‹‹እንደሚንሿሿ ጸናጽል ሆኛለሁ›› (፩ኛቆሮ.፲፫፥፩)

                                                                                                 ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ 

ጸናጽል ድምፁ መልካም የሆነ የምስጋና መሳርያ በመሆኑ ከቀደሙት ሌዋውያን አሁን እስካሉት የሐዲስ ኪዳን ቤተ መቅደስ መዘምራን ፣ ከቀደመው የሙሴ ድንኳን ዛሬ ቤተ ክርስቲያን ድረስ በእግዚአብሔር ፊት ይዘነው የምንቆመው መሳርያ ነው፡፡ ምስጋናችንም ሆነ መዝሙራችን ያለከበሮና ጸናጽል ምን ውበት ሊኖረው ይችላል ብለን እንጀምራለን? አንጀምረውም፡፡ የሊቃውንቱ መዳፍ ያለ ጸናጽል አይንቀሳቀስም፣ ቅኔ ማኅሌቱም ያለ ከበሮ አይደምቅም ፤ እንደ ጾመ ኢየሱስ ያለ ቀን ካልገጠመው በስተቀር ቅኔ ማኅሌት ከነዚህ  ነገሮች አይለይም፤ ይገርማል! ዳሩ ግን አንድም ቀን ቢሆን በዚህ ሁሉ የአገልግሎት ዘመናቸው ወደ ቤተ መቅደስ ገብተው ለሥጋውና ለደሙ ክብር በሚደረገው አገልግሎት ተሳትፈው አይተናቸው አናውቅም፤ ጥንትም ሆነ ዛሬ አገልግሎታቸው ከውጭ ብቻ ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ የባዶ ሕይወት ተምሳሌት አድርጎ ተጠቅሞበታል፤ “የሰውን ሁሉ ልሳን ባውቅ፣ በመላእክትም ቋንቋ ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ ነሐስ፤ እንደሚንሿሿም ጸናጽል ነኝ” (፩ቆሮ ፲፫÷፩) ይላል፡፡ ይህን ስመለከት ከልጅነቴ ጀምሮ በቤተ መቅደሱ ያደገች ነፍሴን አሰብኩና እስራኤል ሲማረኩ “ጽዮንን ባሰብናት ጊዜ አለቀስን” ብለው እንደተናገሩ እኔም ለተማረከችውና ባዶዋን ለቀረችው ጽዮን ሰውነቴ አለቀስኩላት፤ ከኔ በቀር ጽዮን ሰውነቴ ባለተስፋ ምድር መሆኗን ማን ያውቅላታል? የተገባላትንስ ቃል ኪዳን ከኔ በቀር ማን ያውቅላታል?

ስለዚህ ደጋግሜ በባቢሎን ወንዞች አጠገብ ሆኜ ምርር ብየ አለቀስኩላት፤ ደግሜ ደጋግሜም እንዲህ አልኳት፤ እንደሚጮኽ ነሐስ፣ እንደ ሚንሿሿም  ጸናጽል ነሽ አልኳት፡፡ እስኪ አስቡት! ያለኔ ማኅሌቱ አይጀመር፣ ዝማሬው አይደምቅ ፣ የሊቃውንቱ ጉሮሮ አይከፈት፣ ሽብሻቧቸው አያምርበት ፣ እጃቸው ያለኔ አይንቀሳቀስ፣ ቅኔው አይጸፋ፡፡ እስኪ ንገሩኝ! ምኑ ነው ያለኔ የሚያምረው፤ በየትኛው አገልግሎት ነው እኔ የማልገባው፤ የትኛውስ ሊቅ ነው ያለኔ በእግዚአብሔር ምስጋና ላይ የተገኘው ፤ ጥንትም ሆነ ዛሬ እኔ ለዚች ቤተ መቅደስ አገልግሎት አስፈልጋለሁ ፡፡

ያለበለዚያማ ማኅሌቱ ምን ውበት ሊኖረው፤ ማንስ ነው እኔ በሌለሁበት ያለ እንቅልፍ የሚያገለግለው፤ ከከበሮው ተስማምቶ በሚወጣው መልካሙ ድምፄ ብዙዎቹ ይመሰጣሉ፣ የድምፄን ውበት በውስጠኛው ጆሯቸው እየሰሙ እንዲህ አሳምሮ የፈጠረኝን “ድምፁ መልካም በሆነ ጸናጽል አመስግኑ” እያሉ ያመሰግናሉ፡፡ የድምፄን መልካምነት ብቻ እየተመለከቱ ወይ መታደል ብለው ያደንቃሉ፤ እኔ እስከማዜም ድረስ በጉጉት ይጠባባቃሉ ፤ሰው ሲዳር፤  ሲሞትም ሆነ ሲሾም ያለኔ ምኑ ያምራል፤ አምጡት፣ አምጡት ይባላል፡፡

ይህን ሁሉ ክብሬን አየሁና በሰዎች መካከል በኩራት ተቀምጨ ሳለሁ ከዕለታት አንድ ቀን የሥጋየን መጋረጃ ግልጥ አደረግሁና ነፍሴን ተመለከትኋት፤ ትጮኻለች! አዳመጥኳት፤ ላደርገው የሚገባኝን እንኳን ያለደረግሁ፤ የማልጠቅም ባሪያ ነኝ፡፡ እንደሚጮኽ ነሐስ፣ እንደሚንሿሿም ጸናጽል ሆኛለሁ እያለች ታንጎራጉራለች፡፡

የሚጎሰመው ነጋሪት፣ የሚመታው ከበሮ፣ የሚንሿሿው ጸናጽል ለራሳቸው ምን ተጠቅመዋል? ከነሱ በኋላ እየተነሣ ስንት ትውልድ ነው የእግዚአብሔርን መንግሥት የወረሰ፣ ከተስፋው  የደረሰ፤ ሌላው በነሱ ተጠቅሞ አድማሳትን በቅድስናው ሲያካልል፣ መላእክትን ሲያክል፤ እነሱ ግን አሁንም ምድራውያን ናቸው፡፡ በዚህኛው ትውልድም አልተለወጡም፤ ጌታ እስኪመጣ ከዚህ ዓይነት ሕይወት የሚወጡም አይመስሉም፤

እኔም እንደነሱ ነኝ! ቃሉን እሰብካለሁ፣ ዝማሬውን እዘምራለሁ፣መወድሱን እቀኛለሁ፣ሰዓታቱን አቆማለሁ፤ ኪዳኑን አደርሳለሁ፤ መጽሐፍ ቅዱስን ከዳር እስከዳር አንብቤአለሁ፡፡ ዳሩ ግን መች እኖርበታለሁ ፤ ሰዎቹ ከአፌ የሚወጣውን ቃሉን እየሰሙ የሕይወቴ ነጸብራቅ እየመሰላቸው ይገረማሉ፤ እንደኔ ለመሆን ይቀናሉ፤ እኔ ግን ሳላስበው እንደሚጮኽ ነሐስ፣ እንደሚንሿሿም ጸናጽል ሆኛለሁ፡፡  እጮኻለሁ እንጅ  ለምን እንደምጮኽ እንኳን አላውቅም፤ በምጮኸው ጩኸት ከቶ አልለወጥም፤ ከኔ በኋላ እየተነሱ ብዙዎቹ ከምሥራቅና ከምዕራብ እየመጡ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ገብተዋል ፤ ከኔ በኋላ ቃሉን የሰሙት በቃሉ ተለውጠው ንስሓ ገብተዋል፡፡ እኔ ግን ዛሬም ሳያውቅ እንደሚጮሕ ነሐስ፣ ሳይወድ እንደሚንሿሿውም ጸናጽል ሆኛለሁ፡፡

የምጮኸው ገብቶኝ ቢሆንኮ ከኔ የሚቀድም ማንም አልነበረም፡፡ ነገር ግን ይህ እንዳይሆን ሕይወት የሌለኝ ቆርቆሮ ነኝ፤ ድምፄ መልካም ነው፣ ትጋቴ ግሩም ነው፡፡ ከምስጋናው ጋር መስማማቴ፣ በሁሉም እጅ መግባቴ መልካም ነበር፤ ሆኖም ፍቅር የለኝምና ምን ይሆናል፡፡  ሥጋየን ለሰማይ አዕዋፍ ብሰጥ ፣ያለኝንም ለድሆች ባካፍል ፣ የድሆች አባት ብባል ፣አጥንቴም እስኪታይ ብጾም ብጸልይ ፍቅር ግን ከሌለኝ ያው እንደሚጮኸው ነሐስ እንደሚንሿሿውም ጸናጽል መሆኔ አይደለ? ሥጋውን ደሙን ካልተቀበልኩ የኔ መጮኽ ምን ሊጠቅም ! ለካ ለሥጋውና ለደሙ የሚያስፈልገው በበጎ ዝምታ ዝም ያላለው እንደኔ የሚንሿሿው ጸናጽል አይደለም ብላ ነፍሴ ስታለቅስ እኔንም አስለቀሰችኝ ፡፡

ኦ!አምላኬ ጸናጽልነቴን ለውጥልኝ፣ነሐስነቴን አርቅልኝ!

ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ጋር የሚጻረር የሥልጣኔ ተጽእኖ

በሕይወት ሳልለው

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥነ ምግባርን፤ ጥበብን፤ ጽሕፈትን፤ ሥነ ጥበብንና ኪነ ሕንፃን የምታስተምር፤ አንድነትን፤ ፍቅርን እና መተሳሰብን የምትሰብክና ምእመናን ሰብስባ የምትይዝ የክርስቶስ ቤት ናት፡፡

ከጥንት ጀምሮ ቤተ ክርስቲያን የሀገር መሪም ነበረች፡፡ ልጆቿንም በሥርዓት ታሳድግና ታስተምር ነበር፡፡ ነገሥታት በቤተ ክርስቲያን ሕግ በሚመሩበት ወቅት ዜጎቿም በሥነ ምግባር የታነፁ ነበሩ፡፡ የአክሱምና የጎንደር ዘመነ መንግሥትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚያን ዘመን ጀምሮም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወደ ውጭ ሀገራትም ተስፋፍታለች፡፡

ከጥቂት ዓመታት በፊት የቤተ ክርስቲያን ቀኖና እና ትውፊት ያልሆኑ ሥርዓቶች  በተለይም የበዓላት አከባበርና የክርስቲያናዊ አለባበስ ላይ ሥልጣኔ ተፅዕኖ አሳድሯል፡፡ ለምሳሌ የልደት በዓል አከባበር መቀየር ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ የምዕራባውያን ተፅእኖ ካሳደረው የአመለካከት ለውጥ የተነሣ ያልተለመዱ ምግባሮችን ከፈረንጆች በመውረስ ከክርስትና ጋር የሚጻረር ሥርዓት መከተል የጀመሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ የገና ዛፍ በሚል ስያሜ፤ ፅድ መሰል ሰው ሰራሽ ዛፍ በማስጌጥ አላስፈላጊ ክብር እየሰጡ፤ እንዲሁም ክርስቲያናዊ ምግባሮችን በመዘንጋት አብዛኛውን ጊዜ ትኩረታቸውን የቴክኖሎጂ ምርቶች ላይ በማድረግ ግለኝነትና እራስ ወዳድነትን በመላበስ ከቤተሰብ ፍቅርና ከቀኖናዊ ሕይወት የራቁ በርካቶች አሉ፡፡ ከገና በዓል አከባባር ጋር ተያይዞም ከምዕራባውያን  የወሰዱትን ልምድ ማለትም፤ የገና አባትን በመምሰልና ለሕፃናት ማጫወቻ በአሻንጉሊት መልክ በመሥራት አላስፈላጊ ወጪ ከማውጣታቸው ባሻገር የእኛን ሥርዓት እንደሚበርዝ ባለማስተዋል የተሳሳተ መንገድ ይከተላሉ፡፡

የአለባበስ ሥርዓትን ስንመለከት ሥነምግባርን የሚገልፅ በመሆኑ ከክርስቲያናዊ አለባበስ ውጪ ከሆነ ሰውነትን የሚያዋርድ ይሆናል፡፡ የሰው ልጅ በክብሩ በገነት ሲኖር፤ ልብሰ ብርሃንን /የፀጋ ልብሱን/ ሲገፈፍበትና ራቁቱን መሆኑን ሲያውቅ ሰውነቱን ለመሸፈን ቅጠል ለብሷል፡፡ ሥልጣኔ ራቁት የሚያስኬድ ከሆነ የሰውን ልጅ ክብር ይገፋል፡፡ ክርስቲያናዊ አለባበስን የሚጻረር ልብስ፤ (ሴቶች  እኅቶቻችን የተቦጫጨቀ ሱሪ፤ ከጡታቸው በታች የሆነ ልብስ ሲያደርጉ፤ ወንዶች ደግሞ ሱርያቸውን መቀመጫቸው እስኪታይ ድረስ ወደታች በጣም ዝቅ አድርገው) ይለብሳሉ፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያንንና ትምህርተ ሃይማኖትን አለማወቅም ጭምር ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ያስተማረችን ሰውነትን የሚሸፍን፤ ረጅም ቀሚስ እና ነጠላ መልበስ ነው፡፡ ሴቶች አንዳንድ ጊዜ በጣም አጭር ነጠላ በመልበስ ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ ከግራና ቀኝ ትከሻቸው ላይ ለመልበስ በሚሞክሩ ጊዜ ስለማይበቃቸው ሲጨናነቁ እናያለን፡፡ ወንድ የሴት፤ ሴት ደግሞ የወንድን ልብስ ማድረግ ሕጉ ይከለክላል፤ (ዘዳ ፳፪-፭)፡፡ ካህናትም ይህንን ተግባር ላይ ለማዋል በቤተ ክርስቲያን ከራሳቸው ጀምሮ የአለባበስ ሥርዓትን መጠበቅ፤ ሌሎችንም ማስተማር፤ማሳወቅና መገሰፅ አለባቸው፡፡ ትውልዱ ከግማሽ ወደሙሉ ራቁትነት ከመሻጋገሩ በፊት ማስተማር ይገባል፡፡

የማስተማር ኃላፊነት የአለባቸው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት መሪዎች፤ የቤተ ክርስቲያን  አገልጋዮች እንዲሁም ወላጆችና ቤተስቦቻቸው ናቸው፡፡ በልጆችና ወጣቶች ምግባረ ብልሹነት ተጠያቂ በመሆናቸው መገሰፅ፤ ማስተማርና ትክክለኛውን ሕግ ማሳወቅ ያስፈልጋል፡፡

ወደ ቅደስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ለማስቀደስና ጉባኤ ለመካፈል ሲመጡ ክርስቲያናዊ አለባባስ መልበስ እንዳለባቸው ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ነገር ግን ካህናቱም ቢሆን ደፍረው አይገስፁም፡፡ በዚህም የተነሣ አንዳንድ የነፍስ ልጆች የሌላቸው ካህናት እንዲሁም የንስሐ አባት የሌላቸው ክርስቲያኖች ኃላፊነታቸውን ለመወጣት አልቻሉም፡፡ እውነቱን መንገር ግን ያስፈልጋል፡፡ መጽሐፉ “ሕዝቤ ዕውቀት በማጣቱ ጠፍቷል” ይላል (ሆሳዕ ፬፥፮)፡፡

የአለባበስ ሥርዓትን ለማስተካካል ኃላፊነት ያለባቸው የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ብቻ ሳይሆኑ ወላጀችም ጭምር በመሆናቸው ሕገ ቤተ ክርስቲያን የሚፈቅደውን የአለባበስ ሥርዓት ለልጆቻቸው ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የመንፈስ ቅዱስ ልጁን ጢሞቴዎስን አርአያ እንዲሆን መክሮታል፤ (፩ኛጢሞ ፬፥፲፪)፡፡

የምእመናን ተሳትፎ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት የጠበቀ ሊሆን ይገባዋል

                     

በሕይወት ሳልለው

የሰው ልጅ ሕይወት፤ድኀነት፤ሰላም፤ ፍቅርና ደስታ መገኛ እግዚአብሔር፤ ከሕገ ኦሪት ጀምሮ በሰጠን የድኀነት መንገድ፤ በመስቀሉ ላይም በከፈለልን መሥዋዕትነት የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ከጥንት ጀምሮ ምእመናንን በመሰብሰብና በማሰተባበር ሥርዓተ አምልኮን እንዲፈጽሙ ስታስተምር ኖራለች፡፡ በሕገ ወንጌልም አምላካችን በአስተማረን መሠረት የክርስቲያኖች መማፀኛ የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ልጆቿን በፍቅርና በሥርዓት እንድታሳድግ ፈቅዷልና በእምነት፤ እንድናከብራት የእግዚአብሔር  ፈቃድ ነው፡፡

 “በብሉይ ኪዳን ይኖሩ የነበሩ ምእመናን በሕገ ልቦና (ባልተጻፈ ሕግ) ይመሩ የነበሩ አበው እና በሕገ ኦሪት (በተጻፈ ሕግ) የነበሩ ቅዱሳን አባቶች አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር በማድረጋቸው የእግዚአብሔር ረድኤት ያልተለያቸው ነበሩ፡፡የሐዲስ ኪዳንን ስንመለከት “በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕር አምላክነት አምነው፤ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተጠመቁ ክርስቲያኖች ናቸው”፤ (የምእመናን ድርሻ በቤተ ክርስቲያን)፡፡

 አንድ አምላክ፤አንዲት ጥምቀት፤ አንዲት ሃይማኖት፤(ኤፌ4፥4) ይህን የክርስትና ሕይወት መርሕ መሠረት አድርገው የሚኖሩ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች፤ ለብዙ ዓመታት  ሥርዓተ አምልኮን በሚፈጽሙባት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሃይማኖት አባቶች፤ ከካህናት፤ እንዲሁም ከሌሎች አገልጋዮች ጋር የሚያደርጉት ሱታፌ እምነታችውን፤ሥርዓታቸውንና አምልኮታቸውን ለማጠንከር ይረዳልና፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያን መኖር ያስፈልጋል፡፡ አብዛኞቹ  ኦርቶዶክሳውያን  ምእመናን  ዓመታዊ ክብረ በዓላት ላይ ብቻ ነው፡፡

መንክር መኩሪያና ዳዊት ጌታቸው ጥር ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ የጥምቀት በዓልን በጃንሜዳ ሲያከብሩ ያገኘናቸው ወጣቶች ናቸው፡፡መንክር ጥምቀትን ከልጅነት ጀምሮ ስለሚያከብር በየዓመቱ ጃንሜዳ ይመጣል፡፡“በዘንድሮ በዓል በበገናውና መሲንቆ፤በመዘምራንንና መዝሙሮች የቀደመውን ሥርዓት የበለጠ ወድጄዋለው፡፡አገልጋዩቹም ባሕልና ትውፊታቸንን ይዘው በመቅረባቸው እናመሰግናቸዋለን”፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ትውፊት፤ሥርዓትና፤ቀኖና በዓላትን ከማክበር በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት በተገቢው የመፈጸም ኃላፊነት እንዳለብን ያስታውሰናል፡፡ ወጣት  መንክር “አንዳአንድ የአስተዳዳር ችግር በመኖሩ ቅር ብሎኛል፡፡ካህናት እንዲሁም ሌሎች አገልጋዩች እኛን ሰብስበው አልያዙንም ከዘመኑ ጋር የመራመድ መሠረታዊ ችግር አለ፡፡ በዓልን ለማክበር ብቻ መገናኘት በቂ  አይደለም፡፡ የሃይማኖት አባቶች በጎቻቸውን  ተግተው መጠበቅ ይኖርባቸዋል”፤ሲል ቅሬታውን ገልጿል፡፡ዳዊትም ይህንን ሀሳብ በመጋራት “የአከባበር ሥርዓቱ ደስ ቢልም፤ የካህናትና የምእመናንን ኅብር ለበዓል ብቻ መሆን የለበትም፡፡ካህናት የሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማበረታታና ድጋፍ መስጠት አለባቸው”፡፡ ብሏል

አስተባባሪዎችና ሌሎች የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች አስፈላጊውን አገልግሎት በበዓላት ቀንና በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በወቀቱ እንደሚሰጡ ቢታመንም፤እነዚህ ችግሮች ሊከሰቱ የቻሉት በአስተዳደር ችግር መሆኑን እንደ መንክር ያሉ ግለሰቦች ይናገራሉ፡፡

 የቅዱስ ጳውሎስ የሐዲስ ኪዳን መምህር መጋቤ ሐዲስ አእምሮ ደምሴ ስለዚህ ጉዳይ አነጋግረናቸው ነበር፡፡ እሳቸውም “ጉድለቶች አይጠፉም፡ የምእመናን ሱታፌ ለመጨመር ሁሉም የየድርሻቸውን መወጣት አለበት፡፡የካህናቱ ድርሻ መቀደስ፤ ማስተማርና  እና መዘመር በመሆኑ ከምእመናኑ ጋር ኅብር ለመፍጠር የሚቻለው ምእመናን የምስጋናንና፤የመዘመርን ሥርዓት ሲያዘወትሩ ነው” ይላሉ፡፡ሆኖም ግን ትምህርተ ሃይማኖትን በበቂ ሁኔታ አለመማርና አለመተግበር በወጣቱ ላይ ያመጣው አሉታዊ ተፅእኖ እንዳለም ጨምረው ገልጸዋል፡፡ በማኀበር የተደራጁ ወጣቶች ስሕተት መሆኑን ባለመረዳት ቅዱሳት ሥዕላትን ባልሆነ ቦታ ላይ የሚለጥፉና ለማስዋቢያ የሚጠቀሙ እንዳሉም ታይቷል፡፡ነገር ግን እነዚያ ቅዱሳት ሥዕላት በክብር ቦታቸው ሆነው የሚጸለይባቸው ስለሆኑ ተገቢ ባልሆነ ስፍራ መታየት እንደሌለባቸው በአጽንዖት አሳስበዋል፡፡

 “በቲሸርትና ሌሎች አልባሳት ላይ ቅዱሳት ሥዕላትን ማሳተም ትክክል አይደለም፡፡ ምክንያቱም ልብሱ ሊቆሽሽ፤ሊቀደድና ሊጣል ይችላል፡፡እነዚያ ሥዕሎች ቅዱስ በመሆናቸው ለበረከት ብለን የምናደርገው ወደ መርገም እንዳይለወጥብን ለቅዱሳት ሥዕላት ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፡፡የምናገለግለውንም አገልግሎት ያደበዝዝብናል፡፡ሌሎች ጹሑፎችን መጻፍ ለምሳሌ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክትን ማስተላለፍ ይቻላል” ይህ የግንዛቤ እጥረት የፈጠረው ችግር ለምእመናን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት  ሥርዓትና ትውፊት እንዳልሆነ ማስረዳት ይገባል፡፡እነዚህንም ወጣቶች ከስሕተት ለመመለስ የሃይማኖት መሪዎች የማስተማርና የመምከር ከባድ  ኃላፊነት አለባቸው፡፡

በሌላ በኩል ግን መጋቤ ሐዲስ  አእምሮ የበዓል አከባባር ላይ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን የማገልገል ሥራ በራሳቸው ተነሳሽነትና ለበረከትም የሚያደርጉትን ተግባር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የጠበቀ እንዲሆን በማስገንዘብ፤ በዐበይት በዓላት አከባባር ላይ ከአዲስ አበባ ጅምሮ እስከ ገጠር ቤተ ክርስቲያን ድረስ ወጣቱ የሚሰጠው አገልግሎት በአስተማሪነቱ የሚወሰድ መልካም ተግባር ነው፡፡ታቦታት ወደ ማደሪያቸው ከመድረሳቸው አስቀድመው አካባቢውን በማጽዳት፤ ሕዝቡን በመቀስቀስ፤ታቦታቱ የሚያርፉበትንና የሚጓዙበትን መንገድ በማስዋብ፤ ምንጣፍ በማንጠፍና ቄጤማ በመጎዝጎዝ፤ አቧራንና ድካምን ችለው ሲያገለግሉ ይውላሉ” ሲሉ የወጣቶችን ተሳትፎ በአድናቆት ይገልጹታል፡፡

  የ፳፻፲፩ ዓ.ም የአጽዋማት ባሕረ ሐሳባዊ ቀመር

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

በዘመናት ሁሉ የነበረው ያለውና የሚኖረው፣ ሁሉን የፈጠረ በሁሉም ያለ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ለእርሱ በዚህን ጊዜ መኖር ጀመረ፣ በዚህን ጊዜ መኖር ያቆማል የማይባልለት የህልውናው መጀመሪያም ሆነ መጨረሻ የሌለው ዘለዓለማዊ ነው፡ “ተራሮች ሳይወለዱ ምድርም ዓለምም ሳይሠሩ ከዘላለም እስከ ዘለዓለም ድረስ አንተ ነህ”፡፡ “ኢየሱስም እውነት እውነት እላችኋለሁ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ አላቸው፡፡”፣ ብሏል፡፡ በተጨማሪም፣ “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘለዓለም የሚኖር እርሱ ነውና” እንዲል /መዝ.89÷2፣ዮሐ. 8÷56-69 ዕብ.13÷8/፡፡

የሰው ልጅ ሐሳቡ፣ ንግግሩና ተግባሩ የሚከናወነው በጊዜ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ ዘመን ማለት በኅሊና ሲመረመር የጊዜና የዕድሜን መጠንና ልክ የሚወስን መሆኑን መጽሐፈአቡሻኸር ያስረዳል፡፡  ይህ ዘመን የሚባለው የጊዜ ዕድሜ በስያሜው አጠራር መሠረት ኃላፊ፣ የአሁንና የትንቢት/የወደፊት/  ጊዜ ተብሎ በሦስት ክፍላተ ጊዜ ይመደባል፡፡ «ወፉካሬሁሰ ለዘመን በውስተ ልብ አርአያ ወሰን ውእቱ ለጊዜ ዕድሜ ወዝንቱሰ ጊዜ ዕድሜ ዘስሙ ዘመን ይትከፈል እመንገለ ስሙ ኅበ ሠለስቱ ክፍል ኀበ ዘኅለፈ ዘመነ ወኀበ ዘይመጽእ ወኀበ ዘሀሎሂ እንዲል[1]፡፡

ከጥንተ ፍጥረት እስከ ዳግም ምጽአት ድረስ ያለው ዘመን ሁሉ በእነዚህ ሦስት ጊዜያት ሲሠፈርና ሲቆጠር ይኖራል፡፡ ያለፈውንና የሚመጣውን ዘመን ቆጥሮና ሠፍሮ መረዳትና ማስረዳት  እንደሚገባ ሲገልጽ ደግሞ፣  “ተሰአሉ  ዘቀደሙ መዋዕለ ዘኮነ እምቅድሜክሙ እምአመ ፈጠሮሙ እግዚአብሔር ለእጓለ እመሕያው ዲበ ምድር እም አጽናፈ ሰማይ እስከ አጽናፈ ሰማይ ለእመ ኮነ ዝንቱ ነገር፤ እግዚአብሔር  ሰውን በምድር ላይ ከፈጠረው ጀምሮ ከሰማይ ዳር እስከ ዳርቻዋ ድረስ ከቶ እንዲህ ያለ ታላቅ ነገር ወይም እንደ እርሱ ያለ ተሰምቶ እንደሆነ ከአንተ በፊት የነበረውን የቀድሞው ዘመን ጠይቅ”  ተብሎ ተጽፏል /ዘዳ.4÷32 ፡፡

ልበ አምላክ ዳዊትም ያለፈውን ዘመን በማስታወስ “የድሮውን ዘመን አሰብሁ፤ የዘለዓለሙን ዓመታት አሰብሁ፤ አጠነጠንሁም” በማለት ተናግሯል /መዝ.76÷51/፡፡

ዳግመኛም ይህ ዓመታትን ቆጥሮ ዘመኑን ያወቀው ልበ አምላክ ዳዊት ሲጸልይ፣ “ንግረኒ ውኅዶን ለመዋዕልየ፤ የዘመኔን አነስተኛነት ንገረኝ” ብሏል/መዝ.101÷23፡፡ ክቡር ዳዊት የዘመኑን ቁጥር ሲያሰላ እየቀነሰ እንደሚሔድ ገብቶታል፡፡ ይህ ግን ከኃጢአቱ የተነሣ አይደለም፡፡ ይልቁንም ስለ እርሱ የተጻፈው ምሥክርነት “ዳዊትም በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን አሳብ ከገሰገሰ በኋላ አንቀላፋ”  ይላል/ሐዋ.13÷37/፡፡ ይህ ደግሞ ዘመንን ታረዝማለች፡፡ እንዲል /ምሳ.10÷27/

በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን አባቶቻችንን ሥርዓት ጠብቀን፣ ሕገ እግዚአብሔርን አክብረን፣ እግዚአብሔር ሠፍሮ የሰጠንን ዘመን እርሱ በገለጸልን አቆጣጠር እየተጠቀምን በየዓመቱ አጽዋማትን እንጾማለን፣ በዓላትን እናከብራለን፡፡ በመሆኑም እንደእስካሁኑ ሁሉ ዛሬም የ2011 ዓ.ም አጽዋማትንና በዓላትን እንደሚከተለው እናወጣለን፡፡

                                                                  መባጃ ሐመር
ለአጽዋማትና በዓላት ማውጫ ወሳኝ የሆነው ነጥብ መባጃ ሐመር ነው፡፡ መባጃ ሐመር መባጊያ ሐመር እየተባለም ይጠራል፡፡ መባጊያ ሐመር ሲሆን የበጋ መመላለሻ የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ በሌላ በኩል መባጃ በራሱ ማቆያ፣ ማክረሚያ ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ሐመር መርከብ፣ መጓጓዣ የሚለውን ትርጉም ያስገኛል፡፡ መባጃ ሐመር የመጥቅዕና የዕለታት ተውሳክ ድምር ሆኖ አጽዋማትና በዓላት የሚውሉበትን ቀን ያመለክታል፡፡ በሐመር የተመሰለውም አጽዋማትና በዓላት ወደ ላይና ወደታች የሚመላለሱበት ሥርዓት /መርከብ/ ስለሆነ ነው፡፡

በአጠቃላይ መባጃ ሐመር ማለት የአጽዋማትንና የበዓላትን መዋያ ወይም መግቢያ ቀን ለማወቅ የሚያገለግል ልዩ ቁጥር ማለት ነው፡፡ [2]

ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አራቱ በመባጃ ሐመር መሠረት በየዓመቱ እየተቀያየሩ ወይም ቀመር እየተሠራላቸው የሚወጡ ሲሆን፣ ሦስቱ ግን ያለ መባጃ ሐመር በየዓመቱ በተመሳሳይ ወቅት ይባጃሉ፡፡

በመባጃ ሐመር የሚባጁት አራት አጽዋማት ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ድኅነት፣ ጾመ ነነዌና ጾመ ሐዋርያት ሲሆኑ፣ ያለ ማባጃ ሐመር በየዓመቱ ቋሚ ጊዜ ይዘው የሚብቱት ሦስቱ አጽዋማት ደግሞ ጾመ ነቢያት፣ ጾመ ገሃድና ጾመ ማርያም /ፍልሰታ/ ናቸው፡፡

ከላይ በተመለከትነው መሠረት መባጃ ሐመር የአጽዋማትና የበዓላት ማስገኛ ልዩ ቁጥር ነው ካልን ቁጥሩ እንዴት እንደሚገኝ ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ መባጃ ሐመርን ለማግኘት መጥቅዕንና በዓለ መጥቅዕ የዋለበትን ዕለት ተውሳክ እንደምራለን፡፡ ይቆየን

ተውሳክ
ተውሳክ ማለት ለአንድ ጾም ወይም ለአንድ ዕለት የተሰጠ ልዩ ቁጥር (ኮድ) ማለት ነው፡፡ በዚህ ቁጥር መሠረትም አጽዋማትንና በዓላትን ማውጣት ይቻላል፡፡

ተውሳክ ማለት ጭማሪ፣ ተጨማሪ ማለት ሲሆን ለበዓላትና ለአጽዋማት ማውጫ ያገለግላል፡፡[3] እንዲል፡፡

መጥቅዕ ማለት ነጋሪት ወይም ደወል ማለት ነው፡፡ ነጋሪት ሲመታ፣ ደወል ሲደወል ሕዝብ ይሰበሰባል፤ መልእክትም ይተላለፋል፡፡ በዓላትና አጽዋማትም በመጥቅዕ ይሰበሰባሉ፤ መዋያቸውንም በዚህ ማወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዕለታት ተውሳክ ጋር ተደምሮ መባጃ ሐመርን ያስገኛል፡፡

      መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ= ያለፈው ዓመት መጥቅዕ + ጥንተ መጥቅዕ (ጥንተ መጥቅዕ በየዓመቱ የማይቀያየር ቁጥር ሲሆን ይኸውም 19 ነው፡፡)

መጥቅዕን በዚህ መንገድ ማግኘት ከቻልን፣ በዓለ መጥቅዕ እንዴት እንደሚገኝ አሁን እንመለከታለን፡፡

‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ››

ይህ ታላቅ መልእክት ያለው የአባቶቻችን አባባል ሲሆን ለበዓለ መጥቅዕ ማውጫ የሚያገለግል ንግግራዊ ፎርሙላ ወይም ቀመር ነው፡፡ መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ ማለት በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውል ማለት ሲሆን፣ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ ማለቱ መጥቅዕ ባነሰ ጊዜ በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውለው ማለት ነው፡፡

መጥቅዕ በዛ የሚባለው ከዐሥራ አራት በላይ ሲሆን ነው፤ አነሰ የሚባለው ደግሞ ከዐሥራ አራት በታች ሲሆን ነው፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በላይ ከሆነ በዓለ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ከሆነ ደግሞ በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት ይውላል፡፡ ይህ ሁል ጊዜም ቢሆን የሚያገለግል ሕግ ነው፡፡ ለዚህም ነው አበው ‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረምንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ›› ያሉት፡፡

ለምሳሌ የ2011ን መባጃ ሐመር እንፈልግ፡፡

መባጃ ሐመርን ከመፈለጋችን በፊት ግን መጥቅዕን ማወቅ የግድ ነው፡፡ መጥቅዕን ለማወቅ ደግሞ የወንበርን ዓመታዊ ስሌት ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም፤

ወንበር = ቅልክ+ድልክ – 1

19

=5500+2011 -1

19

=395 ቀሪ 6-1

ወንበር =5

የ2011 ወንበር 5 ነው ማለት ነው፡፡

ከዚህ በመነሣት መጥቅዕን ለማግኘት፤

መጥቅዕ= ወንበር (ጥንተ መጥቅዕ)

= 5(19)

30

= 3 ቀሪ 5

መጥቅዕ = 5

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕን ለማግኘት፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ስለሆነ ጥቅምት ላይ በዓለ መጥቅዕ ይውላል፡፡ ስለዚህ ጥቅምት 5 ሰኞ በዓለ መጥቅዕ ሲሆን፤ ይህ በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ሰኞ ተውሳኩ 6 ነው ማለት ነው፡፡

ስለዚህ፤

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት = ሰኞ

የሰኞ ተውሳክ = 6

መባጃ ሐመር = 5 + 6 = 11

ስለዚህ የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር 11 ስለሆነ በዚህ መሠረት የ2011ን በዓላትና አጽዋማት ማውጣት ይቻላል፡፡

የመባጃ ሐመር ዋነኛ አገልግሎት ከአጽዋማት ተውሳክ ጋር እየተደመረ በዓላትንና አጽዋማትን ማስገኘት ነው፡፡ ስለዚህ የአጽዋማትንና የበዓላትን ተውሳክ ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡በመሆኑም መባጃ  ሐመሩንና የበዓላትና የአጽዋማትን ተውሳክ በመጠቀም የ2011ን የበዓላትና የአጽዋማትን መግቢያ እናገኛለን፡፡

ጾመ ነነዌ
ጾመ ነነዌ የራሱ የሆነ ተውሳክ የለውም፡፡ የሚወጣውም ያለ ተውሳክ በመባጃ ሐመር ብቻ ነው፡፡

ሀ. በዓለ መጥቅዕ በመስከረም በሚውልበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በጥር ይውላል፡፡

ለ. በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ሐ. መጥቅዕ ከ፲፬(14) በላይ ሆኖ ከዕለት ተውሳክ ጋር ስንደምረው ከ፴(30) ከበለጠ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ከላይ የተዘረዘሩት አራት ነጥቦች መቼም ቢሆን የማይለወጡ ቋሚ ሕጎች ናቸው፡፡ በመሆኑም እነዚህን አራቱን በቃል አጥንቶ መያዝ ያስፈልጋል፡፡

ምሳሌ፡- ከላይ የተመለከትነውን የ2011 ዓ.ምን ጾመ ነነዌ እናውጣ፡፡

መጥቅዕ 5 ሲሆን በዓለ መጥቅዕ ጥቅምት ሰኞ ነው፡፡ መባጃ ሐመሩ ደግሞ 11 ነው፡፡ ከላይ በ‹‹ለ››እንደተመለከትነው በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል ብለናል፡፡ በተጨማሪም ጾመ ነነዌ ተውሳክ ስለሌላት በመባጃ ሐመርብቻ ነው የምትወጣ ብለናል፡፡ ስለዚህ መባጃ ሐመሩ 11 ስለሆነ የካቲት 11 ቀን ጾመ ነነዌ ትገባለች ማለት ነው፡፡

ዐቢይ ጾም
የዐቢይ ጾምን ተውሳክ ለማግኘት ከጾመ ነነዌ ማግስት ጀምሮ እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት መቁጠር ነው፡፡ እኒህም ቀናት ፲፬(14) ናቸው፡፡ በመሆኑም የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ማለት ነው፡፡

ለምሳሌ በ2011 ዓ.ም ዐቢይ ጾም የገባው፤

የዐቢይ ጾም መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የዐቢይ ጾም ተውሳክ

መባጃ ሐመር = 11

የዐቢይ ጾም ተውሳክ = ፲፬(14)

የዐቢይ ጾም መግቢያ = 11 + 14 = 25

የካቲት 25 የዐቢይ ጾም መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት ቆጥረን የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ብለናል፡፡ የደብረ ዘይትን ተውሳክ ለማግኘትም በተመሳሳይ መልኩ ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ደብረ ዘይት ያሉትን ቀናት ስንቆጥር ፵፩(41) ቀናትን እናገኛለን፡፡ ለ፴(30) ሲካፈል ቀሪ (፲፩)11ን እናገኛለን፡፡ ስለዚህ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፲፩(11) ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የደብረ ዘይት ተውሳክ

= 11 + 11

= 22

ከየካቲት ቀጥሎ ያለው ወር መጋቢት ስለሆነ መጋቢት 22 ደብረዘይት ነው ማለት ነው፡፡

ሆሣዕና
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ሆሣዕና ያሉት ቀናት ፷፪(62) ናቸው፡፡ እንደተለመደው ለ፴(30) ስናካፍለው ፪(2) ቀሪ እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የሆሣዕና ተውሳክ (፪)2 ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ሆሣዕና መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የሆሣዕና ተውሳክ

= 11 + 2

= 13

ሚያዝያ 13 በዓለ ሆሣዕና ነበር ማለት ነው፡፡

ስቅለት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ስቅለት ያሉት ቀናት ሥልሳ ሰባት ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፯(7)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የስቅለት ተውሳክ ፯/7/ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ስቅለት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 7

= 18

ሚያዝያ 18 ስቅለት ነው ማለት ነው፡፡

ትንሣኤ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ትንሣኤ ያሉት ቀናት ሥልሳ ዘጠኝ ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፱(9) እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የትንሣኤ ተውሳክ ፱ (9) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ትንሣኤ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የትንሣኤ ተውሳክ

= 11 + 9

= 20

ሚያዝያ 20 ትንሣኤ ነው ማለት ነው፡፡

ርክበ ካህናት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ርክበ ካህናት ያሉት ቀናት ፺፫(93) ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለውቀሪ ፫(3)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫(3) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ርክበ ካህናት = የ2011 መባጃ ሐመር + የርክበ ካህናት ተውሳክ

= 11 + 3

= 14

ግንቦት 14 ርክበ ካህናት ነው ማለት ነው፡፡

ዕርገት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ በዓለ ዕርገት ያሉት ቀናት ፻፰(108) ናቸው፡፡ ፻፰(108)ን ለ፴(30) ስናካ ፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፲፰(18) ይቀራል፡፡ በመሆኑም የዕርገት ተውሳክ ፲፰(18) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ዕርገት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 18

= 29

ግንቦት 29 ዕርገት ነው ማለት ነው፡፡

ጰራቅሊጦስ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጰራቅሊጦስ ያሉት ቀናት ፻፲፰(118)ናቸው፡፡ ፻፲፰(118)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ቀሪ ፳፰(28) ይሆናል፡፡

፳፰(28) የጰራቅሊጦስ ተውሳክ ይሆናል፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጰራቅሊጦስ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጰራቅሊጦስ ተውሳክ

= 11 + 28

= 39

ለ፴(30) ሲካፈል 9 ቀሪ ይሆናል፡፡ ጰራቅሊጦስ ሰኔ 9 ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ሐዋርያት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ሐዋርያት ያሉት ቀናት ፻፲፱(119) ናቸው፡፡ ፻፲፱ (119)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፳፱ (29) ይቀራል፡፡

፳፱(29) የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ሐዋርያት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ

= 11 + 29

= 40

40 ለ30 ሲካፈል 1 ቀሪ 10 ይሆናል፡፡

ስለዚህ ሰኔ 10 የጾመ ሐዋርያት መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ድኅነት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ድኅነት ያሉት ቀናት ፻፳፩(121) ናቸው፡፡ ፻፳፩(121) ለ፴(30) ሲካፈል ፬(4) ጊዜ ደርሶ ፩(1) ይቀራል፡፡ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩(1) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ድኅነት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ድኀነት ተውሳክ

= 11 + 1

= 12

ሰኔ 12 የጾመ ድኅነት መግቢያ ዕለት ነው ማለት ነው፡፡

በአጠቃላይ የአጽዋማቱ ተውሳክ እንደሚከተለው ነው፡፡

አጽዋማት       ተውሳክ           የመዋያ ዕለት

ጾመ ነነዌ        = አልቦ (0)         የካቲት 11

ዐቢይ ጾም        = ፲፬(14)           የካቲት 26

ደብረ ዘይት       = ፲፩(11)          መጋቢት 22

ሆሣዕና          = ፪(2)             ሚያዝያ 13

ስቅለት           = ፯(7)             ሚያዝያ 18

ትንሣኤ          = ፱(9)             ሚያዝያ 20

ርክበ ካህናት      = ፫(3)             ግንቦት 14

ዕርገት           = ፲፰(18)          ግንቦት 29

ጰራቅሊጦስ       = ፳፰(28)          ሰኔ 9

ጾመ ሐዋርያት    = ፳፱(29)          ሰኔ 10

ጾመ ድኅነት       = ፩(1)            ሰኔ 12

ኢየዐርግና ኢይወርድ
እነዚህ አጽዋማት ምንም እንኳን በየዓመቱ የየራሳቸው ቀመራዊ ማውጫ ቢኖራቸውም ገደብ ግን አላቸው፡፡ ገደባቸውም በግእዝ ኢይወርድና ኢየዐርግ ሲባል፣ ኢይወርድ የታችኛው እርከን፣ ኢየዐርግ ደግሞ የላይኛው እርከን ነው፡፡ በአማርኛው ገደብ ልንለው እንችላለን፡፡ በዚህም መሠረት የአጽዋማት ገደብ የሚከተለውን ይመስላል፡፡

አጽዋማትና በዓላት          ኢይወርድ    ኢየዐርግ

ጾመ ነነዌ             ጥር 17             የካቲት 21

ዐቢይ ጾም           የካቲት 1             መጋቢት 5

ደብረ ዘይት          የካቲት 28            ሚያዝያ 2

ሆሣዕና             መጋቢት 19           ሚያዝያ 23

ስቅለት          መጋቢት 24           ሚያዝያ 28

ትንሣኤ            መጋቢት 26           ሚያዝያ 30

ርክበ ካህናት        ሚያዝያ 20             ግንቦት 24

ዕርገት             ግንቦት 5                ሠኔ 9

ጰራቅሊጦስ         ግንቦት 15               ሠኔ 19

ጾመ ሐዋርያት      ግንቦት 16               ሠኔ 20

ጾመ ድኅነት        ግንቦት 18               ሠኔ 22

ቋሚ የመግቢያ ጊዜ ያላቸው አጽዋማት
                               ጾመ ነቢያት
ጾመ ነቢያት በአራቱም ዘመናት ምን ጊዜም ኅዳር ዐሥራ አምስት እንዲጾም ተወስኗል፡፡

                                   ጾመ ገሀ  ድ
ጾመ ገሀድ የትክ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም ዓርብንና ሮብን የሚያሽር በዓል በዓርብና በሮብ ሲውል በትኩ በዋዜማው የሚጾም ጾም ነው፡፡ ለምሳሌ ጥምቀት ዓርብ ቢውል ሐሙስ ጾመ ገሀድ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አበው ለጾም ማድላት አለብን በማለት ጾመ ገሀድ ምንጊዜም ጥምቀት በጾም ቀን ዋለም አልዋለም በዋዜማው እንዲጾም ወስነዋል፡፡

                                   ጾመ ፍልሰታ 
ሐዋርያት የእመቤታችንን ትንሣኤ ለማየት ይበቁ ዘንድ ሱባኤ ገብተው የጾሙት ጾም ሲሆን ምንጊዜም ነሐሴ አንድ ቀን ገብቶ ከሁለት ሱባኤ በኋላ የእመቤታችን ዕርገት ይፈጸማል፡፡

[1]  አቡሻኸር አንቀጽ 1 ገጽ 17 (የብራና ጽሑፍ)

[2] ዲ/ን ታደለ ሲሳይ ባሕረ ሐሳብ በቀላል አቀራረብ ገጽ 71

[3]  ዝኒ ከማሁ ገጽ 66

የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል

ምዕዳነ አበው

በዲ/ን ኅሩይ ባየ እና በደረጀ ትዕዛዙ
 ሰኔ 17 ቀን 2003 ዓ.ም
/ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት1-15፣ 2003 ዓ.ም/ 
 
የቅዱስ ሲኖዶስ የርክበ ካህናት ጉባኤ ከግንቦት 10-16 ቀን 2003 ዓ.ም ሲካሔድ ቆይቶ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ተጠናቋል፡፡ ስለ ጉባኤው ሒደት አስተያየታቸውን እንዲሰጡን፤ ተሳታፊ ከነበሩት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ይመለከታቸዋል ብለን ያሰብናቸውን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት አነጋግረን የዚህ ዕትም የአብርሃም ቤት እንግዳ አድርገናቸዋል፡፡

«ያሳለፍናቸው ውሳኔዎች በሥራ ላይ መዋል አለባቸው፡፡»

  የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል

ስምዐ ጽድቅ፡- የግንቦቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የርክበ ካህናት ጉባኤ ስለተወያየባቸው አጀንዳዎች ቢገልጹልን? 

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ተወያይተን ውሳኔ ያሳለፍንባቸው አጀንዳዎች ወደ ዐሥራ ሦስት ይሆናሉ፡፡ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የጉባኤ መክፈቻ ንግግር፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ዓመታዊ የሥራ ክንውን፣ በቅርቡ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ሠራተኞች ስለተደረገው የደመወዝ ጭማሪ፣ የኢትዮጵያ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ፣ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ችግር፣ መንፈሳዊ ተቋማትን በተመለከተ፣ የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ኤች አይ ቪ/ ኤድስ መከላከያና መቆጣጠሪያ መምሪያ ሥራ አፈጻጸም፣ ልማትን በተመለከተ፣ የስብከተ ወንጌል ጉዳይ፣ የሊቃነ ጳጳሳት ዝውውር፣ በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ እና በማኅበረ ቅዱሳን የተፈጠረውን አለመግባባት በተመለከተ፣ የቀጣዩ ቋሚ ሲኖዶስ አባላት ምርጫና ልዩ ልዩ የሚሉ ናቸው፡፡
 
የደመወዝ ጥያቄን በተመለከተ ማስተካከያ አድርገናል፡፡ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ችግር እንዲፈታ ተመድበው የነበሩት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ እና የሐዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪ እንዲነሡ ወስነናል፡፡ ለቀጣዩም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ለሥራው ይስማማል ብለው ያመኑበትን ሥራ አስኪያጅ እንዲያቀርቡ እና በጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ትእዛዝ ሥራውን እንዲጀምሩ ወስነናል፡፡
ዝውውር የጠየቁ ሊቃነ ጳጳሳትም ለጥያቄያቸው ምላሽ አግኝተዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ቁልፍ የሆነው ስብከተ ወንጌል መሆኑ ይታመናል፡፡ በመሆኑም በስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ ቤተ ክርስቲያኒቱ የማታውቃቸው ሕገ ወጥ ሰባክያን እንዳይሰብኩ አግደናል፡፡ ሕገ ወጥ ሰባክያን ብቻ ሳይሆኑ ሕገ ወጥ ዘማርያንም በየትኛውም የስብከተ ወንጌል ዐውደ ምሕረት ቆመው እንዳያገለግሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጀ መምሪያ እና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ያለውን አለመግባባት ለመቅረፍ ከሊቃነ ጳጳሳት ሦስት አባቶች ከሊቃውንት ጉባኤ አራት ምሁራን ተመርጠው ጉዳዩን አጣርተው ለጥቅምት ሲኖዶስ እንዲያቀርቡ ኮሚቴዎችን ሰይመናል፡፡

ለቀጣዩ ስድስት ወራት የሚያገለግሉ ቋሚ የሲኖዶስ አባላትም ተመርጠው ሥራቸውን እንዲቀጥሉ አድርገናል፡፡ በተጨማሪም ከገጠሪቱ ክፍሎች ትምህርት ቤታቸውን ለቅቀው ወደ አዲስ አበባ እየፈለሱ የሚመጡ ሊቃውንት ባሉበት እንዲረጉ ለማስቻል በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ እና በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በኩል ችግሩ እንዲቀረፍ አቅጣጫ ሰጥተናል፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስብከተ ወንጌል በተመለከተ ቀደም ብለው ሲገልጡልን ሕገ ወጥ ሰባክያን እና ዘማርያን ታግደዋል ብለውናል፡፡ ሕገ ወጥ ሰባክያን እና ዘማርያን ሲባል ምን ማለት ነው? ቅዱስ ሲኖዶስ ስለዚህ ጉዳይ ከዚህ ቀደም ወስኖ አልነበረም?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ሕገ ወጥ ሰባክያን እና ዘማርያን ማለት ቤተ ክርስቲያኒቱ ያላስተማረቻቸው የማታውቃቸው ያልተፈቀደላቸው ማለት ነው፡፡ እነዚህን ሕገ ወጥ ሰባኪያን እና ዘማርያን ባለፈው ጥቅምት ጉባኤ እንዲታገዱ ብለን መወሰናችን እርግጥ ነው፡፡ አሁን ግን ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ የሆነ ውሳኔ ነው ያስተላለፈው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ሰባክያን እና ዘማርያን ሕጋውያን ናቸው ለማለት መሥፈርቱ ምንድን ነው?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ሕጋውያን ሰባኪያን እና ዘማርያን የምንላቸው በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ የተካተቱ /የታቀፉ/ የአሠራር መዋቅርና መመሪያዋን የሚያከብሩ ማለታችን ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በጉባኤው የተወሰኑ ውሳኔዎች አፈጻጸማቸው እንዴት ይከናወናል?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ቅዱስ ሲኖዶስ ይሆናል ይጠቅማል እና ይበጃል ያለውን ነገር በሙሉ ወስኗል፡፡ ውሳኔውም በሚመለከታቸው አካላት ተግባራዊ መሆን አለበት፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በጉባኤው ላይ የነበረው ውይይት ውጤታማ ነበር ማለት እንችላለን?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- አዎ ውጤታማ ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡ በመጨረሻ መግለጽ የምፈልገው፤ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በሕገ ልቡና የነበረ በሕገ ኦሪት የጸና በሕገ ወንጌል በሐዋርያት፣ በሊቃውንት በጳጳሳት እና በካህናት እየተከናወነ ለዚህ ደርሷል፡፡ ከዘመነ መሳፍንት፣ ከዘመነ ነገሥት እና ከዘመነ አበው እየተወራረደ እስከ ዘመነ ሥጋዌ ዘልቆ ለዚህ ትውልድ የተላለፈ ባሕል፣ ሃይማኖት ቀኖና ትውፊት እና ዶግማ አለን፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዚህች ሀገር ታላቅ ድርሻ ያላት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ብዕር ቀርጻ፣ ቀለም በጥብጣ፣ ብራና ዳምጣ፣ የጽሕፈት መሣሪያ በሌለበት ጊዜ አሁን የምንገለገልበትን የብራና መጻሕፍት ጽፋ ታሪክ ጠብቃ ያኖረች ነች፡፡ ፊደልን አዘጋጅታ ሀ ሁ ብላ ያስተማረች ገንዘብ ሚኒስቴር ትምህርት ሚኒስቴር ሆና ያገለገለች ለትውልድ የዕውቀት እንጀራ ጋግራ ያሰናዳች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ የውጭ ወራሪ፣ የውስጥ መስሎ አዳሪ ጠላት በተነሣ ጊዜ ታቦት በራሷ፣ ቃጭል በጥርሷ ይዛ አዋጅ እየነገረች፣ ፍርሃት እንዳይመጣ እያበረታታች ድንኳን ተክላ ሥጋ ወደሙ ለሚገባው ሥጋ ወደሙ እየፈተተች እያቀረበች እያስተማረች እያጽናናች የታመመውን እያስታመመች የሞተውን እየቀበረች የሀገርን አንድነት ያስጠበቀች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ከትናንት እስከ ዛሬ የዘለቀውን የቤተ ክርስቲያን ውለታ እንዘርዝረው ከተባለ ጊዜው አይበቃንም፡፡ ትውልዱም ይኼን ታሪክ አውቆ በማንነቱ ኮርቶ በሃይማኖት ጸንቶ የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ሥርዓት ቀኖና እና ዶግማ እንዲጠብቅ አደራን አስተላልፋለሁ፡፡

 
ስምዐ ጽድቅ፡- ስለነበረን መልካም ቆይታ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- እናንተንም እግዚአብሔር ይጠብቃችሁ አገልግሎታችሁንም ይባርክ፡፡

«ጅራቱን አትልቀቅ ቀንዱን ትይዘዋለህ»
 

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የምዕራብ ትግራይ ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ 

ስምዐ ጽድቅ፡- የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የተጠበቀውን ያህል ውጤታማ ነበር ማለት ይቻላል?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- ውይይቱ ቢያውልም፣ ቢያሰነብትም፣ ቢያከራክርም፣ ቢያዘገይም፣ ቢጎተትም ለቤተ ክርስቲያን ይጎዳሉ፣ ለምእመናን አይጠቅሙም፣ ለሀገር አይበጁም ያልናቸው ችግሮች ሁሉ እንዲቆሙ አድርገናል፡፡ ስለዚህ ውይይቱ ውጤታማ ነበር ማለት ይቻላል፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ስብከተ ወንጌል ምን የተወሰነ ነገር አለ?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- ስብከተ ወንጌል የቤተ ክርስቲያኒቱ የጀርባ አጥንት ነው፡፡ በስብከተ ወንጌል ውስጥ የማይመለከታቸው አካላት ሰርገው ገብተው ጥንት የነበረውን ሥርዓታችንን እንዳያበላሹ ጥንቃቄ መደረግ አለበት፡፡ የቆየው ሥርዓታችን ተንዶ አዲስ ሥርዓት መተካት የለበትም፡፡ እነዚህን ሕገወጥ ሰባክያን በተመለከተ ባለፈው የጥቅምት ጉባኤ የተወሰነ ውሳኔ ነበር፡፡ አፈጻጸም ላይ ግን ተግባራዊ ሳይሆን ቆይቷል፡፡ ከአሁን በኋላ ግን በተግባር ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ወስኗል፡፡ «ጅራቱን አትልቀቅ ቀንዱን ትይዘዋለህ» እንደሚባለው ስብከተ ወንጌል ተዛብቷል፣ አብነት ት/ቤቶች ተዳክመዋል፣ ገዳማቱ ተቸግረዋል፡፡ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን እየጎነተሉን ነው እያልን፤ ከቀላል ወደ ከባድ፣ ከታች ወደ ላይ እየተጓዝን ነው፡፡ በዙሪያችን የሚታዩትን ችግሮችን በጋራ መቅረፍ አለብን፡፡ ሕገ ወጥ ሰባክያኑን በተመለከተ የተወሰነው ውሳኔ በመምሪያው ሊቀ ጳጳስ በኩል ተፈጻሚ እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አጠቃላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አፈጻጸም እንዴት ሊከናወን ይችላል?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥራዋን የምታንቀሳቅሰው በሕገ ቤተ ክርስቲያን እና በቃለ ዓዋዲው መሠረት ነው፡፡ በተለይ በአፈጻጸም እና በአሠራር በኩል ሙሉ በሙሉ የምታከናውነው በቃለ ዓዋዲው ነው፡፡ ቃለ ዓዋዲው የተመሠረተው በሦስት አካላት ነው፡፡ ሦስቱ አካላትም አንደኛ የካህናት ጉባኤ ሁለተኛ የምእመናን ጉባኤ ሦስተኛ የወጣቶች ጉባኤ በመባል ይታወቃሉ፡፡ እነዚህ ሦስቱ ክፍሎች በመደማመጥ፣ በመቻቻል፣ በመወያየት በመናበብ እና በመተያየት ሥራቸውን ሙሉ በሙሉ ያካሒዱታል፡፡ ከታች እነዚህ አካላት ሆነው ከላይ ያለው የቤተ ክርስቲያኒቱ የሥልጣን አካል ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ምንጊዜም ቢሆን መመሪያ ነው የሚያስተላልፈው፡፡ የሚሠራውና የማይሠራውን የሚሆነውን እና የማይሆነውን ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔውን የሚያስተላልፈው ከላይ ለተገለጡት ሦስት አካላት ነው፡፡ በዚህም መሠረት ከሕፃናት እስከ ዓዋቂ ከካህናት እስከ ምእመን የየራሳችን ድርሻ አለን ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ገበሬው መገበሪያ ያቀርባል፡፡ ካህኑ ይረከበዋል፡፡ ሊቀ ጳጳሱ ይባርከዋል ለአገልግሎትም ይውላል፡፡ ሸማ ሠሪው ልብስ ይሠራል ለካህኑ ይሰጠዋል ሊቀ ጳጳሱ ይባርከውና ልብሱ ይቀደስበታል፡፡ አንጥረኛው መስቀል ይሠራል፡፡ ሠርቶም ለካህኑ ይሰጠዋል፡፡ ካህኑም ለሊቀ ጳጳሱ ያቀርበዋል ሊቀ ጳጳሱ ባርኮ እንዲባርክበት መልሶ ለካህኑ ይሰጠዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የተሟላ የሚሆነው ሁላችንም ተባብረን ስናገለግል ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ወስኖ ውሳኔውን በተግባር ፈጽሞ እንዲያሳያቸው የሚጠብቁ ሰዎች አሉ፡፡ ይኼ ግን ስሕተት ነው፡፡ የተወሰኑ ውሳኔዎችን መፈጸም እና ማስፈጸም የምእመናን ድርሻም እንደሆነ መታወቅ አለበት፡፡ የስሕተት ትምህርቶች ሲሰጡ፣ የቤተክርስቲያኒቱ ሥርዓት ወዳልተፈለገ ጎዳና ሲያዘነብሉ ምእመናን ዝም ማለት የለባቸውም፡፡ ከሊቃነ ጳጳሳትም ጀምሮ እስከ ምእመናን ድረስ የድርሻችንን ስንወጣ ቤተ ክርስቲያኒቱ በትክክል ትጓዛለች፡፡

ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚነቅፉ፣ ቅዱሳን መላእክትን የሚቃወሙ፣ ቅዱሳኑን የሚተቹ ትምህርቶች በየዐውደ ምሕረቶቻችን ይሰጣሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ምእመናን ዝም ማለት የለባቸውም፡፡ ንስጥሮስ የክሕደት ትምህርት ሲሰጥ ሰምተው የማናውቀውን እንግዳ ትምህርት አንተ ከየት አመጣኸው? ብለው የተቃወሙት ምእመናን ናቸው፡፡ ስለዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተፈጻሚ የሚሆነው በካህናት እና በምእመናን ሲተገበር ነው፡፡ መሐንዲስ ፕላን ማውጣት እንጂ ግንብ መገንባት ላይጠበቅበት ይችላል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ያወጀውን አዋጅ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ ለጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ያቀርቡታል፡፡ ከጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ድረስ በመሸኛ ይልኩታል፤ በዚህ መልኩ ይፈጸማል ማለት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በቅርቡ የሐዋሳ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሆነው የተመደቡት ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ለመነሣታቸው ምክንያቱ ምንድን ነው?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- በቃለ ዓዋዲው እና በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ደንብ መሠረት የሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች የሚሾሙት በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቅራቢነት በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ በጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ፈቃድ በምእመናኑ ይሁንታ ሲያገኙ ነው፡፡ የሐዋሳው ሥራ አስኪያጅ ግን ሊቀጳጳሱ ስላልፈቀዱላቸውና ምእመናን መቃወማቸውን ቅዱስ ሲኖዶስ ስለተረዳ ሊነሡ ችለዋል፡፡ የማይሆን ነገር አይሆንም ማለት ነው፡፡ በግዴታ የሚሆን አንዳች ነገር የለም፡፡

ስምዐ ጽድቅ ፡- በመጨረሻ የሚያስተላልፉት መልእክት ካለ?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- ለቤተ ክርስቲያናችን ሁለንተናዊ ተልእኮ የሁላችንንም ትብብር ይጠይቃል፡፡ እርስ በእርሳችን በመተያየት በመደማመጥ አብረን ለመሥራት እንነሣ፡፡ ገብረ ማርያም ተብለን በስመ ጥምቀት መጠራት ብቻ ሳይሆን ለማርያም ምን አደረግሁ ብለን መጠየቅ አለብን፡፡ ሰይፈ ሚካኤል ከተባልን ለሚካኤል ምን አደረግሁ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ የድርሻችንን ለመወጣት ጠንክረን እንሥራ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ሰጡን ማብራሪያ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ ሰላሙንም ያብዛላችሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አሜን ብፁዕ አባታችን፡፡

«ውሳኔዎቻችን ወረቀት ውጧቸው እንዳይቀሩ የሚያስተገብር አስፈጻሚ ያስፈልጋል»

 

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የሲዳማ፣ ጊዲዮ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ሰብከት ሊቀጳጳስስምዐ ጽድቅ፡- በሲኖዶሱ ጉባኤ ስለእርስዎ ሀገረ ስብከት ምን ተወሰነ? በውሳኔው መሠረት በሀገረ ስብከትዎ ምን ምን ተግባራት ለማከናወን ታስቧል?
ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- ያው በሐዋሳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጵጵስናዬን ይዤ እንድቀጥል ተወስኗል፡፡ በፊትም የቆመ ነገር የለም፡፡ የእርስ በርስ ብጥብጥ ስለነበረ ቅዱስ አባታችን እዚህ ቆይ ስላሉኝ ትንሽ እዚህ ቆይቼ ነበረ፡፡ አሁንም ሥራችንን ከቀጠልን ልንሠራቸው ያሰብናቸው ነገሮች አሉ፡፡ የስብከተ ወንጌሉን አገልግሎት ቅድሚያ ሰጥተን፣ ካህናትን እያሠለጠንን ሕይወት ለዋጭ የሆነውን ትምህርተ ወንጌል ለማስፋፋት ነው የምንሠራው፡፡ ሁለተኛ ልማት ላይ እናተኩራለን፡፡ በቀበሌ ኪራይ ላይ ያለውን የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ለማሠራት ዕቅድ አውጥተናል፡፡ ሦስተኛ የተጀመረ ማሠልጠኛ አለ፤ አዳሪ ተማሪዎችን ቁጥራቸውን በማሳደግ ጥራት ያለውን ትምህርት ለመስጠት አቅደናል፡፡ ከዚህ በተረፈ እርቅና ሰላምን በመስበክና በማስታረቅ ሰላም እንዲመጣ መጣር ዋናው ዕቅዳችን ነው፡፡ ይህን ከሁሉ ቀድመን የምንፈጽመው ይሆናል፡፡ ሰላም ከሌለ ምንም የለምና፡፡ ወንጌል ሰላም ነው፣ ትህትና ነው፣ አንድነት ነው፡፡ ቅዱስ ወንጌልን መሠረት ያደረገ ሰላምን ለመስበክ እንጥራለን፡፡ እርቅና ሰላሙ በተግባር መገለጥ ያለበት በመሆኑ ይህንኑ በስፋት እንገባበታለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ይህንን ለመፈፀም ከምእመናኑም ሆነ ከአገልጋዮች ምን ይጠበቃል ይላሉ?

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- ምእመናንና ካህናት ሁሌም ኅብረት መፍጠር አለባቸው፡፡ ካህናት በጸሎታቸው ምእመናን በገንዘባቸው በሙያቸው፣ በጉልበታቸው ልማትን ማፋጠን ይችላሉ፡፡ ስለዚህ የተዘረዘሩትን የልማት ዕቅዶች እውን የምናደርገው ኅብረት፣ ፍቅርና አንድነት ሲኖር ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያኒቱ የተመሠረተችው በምእመንና በካህናት ነው፡፡ ካህናት ስንል ብፁዓን አባቶችም በዛ ውስጥ አሉ፡፡ ስለዚህ ኅብረት እንዲኖር መጸለይ፣ መስማማት፣ መታረቅ ያስፈልጋል፡፡ ካለፈው ዓመት ጀምሮ ሁከት ስለነበረ ምንም ሳናለማ ነው የቆየነው፡፡ እርስ በእርስ መስማማቱ ጠፍቶ ነበር፡፡ እኔም ከተመደብኩ ጀምሮ ለማስታረቅ ብዙ ሞከርኩኝ ችግሩ እዛ አካባቢ ሳይሆን ከሌላ አካባቢ የተለኮሰ ስለሆነ በቀላል ሊበርድ አልቻለም፡፡ እዛ ብቻ ቢወሰን ኖሮ ያን ያህል አያስቸግርም ነበር፡፡ ዘርፍ ያለው፣ ሽቅብ ቀንድ ያለው፣ የሚያድግ፣ ቁልቁለትም አቀበትም ያለው ስለሆነ ብዙ አስቸጋሪ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ያ እንዲቀር ነው ጸሎታችን፡፡ ለዚህ ኅብረት ያስፈልጋል፤ ቤተ ክርስቲያናችን መለያየትን አትወድም፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዐይኖችም እጆችም እግሮችም ሁሉም ሕዋሳት ተባብረው እንዲሠሩ አስተምሮናልና፣ ሳይንሱም ያዘናል፡፡ ይህን አንድነት እንድናገኝ እንጸልይ፡፡ ችግራችንን እንወቅ፣ ከባድ የሆነ አደጋ እንደከበበን ዐውቀን እንጠንቀቅ፣ ይህ አደጋ መለያየት መሆኑን ተገንዝበን እንንቃ፡፡ ስለዚህ መለያየታችንን በትዕግሥትና በእርቅ ማስወገድ ሐዋርያዊ ሥራ፣ ቤተ ክርስቲያናዊ ሥራ፣ ሕዝባዊ ሥራ መሥራት እንችላለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በቀጣይ በአካባቢው ሰላም አንድነትና ሥርዓት ተጠብቆ እንዲሔድ ያስችላል የሚል እምነት አለዎት?

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ሊቃውንት በቃለ ወንጌል ለማረጋጋት፣ ሰላም ለመስበክ ይሔዳሉ፡፡ እነርሱ ፈጽመው ከተመለሱ በኋላ ሥራችንን ለመቀጠል እንሔዳለን፡፡ ምእመናኑ ዘጠና ዘጠኝ በመቶ ከእኔ ጋር ናቸው፡፡ እነዛም ወንድሞቼ ልጆቼ ናቸው፡፡ አለመግባባት ነው እንጂ፡፡ ስለዚህ የአምላካችን ፈቃድ ከሆነ ሥራችንን እንቀጥላለን፡፡ እና ቅዱስ ሲኖዶስ በሁሉም የሀገሪቱ ክፍል ሰላም፣ አንድነት እንዲሰፍን ጸሎቱም ሥራውም ስለሆነ የታሰበው ይፈጸማል ብዬ አምናለሁ፡፡ በተለይ በደቡብ አካባቢ ትንሽ ስለሆንን ሌትም ቀንም እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ይፈልጋል፡፡ ይህ ፍላጎት እንዲሟላ እግዚአብሔር እንዲረዳን ከልብ እንጸልያለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- እርስዎ በቅዱስ ሲኖዶሱ አንጋፋ አባት እንደመሆንዎና በአገልግሎትም ረጅም ዘመን እንደ መቆየትዎ ከሕገ ቤተ ክርስቲያን አንጻር የሲኖዶሱን ውሳኔዎች አፈጻጸም ካለፉት ዓመታት ጋር እንዴት ያነጻጽሩታል? የሌሎች ሀገሮች ተሞክሮም ካለ ቢያካፍሉን?

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- «ሲኖዶስ» በኢትዮጵያ ኦርቶዶስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕግና ሥርዓት መሠረት የሐዋርያትን ሲኖዶስ ተከትሎ የሚሔድ ነው፡፡ ከሐዋርያት ጀምሮ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚመሰለው በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ውሳኔ ደግሞ ይግባኝ የለውም፡፡ ግን ሲኖዶስን የሚያጅቡ ፍቅር፣ ጸሎት፣ ሰላም፣ ትህትና፣ ይቅርታ ናቸው፡፡ እነዚህን ሁሉ ተላብሶ ወንጌል እንዲሰብክ የሚወስን ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያንን ዶግማዋን ሥርዓቷን የሚጠብቅ ነው፡፡ ምእመናን በጎቿን የሚጠብቅ፣ የሚያስጠብቅ ነው፡፡ በዚህ መሠረት ከቀደምት ጊዜያት ጀምሮ ውሳኔ ይወሰናል ነገር ግን ውሳኔን ማስፈፀም ላይ ችግር አለ፡፡ በጣም አስፈላጊ የሆኑ ውሳኔዎች ላይ አስፈጻሚ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የሲኖዶሱን ውሳኔ ከፓትርያርኩ ጎን ሆኖ የሚያስፈልጽም አካል ያስፈልጋል፡፡

ውሳኔዎቻችን ወረቀት ውጧቸው እንዳይቀር በተግባር የሚያስፈጽም ታላቅ ኃይል የለንም፡፡ ከጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ጋር ተባብረው የሚሠሩ ቢያንስ ዐሥራ ሁለት ሊቃነ ጳጳሳት ያሉበት አስፈጻሚ አካል ያስፈልጋል፡፡

የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጠንካራ የሆነበት ምክንያት ከፓትርያርኩ ጋራ ዐሥራ ሦስት አባላት ያሉበት አስፈጻሚ በመኖሩ ነው፡፡ እኔ ዘጠኝ ዓመት እዛ ስቀመጥ ያየሁት ጠንካራ ነገር ይህ ነው፡፡ ምልዐተ ጉባኤው ወስኖ ሲሔድ እነዚህ አስፈጻሚዎች ተግባራዊ እንዲሆን ያደርጋሉ፡፡ እያንዳንዱ ውሳኔ አይባክንም፡፡ እንዲህ ዓይነት አሠራር በሲኖዶሳችን ሊኖር ይገባል፡፡ መወሰን ብቻ ዋጋ የለውም፡፡ አፈጻጸሙን መከታተል ይገባል፡፡ መፈጸሙን ማረጋገጥ ይገባል፡፡ ከዚህ አንጻር ሲኖዶሳችን አስፈጻሚ ክፍል እንዲኖረው ይደረግ ነው የምለው፡፡ በሕገ ሲኖዶስ እየተመራ የሚሠራ ጠንካራ አስፈጻሚ ክፍል ቢያንስ መቋቋም አለበት፡፡ ብዙ ወስነን ጥቂቶቹ ብቻ ናቸው ተግባራዊ የሚሆኑት፡፡ ያ ስለሆነ ነው አስፈጻሚ ክፍል አስፈላጊ ነው የምለው፡፡

«ሁሉም የቤተክርስቲያን አካላት ግዴታቸውን መወጣት አለባቸው»

 
የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስስምዐ ጽድቅ፡- በስብከተ ወንጌል ረገድ የዘንድሮው ግንቦት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ውሳኔና ሐዋርያዊ ተልእኮ ምን ይመስላል? አፈጻጸሙስ ላይ ምን ታስቧል?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ላይ ያለው ችግር ውሎ ያደረ ውዝፍ በመሆኑ ለማስተካከል ጊዜ ይጠይቃል፡፡ መዋቅራዊ ሰንሰለቱን፣ ጠብቆ ማስቀጠል ግድ ይላል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ውጪ የሚንቀሳቀሱ እና ጥልቀት የሌለው ትምህርት ያላቸው፤ ከገንዘብና ከጥቅም ጋር የተያያዘ ችግር ያለባቸው ናቸው ይህን ችግር እየፈጠሩ ያሉት፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረት እየሰጠ በመዋቅር ደረጃ አገልግሎቱ እንዲሰፋ እያደረገ ነው፡፡ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ በዘርፉ አባት አስቀምጧል፡፡ የአንድ አባት /ሊቀ ጳጳስ/ ዓላማው ወንጌልን መስበክ ነው፡፡ ከጥንተ ስብከት ጀምሮ ወደ ዓለም ሒዱ ነው፡፡ ወንጌል ለሁሉም ነው፡፡ ድኅነት ስለሆነ፡፡ ከዚህ አንጻር ወደ ቤተ ክርስቲያናችን ስንመጣ አፈጻጸሙ ላይ ችግር አለ፡፡ ማእከላዊነቱን አለመጠበቅ አለ፡፡ አምና ተወስኖ ነበር የአፈጻጸም ችግር ስላለ አልተተገበረም፡፡ ዘንድሮም ያንኑ ውሳኔ በማንሳት በበለጠ መሥራት እንዳለብን ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ ስብከተ ወንጌል መምሪያው ሳያውቀው፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈቃድ ያልሰጠቻቸው ሰባኪያን በየትኛውም ቦታ እንዳይንቀሳቀሱ ተብሎ ውሳኔ ተላልፏል፡፡ ይህንን መምሪያው፣ የየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት የሌሎችም የእምነቱ ተከታዮች አፈጻጸሙ ላይ ትኩረት ሰጥተው /ሰጥተን/ በጋራ መሥራት አለብን፡፡ በሴርኩላር የሚተላለፈውን መመሪያ በየደረጃ መፈጸም ግድ ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ከቤተ ክርስቲያን ዕውቅና ውጪ የሚንቀሳቀሱ ሰባክያነ ወንጌል ላይ የተላለፈው ውሳኔ ተግባራዊ አለመሆኑ የሚያስከትለው ተፅዕኖ ምንድነው ይላሉ?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ወንጌል ሰላም ነው፡፡ ትርጉሙ አንድነት ነው፡፡ ጉዳቱ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያልዘለቁ፣ በመምህራን እግር ሥር ዕውቀትን ያልቀሰሙ እናስተምር ሲሉ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ትክክለኛው ወንጌል፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ ወደ ምእመናን ይደርሳል ለማለት አይቻልም፡፡

አንዳንድ ማሠልጠኛ ገብተው በለብለብ ምኑንም ሳያውቁ እያቋረጡ እየወጡም ገበያው ሲመቻችላቸው ዕውቅና እያገኙ ሲሔዱ ዓውደ ምሕረቱን እንደራሳቸው ያደርጉታል፡፡ ይህ ተገቢ አይደለም፡፡ ተስተካክሎ የሚያገለግል ብናገኝ እሰየው ነው፡፡ ሰው ያንሰናል እንጂ አይበዛብንም፡፡ ሁሉም የቤተ ክርስቲያን ልጆች ናቸው፡፡ ነገር ግን ከታች አጥቢያ ጀምሮ እስከ መንበረ ትርያርኩ ድረስ በመመሪያ የሚመጡ የሚወርዱ መሆን አለባቸው፡፡ ዋናው ተወስኗል፡፡ አፈጻጸሙ ላይ የሁሉም የቤተ ክርስቲያን አካላት ግዴታቸውን መወጣት አለባቸው፡፡

ያለፈቃድ ሊሰብክ የሚወጣ ካለ መቃወም፣ መከልከል ይገባል፡፡ ይህ መምሪያው ብቻውን የሚወጣው አይደለም፡፡ ጥቃቅን ችግሮች ሊያጋጥሙ ይችላሉ፡፡ ሃይማኖቱ ላይ መጠንከር ግን ይገባቸዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና ሥርዓት መሠረት አሰረ ክህነት የሌለው ወንጌል አይሰብክም፡፡ ይህ ካልሆነ ከፕሮቴስታንቱ ምን ልዩነት አለን፡፡ አሁን የመጣ እንጂ ቢያንስ ዲቁና የሌለው እንዴት ይሰብካል? በማብቂያ ምን አድርጉ ሊል ነው? የወንጌል ማሰሪያው ንስሐ ግቡ፣ ሥጋውን ደሙን ተቀበሉ ነው፡፡ ያኔ ምእመኑን ምን ሊል ይችላል? ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንን የማያውቅ፣ ቢያንስ ዲቁና የሌለው ሲያስተምር እናያለን ይህ ጊዜው ዝም ብሎ ያመጣው ነው እንጂ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት አይደለም፡፡

ይህንን መምሪያው እያጣራ ነው፡፡ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ጠብቀው ማኅበር መሥርተው ሲመጡ እንቀበላቸዋለን፤ መምህራኑ ግን ይህን ደረጃ ማለፍ ያለባቸው መሆኑን እናረጋግጣለን፡፡ ይህ የመምሪያው ሓላፊነት ነው፡፡ የወጣቱ ወደ ቤተ ክርስቲያን መምጣት ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ አካሔዱ ግን የመምሪያው ነው፡፡ መዝሙራቸው ሥርዓት መያዝ አለበት፡፡ ትምህርታቸው ሥርዓትን የጠበቀ መሆን አለበት፡፡ ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ ነው፡፡ አፈጻጸሙ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ፣ መምሪያው እና የየአህጉረ ስብከቶቹ ትብብር እና የምእመኑ እገዛ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ውጭ የሚንቀሳቀሱ ያመጡት ጉዳት ለተባለው ጤናማውን ምእመን እየበረዙ እየለያዩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ አደጋ መፍጠር ነው፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለኅብረተሰቡም ሆነ ለመንግስት አደጋ ነው፡፡ ዛሬ በልማት እየተደረገ ያለውን ሩጫ ያደናቅፋል፡፡ ሕዝቡ ሰላም ሳይኖረው ልዩነት ካለ አደጋ ነው፡፡

ይህ ድርጊት በእምነት፣ በቀለም፣ በጎሳም አይደለም፡፡ አጠቃላይ የሰውን ልጅ ሰላም የሚነካ ነው፡፡ ስለዚህ የኛ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ትምህርት ሰላም ስለሆነ ይህንኑ ማስፈጸም ላይ መትጋት ነው፡፡ ሰላማዊውን ሕዝብ ሰላም የሚነሳ ከሆነ ይህ ሰይጣናዊ ስብከት ነው፡፡ ይህን ሕዝቡ ስለሚያውቀው እኛም እግዚአብሔር የፈቀደልንን ያህል ድርጊቱን ለማስቆም እንሔዳለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የተጠበቀውን ያህል ውጤታማ ነበር ማለት ይቻላል?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ጥሩ ነበር፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሩ እድገት እያሳየ ነው፡፡ የአባታዊነትን ግዳጅ እየተወጣ ነው፡፡ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን እንዲከበር እየጣረ ነው፡፡ በነገሮች መሰናክል አይጠፋም ነገር ግን በትዕግሥት ነጥቡን እያየን ነገሮች ሁሉ ዓላማቸውን ሳይስቱ ጉባኤው በጥሩ ግብ ላይ ነው የተደመደመው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ላይ ምን የታሰበ አቅጣጫ አለ?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ይህ ጉዳይ ሕጋውያን ሰባኪያን ካልሆኑት ጋር የሚገናኝ ጉዳይ ነው፡፡ ማንኛውም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ በሚሰጠው በየትኛውም ትምህርት አግባብ መስሎ ያልታየውን ተከታትሎ መረጃ መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ ዛሬ ማእከላዊነት ስላልተጠበቀ ማንን ከማን መለየት አስቸግሯል፡፡ ማእከላዊነቱን በጠበቀ መልኩ ሁሉም ነገር ከአጥቢያ እስከ መንበረ ትርያርክ ሲኬድ ሁሉም ግልጽ ይሆናል፡፡ አንዳንዶች በየአጥቢያው ቤተ ክርስቲያን የግል ደጋፊ /ቲፎዞ/ ያበጃሉ፡፡ እነዚህ በገንዘብ፣ በጥቅም… ስለሚገቡ አጥቢያዎች የራሳቸውን ጥረት አድርገው በጥንቃቄ መለየት አለባቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት የመናፍቃን እንቅስቃሴ ይህ ነው አይባልም፤ እንደአሸን ፈልተዋል፡፡

በኑሮ እያሳበቡ አንዳንዶች መምህራንና መነኮሳት ጭምር ስም ለውጠው ወደ ሌላ ሔደዋል የሚባል ነገር ይሰማል፡፡ ሃይማኖት ደግሞ ከኑሮ ጋር አይያያዝም፡፡ ይህ እንዲቆም ሁሉም መትጋት አለበት፡፡ ስለዚህ መጠንከር ነው፡፡ በተለይ ብፁዓን አባቶች መጠንከር አለባቸው የሲኖዶስ ጥንካሬ ነው መፍትሔው፡፡ ነገሮችን አይቶ መዝኖ ይወስናል፡፡ አፈጻጸሙን ይከታተላል ያኔ መናፍቃን ይህን መንጋ ይወስዳሉ ብለን አንሰጋም፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የቤተ ክርስቲያኒቱ ልዕልና እንዲከበር፣ ታሪኳ፣ ቅርሷ፣ ትምህርቷ ዶግማዋና ቀኖናዋ ተጠብቆ ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ ከምእመናንም ሆነ ከሌሎች የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮች ምን ይበቃል?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ከታች እስከ ላይ የወንጌል መረብ እንዲዘረጋ በቀና መንፈስ ነገሮችን መመልከት ነው፡፡ ዘመኑን የዋጀ ትምህርት ለምእመናን ማድረስ ቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት አለባት፡፡ ሕዝቡም መመሪያ ጠብቆ መገልገል አለበት፡፡ የጸሎት፣ የንስሐ ትምህርትን ማግኘት አለበት፡፡ ለዚህ ቀና መሆን ነው፡፡ በፍቅር በአንድነት ለአንድ ዓላማ መቆም ነው፡፡ እናት ቤተ ክርስቲያን ሁሉን ትይዛለች፤ የሕዝቡን ሥነ ምግባር፣ ሞራል፣ ሥርዓት ጠብቃ የኖረች ናት፡፡ ይህ አዲስ አይደለም፡፡ አሁን የመጣው ዕውቀት ሳይኖረው ሰባኪ ነኝ እያለ ሕዝቡን ማለያየት ሁከት መፍጠር ነው፡፡ የሚገባው ግን እውነተኛውን ወንጌል፣ የቅዱሳንን ታሪክ ገድላቸውን መስማት ነው፡፡ ይህ ትጥቅ ነው፡፡ ቅዱሳኑ እንዴት ሆነው እንደሞቱ፣ መከራን እንደተቀበሉ እንደሽንኩርት እንደድንች እንደተላጡ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ እንዲህ ሆነው ያለፉት ወንጀል ፈጽመው አይደለም ዓለምን ለማዳን ነው። ስለዚህ ብዙ ችግር የለም መዋቅር መጠበቅ ብቻ ነው፡፡ ሰፊ ክፍተት ስንፈጥር ነው ሌላው ያለአግባብ ውስጣችን የሚገባው፡፡

እስካሁን ያለፈው ሳያስጨንቀን ለወደፊቱ ተግቶ መሥራት ነው፡፡ ወንጌል በጥላቻ አይሰበክም፡፡ ፍቅርን ሰላምን ለማምጣት ትክክለኛው የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መጠበቅ ነው፡፡ ዋናው ለቤተ ክርስቲያን መኖር ነው፡፡ መኖር ማለት እናት ለልጇ አባትም ለልጁ እንደሚኖሩት ማለት ነው፡፡ የእነርሱ ተግባር አስፈላጊውን መስዋዕት ከፍሎ ልጅን ማሳደግ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ምእመናንም እንደዚያ መኖር አለባችሁ፡፡ ንስሐ መግባት፣ ሥጋውን ደሙን መቀበል፣ ጥላቻን ማስወገድ፣ እውነተኛ ሰባኪያንን አይዟችሁ ማለት ይገባል፡፡ አይሁድ «ትንሣኤው የለም» በማለት ወንጌል ረጭተዋል፤ ምእመናን ደግሞ «ወንጌል አለ ትንሣኤ አለ» በማለት ገንዘብ ማውጣት አለባቸው፡፡ ስለዚህ እርሱን ነው ለቤተ ክርስቲያን መኖር የምንለው፡፡ በተረፈ በጥላቻ የሚሆን ነገር የለም፤ በውይይት ግን ድል እናደርጋለን እግዚአብሔርም ይረዳናል፡፡

«ሌሎችን ለማምጣት እያሰብን ያሉትን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይኖርብናል»

 ብፁዕ አቡነ ቀሌሜንጦስ/ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስስምዐ ጽድቅ፡- የቅዱስ ሲኖዶስ የርክበ ካህናት ጉባኤ አጀማመርና አጨራረስ ምን ይመስል ነበር?
ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- ጥሩ ነው፤ መጨረሻው ሁሉም እንዲታይ ሆኖ ተካሒዷል፡፡ ውሳኔዎቹ ሁሉም ጥሩ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ የጉባኤው አፈጻጸም ጥሩ ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ እና ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በተያያዘ የተነሡ አሳቦች እና ውሳኔዎች ምን ይመስሉ ነበር?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡ – አንዱ በአጀንዳነት የተያዘው ይኸው ነበር፡፡ በሁለቱም ወገን ችግሮችና ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ ችግሩ ይታይ የሚለው የኛ አቋም ነበር፡፡ ለሁለቱም አካላት ደንብ የሰጠ ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡ ማየትም የሚችለው ቅዱስ ሲኖዶስ በመሆኑ ችግሩ ተጠንቶ ይቅረብ ወደሚለው መደምደሚያ ላይ ተደርሷል፡፡ ውሳኔውም ይኸው ነው፡፡ በአሠራር ማለትም በአገልግሎትም ይሁን በግል ጉዳይ ችግሩ የት እንደሆነ አጥንቶ የሚያቀርብ አካል ተመርጧል፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አጣሪው አካል ማነው? ማንን ማንን ያካትታል?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- ከአባቶችና ከሊቃውንት የተውጣጣ ነው፡፡ ሦስት ሊቃነ ጳጳሳት ማለትም፤ አቡነ ገሪማ፣ አቡነ ሕዝቅኤል፣ አቡነ ማርቆስ እንዲሁም መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን፣ ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገ/አማኑኤል፣ መልዐከ ምሕረት ዓምደ ብርሃን፣ ከሊቃውንት ጉባኤ፣ ከሕግ ክፍል አቶ ይስሐቅ ናቸው፡፡ ከአሁን ጀምሮ ሥራቸውን ይጀምራሉ ማለት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በሁለቱም ወገን ያለው ችግር መንሥኤ ምን ይሆናል ብለው ያስባሉ?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- በውጭ ሰፍቶ የምናየው ችግር ውስጡ ገብተን ብናየው ቀላል ሊሆን ይችላል፡፡ ክፍተት ግን አለ፡፡ ምናልባት የአሠራር ወይንም የአፈጻጸም ችግር ጉዳዩን እንዲጎላ አድርጎታል ብዬ አስባለሁ፡፡ ከሁለቱም ወገን ስሕተቱ የት ነው የሚለውን ለመለየት የጥናቱ ውጤት ወሳኝ ነው፡፡ ማን ምንድነው? ደንቡስ ምን ይላል? የሚለው በአጥኚዎች ተፈትሾ ለምልዐተ ጉባኤው ሲቀርብ ውሳኔ ይሰጥበታል፡፡ ዝርዝር ችግሮቻቸው ምንድናቸው የሚለውን አሁን ማወቅ አይቻልም መንሥኤውንም እንዲሁ የአጥኚዎቹ ሥራ ነው፡፡ ለሚቀጥለው ጥቅምት የጥናቱ ውጤት ይታያል ማለት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ኮሚቴ መዋቀሩና ጥናት መካሔዱ ለችግሩ መፍትሔ ያመጣል ብለው ያስባሉ?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- አዎ ያመጣል ጉዳዩ ሰፋ እያለ ሲሔድ ሁለቱንም አካላት የሚያወዛግባቸው ነገር ግልጥ እያለ ይሔዳል፡፡ ጉባኤውም የጥናት ውጤቱን ተከትሎ የሚሰጠው ውሳኔ መፍትሔን ያመጣል ብዬ አምናለሁ፡፡ ከሕግ ስሕተትም ካለ እየታረመ፣ ማስጠንቀቂያም እየተሰጠ ችግሮች እየወጡ መወያየት የሚቻልበትን ሁኔታ መፍጠር ይገባል፡፡ ማመንም ማሳመንም ይገባል፡፡ ይህ የአሠራር ሒደት ነው፡፡ ስለዚህ ማደራጃ መምሪያው ዋናው ሥራው ወጣቱ ላይ ነው፡፡ አይደለም ያሉትን እና የተያዙትን ሌሎችንም ወጣቶች ወደ ቤተ ክርስቲያኒቱ መሳብ ይገባዋል፡፡ ካሉት ጋራ ውዝግብ ከመፍጠር አገልግሎት ላይ ትኩረት ማድረግ የተሻለ ነው፡፡ ተገቢው ነገር ደንብና ሥርዓት ተከብሮ በመነጋገር ጥቃቅን ችግሮችን መፍታትና ወጣቱን መያዝ የሚገባ ነው፡፡ ሌሎችን ለማምጣት እያሰብን ያሉትን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡ ይህንን ቀላል ጉዳይ ተነጋግረን መፍታት ካልቻልን ሑከት ፈጣሪዎች እኛው ነን ማለት ነው፡፡ ይህ በጣም ለልማት እንቅፋት መሆን ማለት ነው፡፡ እኛ መርዳት እና ለሰላም አስተዋጽኦ ማድረግ ሲገባን እንዲህ ውዝግብ ውስጥ መግባቱ አግባብ አይደለም፡፡ ዓለም እየሮጠ ነው፡፡ ሕዝቡን በሰላምና በፍቅር አሰልፈን መጓዝ አለብን፡ ዋናው ትኩረታችን ወጣቱ ነው፡፡ እነርሱ ላይ መሥራት አለብን ይህ የተደራጀው ኃይል ለሀገርም ለቤተ ክርስቲያንም ጠቃሚ ኃይል ነው፡፡ በአእምሮው፣ በገንዘቡ፣ በጉልበቱ ሀገሩን እና ቤተ ክርስቲያንን የሚያለማውን ወጣት ማገዝ ይገባል፡፡ መምራት ይገባል፡፡ እነርሱ ዘንድ ጥፋት ካለ በእኛ ምክርና ግሳጼ ይታረማሉ ብለን እናምናለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በመጨረሻ የሚያስተላልፉት መልእክት አለ?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- ሰላም ለሁሉም ወሳኝ ነው፡፡ ሰላም ብለን ስንናገር ቀላል ነው፡፡ ወደ ሥራው ስንገባ ያደክማል፡፡ ሰው ራሱን ለሰላም ማዘጋጀት አለበት፡፡ ስለዚህ ሁለቱም አካላት ለዚህ ተገዢ መሆን አለባቸው፡፡ ደንቡ ሥርዓቱ ሊገዛቸው ይገባል፡፡ ለዚህ መቻቻል መከባበር ይገባል፣ የግል ጉዳይ የለም ሁሉም የሚሠራው ለቤተ ክርስቲያኒቱ ነው፡፡ አጀንዳችን ሁሉ ቤተ ክርስቲያን መሆን አለበት፡፡ ሰላም ካለ ለመደመጥም፣ ለማዳመጥም ለመምራትም ለመመራትም ይበጃል፡፡ የሁለቱም ወገን ሓላፊዎች ለዚህ ተገዢ መሆን አለባቸው፡፡ ያለ ኘሮግራም የሚሠራ ነገር ሁሉ ዋጋ የለውም፡፡ ሁሉም በፕሮግራም መመራት አለባቸው፡፡ ሁለቱም በመመሪያ እና በሕግ ቢመሩ ክብር አላቸው፣ ተወዳጅነት አላቸው፣ ውጤታማ ሥራም ይሠራል፣ ግንኙነታቸውም ይጠብቃል፡፡

ሕገ ቤተ ክርስቲያን ስለ ቅዱስ ሲኖዶስና ስለ ቅዱስ ፓትርያርክ ምን ይላል?

ግንቦት 11፣2003ዓ.ም

ቅዱስ ሲኖዶስ በ1991 ዓ.ም ባወጣው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለ ቅዱስ ሲኖዶስና ስለ ቅዱስ ፓትርያርክ የሚናገሩ ምዕራፎች እና አንቀጾችን አቅርበናል፡፡

ምዕራፍ ሁለት

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ

አንቀጽ 5
የቅዱስ ሲኖዶስ ልዕልና /የበላይነት/

1.    በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ የመንበረ ሐዋርያት ወራሽ ስለሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ የመጨረሻው ከፍተኛ ሥልጣን ባለቤት ነው፡፡

2.    ከማንኛውም የቤተ ክርስቲያኒቱ የሥልጣን መዋቅር ሁሉ የበላይ አካል ቅዱስ ሲኖዶስ ስለሆነ ሕጐችን፣ ልዩ ልዩ ደንቦችንና መመሪያዎችን የማውጣትና የዳኝነት ሥልጣን አለው፡፡

አንቀጽ 5

የቅዱስ ሲኖዶስ ዓላማ

1.    ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለመጠበቅ አገልግሎቱም የተሟላ እንዲሆን ለማድረግ፣

2.    የሃይማኖትና ቀኖና ቤተ ክርስቲያን እንዳይፋለስ ለመጠበቅና ለማስጠበቅ፣

3.    ጥንታዊውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ለመጠበቅና ለማስፋፋት፣

4.    ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋትና ለማጠናከር፣

5.    ወጣቶች ከአበው የተቀበሉትን ሃይማኖትና ሥርዓት ጠብቀው በትምህርትና በሥነ ምግባር ታንጸው እንዲያድጉ ሰንበት ትምህርት ቤትን ለማጠናከርና ለማስፋፋት፣

6.    የሰው ዘር ሁሉ ከርሃብ፣ ከእርዛት፣ ከበሽታና ከድንቁርና ተላቆ በሰላምና በአንድነት በመተሳሰብና በመረዳዳት በመንፈሳዊ ሕይወት እንዲኖር ማስተማርና መጸለይ፣

አንቀጽ 7

የቅዱስ ሲኖዶስ ሥልጣንና ተግባር

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሐዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የሚከተለው ሥልጣንና ተግባር ይኖረዋል፡፡

1.    ቅዱስ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያንን በበላይነት ይመራል፣ ይጠብቃል፡፡

2.    ሕገ ቤተ ክርስቲያን በሚፈቅደው መሠረት ሕጎችን፣ ደንቦችንና ልዩ ልዩ መመሪያዎችን ያወጣል፣ ያሻሽላል፡፡

3.    የቤተ ክርስቲያኒቱን አጠቃላይ የምጣኔ ሀብታና የሙዓለ ንዋይ መመሪያዎችን /ፖሊሲዎችን/ ይወስናል፡፡

4.    ዓመታዊውን በጀት ያጸድቃል ተግባራዊነቱንም ይቆጣጠራል፡፡

5.    የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደራዊ መዋቅር እንዲሁም የጽሕፈት ቤቶችን ደረጃና ተጠሪነት ይወስናል፡፡

6.    የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደርና አገልግሎት በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት እንዲመራ ያደርጋል፡፡

7.    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት በአገር ውስጥና በዉጭ አገር እንዲስፋፋ ያደርጋል፡፡ ትምህርት ቤቶችንም ያቋቁማል፡፡

8.    የክርስቶስን ወንጌለ መንግሥትና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ያስተምራል ያስፋፋል፡፡

9.    በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገር አዲስ የሀገረ ስብከት ጽ/ቤትና መንበረ ጵጵስና እንደ አስፈላጊነቱ ያቋቁማል፡፡

10.    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከውጭ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ያላትን ግንኙነት ያስፋፋል ያጠናክራል፡፡

11.    በውጭ አገር በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አህጉረ ስብከትና አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ለአገልግሎት የሚመደቡና እንደዚሁም በአገር ውስጥ የሚሰጠውን የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት ተምረው የውጭውን ትምህርት መማር የሚችሉ ካህናትን እየመረጠ እንዲላኩ ያደርጋል፡፡

12.    ማንኛውም ሰው ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክሎ ለሥራም ሆነ ለጉብኝት ወደ ውጭ አገር በሚላክበት ጊዜ ቅዱስ ሲኖዶስ እየፈቀደ ነው፡፡

13.    ኤጲስ ቆጶሳት እንዲሾሙ አስፈላጊ ሆኖ በተገኘ ጊዜ ቅዱስ ሲኖዶስ በምልዓተ ጉባኤ እየወሰነ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ መሠረት እንዲመረጡና እንዲሾሙ ያደረጋል፡፡ እንዲሁም ሊቃነ ጳጳሳትንና ኤጲስ ቆጶሳትን በየሀገረ ስብከቱና በተለያዩ የሥራ ክፍሎች ይመድባል በበቂ ምክንያት ያዘዋውራል፡፡

14.    በቋሚ ሲኖዶደስ የሚያገለግሉ ጳጳሳትን በየሦስት ወሩ እየመደበ እንዲሠሩ ያደርጋል፡፡

15.    በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ሥልጣን ላይ የሚመደቡትን

ሀ. የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ

ለ. የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ

ሐ. የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቱ ም/ሥራ አስኪያጅ

መ. የልማት ኮሚሽን ኮሚሽነር

ሠ.የውጭ ጉዳይ መምሪያ ሓላፊ

ረ. የልዩ ልዩ ሥራ ዘርፎች ቦርድ አባላት እየመረጡ እንዲሾሙ ያደርጋል፡፡

16.    ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው በሚያደርጋቸው ስብሰባዎች የሚቀርቡትን አጀንዳዎች ያጸድቃል እንደአስፈላጊነቱም ያሻሽላል፡፡

17.    ቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ ይሆናል፡፡ ለጥፋተኞችና ለበደለኞችም ምሕረትና ይቅርታ የመስጠት ሥልጣን የቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡

18.    በዚህ ሕግ ባልተካተቱ በማናቸውም በቤተ ክርስቲያኒቱ ጉደዮች ላይ ሁሉ ቅዱስ ሲኖዶስ የመወሰን ሥልጣን አለው፡፡

አንቀጽ 8

የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

1.    በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ፓትርያርክ፣ ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት ሆነው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አህጉረ ስብከትና በልዩ ልዩ የሥራ ክፍሎች የተሾሙ ሁሉ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ናቸው፡፡

2.    ከፓትርያርኩ ጀምሮ እያንዳንዱ ሊቀ ጳጳስ፣ ጳጳስና ኤጲስ ቆጶስ ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡

3.    የቅዱስ ሲኖዶስ አባልነት ዕድሜ ልክ ይሆናል፡፡

4.    አንድ የቅድስ ሲኖዶስ አባል ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚያፋልስ ሆኖ ከተገኘ ከአባልነቱ ይሠረዛል፡፡

5.    ይህም የሚሆነው በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ከተሰጠ በኋላ ነው፡፡

6.    በሃይማኖትም ሆነ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የተከሰሰ የሲኖዶስ አባል በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ቀርቦ ራሱን የመከላከል መብቱ የተጠበቀ ነው፡፡

7.    አንድ የሲኖዶስ አባል ስለራሱ ጉዳይ በሚታይበት ስብሰባ ላይ በአባልነት መገኘት አይችልም፡፡

አንቀጽ 9

የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ

1.    የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ በፓትርያርኩ ሰብሳቢነት ይመራል፡፡ ፓትርያርኩ በልዩ ልዩ ምክንያት ጉባኤውን መምራት ባይችል ከአባላቱ መካከል እሱ የሹመት ቅድምና ያለውን አባት በመወከል ስብሰባው ሊመራ ይችላል፡፡

2.    ከዚህ በታች ከተመዘገቡት በሦስት ምክንያቶች ካልሆነ በቀር ፓትርያርኩ ርዕሰ መንበር ያልሆነበት የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ሊካሔድ አይችልም፡፡

ሀ. ፓትርያርኩ በዕርጅናና በጤና ጉድለት ምክንያት ጉባኤውን የሚመራ አባት መወከል ካልቻለ፣

ለ. የቤተ ክርስቲያንን እምነትና ቀኖና በተመለከተ የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ እንዲደረግ የሲኖዶሱ አባላት ሲጠይቁት ፈቃደኛ ሳይሆን ከቀረ፣

ሐ. ስብሰባው ፓትርያርኩን የሚመለከት ጉዳይ ከሆነ በፍትሕ መንፈሳዊ መሠረት ይፈጽማል፡፡

3.    ከዚህ በላይ በተዘረዘሩት ምክንያቶች ፓትርያርኩ ጉባኤውን መምራት ካልቻለ በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በተመረጡ የሹመት ቅድምና ባለው አንድ አባት ስብሰባው ሊካሔድ ይችላል፡፡

አንቀጽ 10

የቅዱስ ሲኖዶስ የስብሰባ ሥርዓት

1.    ፍትሕ መንፈሳዊ በአምስተኛው አንቀጽ ቁጥር 164 በሚያዝዘው መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜ መደበኛ ስብሰባ ያካሒዳል፡፡ የስብሰባውም ጊዜ፣

ሀ. የመጀመሪያው ጉባኤ በየዓመቱ ጥቅምት 12 ቀን

ለ. የሁለተኛው ጉባኤ ትንሣኤ በዋለ በሃያ አምስተኛው ቀን /በርክበ ካህናት/ የሚካሔደው ነው፡፡

2.    አስቸኳይና ድንገተኛ ጉዳይ ሲያጋጥም፣

ሀ. ቅዱስ ፓትርያርኩ ወይም ቋሚ ሲኖዶስ በሚያደርጉት ጥሪ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ሊካሔድ ይችላል፡፡

ለ. ከጠቅላላው አባላት ከሦስት ሁለት እጁ የሚሆኑ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ምልዓተ ጉባኤ እንዲደረግ በጠየቁ ጊዜም ጥሪ ሊደረግና ስብሰባው ሊካሄድ ይችላል፡፡

3.    የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የሚባለው ከዓቅም በላይ የሆነ ዕክል ካላጋጠመ በቀር መላው አባላት የተገኙበት ጉባኤ ሲሆን ነው፡፡

4.    በዚሁ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ 3 የተገለጸው እንደተጠበቀ ሆኖ በሕመምና በልዩ ልዩ ከዓቅም በላይ በሆነ ምክንያት አንዳንድ አባላት ባይገኙ፣

ሀ. ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን በሚመለከት ጉዳይ ከጠቅላላው አባላት ከአራት ሦስት እጅ የተገኙ ከሆነ፣

ለ. አስተዳደርን በሚመለከት ጉዳይ ከጠቅላላው አባላት ከሦስት ሁለት እጅ የተገኙ ከሆነ ነው፡፡

5.    ቅዱስ ሲኖዶስ በማናቸውም ስብሰባ ላይ ውሳኔዎችን ሲያሳልፍ፣

ሀ. አስተዳደርን የሚመለከት ጉዳይ ከሆነ ከተገኙት አባላት መካከል ከግማሽ በላይ በሆነ ድምጽ የተደገፈው ሐሳብ ያልፋል፡፡

ለ. አንድን ጉዳይ ለመወሰን የአባላቱ ድምፅ እኩል በኩል ከሆነ ቅዱስ ፓትርያርኩ ያለበት ያልፋል፡፡

ሐ. ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከት ከሆነ በሙሉ ድመፅ ያልፋል፡፡

ምዕራፍ አራት

የኢትዮጵያ ፓትርያርክ

አንቀጽ 13

ስለ ቅዱስ ፓትርያርክ ምርጫ

1.    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ ቀኖና በሚፈቅደው መሠረት ተመርጦ ይሾማል፡፡

2.    ቅዱስ ሲኖዶስ ስለ ፓትርያርክ ምርጫ በሚወስነው ቁጥር መሠረት አስመራጭ ኮሚቴ ይቋቋማል፣

3.    ለፓትርያርክነት የሚመረጡት ዕጩዎች ከሊቃነ ጳጳሳት ከጳጳሳትና ከኤጲስ ቆጶሳት መካከል ሲሆን ብዛታቸው ከሦስት ያላነሡ ከአምስት ያልበለጡ ይሆናል፡፡

4.    አስመራጭ ኮሚቴው እጩዎችን ጠቁሞ ለቅዱስ ሲኖዶስ ያቀርባል፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና ሥርዓት መሠረት ምርጫው እንዲካሔድ ይደረጋል፡፡

5.    መራጮች የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በሙሉ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ፣ የየመምሪያና ድርጅት ሓላፊዎች፣ የጥንታውያን ገዳማት አበምኔቶች የአድባራት አስትዳዳሪዎች ከየሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤያት በዕድሜ ከሠላሳ ዓመት ያላነሱ የካህናትና የምእመናን ተወካዮች እንዲሁም ዕድሜያቸው ከ22 አስከ 30 ዓመት የሆኑ የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች ሲሆኑ በጠቅላላው በሰበካ ጉባኤው የሚወከሉት ከአንድ ሀገረ ስብከት አሥራ ሁለት ሆነው በሥጋወደሙ የተወሰኑ በሕገ ቤተ ክርስቲያን የጸኑ መሆን አለባቸው፡፡

6.    የምርጫው አፈጻጸም ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያወጣው መመሪያ መሠረት ይሆናል፡፡

7.    የተመረጠው ፓትርያርክ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖትንና ቀኖናዋን ሊጠብቅና አድልዎ በሌለው መልኩ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሊያስተዳድር ቃለ መሐላ ይፈጽማል፡፡

8.    ከዚህ በላይ የተደነገገው እንደተጠበቀ ሆኖ ስለ ፓትርያርክ ምርጫ ቅዱስ ሲኖዶስ ደንብ ያወጣል፡፡

አንቀጽ 14

የፓትርያርኩ የማዕረግ ስምና መንበር

1.    ፓትርያርኩ ከተሾመበት ቀን ጀምሮ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ እገሌ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ይባላል፣ ስሙም በመላዋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጸሎት ይጠራል፡፡

2.    ፓትርያርኩ በአገር ውስጥም ሆነ በውጨ አገር ለሚኖሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ምእመናን መንፈሳዊ አባት ነው፡፡

3.    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ መንበር በአዲስ አበባ ከተማ በቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ነው፡፡

አንቀጽ 15

የፓትርያርኩ ሥልጣንና ተግባር

1.    ፓትርያርኩ በተሰጠው ኃላፊነት መሠረት ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቃል፣ ያስጠብቃል፡፡

2.    በዚህ ሕግ አንቀጽ 9 ንዑስ አንቀጽ 1 መሠረት ፓትርያርኩ የቅዱስ ሲኖዶስን ጉባኤ በሊቀ መንበርነት ይመራል፡፡

3.    ፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 እና በዚሁ ሕግ አንቀጽ 7 ንዑስ አንቀጽ 13 መሠረት ፓትርያርኩ ከቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ጋር ሆኖ ኤጲስ ቆጶሳትን ይሾማል፣ እንዲሁም ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያወጣው መመሪያ መሠረት ሲስማማበት ለብፁዓን ጳጳሳት የሊቀ ጵጵስና ማዕረግ ይሰጣል፡፡

4.    በዚህ ሕግ አንቀጽ 7 ንዑስ አንቀጽ 15 መሠረት የተመረጡትን የሥራ ሓላፊዎች ይሾማል፤ በቀደምትነትና በታሪክ የታወቁትን የታላላቅ ገዳማት አበምኔቶችና የከፍተኛ አድባራት አስተዳዳሪዎች በየሀገረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት እየተመረጡ ሲቀርቡለት የማዕረግ ስም እየሰጠ ይሾማል፡፡

5.    ስለ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የመንግሥትን ፈቃድ ማግኘት በሚያስፈልግበት ጊዜ በቅዱስ ሲኖዶስ እያስወሰነ በተግባር ላይ ያውላል፡፡

6.    ቅዱስ ፓትርያርኩ በዓበይት ጉዳዮች ላይ ሁሉ በቅዱስ ሲኖዶስ አያስወሰነ ይሠራል፡፡

7.    በቅዱስ ሲኖዶስ የወጡ ሕጐች፣ የተላለፉ መመሪያዎችና ውሳኔዎች ሁሉ በተግባር ላይ መዋላቸውን ይከታተላል፣ ይቆጣጠራል፡፡

8.    በቅዱስ ሲኖዶስ የሚወጡትን ሕጐችን፣ ደንቦችንና መመሪያዎችን በፊርማው ያስተላልፋል፡፡

9.    ከመንግሥታውያንም ሆነ መንግሥታውያን ካለሆኑ መ/ቤቶች ድርጅቶችና ግለሰቦች የሚቀርቡ ደብደቤዎች ወይም አቤቱታዎችን ደረጃቸውን ጠብቀው በሕግ መሠረት ይፈጸሙ ዘንድ ለጠቅላይ ጽ/ቤት ያስተላልፋል፡፡

10.    በውጭ አገር በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አህጉረ ስብከት ለማገልገል ወይም የነፃ ትምህርት ለመማር የሚላኩ ካህናት በዚሁ ሕግ አንቀጽ 7 ንዑስ አንቀጽ 11 መሠረት ተመርጠው ሲቀርቡ እንዲላኩ ያደርጋል፡፡

11.    ከውጭ የሚመጡትን እንግዶች በውጭ ጉዳይ ኃላፊ አቅራቢነት እየተቀበለ ያነጋግራል፡፡

12.    ፓትርያርኩ በውጭ አገር በሚደረግ በማናቸውም ስብሰባ ላይ ለመገኘትና ጉብኝት ለማካሔድ በሚያስፈልግ ጊዜ ስለተልዕኮው ጉዳይ አስቀድሞ በቅዱስ ሲኖዶስና በቋሚ ሲኖዶስ ያስወስናል፡፡

አንቀጽ 16

የፓትርያርኩ ከማዕረግ መውረድ

1.    ፓትርያርኩ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ከተሾመ በኋላ የተቀበለውን ሓላፊነት በመዘንጋት፡-

ሀ. የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖትን የሚያፋልስ፣ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የማይጠብቅ ቤተ ክርስቲያንን የሚያሰነቅፍ ተግባር ፈጽሞ ከተገኘ፣

ለ. በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ከቁጥር 172 እስከ 208 በተደነገገው መሠረት በደለኛ መሆኑ ከታመነበት፣

ሐ. በቃሉ የማይገኝና በዚህ ሕግ አንቀጽ 13 ንዑስ አንቀጽ 7 ድንጋጌ መሠረት በተሾመበት ቀን የፈጸመውን ቃለ መሐላ ያልጠበቀ በአጠቃላይ ታማኝነቱና መንፈሳዊ አባትነቱ በካህናትና በምእመናን ዘንድ ተቀባይነትን ያጣ ሆኖ ቤተ ክርስቲያኒቱን የሚያስነቅፍ መሆኑ በትክክል ከተረጋገጠ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ከሥልጣኑ ይወርዳል፤ በምትኩም ሌላ ፓትርያርክ ተመርጦ ይሾማል፡፡

2.    ከዚህ በላይ በተደነገገው መሠረት ከሥልጣኑ የተገለለ ፓትርያርክ በቀኖና ተወስኖ በገዳም ይቀመጣል፡፡

3.    ከሥልጣን የተገለለው ፓትርያርክ በገዳም አልቀመጥም በቀኖናም አልወሰንም በማለት እምቢተኛ ከሆነ ተወግዞ ከቤተ ክርስቲያን አንድነት ይለያል፡፡

4.    ፓትርያርኩ መንፈሳዊ ሥራውን በማካሔድ ላይ እያለ እሥራትና ግዞት ቢደርስበት ቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ ትመራለች እንጂ ሌላ ፓትርያርክ አይሾምም፡፡

5.    ከዚህ በላይ የተዘረዘረው ሁሉ ፍትሕ መንፈሳዊ በሚያዝዘው መሠረት ይፈጸማል፡፡

አንቀጽ 17

ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ

1.    ፓትርያርኩ በሞት ሲለይ ወይም በዚህ ሕግ አንቀጽ 16 መሠረት ከሥልጣኑ ሲወርድ ቅዱስ ሲኖዶስ በሹመት ቀደምትነት ካላቸው ሊቃነ ጳጳሳት መካከል በዕለቱ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ መርጦ ይሾማል፡፡ የተተኪው ፓትርያርክ ምርጫም ይካሔዳል፡፡

2.    የተተኪው ፓትርያርክ ምርጫ አፈጻጸም እንደጊዜውና እንደሥራው ሁኔታ እየታየ ከ40 እስከ 80 ቀን ባለው ጊዜ ይሆናል፡፡

3.    የዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ተግባር

ሀ. ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ጊዜያዊ ጉደዮችን ከቋሚ ሲኖዶስ ጋር እየመከረ ያከናውናል፡፡

ለ. በፓትርያርኩ ምርጫ ጊዜም የቅዱስ ሲኖዶስ ሊቀ መንበር ሆኖ ምርጫውን ያስፈጽማል፤ እርሱ ግን ከምርጫው አይገባም፡፡

/ምንጭ፦ ሕገ ቤተ ክርስቲያን 1991 ዓ.ም/

ሥርዓተ ቤተክርስቲያን

በሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ
 
ሥርዓት ማለት ‹‹ሠርዐ›› ሠራ ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ የምዕላድነት ዘር ያለው ስም ነው፡፡ ትርጉሙ ሕግ ደንብ አሠራር መርሐ ግብር ማለት ነው፡፡