‹‹ሕፃናት ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተውአቸው፤ አትከልክሉአቸውም›› (ሉቃ.፲፰፥፲፮)
አእምሯቸው ብሩህ ልቡናቸው ንጹሕ የሆኑት ሕፃናት ተንኮል፣ ቂም፣ በቀል የሌለባቸው የዋሃን ናቸው፡፡ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕፃናትን ወደ እርሱ እንዲያመጡ አድርጎ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ እንደ እነርሱ (ሕፃናት) ተንኮል፣ ቂም፣ በቀልን በልቡና መያዝ እንደማያስፈልግ ከክፋት መራቅ እንዳለብን አስተማረባቸው፡፡
ወላጆች እንደ ልማዳቸው ለማስባረክ ሕፃናትን ወደ ጌታችን ሲያመጧቸው ደቀ መዛሙርቱ ‹‹ለምን አመጣችሁ!›› ብለው ወላጆችን በተናገሩ ጊዜ ጌታን ‹‹ተዋቸው›› አለ፤ ደቀ መዛሙርቱ መከልከላቸው ትምህርት ያስፈቱናል (ሕፃናት ናቸውና ይረብሻሉ) በማለት ነው፡፡ ጌታችን ግን እንዲመጡ አደረጋቸው፤ ባረካቸው፤ እነዚህ ሕፃናት ቁጥራቸው ከ፪፻ መቶ በላይ እንደሆነ መተርጉማነ አበው ያብራራሉ፤ በዚያን ጊዜ ከጌታችን የተባረኩት ሕፃናት አድገው ጳጳስ፣ ኤጲስ ቆጶስ ሆነዋል፤ ከፍጹምነት ማዕረግ ደርሰዋል፡፡ (የማቴዎስ ወንጌል አንድምታ ፲፱፥፲፭)