኘ ሲሆን “መውቃት፣ ማምረት፣ መሰብሰብ፣ መክተት” የሚል ትርጉም ይኖረዋል ካሉ በኋላ ይህንም ስም ያገኘው የካቲት ወር አዝመራ (ምርት) ወደ ጎተራ የሚከተትበት ወራት በመሆኑ ነው ብለዋል። (ኅብረ ኢትዮጵያ፣ ከቴዎድሮስ በየነ፣ አዲስ አበባ ፲፱፻፺፱ ዓ.ም፡፡ አንድሮ ሜዳ፣ ገጽ ፫፻፺፭፣ አቡሻክር የጊዜ ቀመር፣ በኢንጅነር አብርሃም አብደላ ገጽ ፵፱) በቁጥር ትምህርት አንዱ ወር በባተበት የትኛው ወር እንደሚብት በቃል የሚጠና ሲሆን የካቲት በባተችበትም ጳጕሜን እንዲሁም የካቲት በባተበት ሳኒታ ሰኔ ይብታል፡፡



