ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነት ዕርቅና ሰላም መሠረት ናቸው
መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም.
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዘመኑ የተለያዩ ፈተናዎች የተፈራረቁባት ሲሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነችና የመጣውን የፈተና ጎርፍና ነፋስ ሁሉ ተቋቁማ አሁን ላለንበት ዘመን ደርሳለች፡፡ የዐላውያን ገዢዎችን ሰይፍ ከውስጥም ከውጭም የነበሩ መናፍቃንን ቅሰጣ ተሻግራ እስከአሁን የሐዋርያትን፣ የቅዱሳን ሊቃውንትን የአትናቴዎስን የቄርሎስን ሃይማኖት ይዛ ተገኝታለች፡፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን የሚመጡባትን ፈተናዎች የምታደንቅ፣ በዚያም ተስፋ የምትቆርጥ አይደለችም፡፡ ሁል ጊዜም ቢሆን የገሃነም ደጆች የሚሰብቁት ግልጽና ስውር ጦር እንዳለ ስለምታውቅ ከሚመጣው ፈተና ሁሉ አሸንፋ ትወጣ ዘንድ ወደ አምላኳ ትለምናለች እንጂ፡፡