የደሴ ማእከል የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ሊያካሂድ ነው

ግንቦት 19 ቀን 2007 ዓ.ም

ከደሴ ማእከል

01desieበማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከል የአካባቢውን ማኅበረ ምእመናን በማሳተፍ ወደ ታሪካዊው ደብር ቦሩ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሰኔ 7 ቀን 2007 ዓ.ም የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ያካሂዳል፡፡

መርሐ ግብሩ የተዘጋጀበት ዓላማ ምእመናን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሕይወታቸውን ለማነጽ፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መንፈሳዊ ጉዞ ምን መምሰል እንዳለበት ግንዛቤ ለመፍጠር፤ እንዲሁም ወደ ገዳማትና አድባራት በመሄድ በረከት እንዲያገኙ እንደሆነ የማእከሉ ጸሐፊ ዲ/ን ሰሎሞን ወልዴ ገልጸዋል፡፡

በመርሐ ግብሩም የአባቶች ቡራኬ፣ ትምህርተ ወንጌል፣ ያሬዳዊ መዝሙር፣ ምክረ አበው፣ ቅኔ፣ ጉብኝት፣ የፕሮጀክት ምረቃ እንደሚኖሩ ተገልጿል፡፡

የጉዞው መነሻ ቦታ የደሴ ማእከል ጽ/ቤት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ከጠዋቱ 12፡00 ስዓት ሲሆን፤ የጉዞው ሙሉ ወጪ (ቁርስና ምሳን ጨምሮ) 60 ብር እንደሆነ ዲ/ን ሰሎሞን ገልጸዋል፡፡

ምእመናን የጉዞ ትኬቱን በማእከሉ ጽ/ቤት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ግቢ ውስጥ፣ በማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ቤት፣ በደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መዝሙር ቤት (ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መግቢያ በር)፣ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን መዝሙር ቤትና ተድባበ መዝሙር ቤት እስከ ግንቦት 30 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ ማግኘት እንደሚችሉ የደሴ ማእከል ጸሐፊ አስታውቀዋል፡፡

ለአብነት መምህራንና ተማሪዎች ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት የሚያግዝ ስልጠና ተሰጠ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከልና ደሴ ወረዳ ማእከል አስተባባሪነት ከሚያዚያ 18 – 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ከዘጠኝ ወረዳዎች ለተውጣጡ ዐሥራ ስምንት የአብነት መምህራንና ተማሪዎች ለሐዋርያዊ አገልግሎት የሚያበቃ ስልጠና ተሰጠ፡፡

ለተከታታይ ለሰባት ቀናት በተሰጠው ስልጠናም ትምህርተ ሃይማኖት፤ ሐዋርያዊ ተልእኮ፤ ትምህርተ ኖሎት እና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ስልጠናው ተሰጥቷል፡፡

በስልጠናው ላይ የተሳተፉት መምህራንና ተማሪዎቹ ከፍተኛ ተሳትፎ ያደረጉ ሲሆን፤ የተሰጣቸው ስልጠና ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት በንቃት እንድንሳተፍ ያደርገናል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

በሥልጠናው ማብቂያ ላይ በማእከሉ የሕክምና ቡድን ለሁሉም ሠልጣኖች የተሟላ የጤና ምርመራ በማድረግ የመድኃኒት ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡

ለካህናት የዐቅም ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጠ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በደሴ ከተማ ቤተ ክህነት፤ በማኅረ ቅዱሳን ደሴ ማእከልና ደሴ ወረዳ ማእከል አስተባባሪነት ሚያዚያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ደሴ ከተማ ለሚገኙ ከሰባ በላይ ለሚደርሱ የደብር አስተዳዳሪዎች፣ ካህናት በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ የአንድ ቀን ስልጠና ተሰጠ፡፡

ስልጠናው የተዘጋጀበትን ዓላማ የደሴ ከተማ ቤተ ከህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ መምህር ቆሞስ አባ ለይኩን ወንድይፍራው ሲገልጹ በከተማው ከዐሥር በላይ አብያተ ክርስቲያናት እና በርካታ ካህናት ስለሚገኙ በዞን ከተማነቱም ለምዕራብ ወሎ እና ለሌሎችም አጎራባች አካባቢዎች መጋቢ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የካህናትን አቅም በሥልጠና ማገዝ እያጋጠሙን ባሉት ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው ዙሪያ መወያየት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ መርሐ ግብሩ እንደተዘጋጀ ገልጸዋል፡፡

ለአንድ ቀን በቆየው ሥልጠና ትምህርተ ኖሎት፤ የካህናት ሚና ከቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች እና ከዓለም አቀፍ ነባራዊ ሁኔታዎች አንጻር በሚል ርእስ ቤተ ክርስቲያን ከውጭ እና ከውስጥ እያገጠሟት ባሉ ፈተናዎች እና መፍትሔዎቻቸው እንዲሁም የካህናት ድርሻ ምን መሆን አለበት በሚሉት ርእሰ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

በውይይቱ ወቅት በንስሓ ልጆች አያያዝ ዙሪያ እያጋጠሟቸው ስላሉ ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው፣ ዐሥራት አለመክፈል በቤተ ክርስቲያን ላይ እያደረሰ ስላለው ጉዳት፣ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ አሁን ያለበት ደረጃ፣ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች እያጋጠማቸው ስላሉ ፈተናዎች እና ሌሎችም ቤተ ክርስቲያንን ከውጭና ከውስጥ እያጋጠሟት ስላሉ ፈተናዎች እና መፍትሔዎቻቸው በማንሳት የጉባኤው ተሳታፊዎች ሰፊ ውይይት አድርገዋል፡፡

ለአብነት ተማሪዎች የአልባሳት ድጋፍ ተደረገ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከል የቅዱሳት መካናት ማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል አስተባባሪነት በሰሜን ወሎ ደላንታ እና መሀል ሳይንት ለሚገኙ የአብነት ተማሪዎች የአልባሳት ድጋፍ ተደረገ፡፡

በነዚህ ወረዳዎች ብዛት ያላቸው የአብነት ተማሪዎች የሚገኙ ሲሆን፤ ከሚያጋጥሟቸው ችግሮች አንዱ የሆነውን የአልባሳት ችግር ለመቅረፍ ከማእከሉ አባላት፣ ከግቢ ጉባኤያት እና ከምእመናን አልባሳትን በማሰባሰብ ድጋፍ ማድረጉን ማእከሉ ገልጿል፡፡

ማእከሉ በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች የሚያጋጥሟቸውን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግሮች ለመቅረፍ ጊዜያዊ እና ቋሚ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ የሚገኝ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት በዘመናዊ ትምህርት፣ በጤና አጠባበቅ እና በአልባሳት ከሚደረጉ ድጋፎች በተጨማሪ ለዘጠኝ (9) የአብነት መምህራን ለእያንዳንዳቸው ብር 200.00 ወርሃዊ ድጎማ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ለአንድ የአብነት ት/ቤትም ቋሚ የገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት ቀርጾ ተግባራዊ በመደረግ ላይ መሆኑን ማእከሉ ገልጿል፡፡

 

በሊቢያ ለተሠዉ 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች የመታሰቢያ ጉባኤ ተካሄደ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ(ከጎንደር ማእከል)

በሊቢያ ለተሠዉ 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በጎንደር ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ለ3 ቀናት የቆየ የመታሰቢያ ጉባኤ ተካሄደ፡፡

ጉባኤውን ያዘጋጁት የጎንደር ከተማ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት፣ በማኅበረ ቅዱሳን የጎንደር ማእከል እና የጎንደር ከተማ የጥምር መንፈሳዊ ማኅበራት በጋራ በመተባበር ሲሆን፤ ከሚያዚያ 24 – 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ጉባኤው ተካሂዷል፡፡

ጉባኤው የተጀመረው ቅዳሜ ሚያዝያ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ከ7፡00 ሰዓት ጀምሮ ሲሆን፤ ለሦሰት ቀናት በቆየው ጉባኤ በሰባኪያነ ወንጌል ትምህርት፤ ሰማዕታቱን የሚዘክሩ መነባንብ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ቅኔ፤ ከምእመናን ለቀረቡ ጥያቄዎች በሊቃውንተ ቤተ ክረስቲያን መልስ፤ መዝሙር በጎንደር ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት እና በተጋባዥ መዘምራን፤ የጧፍ ማብራት ሥነ ሥርዓት ተከናውኗል፡፡

በተያያዘ ዜና የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በሊቢያ ለተሠዉት 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች የከተማው ምእመናን በተገኙበት ሚያዚያ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በርዕሰ አድባራት አደባባይ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ጸሎተ ፍትሐት ተደርጎላቸዋል፡፡ በዕለቱም 30 ሻማዎች በርተዋል፡፡

የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

001sinoddd

ሚያዝያ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ከቀኑ 10፡00 ሰዓት በጸሎት የተጀመረው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ሲካሔድ ቆይቶ ዛሬ ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ረፋድ ላይ ተጠናቅቆ የሚከተለውን መግለጫ ሰጥቷል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 ላይ በተደነገገው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ ይካሄዳል፡፡

ከሁለቱ አንዱ ከጌታችን ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን በዕለተ ረቡዕ የሚውለው የርክበ ካህናት ጉባኤ ነው፡፡

በመሆኑም የርክበ ካህናቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ሚያዝያ 27 ቀን ከሰዓት በኋላ በጸሎት ተከፍቶአል፡፡

በመቀጠልም ሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም መደበኛ ስብሰባን በጸሎትና በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የመክፈቻ ንግግር ተጀምሮ ለሦስት ቀናት ሲካሄድ ሰንብቶአል፡፡ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችንና መመሪያዎችንም አስተላልፎአል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ለዐራት ቀናት ያህል ባካሄደው ቀኖናዊ ጉባኤ፡-

-ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚጠቅሙትን፣

-ለልማትና ለሰላም የሚበጁትን፣

-ከሀገር ውጭ ለሚገኙና በሀገር ውስጥ ላይ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ሁለንተናዊ ሕይወት መጠበቅ የሚያስችሉትን ርእሰ ጉዳዮች በማንሣት በስፋትና በጥልቀት አይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፎአል፡፡

1.ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በጉባኤ መክፈቻ ያደረጉት ታሪካዊ ንግግር የቤተ ክርስቲያንን ሁለንተናዊ ሕይወት የቃኘ የሀገራችን ዕድገትንና የሰላም አስፈላጊነት በስፋት የገለጸ በመሆኑ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡

2.ምልአተ ጉባኤው በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ተዘጋጅቶ የቀረበውን ዓመታዊ የሥራ መግለጫ ሪፖርት አዳምጦ አንዳንድ ማስተካከያዎችን በማድረግ በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡

3.ምንም ጥፋትና በደል ሳይኖርባቸው ክርስቲያኖች በመሆናቸው ብቻ በሊቢያ ሀገር አይ ኤስ በተባለ የአሽባሪዎች ቡድን በግፍና በሚዘገንን ሁኔታ የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችንና የግብፅ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችን በተመለከተ ቋሚ ሲኖዶስ ቀደም ሲል በሟቾቹ መንፈሳዊ ሕይወት ላይ ተወያይቶ ባቀረበው ሐሳብ መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ያለውን ሁኔታ በጥልቀት ከተረዳ በኋላ ሟቾቹ የዘመኑ ሰማዕት እንዲባሉ ተስማምቶ ወስኗል፡፡

4.እንዲሁም እንደ ኢትዮጵያውያን አቆጣጠር ሚያዝያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም በሊቢያ የተሠውት 30 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማኞች ልጆቻችን እና እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር የካቲት 15 ቀን 2015 ዓ.ም በሊቢያ የተሠውት 21 የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባላት ክርስቲያኖች በሁሉቱም አብያተ ክርስቲያኖች ሲኖዶስ የሰማዕትነት ክብር የተሰጣቸው ስለሆነ፣ የሁለቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት የ21ኛው ክፍለ ዘመን ሰማዕታት ተብለው በአንድነት እንዲታሰቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተስማምቷል፡፡

5.በልዩ ልዩ ምክንያት ከኢትዮጵያ ሀገራቸው ወጥተው በባዕድ ሀገር የሚገኙትንና ወደ ሀገራቸው በመመለስ ላይ ያሉትን ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንን ከማንኛውም ጥቃት ለመከላከልና ለማቋቋም ቤተ ክርስቲያናችን መንግሥት ከሚያደርገው ጥረት በመቀናጀት አስፈላጊውን ሁሉ እንድታደርግ፣ ይህን በተመለከተ ጉዳዩን የሚከታተል ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያናችን የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽንም እርዳታ ሰጪዎችን በማስተባበር ኃላፊነቱን ወስዶ በንቃትና በትጋት እንዲሠራ ጉባኤው ወስኖአል፡፡

6.ሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ አምስተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ለማከናወን በሂደት ላይ መሆኗን ቅዱስ ሲኖዶስ አውስቶ ምርጫው ሰላማዊና ፍትሐዊ ሆኖ በሰላም ይጠናቀቅ ዘንድ ቤተ ክርስቲያናችን በጸሎት እንድትተጋ ጉባኤው መልእክቱን አስተላልፏል፡፡

7.ኢትዮጵያ ሀገራችን ለብዙ ዘመናት ተጭኖአት ከቆየ የድህነት አረንቋ በተጨማሪ የእርስ በእርስ ግጭት ጥሎባት ባለፈ ጠባሳ ክፉኛ የተጎዳች ብትሆንም በተገኘው ሰላም ምክንያት ባሳለፍናቸው ዓመታት እየታዩ ያሉ የልማትና የዕድገት፣ የእኩልነትና የአንድነት እመርታዎች የሰላምን ጠቃሚነት ከምንም ጊዜ በላይ መገንዘብ የተቻለበት ስለሆነ፤ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምንም በላይ ሰላሙንና አንድነቱን አጽነቶ በመያዝ ሀገሩን ከአሸባሪዎችና ከጽንፈኞች ጥቃት ነቅቶ እንዲጠበቅ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ያሳስባል፤

8.ሀገራችን ኢትዮጵያ የቴክኖሎጂና የካፒታል እጥረት እንደዚሁም በሀገር ውስጥ ሠርቶ የመበልፀግ ግንዛቤ ማነስ ካልሆነ በቀር በተፈጥሮ ሀብትም ሆነ በማናቸውም መመዘኛ ከሌላው የተሻለች እንደሆነች የታወቀ ስለሆነ፤ ወጣቶች ልጆቻችን ወደ ሰው ሀገር እየኮበለሉ ራሳቸውን ለአደጋ ከሚያጋልጡ በሀገራቸው ሠርተው የተሻለ ኑሮ እንዲኖሩ ኅብረተሰቡም ይህንን ከግንዛቤ ውስጥ አስገብቶ በሰፊው እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ መልእክቱን አስተላልፏል፤

9.ለሀገራችንና ለሕዝቦቻችን ችግሮች ቁልፍ መፍትሔ ሊሆን የሚችለው ልማትን በማጠናከርና ዕድገትን በማረጋገጥ ድህነትን ማስወገድ ስለሆነ ሕዝባችን ይህን ከልብ ተቀብሎ በየአቅጣጫው የተጀመሩትን የልማት ሥራዎች በመደገፍ ሀገሪቱን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገሮች እኩል ለማሰለፍ የሚደረገውን ሀገራዊ ርብርቦሽ ለማሳካት በርትቶ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፤

10.በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያ ክርስቲያናት በየቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ ሁሉ የአረንጓዴ ልማትና የራስ አገዝ ልማት በማካሄድ ልማትን እንዲያፋጥኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ መመሪያ አስተላልፎአል፡፡

11.በውጭ ሀገር ከሚገኙ አባቶች ጋር ተጀምሮ የነበረው የእርቀ ሰላም ድርድር ለሀገራችን ልማትና ለሕዝባችን አንድነት የሚሰጠው ጥቅም የማይናቅ ስለሆነ የቤተ ክርስቲያናችን በር ለሰላምና ለእርቅ ክፍት መሆኑን ምልዓተ ጉባኤው ገልጿል፡፡

12.ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ በተገለፁትና በሌሎችም መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ሲወያይ ሰንብቶ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቆአል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን ለሕዝባችንና ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ምሕረቱንና ፍቅር አንድነቱን ይስጥልን፤

እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

የጅማ ማእከል የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር እንደሚያካሄድ ገለጸ

ሚያዝ 29 ቀን 2007 ዓ.ም.

በጅማ ማእከል

001jimaaበማኅበረ ቅዱሳን የጅማ ማእከል ሁለተኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ግንቦት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. በሊሙ ኮሳ ወረዳ ቤተ ክህነት በምትገኘው ጥንታዊና ታሪካዊ በሆነችው ኮሳ ቅደስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እንደሚያካሄድ ገለጸ፡፡

የኮሳ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከጅማ 50 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ ሲሆን፤ የትኬቱ ዋጋ ምሳን ጨምሮ 150፡00 ብር መሆኑን ማእከሉ ገልጿል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የወንጌል ትምህርት በተጋባዥ መምህራን፤ ያሬዳዊ ወረብ እና ቅኔ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ምክረ አበው /ከምእመናን ለሚጠየቁ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥበት/፤ ያሬዳዊ ዝማሬ በማእከሉ መዘምራን፤ በተጋባዥ ዘማርያንና በአጥቢያው ሰንበት ትምህርት ቤቶች መዘምራን ይቀርባል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ተወካዮች፤ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች፤ የሊሙ ሰቃ፤ የሊሙ ኮሳ፤ የአጋሮና ቀርሳ እንዲሁም የጅማ ከተማ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ ይሳተፈሉ ሲል ማእከሉ አስታወቋል፡፡

ጥያቄ ለመጠየቅ ለሚፈልጉ ምእመናን በሚከተለው የኢሜል አድራሻ መላክ እንደሚችሉ ማእከሉ አሳስቧል፡፡

jimmamkhh2@gmail.com ወይም aynisha5@gmail.com

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ያስገነባው መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤት ተመረቀ

ሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

001deb002deb

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በደብረ ብርሃን ከተማ ያስገነባው ለመንበረ ጵጵስና እና ለጽ/ቤት አገልግሎት የሚውል ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሚያዝያ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመረቀ፡፡

በሀገረ ስብከቱ የተገነባውን ሕንፃ ለመመረቅ ቅዱስ ፓትርያርኩ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና የጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያ ሓላፊዎች ከአዲስ አበባ ወደ በደብረ ብርሃን ሲመጡ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የሃያ ዘጠኝ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዞኑ እና የከተማው የመንግሥት ባለሥልጣናት፤ እንዲሁም የደብረ ብርሃን ከተማ ምእመናን አቀባበል አድርገውላቸዋል፡፡

003deb004deb

ቅዱስነታቸው ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን ሕንፃውን ከመረቁ በኋላ አገልግሎት የሚሰጡትን ክፍሎች በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ኤፍሬምና በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እየተመሩ ጎብኝተዋል፡፡

በዐፄ ዘርዓያዕቆብ ደባባይ በተከናወነው መርሐ ግብር ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት መልእክት በደብረ ብርሃን ከተማ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እየተሠሩ ያሉ የልማት ሥራዎች የሚያስደስቱ ናቸው፡፡ ከመንበረ ጵጰስናው ግንባታ በተጨማሪ በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ደባባይ እየተገነባ የሚገኘው ባለ 5 ፎቅ ሕንፃም ሀገረ ስብከቱ ለሚያከናውነው መንፈሳዊ አገልግሎት ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ተጨማሪ ሀብት የሚያስገኝ በመሆኑ ሌሎችም አህጉረ ስብከቶች ከዚህ ልማት ሊማሩ ይገባል ብለዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ አባ ዘውዱ በየነ ባቀረቡት ሪፖርት በሀገረ ስብከቱ 29 ወረዳ ቤተ ክህነት፤ 2000 አብያተ ክርስቲያናት እንዳሉ የገለጹ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ360 በላይ አብያተ ክርስቲያናት ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ወደ ሀገረ ስብከቱ ከመጡ በኋላ እንደታነጹ አብራርተዋል፡፡

006deb005deb

ለካህናት ሥልጠና በመስጠት፤ የሰበካ ጉባኤ ክፍያን በማሳደግና በማሰባሰብ፤ ስብከተ ወንጌል በማስፋፋት፤ መምህራንን በማፍራትና በመመደብ፤ በአረንጓዴ ልማት፤ በደብረ ብርሃን ሥላሴ ሰባት መምህራንን በመመደብ በአብነት ትምህርት በርካታ ደቀ መዛሙርትን በማፍራት፤ የካህናት ደዝን በማሳደግ ሀገረ ስብከቱ አገልግሎቱን በማፋጠን ላይ እንደሚገኝ ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡

ቀድሞ የነበረው የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና በንግድ ማእከላት አካባቢ በመሆኑና ምቹ አገልግሎት ለመስጠት ባለማስቻሉ ሌላ ባለ ሁለት ፎቅ መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤትን አጠቃሎ የያዘ ሕንፃ በመገንባት ለዛሬው ምረቃ መብቃቱን ያብራሩት ሥራ አስኪያጁ ባለ አምስት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃም በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ በሪፖርታቸው ከተዳሰሱት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያሬዳዊ ወረብ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ያሬዳዊ መዝሙር፤ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር ቅኔ ቀርቧል፡፡

010de009deb

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጸሎት ተጀመረ

ሚያዝያ 27 ቀን 2007ዓ.ም

100sinodossበዓመት ሁለት ጊዜ የሚደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ዛሬ ሚያዝያ 27 ቀን 2007ዓ.ም. ከቀኑ ዐሥር ሰዓት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በጸሎት ተጀመረ፡፡

የቅዱስ ጊዮርጊስ ሰማዕትነት በመጽሐፈ ስንክሳር

ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም.

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አምላክ አመ ዕሥራ ወሠሉሱ ለሚያዝያ በዛቲ ዕለተ ኮነ ፍጻሜ ስምዑ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰማዕት ዐቢይ ወክቡር ዘተሰምየ ፀሐየ ወኮከበ ጽባሕ፡፡

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ሦስት በዚች ቀን ፀሐይና የአጥቢያ ኮከብ የተባለ ታላቅና ክቡር የሆነ የሰማዕቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ የምስክርነት ፍጻሜ ሆነ፡፡

የዚህም ቅዱስ አባቱ መስፍን ነው፡፡ ስሙም አንስጣስዮስ ይባላል፡፡ ከቀጰዶቅያ አገር ነው፡፡ የእናቱም ስም ቴዎብስታ ይባላል ከፍልስጥዔም አገር ናት ታናሽ ሆኖ ሳለ አባቱ ዐረፈ፡፡

ሃያ ዓመትም በሆነው ጊዜ የአባቱን ሹመት ሊቀበል ወደ ንጉሥ ዱድያኖስ ዘንድ ሔደ፡፡ ንጉሡም ጣዖትን እንዲአመልኩ ሰዎችን ሁሉ ሲያስገድዳቸው አገኘው፡፡

ይህንንም አይቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ እጅግ አዘነ በእርሱ ዘንድ ያለውን ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች፣ ለምስኪኖች ሰጠ ባሮቹንም ነፃ አወጣቸው፡፡

ከዚህ በኋላ በንጉሥ ፊት ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ፡፡ ንጉሡም አባበለው ብዙ ቃል ኪዳንም ገባለት እርሱ ግን አልተቀበለውም፡፡

ለመስማት እንኳ የሚያስጨንቅ ሥቃይን አሠቃየው ጌታችን ግን ያጸናዋል ቍስሉንም ያድነዋል ሦስት ጊዜም እንደሚሞት እርሱም እንደሚአስነሣው በአራተኛውም የምስክርን አክሊልን እንደሚቀበል ነገረው፡፡ ቃል ኪዳንም ሰጠው ስሙ በዓለሙ ሁሉ የተገለጠ ይሆን ዘንድ በተጋድሎና መከራ በመቀበልም ጽኑዕ በሆነ ሥቃይም ሰባት ዓመት እንደሚኖር መላእክትም እንደሚአገለግሉት ነገረው፡፡

ንጉሡም ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለመታዘዙና ባለመመለሱ እጅግ አዘነ፡፡ ስለዚህም አትናስዮስ የሚባል ታላቅ ሥራየኛ አመጣ፡፡ እርሱም መርዝን ቀምሞ በጽዋ መልቶ አስማት ደግሞ እንዲጠጣ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰጠው፡፡ ወዲያውኑ የሚሞት መስሎት ነበር፡፡ ቅዱሱም ያንን ጽዋ ጠጣው ምንም ጉዳት አልደረሰበትም፡፡

ያ መሠርይም በክብር ባለቤት በጌታ በኢየሱስ አምኖ በሰማዕትነት ሞተ፡፡ ከእርሱም ጋር ሌሎች ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት ሙተው የሕይወት አክሊል ተቀበሉ ቁጥራቸውም ሠላሳ ሺህ ሰባት መቶ ነፍስ ነው፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስም በዱድያኖስና በሰባ ነገሥታት ፊት በቆመ ጊዜ በዚያም የተቀመጡባቸው የዕንጨት ወንበሮች ነበሩ፡፡ ቅዱሱንም እሊህን የተቀመጥንባቸውን ወንበሮች እንዲበቅሉ እንዲአብቡና እንዲአፈሩ ታደርጋቸው ዘንድ ከአንተ እንሻለን አሉት፡፡ በዚያን ጊዜ ጸለየ እንዳሉትም አደረጋቸው ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ቍጥር የሌላቸው ብዙ አሕዛብ በጌታችን አመኑ፡፡

ከዚህም በኋላ ቅዱሱን ወስደው በጐድጓዳ ብረት ምጣድ ውስጥ አበሰሉት፡፡ አቃጥለው አሳርረውም ሥጋውንና ዐጥንቱን ፈጭተው አመድ አድርገው ከረጅም ተራራ ላይ በተኑት፡፡ ጌታችንም ነፍሱን ወደ ሥጋው መልሷት ደግሞ አስነሣው፡፡ ወደ ነገሥታቱም ተመልሶ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ስም ሰበከ፡፡ ቍጥር የሌላቸው አሕዛብ አይተው አደነቁ በጌታችንም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ፡፡

ነገሥታቱም ደግመው ሙታኖችን ብታሥነሣ አምላክህ ዕውነተኛ አምላክ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ በእርሱም እናምናለን አሉት፡፡ ቅዱሱም ጸለየ ከጒድጓድም ውስጥ ወንዶችና ሴቶችን ጐልማሶችንም አስነሣላቸው እነዚያም በክብር ባለቤት በጌታችን ስም አስተማሩ የገሀነምንም ወሬ ተናገሩ ጥምቀትንም ተቀብለው ተመልሰው ዐረፉ፡፡

ከሀድያን ነገሥታት ግን ሙታንን ያስነሣህ አይደለም የረቀቁ ሰይጣናትን አሳየህ እንጂ ብለው ተከራከሩ፡፡ ከዚያም ከጭንቀታቸው ብዛት የተነሣ ከአንዲት ድኃ ሴት ዘንድ አስጠበቁት እርሷም እንጀራ ልትለምንለት ወጣች የእግዚአብሔርም መልአክ በላዩ ከበጎ ነገር ሁሉ የተመላ ማዕድን አቀረበለት፡፡ የዚያች መበለትም የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍን አበቀለ ታላቅ ዛፍም ሆነ፡፡

ያቺም መበለት በተመለሰች ጊዜ የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍ አብቅሎ ታላቅ ዛፍ እንደሆነ ስለ ማዕዱም ይህን ታላቅ ምልክት አይታ የክርስቲያኖች አምላክ ሰው ተመስሎ ወደ እኔ መጣ አለች፡፡ ቅዱስም እኔ አምላክ አይደለሁም፡፡ የአምላክ ባሪያ ነኝ እንጂ አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ብላ ለመነችው የአምላክ አገልጋይ ከሆንክ ቸርነትህ እንድትደርሰኝ እለምንሃለሁ፡፡ ዕውር ደንቆሮ ዲዳ ጐባጣ የሆነ ልጅ አለኝና ታድንልኝ ዘንድ እለምንሃለሁ፡፡ ስለ ጌታችን እምነትም አስተማራትና በመስቀል ምልክት አማተበው ያን ጊዜም አየ፡፡ ቅዱሱም በሌላ ጊዜ እንዲሰማ እንዲናገርና እንዲሔድ እንዲአገለግለኝም እኔ እሻለሁ አላት፡፡

በዚያን ጊዜ ንጉሡ በአገሩ ሜዳ ውስጥ ሲዘዋወር ያቺን ዛፍ አይቶ አደነቀ ስለ እርሷም ጠየቀ ቅዱስ ጊዮርጊስ በእርሷ ዘንድ የተቀመጠባት የዚያች መበለት የቤቷ ምሰሶ እንደሆነ ነገሩት፡፡ ንጉሡም ተቆጣ ቅዱሱንም ከዚያ ወስዶ አስገረፈው በመንኰራኵርም አበራዩት ሙቶም ከከተማ ውጭ ጣሉት ጌታም ከሞት አስነሣው ወደ ነገሥታቱም ተመለከተ ንጉሡም አይቶ ደነገጠ ስለ ሕይወቱም አደነቀ፡፡

ከዚህም በኋላ ይሸነግለው ዘንድ ጀመረ በመንግሥቱ ላይም ሁለተኛ ያደርገው ዘንድ ቃል ገባለት ቅዱስ ጊዮርጊስም እየዘበተበት ነገ በጥዋት ለአማልክቶችህ መሥዋዕትን አቀርባለሁ አንተም ሕዝቡ እንዲሰበሰቡ እዘዝ እኔ ስሠዋ እንዲአዩ አለው፡፡ ንጉሡም ዕውነት የሚሠዋ መስሎት ደስ አለው ወደ ቤተ መንግሥቱም እልፍኝ አስገብቶ አሳደረው፡፡

ለጸሎትም ተነሣ የዳዊትንም መዝሙር አነበበ የዱድያኖስ ሚስቱ እለስክንድርያ ንግሥት ሰምታ ቃሉ ደስ አሰኛት የሚያነበውንም ይተረጒምላት ዘንድ ለመናቸው፡፡ እርሱም እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ሰው እስከሆነበት ጊዜ የሆነውን ሁሉ ሊያስረዳትና ሊያስገነዝባት ጀመረ፡፡ ትምህርቱም በልቡዋ ተቀርጾ በክብር ባለቤት በጌታችን አመነች፡፡

በማግሥቱም ቅዱስ ጊዮርጊስ ለአማልክት ሲሠዋ ለማየት ሰው ሁሉ እንዲሰበሰብ ዐዋጅ ነጋሪ ዞረ የቤቷን ምሰሶ ያበቀለላት ያቺ መበለት ሰምታ ዕውነት መስሏት እጅግ እያዘነች ልጅዋን ተሸክማ እያለቀሰችም ወጣች፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስም በአያት ጊዜ ፈገግ አለ ልጅሽን በምድር ላይ አኑሪው አላት፡፡ ከዚያም ልጅዋን ጠርቶ ወደ አጵሎን ሒድ ወደእኔም ይመጣ ዘንድ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ስም እዘዘው አለው፡፡ ያን ጊዜ ያ ልጅ ድኖ ቅዱስ ጊዮርጊስ እንዳዘዘው ወደ ጣዖቱ ቦታ ሒዶ አዘዘው፡፡ በጣዖቱ ያደረ ያ ርኵስ መንፈስም ከማደሪያው ወጥቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አለት መጥቶ እኔ ሰውን ሁሉ የማስት እንጂ አምላክ አይደለሁም ብሎ በሕዝቡ ሁሉ ፊት አመነ፡፡ ቅዱሱም ትውጠው ዘንድ ምድርን አዘዛትና ወዲያውኑ ዋጠችው ጣዖታቱንም ከአገልጋዮቻቸው ጋራ አጠፋቸው ንጉሡም ከወገኖቹ ጋር ዐፈረ፡፡

ብስጭትና ቁጣንም እንደተመላ ወደ ንግሥት ሚስቱ ዘንድ ገባ፡፡ እርሷም አምላካቸው ጽኑዕና ኃያል ነውና ክርስቲያኖችን አትጣላቸው አላልኩህምን አለችው፡፡ ይህንንም ከእርስዋ ሰምቶ በእርሷ ላይ እጅግ ተቆጣ ወደ ክብር ባለቤት ክርስቶስ እምነት የከበረ ጊዮርጊስ እንደአስገባት አወቀ፡፡

ከዚህም በኋላ ከከተማ ውጭ እንዲጐትቷትና በመጋዝም እንዲሰነጥቋት አዘዘ፡፡ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች፡፡

በዚያም ጊዜ ስለ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሥራ ነገሥታቱ ሁሉም ደነገጡ ኀፍረት ደግሞ እንዳይጨምርባቸው ከእርሱም እንዲአርፍ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ እንዲጽፍ ንጉሥ ዱድያኖስን መከሩት፡፡

ያን ጊዜም የክቡር ጊዮርጊስን ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ድል አድራጊ ጊዮርጊስም እጅግ ደስ አለው፡፡ እሳት ከሰማይ አውርዶ ሰባውን ነገሥት ያቃጥላቸው ዘንድ መከራውም ከክርስቲያን ወገን ጸጥ ይል ዘንድ ጌታችንን ለመነው፡፡ ወዲያው እሳት ወርዶ ከሠራዊታቸው ጋር ሰባውን ነገሥታት አቃጠላቸው፡፡

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተገልጾ ብዙ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ በምድር መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ እኔ ኃጢአቱን ሁሉ እደመስሳለሁ በመከራም ውስጥ ሁኖ በባሕርም ሆነ በየብስ ወይም በደዌ በስምህ የሚለምነኝን እኔ ፈጥኜ ከመከራው አድነዋለሁ፡፡ ይህንንም ጌታችን ተናግሮ በክብር ወደ ሰማይ ወጣ፡፡

ከዚህ በኋላ ራሱን ዘንበል አድርጎ በሰይፍ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያት አክሊላትን ተቀበለ፡፡ ከአገልጋዮቹም የቀሩት ሥጋውን ወስደው በልብስ ጠቀለሉት ወደሀገሩ ልዳም ወሰዱት፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው በውስጥዋ አኖሩት ከእርሱም ቍጥር የሌላቸው ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የቅዱስ ጊዮርጊስም በረከቱ ረድኤቱ ሁላችን የክርስቲያን ወገኖችን ከሥጋና ከነፍስ መከራ ይጠብቀን ለዘላለሙ አሜን፡፡